Author Archive

ማእቀብ በወያኔ የገንዘብ ምንጮች ላይ! የኢትዮጵያ አየርመንገድንም ጨምሮ?

Tuesday, March 20th, 2012

በክፍሉ ሁሴን

እንደመንደርደሪያ አንዳንድ ትውስታ

ጊዜው 1967 ዓ.ም ክረምት።ክረምት መሆኑን የማስታውሰው ት/ቤታችን በተለመደው ዋና የዝናም ወራት ተዘግቶ ሰፈር በጭቃ ተራግጠን ውለን ስንገባ ተሸክመን ይዘን በምንገባው ጭቃ ምን ያህል ቤተሰቦቻችንን እንደምናስመርርም ትዝ ስለሚለኝ ነው።በተለይ ግን የስድሳ ሰባቱ ክረምት ከሁሉም በላይ ትክዝ የሚለኝ አንድ ምሽት አንዳፍታ የሚያሸብረን ሁኔታ በመከሰቱ ነው።የአስር አመት ከዘጠኝ ወይም ከአስር ወር ልጅ ስሆን በዚያን ጊዜ ህጻናት ከነበሩት ሶስቱ ወንድሞቼ በቀር ታናሽ ወንድሜና እናቴ በተከሰተው ሁኔታ እጅግ ተረብሸን ነበር።ራስ አሉላ በቀለ የሚባሉ ደርግ ያሰራቸው ወይም የገደላቸው ሰው በጅምር ሳይጨርሱት የተውትን ቪላ የተወረሱ የባለሃብት ቤቶችን እንዲያስተዳድር የተቋቋመው የኪራይ ቤቶች ጅምሩን ጨርሶ ለሩዋንዳ መንግስት ኤምባሲ ጽ/ቤትነት እስኪያከራየው ድረስ ሰፈራችን ይጠራ የነበረው “ቦሌ ድልድይ”ተብሎ ነበር።በተለይ የእኛ ቤት የቡልቡላ ወንዝ ባይኖር ኖሮ ወሎ ሰፈር ተብሎ ከሚታወቀው የጎረቤት መንደር እንዳንዱ ሊሆን በቻለ ነበር።ከወሎ ሰፈር ከወንዙ ወዲህ ማዶ ወደቦሌ በኩል በመሆናችንም የከፍተኛ 17 ቀበሌ 20 በኋላም ሩዋንዳ ኤምባሲ ነዋሪዎች ለመባል መብቃት ብቻ ሳይሆን ወሎ ሰፈርን ጨምሮ በሌሎች አጎራባች ቀበሌ ያሉ ልጆች በብዛት በቀይ ሽብር ሲቀጠፉ የተረፉትም ሰቆቃ ሲፈጸምባቸው አስተዋይና ደግ በነበረው የወቅቱ የቀበሌ ሊቀመንበራችን አቶ ተፈራ እንዳለ ምክንያት አገር አቀፍ ከነበረው ግፍ የእኛ ሰፈር ልጆች በአቶ ተፈራ ደግነት ልንተርፍ ችለናል።

የአሁኑ ዘመንም አሸባሪው የወያኔ አገዛዝ ራሱ ኢትዮጲያውያኖችን አሸብሮ ሌሎችን በአሸባሪነት እየፈረጀ እንደመሆኑ በዚያን ጊዜ በተለይ የእኛን ቤተሰብ ወዳሸበረን ጉዳይ ልመለስ።ከምሽቱ ወደ ሁለት ተኩል አካባቢ ስልካችን ተንጫረረች።እንደተለመደው ማንም ሳይቀድመኝ ተቅለብልቤ አነሳሁ።ፒ 11 ተብሎ ከሚታወቀው የአየር ሃይል የቅጥር ዘመን ጀምሮ ኢትዮጲያ አየርመንገድ በተመሳሳይ ወቅት አብረው እስከተዛወሩበት የአብዮቱ ዘመን መባቻ ድረስ የረጅም ጊዜ የአባቴ ጓደኛ የሆነው ነፍሱን ይማረውና አብራሪ ሻለቃ ጌታቸው ከበደ ነበር የደወለው።ሁሌ እንደሚያደርገው በዚያን ምሽት አባቴን ባወጣለት ቅጽል ስም አልጠራውም።በቀጥታ “አባትህ አለ?”ነበር ያለኝ። “በሯል” ለሚለው መልሴ በመጣደፍ እናቴን እንዳቀርብለት ጠየቀኝ።ጌታቸው በመስመር በራሪነት ተመድቦ በዚያን ጊዜ ሲ 47 ወይም ዳኮታ የሚባለው አውሮፕላን ላይ የሚሰራ ስለነበር የበረራ ተረኛ ካልሆነ በስተቀር እንደሌሎች ሰራተኞች በመደበኛ የስራ ሰአት መ/ቤት መገኘት አይጠበቅበትም ነበር።በተቃራኒው አባቴ በበረራ ማስልጠኛ ት/ቤት በበረራ አስተማሪነት ተመድቦ ይሰራ የነበር ከመሆኑም ባሻገር አልፎ አልፎ ፓይፐር ከብ ተብላ በምትታወቀው አነስተኛ አውሮፕላን በአብዮቱ ዋዜማ በሜካናይዝድ እርሻ ላይ ተሰማርተው ለነበሩ የውጪ አገርና የአገሩ ውስጥ ባለሃብት የቻርተር አገልግሎት በመስጠት እያበረረ ከአዲስ አበባ ውጪ እንደመስመር ፓይለቶች ያድር ነበር።/ባለሃብቶቹ ንብረታቸው ቢወረስም የተወሰኑቱ ፈረንጆች ከውርሱ ጋር በተያያዘ ጭፍጫፊ ምክንያቶች ወደ ቀድሞ ሃብታቸው ከአብዮቱ መባቻም በኋላ በቻርተር አገልግሎት ምልልስ አድርገዋል።/በተረፈ እንደማንኛውም ሌላ የአየርመንገዱ ሰራተኛ በመደበኛ የስራ ሰአት ተማሪዎቹን አስተምሮ ቤቱ ይመለሳል።በዚያን እለት የደንብ ልብሱን ለብሶ እንደወጣ ስላልተመለሰ በደመናና ሌሎችም ምክንያቶች ደጅ ከሚያሳድሩት የቻርተር በረራዎች አንዱ አድርጌ ስለቆጠርኩት መልሴ “በሯል”ሆነ።ለማንኛውም እናቴ ስትቀርብ ተመሳሳይ ጥያቄ ከጠየቃት በኋላ ፍጹም በተረጋጋ ሁናቴ ስለመለሰችለት ተገርሞ “ለመሆኑ ምንም ተኩስ አልሰማሽም ወይም ዜና በቴሌቪዥን?”መልሷ “የምን ተኩስ እነዚህ እየተንጫጩ ምን መስማት ይቻላል፤ቴሌቪዥኑም እንጨት እንጨት ስለሚል ትቼዋለሁ።”እሱም “የቴሌቭዥኑ ይሁን ካልሞታቹህ በቀር የትናየት የሚሰማውን ተኩስ አየርመንገዱ ስር ተቀምጠሽ እንዴት አትሰሚም?”ሲል ያልጠበቅነውን ዱብእዳ ጣለብን።ያኔ ባይገባኝም ከአመታት በኋላ እንደተረዳሁት የአየርመንገዱ ሰራተኛ ለካ “የወዛደር ደመወዝ ሰላሳ ሸመታው ስድሳ”በሚል መሪ መፈክር አድሞ የደመወዝ ጭማሪና ሌሎች ማሻሻያዎች በመጠየቁ “ለሰፊው ህዝብ የመጣው አብዮታዊው መንግስት”ዙሪያውን ከቦ በጥይትና በሰደፍ ሰራተኛውን እንካ ይቀመስልህ ይለው ኖሯል።

በኢትዮጲያ ሰራተኞች ንቅናቄ ታሪክ ውስጥ ስማቸው ዝንተአለም ገናና የሆኑትን አቶ አበራ ገሙ አይነቱን አርበኞች እንዳፈራው የምድር ባቡር ድርጅትና የአቃቂ ጨርቃ ጨርቅ ፋብሪካ ባይሆንም የኢትዮጲያ አየርመንገድ ሰራተኛም በደጉ ዘመን ለመብቱ ወደኋላ የማይል እንደነበር ታሪክ ያወሳል።እኔ በሚገባ እስከማውቀው ድረስ ያ እንቅስቃሴ በአየርመንገዱ ለመጨረሻ ጊዜ የተካሄደ የጋራ የመብት ትግል ነው።እንደአብዛኛው የኢትዮጲያ ህዝብ በግል ከማልጎምጎምና በየመሸታ ቤቱ ሳያስተጓጉል በደል የሚያደርስበትን አገዛዝ ድምጹን ቀብሮ ከማማት በቀር ተደራጅቶ እምቢ ለመብቴ ማለት ከዚያ የደርግ እመቃ በኋላ የፋራ ታሪክ ሆኖ ቀርቷል።በአዲስ የቃላት ሽንገላ የኢትዮጲያን ሰራተኛ “ላብአደር”እያለ የሚጠራው አዲሱ የወያኔ አገዛዝ ደግሞ ጭራሹኑ የኢትዮጲያ አየርመንገድ ሰራተኛ ምን ግፍ ቢውልበት የስራ ማቆም አድማ እንደማይፈቀድለት በአብዮታዊ ዴሞክራሲ መንፈስ አውጆ ሲያበቃ የላብአደሩ መብት ያላንዳች እንከን መረጋገጡን አበሰረ።/በወያኔ ጊዜ በሥራ ላይ ያለውን የአሰሪና ሰራተኛ አዋጅ ይመልከቱ/።ለነገሩ የየትኛውም ድርጅት ሰራተኛ እንኳን ሊያድም ቀርቶ ከአገዛዙ የተለየ ሃሳብ እንዳለው ከተጠረጠረ በቁም ከነቤተሰቦቹ ፍዳውን የሚቀበልበትን ልዩ የወኔ መስለቢያ ስልት ወያኔ ከቀየሰ መቆየቱን ገና በማለዳ በኢትዮጲያ ንግድ ባንክ ሰራተኞችና እንዲሁም ነጻ የሰራተኛ ማህበር ፈጽሞ እንዳይኖር የወሰደው የፈላጭ ቆራጭ ብቻ ሳይሆን የለየለት የወሮበላ ተግባር የሚዘነጋ አይደለም።በዚህ ጉዳይ ላይ መመላለሴ ስለማይቀር የጀመርኩሎትን የቤተሰቤን የዚያን እለት ምሽት ልቋጭልዎ። አባቴ ለበረራ ከተሰማራበት ቦታ ተመልሶ ካረፈ በኋላ አየርመንገዱ በጦርሰራዊት ከመከበቡ ጥቂት ደቂቃዎች በፊት የደንብ ልብሱን ጃኬት በሻንጣው ይዞት በነበረው የሹራብ ጃኬት ለውጦ የእስልምና ሃይማኖት ጥብቅ ተከታይ ለነበሩት እናቱ የገዛዛውን/የእስላም ጾም መግቢያ ወይም መፍቻ ዋዜማ ነበር መሰለኝ/እቃ ለማድረስና ወዲያውም በምንድህስና ሙያ የተመረቀ የቀድሞ የሁለተኛ ደረጃ ት/ቤት ጓደኛው ባደረገለት ግብዣ/እንደ አባቴ ሳይሆን ጓደኛውም የእስልምና ሃይማኖቱን አጥብቆ የያዘ ነበር/በቀጠሮ ለመገኘት ወደሱ ቤት ገሰገሰ።እዚያ በቴሌቪዥን የአየርመንገዱን ረብሻ ከሰማ በኋላ ደውሎልን ተረጋጋን።በዚህ ጽሁፌ ዝቅ ብዬ ላነሳው ካሰብኩት ጉዳይ ጋር ስለሚያያዝ ተጨማሪ አንድ ሁለት ትውስታዎቼን ላክልና ይህን ሁሉ እንድዘበዝብ ወዳረገኝ ዋና ነጥብ ልዝለቅ።

ሻለቃ ጌታቸው ከፓይለቶች ማህበር ክበብ እንዳጣራው አብዛኞቹ የበረራ ማስልጠኛ ት/ቤት ባልደረቦች ወደቤታቸው አለመመለሳቸውንና ቤተሰቦቻቸውም እንደተረበሹ ለእናቴ ስለነገራት አባቴ ደውሎልን እፎይ እስክንል ድረስ ሌላው የአባቴ ጓደኛና በአንጋፋ የበረራ አስተማሪነቱ ወደሚታወቀው ካፕቴን ወይም በአየር ሃይል ማእረጉ ሌተ/ኮሎኔል ቶላ ቢነጋ ቤት መደወል አስፈላጊነቱ ለእናቴ አልታያትም።ይልቁን በዚያ በደጉ ዘመን ባለቤቱ የእናቴ ጓደኛ የሆነች ልጆቹ ደግሞ የእኛ ጓደኛ የሆኑ ጎረቤታችን የሆነና በዚያን ጊዜ በአየርመንገዱ የጄት ሞተር ጥገና ክፍል በመካኒክነት በሌሊት ፈረቃ የሚሰራ ሰው ቤት ሄዳ ለማጣራት ስለወሰነች አብሬያት ሄድኩ።እንደተፈራው መካኒኩ ጎረቤታችን በረብሻው ምክንያት ለሌሊት ፈረቃ ስራው እንዳልሄደና ሁኔታውም ጥሩ እንዳልሆነ ከገለጸልን በኋላ ሲነጋ ማጣራት እንደሚሻል መክሮን ተመለስን።ይህ ሰው ከመጀመሪያውም የአየርመንገዱ ቅጥር ሲሆን ከተራ መካኒክነት ተነስቶ በአየርመንገዱ የአቪዬሽንና ጥገና ት/ቤት በአሰልጣኝነት ከማደግ ጀምሮ ችሎታው እስከፈቀደ ድረስ በደርጉ ስርዐት የጄት ሞተር ጥገና ክፍል ስራ አስኪያጅነት ያላንዳች መድልዎ ተሹሞ ሲያገለግል ቆይቶ በጡረታ ተገልሎ እስከዛሬ በህይወት አለ። “ፈሪ ተራራ ነው ዘላለም ይኖራል፤ጀግና ብርሌ ነው ወድቆ ይሰበራል”የሚለውን አባባል በሚያስታውሰኝ መልኩ የቀድሞው መካኒክ እድሜው አለቅጥ ተንዘላዝሎበት ነው መሰለኝ ወያኔ ካመጣው የጎሳ ፖሊቲካ ጥምቀት ወስዶ በሰብቅ ተግባር በመሰማራት የቀድሞ ባልንጀሮቹን በወያኔ እስከማስወጋት ድረስ ሄዷል።በተለይም ራሱ በአባቷ ከኤርትራ የምትወለድ ሴት አግብቶ ዘጠኝ ልጆች አዲስ አበባ ላይ ወልዶ እንዳልከበረ የወያኔና የሻዕቢያ ከንቱ ደም አፋሳሽ ጦርነት ሲመጣ ቀድሞ በመሰሪ ባህሪውና በደካማ ሰብእናው ይሸነቁጡጥ የነበሩትን አንዳንድ እንደሚስቱ በግማሽ የኤርትራ ውልደት ያላቸውን በኢትዮጲያዊነታቸው እንከን የማይወጣለቸው ብቻ ሳይሆን ለአገራቸው ያበረከቱት አስተዋጽዖ በክብር መዝገብ ላይ የተጻፈላቸውን ሰዎች ሁሉ ከአገር እንዲባረሩ ለማድረግ ፋትሯል።ምን ያህል እንደተሳካለት ባላውቅም ባንድ ኢትዮጲያዊ ላይ ያደረገው ሙከራ ግን በራሱ በወያኔ ካድሬዎች እንዳሰደበው መረጃዎች አሉኝ።ሙሉጌታ ሉሌ እንደሚሉት ድሮ በመሃይማን ካድሬዎችና ሶስተኛ ደረጃ ጮሂዎች ጥቆማ ብዙ ንጹሃን ኢትዮጲያውያን በመደብ ትግል ስም እንዳልተጋዙና እንዳልተቀጠፉ ዛሬ ደግሞ በጎሳው ፖሊቲካ ላይ አምባገነንት ተጨምሮበት ዜጎች የዜግነት መብታቸውንም ጭምር ፍጹም የኢትዮጲያ ጠላት በሆኑ ሰዎች ሰብቅ ያጣሉ።

አሳዛኙ ነገር ግን የዘሬን ብተው ያንዘርዝረኝ በሚመስል መልኩ ልጆቹ ቢያንስ ከልጆቹ አንዱ በለየለት ጎሰኝነት የተለከፈ መምሰሉና ከሃያ አምስት አመት በላይ በነጻነት ማሰብ ማስተዋል መጠየቅና መማር የሚቻልበት አሜሪካ ቢኖርም ሰማይ ጠቀስ ህንጻ እንዲሁም የቀለበት መንገድ በአዲስ አበባና መቀሌ በብዛት ስለተቆለለና ስለተነጠፈ መወድስ ቅኔ ለመለስ ዜናዊ ልታቀርብለት ይገባል ሲል በፌስ ቡክ በኩል ባልንጀራው ካደረገኝ በኋላ እስከዛሬ ይህንኑ ጅል ሃሳብ ሊሸጥልኝ እንደታገለ አለ።የአራተኛ ታናሽ ወንድሜ እኩያ ለሆነውና በዳላስ ቴክሳስ ኗሪ ለሆነው የቀድሞ የሰፈሬ ልጅ ብሩክ አረጋይ ዮሃንስ ኮንፊውሸስ የተባለ የቻይና ፈላስማ “መልካም አስተዳደር ባለበት አገር መናጢ ድሃ መሆን የሚያሳፍር፤ ብልሹ አስተዳደር ባለበት ደግሞ የናጠጠ ሃብታም መሆን እንደሚያሳፍር”የተናገረውን በማንሳት በወያኔ ጋጠወጥ አገዛዝም የሚገነባውና በጥቂት ምርጦች እጅ የሚግበሰበሰው ሃብት ሁሉ የእኛው ፕሮፌሰር መስፍን ወልደማሪያም እንዳሉት

“ቂልነት ነው፤ትዕቢት?
ወይስ ደደብነት?

ነገ የሚፈርሰው ዛሬ የሚካብበት?”ብዬ ላስረዳው ከጀመርኩ በኋላ አውቆ የተኛ ቢቀሰቅሱት አይሰማም አይነት ነገር መሆኑ ስለገባኝ ካልተትረፈረፈኝ በቀር ከብሩክ አይነቱ ሰው ጋር ብዙም ጊዜ ላላጠፋ ወሰንኩ።ይሁንና ይህን የግል ተሞክሮዬንና ትውስታዬን አደባባይ እንዳወጣው የሚያስገደድ አንጋብጋቢ አገራዊ ጉዳይ አጋጠመኝ።

በኢት/አየርመንገድና ተዛማች ጉዳዮች የኤልያስ ክፍሌ ሃሳብ

በራሳችን ስንፍና ራስ ወዳድነትና አርቆ አለማሰብ ከጣሪያ በላይ የሄደው የወያኔ ዘረኛና ግፈኛ አገዛዝ እነበቀለ ገርባንና እነደበበ እሸቱን በድጋሚ ያፈነበትን ምክንያት በማድረግ ኤልያስ ክፍሌ ከወትሮው በተለየ ወያኔን በሚያሽመደምድ ተግባር እንድንሰማራ ሃሳብ አቀረበ።ሃሳቡ በሁለት ተከፍሎ ውጪ አገር ለምንኖርና በአገር ውስጥ ላሉ አገር ወዳድ ኢትዮጲያውኖች የቀረበ ሲሆን እነአንዷአለም የሚከፍሉትን መስዋትነት እንጋራ በሚል መሪ መፈክር ሰባት ነጥቦችን ይዟል።ከነጥቦቹ አንዱ ታዲያ የምመካበትና የአገሬን ሰንደቅአላማ እያውለበለበ በመብረር አገሬን በበጎ በማስጠራቱ ብቻ ሳይሆን እኔንም ያሳደገ በነጻ ቲኬት የተንፈላሰስኩበት አየርመንገድ ላይ ያነጣጠረና ማእቀብ እንድንጥልበት የሚጠይቅ በመሆኑ ላንዳፍታ እንድደነግጥ አደረገኝ።ወደቀልቤ ስመለስ ግን የኤልያስ ሃሳብ በጎና በአስቸኳይ ተወያይተንበት ልናዳብረው የሚገባ መስሎ ስለተሰማኝ ለመጀመሪያ ደረጃ ውይይት በፌስ ቡክ ላይ ሰቀልኩት።ውጤቱ “በጎ ሃሳብ ያላቸው በቸልተኝነት ወይ በፍርሃት ዝም ስለሚሉ ክፉ ሃሳብ ያላቸው ይገናሉ” በሚለው የቆየ ይትባሃል መሰረት ከፌስ ቡክ ባልንጀሮቼ ሁሉ የመለስ ዜናዊ አፍቃሪ የሆነው ሳተናው የቴክሳሱ ነዋሪ ብቻ ብቅ ብሎ “አባትህና አባቴ የሰሩበትን አሁን ደግሞ ወንድምህና ለኔ ደግሞ ‘አብሮ አደግ ጓደኛዬ’የሚሰራበት ‘የቤተሰባችን’ አየርመንገድ ላይ የምታደርገውን አሉታዊ ዘመቻ አቁም!ወንድምህ ስራ አጥ እንዲሆን ትፈልጋለህ ወይ?”ሲል ሁልጊዜም የምጠረጥረውና ወያኔም እንደታላቅ ወንድሙ ሻዕቢያ ተሰደን የምንኖረውን ሲቻል በአፍቅሮ ነዋይ መሸበብ፤ ሳይቻል አገር ቤት ባሉ ቤተሰቦች ህልውና ከሲያትል እስከሜልቦርን ተሰደው የሚኖሩት አብዛኞቹ ኤርትራውያን ስደተኞች ጸጥ በተደረጉበት ዘዴ እኛንም ጸጥ የማድረግ እቅድ እንዳለ ጠቆመኝ።ከንቱ ልፋት! አንደኛ አራተኛ ታንሽ ወንድሜ የአባቱን ኮስታራ ሃሞት ባይወርስ በወጣትነቱ የትልቅ ጄት አውሮፕላን ዋና አብራሪ/pilot in command/አይሆንም ብዬ ስለማምንና ይኸው ሃሞት ለማናቸውም ፈታኝ ሁኔታ አዘጋጅቶታል ብዬ ስለማስብ ነው።በዘመናችን አንዳንድ ፓይለቶችና ሌሎች ባለሙያዎች ላይ እንደሚታየው ተዘናግቶ ተልፈስፍሶና ተስገብግቦ ከአላሙዲን ጋር ባለሟልነት ከቆስጠንጢኖስ ጋር ደግሞ ባልንጀርነት ገብቶ ከሆነ እኔ ለራሴ ኑሮ ሃላፊነቱን እንደወሰድኩት ሁሉ ሃላፊነቱን ይወስዳል።ሁለተኛ በዚህ ረገድ ለሚመጣብኝ ግልጽና ረቂቅ ዛቻ/subtle blackmail/ አንዳርጋቸው ጽጌን በአርዓያነት ስለወሰድኩ ወያኔ ከነጀሌዎቹ ከሚደክም በቀር ይኽ ግድም ማፈግፈግ አይኖርም፤በስደት አብረውን እንደሚኖሩት የቀድሞ ኢትዮጲያውኖች/ኤርትራውያኖቹን ማለቴ ነው/ በነጻነት አገር እየኖሩም በፍርሃት ቆፈን መቀፍደድም የለም።በመሆኑም አሁን በኢትዮጲያ አየርመንገድ አውሮፕላኖች ላይ ባለመሳፈር ማእቀብ የመጣሉን ጉዳይ አግባብነት ወደ መፈተሹ እሄዳለሁ።

ስለኢት/አየርመንገድ ብሄራዊ እሴትነትና የወያኔ የገቢ ምንጭነት

በግሌ እንደማምነው ኢትዮጲያችንና ኢትዮጲያኖች በብዙ ረገድ በተዋረድንበት ዘመን ከለየለት የከፋ ገጽታ የሚታደገን አየርመንገዳችን ሲሆን አትሌቲክስም በቅርብ ከደረሰበት ስብራት በቀር ሌላው መልካም ገጽታችን ነው።በረሃብተኝነት በስደተኝነት በአረብ አገር ግርድና በኤድስ በህገወጥ የሰዎች ሽግግር የሚነሳውን ክፉ ስማችንን ሁልጊዜም በበጎ ሚዛን እንዲደፋ የሚያደርገው አየርመንገዳችን መሆኑ ጥርጥር የለውም።ምንም እንኳን ዛሬ አዛዥ ናዛዥ የሆነበት ወያኔ ቢሆንም የውጪ ምንዛሪ ከማስገባትም በላይ በሚያስገኝልን መልካም ስም የተነሳ ብሄራዊ እሴታችንም አድርጌ እመለከተዋለሁ።ከምር በብሄራዊ እሴትነቱ ወይም ጥሪትነቱ እንዲቀጥል ለማድረግ ግን የአየርመንገዱ ሰራተኞችም ሆኑ ሌሎች ኢትዮጲያኖች ነጻ መሆን አለባቸው።በአፍሪካና በመካከለኛው ምስራቅ የሚገኙ ከኢትዮጲያ አየርመንገድ ያነሰ ትርፍና ስኬት ያላቸው አየርመንገዶች ለሰራተኞቻቸው የተሻለ ክፍያ እንዲሁም በነጻ መደራጀትና ይህንኑ የማስከበር መብታቸውን ያከብሩላቸዋል።ኢትዮጲያ አየርመንገድ ከተመሰረተ ከብዙ አመታት በኋላ የተመሰረተው የጎረቤት ኬንያ አየርመንገድ ዛሬ በተወዳዳሪነት እስከመገዳደር የደረሰው ሰራተኞቹን በተለጣፊ የካድሬ ሰራተኛ ማህበር እየለጎመ በአለማቀፍ ደረጃ የታወቀ እስከ ስራ ማቆም ድረስ የሚያቀዳጅ መብታቸውን እየገፈፈ አይደለም።የኬንያ ኤርዌይስ ሰራተኞች በተለያየ ጊዜ ባደረጉት የስራ ማቆም አድማ የስንግ መንግስታቸውን ይዘው መብታቸውን አስከብረዋል።ኬንያ የራሷን ዜጎች በማሰልጠንና በጥሩ ክፍያ የፓይለቶቿን ቁጥር ስታሳድግ በወያኔ ስርዓት ደግሞ ልምምጥ አከል በሆነ አቤቱታ መልክ ደመወዝ እንዲስተካከልላቸው የጠየቁ ፓይለቶች “መንገዱን ጨርቅ ያድርግላቹህ”አይነት ስለተባሉ በአንድ ወቅት በብዛት ወደመካከለኛው ምስራቅ አገራት አየርመንገድ ፈልሰዋል።ይህ የተፈጸመው ዛሬ ከአምባገነኑ የዘረኛ አገዛዝ ጎራ ወጥቶ የህዝቡን ጎራ በተቀላቀለው ስዬ አብርሃ የቦርድ ሊቀመንበርነት ጊዜ ሲሆን ከዚህም የከፋ ነገር በአየርመንገዱ ተፈጽሞ እንደነበር ይታወቃል።ባጭሩ ግን ድምር ውጤቱ አየርመንገዱን ለከፍተኛ የፓይለት እጥረት ሲያጋልጠው ከስሮ ከተዘጋ እንደጋና አየርመንገድ ከመሳሰሉና መብረር ያቆሙ ፓይለቶችን እስከመቅጠር የሚያደርስ ደረጃ ላይ ተደረሰ።አስገራሚው ነገር ጋናውያኑ ፓይለቶች በእኛው ፓይለቶች የክለሳ ስልጠና ተሰጥቷቸው የሚከፈላቸው ደመወዝ ከእኛ ፓይለቶች የሚበልጥ መሆኑ ነው።እስከዛሬ ድረስ ወያኔ ለኢትዮጲያውን ፓይለቶች ተገቢውን ደመወዝ ላለመክፈል ፈቃደኛ ባለመሆን በብዛት የውጪ አገር ዜጎችን የቀጠረ ሲሆን ምን ያህል እንደሚከፈላቸውም በውል አይታወቅም።ከዚህም ባሻገር አየርመንገዱን ያቆሙት ፓይለቶች ብቻ ይመስል ለሌሎቹ ሰራተኞች የሚከፈለው ደመወዝ ዝቅተኛ በመሆኑ በአብራሪዎችና በሌላው ሰራተኛ መካከል ክፍፍልን የፈጠረ ሁኔታ እንዲኖር አድርጓል።

ወያኔ አየርመንገዱን ሲረከበውም ሆነ ዛሬም ድረስ አንዳችም ብሄራዊ ስሜት ስለሌለው አየርመንገዱን በዘላቂ እድገት ላይ ለማቆም ሳይሆን ለአገዛዙ ከሚሰጠው ትርፍ አኳያና በንግስናቸው ማግስትም ወዲያዉኑ እንደተረዱት በራስ አገር አየርመንገድ መብረር ለሚስገበገቡላት ከይሲ ነፍሳቸውም አስፈላጊ በመሆኑ ነው።በተቀር የአየርመንገዱ መሰረት የሆነውን የኢትዮጲያ አየር ሃይል እንዳልነበር አድርገው በየሳምንቱ ገበያና የእርሻ ማሳዎች ላይ በብዙ ሚሊዮን ዶላር የተገዙ ተዋጊ ጄት አውሮፕላኖችን ወደሚከሰክስ ተቋም ደረጃ በማውረድ ለአገሪቷ ተጨማሪ እዳ እንዳመጡት ሁሉ አየርመንገዱንም ለዚህ ከመዳረግ አይመለሱም ነበር።ይህ ጽሁፍ አለቅጥ ስለረዘመ ነው እንጂ አሁንም ቢሆን አየርመንገዱ ከዚህ አደጋ ሙሉ ለሙሉ አለመላቀቁንና እንዲያውም በጊዜ ብዛት ሊከሰት ስለሚችል የደህንነት ስጋትና የኪሳራ ምልክቶች ብዙ ማለት ይቻል ነበር።ባጭሩ ግን ሁልጊዜም የአየርመንገዱ መሰረት የነበረው አየር ሃይላችን በወያኔ እጅ እንዳልነበር መሆን አየርመንገዱን የጀማሪ አውሮፕላን አብራሪዎች አስተማሪ እጥረት በአንገብጋቢ ሁኔታ እንዲፈጠርበት እያደረገ ሲሆን የዚህ ውጤት በአየርመንገዱ ታሪክ ተሰምቶ በማያውቅ ሁኔታ በስልጠና ላይ የነበረና ለአገር አቋራጭ በረራ ለብቻው/cross country solo/እንዲሄድ የተደረገ ተማሪ ፓይለት ከአንድ ከሁለት አመት በፊት ተከስክሶ መሞቱ ነው።ከዚህ ጋር የተያያዘ ራሱን የቻለ ታሪክ ስላለ እንደስፈላጊነቱ በሌላ ጊዜ የምመለስበት ሲሆን አሁን የማእቀቡን ነገር ልቋጭ።

ሲሆን ሲሆን የኢትዮጲያ አየርመንገድም ሆነ የሌሎች ድርጅት ሰራተኞች የራሳቸውንም ሆነ አገራዊ መብት ለማስከበር በራሳቸው ተነሳሽነት የስራ ማቆምና ሌሎችም ተዛማጅ እርምጃዎችን ሊዎስዱ በተገባ ነበር።እውነታው ይህን የማይፈቅድ ስለሆነ ኤልያስ እንዳቀረበው ሃሳብ የኢትዮጲያውያንና በአጠቃላይ የሰብአዊ መብት መደፈር የሚያንገበግበው በውጪ አገር ነዋሪነቱን ያደረገ ሁሉ የኢትዮጲያ አየርመንገድ ለወያኔ ገቢ ማስገኘት ብቻ ሳይሆን የጥጋብ ምንጭ መሆኑን ተገንዝቦ ራሱን ወያኔን ከሚያደልብ ተግባር የኢትዮጲያ አየርመንገድን ቲኬት ባለመግዛትና ባለመሳፈር ጭምር መግለጽ ይጀምር።ልብ በሉ!ወያኔ የኢትዮጲያ አየርመንገድን በመጥለፍና ከነንጹሃን መንገደኞቹ ጋር ሊያጋዩ የቃጡ እንደማርታ መብራቱና ዋለልኝ አይነት ሽብር ፈጣሪዎችን እንደ ነጻነት አርበኛ የሚያይ ወሮበላና ዘረኛ ቡድን ነው።በኢትዮጲያ ህዝብ ላይ የሚደረገውን ግፍ በህዝባዊ እምቢተኝነት/civil disobedience/በመገዳደር ማእቀብ በኢትዮጲያ አየርመንገድም ሆነ በሌሎች የዘረፋ ተቋማቱ ላይ የሚጠይቁትን ግን ልማታችንን ለማደናቀፍ የተነሱ ሽብርተኞች ናቸው እንደሚልዎት ጥርጥር አይግባዎት።የወያኔን የአብዬን እከክ ለእምዬ እነተወውና በበኩሌ በግሌ የማውቃቸውን የሌላ አገር ዜጎችንም ወያኔ የሰብአዊ መብት አያያዙን በተጨባጭ እስኪያሻሽል ድረስ በኢትዮጲያ አየርመንገድ አትሳፈሩ እያልኩ ከመቀስቀስ ባሻገር በፈረንጅኛም “Proud of Ethiopian Airlines, yet I urge you to boycott it”በሚል ርእስ መጣጥፍ መልቀቄ አይቀርም።ይህ በእንዲህ እንዳለ በሽብርተኝነት ፈርጆ ወያኔ ካገታቸው ኢትዮጲያውያን አርበኞች መካከል ስለአንዱ ብዙም የማይታወቅ ነገር አንስቼ ልሰናበትዎ።

አንጋፋው ተዋናይ ደበበ እሸቱ አውሮፕላን ስለማብረሩ

የኤልያስን ሃሳብ ለማዳበር ስዳክር ብዙ ኢትዮጲያኖች በተለይም ወጣቶች ስለደበበ እሸቱ ያልሰሙት የሚመስለኝን ነገር ልነግራቸው ወደድኩ።ወዲያውም ጉዳያችን ከአቪዬሽን ጋር የተያያዘ በመሆኑ ጥሩ አጋጣሚ መስሎ ተሰማኝ።ደበበ እሸቱ ወደጥበብ ጥሪ በማዘንበል ወደ ትወና ከመግባቱ በፊት በኢትዮጲያ አየር ሃይል በእጩ መኮንነት ተመዝግቦ የአውሮፕላን አብራሪነት ስልጠና ለመውሰድ ገብቶ ነበር።ታዲያ አብራሪነቱ አቅቶት እንዳይመስሎት የወጣው።በተቃራኒው ብዙዎች የማይወጡትን የመጀመሪያ ደረጃ ስልጠና አጠናቆ አውሮፕላን ለብቻው ያበረረ ከመሆኑም ባሻገር እንኳን በኢትዮጲያ ደረጃ ቀርቶ እንደአሜሪካን አገር ባሉ ሃብታም አገሮች ሳይቀር በጉጉት የሚጠበቀውንና የሚቀናበትን ክንፍ/the coveted wing/የሚባለውን ለመውሰድ የጥቂት ሰአታት በረራ ሲቀረው ከአየር ሃይል ግቢ በተደጋጋሚ እያመለጠ ስላስቸገረ ተባረረ።ለመንገደኞች በሚሰጥና በደርግ ጊዜ በታተመ የአየርመንገዱ ሰላምታ መጽሄት ላይ ደበበ እንደገለጸው የወጣበት ምክንያት “ከብረት የጠነከረ የውትድርና ዲሲፕሊን”ስላልተስማማው ከአየር ሃይሉ በተደጋጋሚ እያመለጠ በማስቸገሩ መባረሩን ገልጿል።በመጽሄቱ ላይ አንብቤ ይሁን ባንድ አጋጣሚ ከአባቴ ጋር ቢራ ላይ የመተዋወቅ እድል ባጋጠማቸው ጊዜ የነገረውን ይዤ ይሁን ተዘነጋኝ እንጂ ሳብ ሳፊር በተባለችው አውሮፕላን ወደ 117 ሰአት ገደማ የበረረ ከመሆኑም በላይ የእነሜጀር ጄኔራል አምሃ ደስታ ኮርሰ እንደነበር ገልጿል።ዛሬ ታዲያ ከዚህ ታሪክ እኔን የሚገርመኝ ደበበ ሰው ሁሉ በዚያን ጊዜ ይሻማበት የነበረውን ግን በቀላሉ የማያገኘውን እድል ካገኘ በኋላ የአየር ሃይል ፓይለት መሆን የሚያስገኘው ዝና/glory/ሳያስጎመዠው ጥሎት በመውጣት እግረመንገዱን ከሃይልና ደም ከማፍሰስ ጋር ለተያያዘ ዝና ደንታ እንደሌለው ማስመስከሩ ነው።በህገአራዊት በሚመራው ፍርደገምድሉ ወያኔ ዘንዳ ይህ ትርጉም ስለሌለው አንጋፋው የጥበብ ሰው ዛሬ ከሌሎች አርበኛ ኢትዮጲያውያኖች ጋር አሸባሪ ተብሏል።ከፍጹም ንቀት ጋር የተያያዘውን እንዲህ ያለውን የለየለት ግፍ ለማስቆም መፍትሄው በተጨባጭ የሚታይ ተግባራዊ እርምጃ ብቻ ነው።አንዳንዶቻችን ኤልያስ ክፍሌን በአወዛጋቢነት በመውሰድ ምናልባት ሃሳቡን ከቁምነገር ባንወስደው እንኳን በመሰሪ ተግባር የተካነው ወያኔ ግን ኤልያስ ዝም ብሎ በድህረ ገጽ ብቻ የሚራቀቅና ጸጉር በመሰንጠቅ ጊዜውን የሚያባክን ሰው እንዳልሆነ ያውቃል።በመሆኑም ወያኔ በውጪ አገር ከሚኖሩ ኢትዮጲያውያን አርበኞች መካከል በግምባር ቀደም የሚፈራው የተግባር ሰዎችን ስለሆነ በየወቅቱ በሚፈበረኩ የፈጠራ ክሶች የኤልያስ አይነቱ ስም በማጣፈጫነት ይጠራል።ባጭሩ በወሬ መራቀቅ ቀርቶ ለወያኔ ማናቸውንም ትብብር የሚነፍግ ተግባር መታየት መጀመር አለበት።ከወያኔ ጋር በመሞዳሞድ ንግድ ማኪያሄድን እንደኑሮ መላ የያዙ ወገኖቻችንም የተሰማሩበት ተግባር ንግድ ሳይሆን ዘረፋ መሆኑን ተገንዝበው ከዚህ ተግባር በአስቸኳይ ሊታቀቡ ይገባል።በዚህ መንገድ የተግበሰበሰ ሃብት ሁሉ በድቡሽት ላይ እንደተገነባ ቤት መሆኑን ከቱኒዚያ ግብጽ ሊቢያና ሌሎችም እንዲያጤኑ እየመከርኩ ያልተማረው ገበሬ አጎቴ “ከፈረጃ ጋር የጠጣ ራሱ ፈረጃ ነው”በማለት የተረተልኝንም እንዲያሰላስሉት እተውላቸዋለሁ።

ሊመይሉልኝ ቢሹ kiflukam@yahoo.com

አይጣል ነው፣ የጦርነት ወሬ ፈነዳ

Tuesday, March 20th, 2012

በክፍሉ ሁሴን

ወያኔ አዲሳባ ገብቶ መላ ኢትዮጲያን በተቆጣጠረ ወሩ ማለትም ሰኔ 1983 “ሰፊ መሰረት ያለው”የሽግግር መንግስት ለማቋቋም ጉባኤ ተቀመጠ።ዴሞክራሲያዊ መስሎ አንጀት ለመብላት የወያኔው አለቃ መለስ ዜናዊ ካላዘነባቸው ነጥቦች አንዱ “ሁላችንም ዘላቂ የሆኑ የህዝቡን ጥቅሞች የሚመለከቱ ውሳኔዎችን ለመወሰን የህዝብ ውክልና የለንም።የጉባኤው አላማ ህዝቡ በራሱ ጉዳይ ተወያይቶ ለመወሰን የሚያስችለውን ዴሞክራሲያዊ ስርዐት መሰረት ለመጣል ነው።”እንዲህ ብሎ ሲያበቃ ግን የኤርትራን ሳታውል ሳታድር ከኢትዮጲያ በይፋ የመገንጠልን አጄንዳ ለጉባኤው አቀረበ።ይህም ሲሆን የዚያን ጊዜ የመለስ የጫካ ጓደኛና የረጅም ጊዜ የወንጀል አባሪ ተባባሪው ኢሳያስ አፈወርቂ ለታዛቢዎች በተመደበው የአዳራሹ ሰገነት ላይ ተቀምጦ ወያኔዎቹ በሻዕቢያ የተሰጣቸውን አጄንዳ ያስፈጽሙ እንደሆነ በአንክሮ ይከታተላል። ከልብ ሳይሆን ለማለት ብቻ የተባለችውን “የህዝብ ውክልና የለንም”የምትለዋን የራሱን የመለስ ወሽካታ ንግግር ከመጥቀስ በተጨማሪ ሌሎች እጅግ አሳማኝ ምክንያቶችን ግርማ ሞገስ ከተላበሰ ፍጹም እርጋታ ጋር በማንሳት ፕሮፌሰር አስራት ወልደየስ ተቃወሙ።በጉዳዩ ላይም ድምጸ ተዐቅቦ አደረጉ።ከኢሳያስ በላይ ይህ ያንገበገበው መለስ ሲቃ በያዘው ድምጽ ስለኤርትራ ህዝብ “ከአማራ ቅኝ አገዛዝ ለመላቀቅ ስለተደረገው ረጅም ፍትሃዊ ትግል” ዲስኩር አደረገ።ከዲስኩሩ ውስጥ ጆሮዬ ላይ እስከዛሬ የምትደውል ቃል ብትኖር “እኛ ጦርነትን የምናውቀው በቴሌቪዥን አይደለም”ያላት ናት።ጦርነትን መስራትም ጭምር እንደሚችሉ በሌላ ጊዜም በተግባር ስላረጋገጡልን ይህ ልናስተባብለው የማንችለው እውነት ነው።ለማንኛውም ፕሮፌሰር አስራት ድምጸ ተዐቅቦ አደረጉ አላደረጉ ኢትዮጲያንና የኢትዮጲያ ጦር ሃይልን ባዋረደው የመንግስቱ ሃይለማሪያም ደደብና ራስ ወዳድ አመራር የተነሳ የኤርትራ ጉዳይ ጦር ሜዳ አልቆ ስለነበር መለስ ከዚህ ግዙፍ አጄንዳው በተጨማሪ ባለ “ሰፊ መሰረቱን” የሽግግር መንግስት በሚፈልገው አይነት ጠፍጥፎ ሰራው።እናም “ናይ ብሄረሰብ ዘመጣጠነ ቤት ምኽሪ ንመስርት”የሚሉ የቃላት ኳኳታዎችን በየጎዳናው በተንጠለጠሉ አቡጀዲዎች ላይ ስናነብ ከረምንና የኤርትራ ሬፍረንደም የ “ኢ.ፌ.ዴ.ሪ መንግስት”ምስረታን አስከትሎ መጣብን።

የሬፍረንደሙን “ናጽነት ወይስ ባርነት”በሚል ቧልት የታሰበውን አማራጭ፣ ወደፊት ኢትዮጲያ ከአዲሲቱ ጎረቤት አገር ጋር የሚኖራትን ግንኙነትና እንዲሁም በኢትዮጲያ የሚኖሩ በግልጽ ለሻዕቢያ በማቀንቀን የሚታወቁ ሰዎችን እጣ ፈንታ በተመለከተ የተነሱትን ህጋዊና ተገቢ ጥያቄዎች በደም ጎርፍ ካጠበ በኋላ መለስ ዜናዊ በየወቅቱ የሚያደርጋትን ድራማ ለመከወን በቴሌቪዥን ብቅ አለ።እናም ከገጠገጠው ገለባ ውስጥ እንዲህ የሚል ነበረበት።ሬፍረንደሙ በፍጹም ዴሞክራሲያዊነት እንደሚካሄድ አትቶ “የኢትዮጲያና የኤርትራ ህዝብ ህንድና ፓኪስታን በሄዱበት መንገድ”እንደማይሄዱ ፍርጥም ብሎ ዋስትና ሰጠ።ለነገሩ ሻዕቢያ አስመራን እንደያዘ ከፈጸማቸው የመጀመሪያ ኢሰብአዊ ወንጀሎች አንዱ “ሃድጊ” ብሎ የሚጠራቸውን ሲቪል ኢትዮጲያዊያኖች ወርቅ ጥርሳቸውን ሳይቀር እያስወለቀ በገፍ ያባረረበት ተግባር የሚዘነጋ አይደለም።እነመለስ ይህን እንዲያስተባብልላቸው አከርካሪቢሱን እንድሪያስ እሸቴን በቴሌቪዥን አቅርበው በኢትዮጲያዊያኖች ግፍ ከሻዕቢያ ጋር አብረው ተሳለቁ።በመለስና ኢሳያስ አይነት መሰሪ ሰዎች የተያዘ ፖለቲካ–ፖለቲካ ከተባለ–አይዘልቅምና መለስ “ከእንግዲህ በኋላ በኤርትራ ድንበር አንድም ጥይት አይጮህም፣ኢትዮጲያና ኤርትራ እንደህንድና ፓኪስታን አይሆኑም” ባለበት አፉ ከሬፍረንደሙ አምስት የጫጉላ አመታት በኋላ “የማያምንበት ጦርነት ውስጥ ለድርጅቱ ውሳኔ ለመገዛት ሲል” በብዙ ሺ የሚቆጠሩ ኢትዮጲያውያን ወጣቶችን ከንቱ ጦርነት ውስጥ ማገደ።ከአማራ ቅኝ አገዛዝ(ሲላቸው ከኢትዮጲያ ይሉታል ኢትዮጲያዊነትንና “አማራነትን”ሆነ ብለው በማምታት) ነጻ ለመውጣት ያደረጉትን ደመከልብ ተጋድሎ ሲያሞካሽላቸው የነበሩትንም በኢትዮጲያ ነዋሪ የነበሩ የኤርትራ ደም ያለባቸውንና “የአይናቸው ቀለም”ለዘረኛ ፖለቲካቸው ያልመጠኑትን ሁሉ–ከራሱና በረከት ስምኦን በቀር በዘፈቀደ፣ በግፍና በገፍ አባረረ።በዚህም የተነሳ የሚደሰኩረውና የሚተምነው ቀመር ሁሉ ለምንምና ለማንም እንደማይበጅ ተቆጥሮ በማያልቅ ሁኔታ አስመሰከረ።የተቀረውን “ብሄር ብሄረሰቦች”በሚል ፈሊጥ እርስ በርስ ያናቆሩትን፣የረሱትንና ያስቀየሙትን ህዝብ በከንቱ ጦርነት ለመማገድም ከእልቂት ቀስቃሺያቸው አንዱ የነበረውን ኢያሱ በርሄን “አፋር አለ በለው፣ቤንሻንጉል አለ በለው፣አማራ አለ በለው”እያለ እንዲያቀነቅን አደረጉት።መሬት ይቅለለውና ወያኔ የበታተነውን ኢትዮጲያዊ ኢያሱ መልሶ በዚያ ዘፈን ሊሰበስብ ሲፋትር አቤ ጉበኛ “እሬትና ማር”በሚል ርእስ በ1965 ያሳተመው መድብል ውስጥ የቋጠራትን ግጥም ያስታውሰኝ ነበር።አቤ የሁለተኛ ደረጃ ትምህርታቸውን እንኳ በቅጡ ሳይጨርሱና ሌላ ምንም አይነት የህይወት ተሞክሮ በሌላቸው ጥራዝ ነጠቅ ውርጋጦች(በራሳቸው ስታሊኒስት ቋንቋ ጀብደኛ ይባላሉ) እጅ ኢትዮጲያ ልትወድቅ እንደምትችል ታይቶት ነው መሰለኝ እንዲህ ነበር ያለው።

“የምድሩን ልክ ሳያውቅ ይህ ትንሽ ጉብል
አለና ተነሳ እኔ ዘር ላካፍል”

“ካርቱም ሄዶ ቀረ” እንዲሁም “ካምፓላ ሄዶ ተቀረቀረ”

Monday, March 5th, 2012

ክፍሉ ሁሴን

ስደት ለወሬ ያመቻል እንዲሉ በ1999 ዓ.ም ስደት ከገባሁ ጀምሮ መጽሐፍ እጽፋለሁ እያልኩ እንደፎከርሁ አለሁ። ሳልሞክር ግን አልቀረሁም። በተለያየ ጊዜና በተደጋጋሚ እያነሳሁ ከጣልኩ በኋላ ለስንፍናዬ መጽናኛ ያደረኩት በቅርቡ እስተወዲያኛው ያሸለበው ስብሃት ገብረእግዚያብሄር በአንድ ወቅት በራዲዮ ቃለምልልስ “ከመጻፍ መኖር ይበልጣል፤ የምንጽፈው ከኑሮ ነውና” ያለውን በመውሰድ ‘መች ኖርኩና ለመጻፍ እጋበዛለሁ’ ብዬ ራሴን ቀስ በቀስ በቁመና እየገዘገዝኩት እገኛለሁ።

ስብሃት ስለኑሮ ሲያነሳ እድሜን በራሱ ብቻ ወስዶ ‘ዘለግ ያለ እድሜ የኖረ የበሰለ ስለሆነም ለመጻፍ የታደለ’ማለቱ እንዳልሆነ ከራሱ በወጣትነት ከተጀመረው የተዋጣ ጸሃፊነት መገንዘብ ይቻላል። አሊያማ በምድሪቱ ላይ መኖርን በተመለከተ ስንት ጉድ እያየሁና በራሴ ላይም ጉዱ እየፈላብኝ ስኖር አምስት አስርተ አመታትን ልደፍን ሶስት ፈሪሃ ብቻ ናት የቀረችኝ። ዝም ብሎ መኖር ሳይሆን መኖርን በማስተዋል ማጀብ፤ ያስተዋሉትንም ወደ ቋሚ ቅርስ ከሚቀይር ተሰጥኦ ጋር ተሰጥኦውን ወደ አደባባይ ሊያወጣ የሚችል ወኔ መታጠቅም እንደሚያስፈልግ ከገባኝ ቆየ። ወዴት ወዴት ጠጋ ካልተባልኩ ከፊሉ የስብሃት ታሪክ በሆነው ደራሲው በተሰኘ መጽሃፉ በአሉ ግርማም ይህንኑ ሲያስረግጥ “እውነተኛ ችሎታ አይናፋር ናት። አደባባይ መውጣት ያቅታታል።

”የእኔን መጽሐፍ ለመጻፍ የሚያበቃ ችሎታ እንተወውና በጋዜጣና መጽሄት በማናቸውም ርእስ ጥልቅ የሆኑ ጽሁፎችን የሚያሳትሙ ግን መጽሐፍ ለመጻፍ ቀርቶ እስከዛሬ በየጋዜጣው የጻፉትን እንኳ እንደ ኒዮርክ ታይምስ ጋዜጣ እውቅ አምደኛ ቶማስ ፍሪድማን በመጽሐፍ ጥራዝ ለማውጣት ዳገት የሚሆንባቸው በርካታ አፍሪካዊያን ጸሃፊዎችን ዩጋንዳ ስደት ከገባሁ ጀምሮ ለማየት ችያለሁ።

የዩጋንዳ ስደተኝነቴን ካነሳሁ ዘንዳ ወደተነሳሁበት ርእስ ልምጣ። ምኞት ብቻ ሳይሆን ከአገሬ ውጪ የተለያዩ ጥቂት የአፍሪካ፣የመካከለኛውና ምናልባትም የሩቅ ምስራቅ አገሮችን አይቀሬ ከሆነው አውሮፓና ሰሜን አሜሪካ ጋር አንድ ቀን ለመጎብኘት እንደምችል ባውቅም ጭራሹኑ ዩጋንዳ ተሰድጄ ከዚያም በአገሬ ፓስፖርት ሳይሆን ለስደተኛ በሚሰጥ የጉዞ ሰነድ እምጓዝበት ጊዜ ሊመጣ እንደሚችል አስቤበት አላውቅም።

ይልቁንስ የጊዜ ጉዳይ እንጂ ወያኔ በዚያም ሆነ በዚህ አንድ ቀን ሊያስረኝ እንደሚችል ገና በማለዳ ግምት ወስጄ ስለነበር ጥቅምት 18,1998 በሌሊት ከቤቴ ጎትቶ ከወሰደኝ በኋላ በሙስና ከሶ ዋስትና በመንፈግ ለአንድ አመት ከማእከላዊ እስከ ቃሊቲ ሲያግተኝ አለመደነቅ ብቻ ሳይሆን የመንፈስ ዝግጅቱ ስለነበረኝ ፈረንጆች በፈጣሪ የተረሳ/god forsaken/ከሚሉት የግፍና የሰቆቃ ካምፕ በጽናት እንድወጣ አስችሎኛል። የመንፈስ ዝግጅቱ ነበረኝ እያልኩ ግን ዳግመኛ በወያኔ ላለመታሰር በተፈታሁ ሶስተኛው ወር ተሰደድኩ። የፖሊቲካ ባላንጣን ሙስናን በመዋጋት ስም እንዲያኮላሹ ቀሪውም በሌብነት ከመከሰስ ውርደት ራሱን ለማዳን ፈርቶ ዝም እንዲል ማድረግ የሚችሉ እንደአቡሃይ ጓዴ የመሳሰሉ ወራዳ ህሊና ቢስ የህግ ባለሙያ ተብዬዎችን በመጠቀም የሚያሳድደው ቢሮ ሊያሳድደኝ ከመነሳቱ አንድ አመት በፊት በገዛ ፈቃዴ የለቀኩትን የኢትዮጵያ መድን ድርጅት በህግ ባለሙያነት ስሰራ ክስ ልመሰርትባቸው የሚገቡኝን ጉዳዮች የማይገባ ጥቅም ለማግኘት ሆነ ብዬ ይርጋ በማሳለፍ፤ እንዲሁም ፍርድ ቤት ሳልቀርብና ክስ ሳልመሰርት የሃሰት ሪፖርት በማቅረቤ በደርግ ጊዜ የወጣውን ልዩ የወንጀለኛ መቅጫ ህግ ጨምሮ ሰማያዊውንም ወያኔያዊውንም ድንጋጌ በመተላለፍ አገር ያሸነፍኩ ሙሰኛ ስለሆንኩ እስተወዲያኛው ዘብጥያ እንዲዘጋብኝ ጠየቀ።

ክሱ ጅል እንደነበረ ህግ ጠቅሼ ማስረጃ መዝዤ አላደክሞትም። ሆኖም እኔን ፍርድ ቤት ሳትቀርብና ክስ ሳትመሰርት እንደቀረብክና እንደከሰስክ አስመስለህ ሪፖርት አቅርብሃል–ያውም የንግድ ድርጅትን በሚመለከት የፍትሃብሄር ጉዳይ ላይ–ተብዬ ከቃሊቲ ማጎሪያ ካምፕ እየተጋዝኩ የምቆምበት የወያኔ ፍርድ ቤት ዳኛ ተብዬዎች ከእኔ በፊት ከአምስት አመታት በላይ ከየባንክ ቤቱና ንግዱ ማህበረሰብ ተለቃቅመው ከታሰሩ በኋላ ዋስትና የተነፈጉትን “ጉዳያችሁን መርምረን ብይን ሰጥተን ነበር ሆኖም የፋይል ካቢኔት ቁልፍ ስለረሳን ተለዋጭ ቀጠሮ እንሰጣለን”እያለ ፍጹም ንቀት የተሞላበት ውሸት ጋር ፍርድ የሚያዛባው ተቋም እኔን በሃሰት ሪፖርት አቅራቢነት ይዳኛል።

ከዚህም የባሰ ወያኔ የኢትዮጵያውያኖችን ደም ለከንቱ ጦርነት በከንቱ ካስፈሰሰ በኋላ ባድሜ ሳትፈረድለት ተፈርዶልኛል ብሎ በትልቅ አገራዊ ጉዳይ ላይ ትልቅ የመንግስት ወንበር ላይ ቁጭ ብለው ከመለስ ዜናዊ ጀምሮ ህዝብን የዋሹትንና በውሸት ጉዳይ ህዝቡን አስገድደው ሰልፍ ያስወጡት ባልተጠየቁበት አገር የአቡሃይ ጓዴ ቢሮ አንድ ተራ ነገረፈጅ ላይ በመናኛ የፍትሃብሄር ጉዳይ ሙስናን የሚያህል የካባ ድንጋይ ይጭንበታል። እንዳልኩዎ ክሱ ጅል ስለነበር ቢያንስ ሙሉ ለሙሉ ህሊናቸውን ያላሟጠጡት ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ህግ ፋክልቲ የተመረቁት ሁለቱ “የሙስና ዳኞች”ብቻዬን ያለአባሪ የተከሰስኩበትን በስልጣን አለግባብ መጠቀም፣ሙስና ገለመሌ የሚለውን ክስ ጥለውና የአቡሃይ ቢሮ እኔን ለመክሰስ ስልጣን እንደሌለው ጠቅሰው የካባ ድንጋዩን ሊያነሱልኝ ፈራ ተባ እያሉ ሞከሩ።

“ጊዜ የሰጠው ቅል ድንጋይ ይሰብራል” የሚለውን እንደኔው ሲሰሙ ያደጉ እንደመሆናቸው ምንም እንኳ በሙያ ክህሎት እግራቸው እጣቢ ባይደርስም ከጎሳው በተጨማሪ ጫካ በነበረ ጊዜ ለነመለስ ሻይ ቡና በማቅረብ ይካድም ነበር የሚባለውንና ለውለታው ዋና “የሙስና ሰብሳቢ ዳኝነት”የተሰጠውን መድህኔ ኪሮስን ወያኔዊ ቁጣ ለማብረድ ሲሉ ሙሉ ለሙሉ በነጻ ከመልቀቅ ታቅበው አንዱን ክስ በመያዣነት አንጠልጥለው “በአፋጣኝ ፍትህ”ከአንድ አመት በኋላ በዋስ ወጥቼ በቀሪው ክስ ላይ እንድከላከል መልካም ፈቃዳቸው ሆነ። ዳሩ ግን በሚቀጥለው ቀጠሮ መከላከያ ምስክሮቼን ይዤ ስቀርብ ዳኛ ተብዬዎቹ በከፊል የተቀያየሩ ከመሆኑም በላይ በተለይም ድንክዬ ሰብእናውን የሚያካክስለት እየመሰለው ከሚለብሰው ካባ በላይ በመኮፈስ ምስክሮችን ሳይቀር የሚሳደበው ኑሩ ሰይድ መከላከያዬ እንደማይሰማና የአቡሃይ ጓዴ ቢሮ ባቀረበው ዝባዝንኬ ብቻ በተለዋጩ ቀጠሮ እንደሚፈረድብኝ ቁርጡን ነገረኝ።

ኑሩ በዚያን ጊዜ በብቸኛ የህግ ሊቅነት በደርግ ባለስልጣኖች ላይ ለቀረበው ክስ ቤት ዘግቶ ፍርድ እንዲጽፍ ተብሎ ከሙስና ዳኝነት ገለል ብሎ ነበር። እናም ያንን ግዳጁን አጠናቆ ከፍ ባለ “የፍትህ ስሜት”በእኔ ላይ እንደሚፈረድ አስታወቀኝ። ደግነቱ ሙስና የተባለው ጨዋታ የታለመው ስዬንና ተከታዮቹን ለማስተንፈስ ስለነበር ያም ግቡን ስለመታ የወያኔም አብዮት እንደደርግ አብዮት ሰክኖ ሰው የመቀርጠፍ ሃራራው ለጊዜው በመጠኑ ጋብ ስላለለት በሙስና ሰበብ የሚያግታቸውን ሁሉ ዋስትና መንፈግና የጉዞ ማእቀብ መጣል አቁሞ ነበር። እናም ኑሩና መድህኔም በኔ ላይ የጉዞ ማእቀብ ከማስተላለፍ ተዘናጉ።

እንኳን እኔን የለየለት ወንጀለኛንም ለመዳኘት የሞራል ብቃቱ የሌላቸው ሰዎች በኔ ላይ ፍርድ ሊያስተላልፉ ነው ከሚለው ጭንቀት በተጨማሪ ልዩ ትኩረት የሚሻ አዲስ የቤተሰብ ሁኔታ ለመጀመሪያ ጊዜ ስደትን እንዳሰላስል አደረገኝ። ለስደት ተስፋ ከፈነጠቀችልኝ አገሮች አንዷ ቤልጂየም ብትሆንም በኢሚግሬሽን ቢሮክራሲያዊ ዳተኝነቷ የተነሳ እህል ውሃዬ ወደዩጋንዳ ሆነና ወደዚሁ እንዳቀና ከባለቤቴ እና ጥቂት የቅርብ ወዳጆቻችን ጋር ተመካክረን ወሰን። አጨቃጫቂ የነበረው ጉዳይ ጉዞ በአየር ይሁን ወይስ በመኪና ድንበር ተሻግሮ የሚል ነበር። ስሜ በውስጠ ታዋቂ ለኢሚግሬሽን ተላልፎ ሊሆን ይችላል የሚል ፍርሃት ቢኖርም በበኩሌ የመጣው ቢመጣም በአየር ካልሆነ በመሬት በኬንያ በኩል እንደማላልፍ ወሰንኩ።

ደግነቱ ወያኔ አንዴ ከከረቸመኝ በኋላ ረስቶኛል ወይም የትም ቢሄድ ምንም ከማያመጡት የውጪ አገር ጯሂዎች አንዱ ይሆናል ብሎ ንቆኛል። ያም ሆነ ይህ ዩጋንዳ የቪዛ ጥያቄዬን ወዲያው ስለተቀበለች ኑሩ በአሳዳሪው መድህኔ ኪሮስ ወያኔያዊ የዛር ፈረስ ሊፈርድብኝ እንደነገ እኔ እንደዛሬው በኢትዮጵያ አየርመንገድ ቦይንግ 767 በካፕቴን አረፋይኔ አብራሪነት እብስ አልኩ። እናም ከአንድ ሰዓት አርባ ደቂቃ በረራ በኋላ ኢንቴቤ አረፍኩ። በመሆኑም እንደአቅሚቲ እኔም በዘውዴ ረታ በቀዳማዊ ኃይለሥላሴ ዘመነ መንግስት የኤርትራ ጉዳይ በሚለው መጽሐፍ ላይ “የተከበሩ ስደተኛ”ተብለው እንደተገለጹት ወልደአብ ወልደማሪያም ፓስፖርት ተሰጥቶኝ በአውሮፕላን እየተንፈላሰስኩ መጥቼ ስደተኛ ለመሆን በቃሁ። ልዩነቱ እኔ እንደወልደአብ ወልደማሪያም የኢትዮጵያ አይደለም ይገንጠል የምለው አገር የለኝም። ተወልጄ ያደኩባት አዲስ አበባ መሃል ከመሆኗም በላይ የገዛ አያቶቼንና ወላጆቼን ከኢትዮጵያ ዋና ዋና ማእዘናት በማምጣት እኔን ከፈጠረች በኋላ ፍጹም ኮስሞፖሊታን ብቻ ሳይሆን አገር ወዳድ አድርጋኛለች–አገር ወዳድነት ዛሬ የፋራ ታሪክ ቢመስልም።

እህል ውሃ በዩጋንዳ

እንዳልክዎት የውጪ አገሮችን የመጎብኘት እቅድ ቢኖረኝም ዩጋንዳ በህልሜም በውኔም መጥታ አታውቅም። ያውም እሸሸግበት ጥግ በመፈለግ አንድያዬን ተፈጥሜ ልኖርባት?እንዴት አድርጌ ላስበው እችላለሁ?የሆነው ግን እንዲያ ነው ተስፋዬ ገብረአብ ማለት እንደሚወደው። እናም የውጭ አገር ልጎበኝ እንደምችል የሚያሳየው የመጀመሪያው መርገጭ/ብሩህ አእምሮ ያለው ያልተማረው ጎጃሜ አጎቴ ቪዛን የመሳሰሉ ማህተሞችን መርገጭ ይላቸዋል/በፓስፖርቴ ላይ የተመታው አዲስ አበባ በሚገኘው የዩጋንዳ ኤምባሲ ሆነ። በወቅቱ ከወያኔ ፍርደገምድልነት ማምለጤን እንጂ በፓስፖርቴ ላይ የተመታውን የመጀመሪያ የሆነውን የመርገጩን ጉዳይ እምብዛም አላጤንኩትም። ምንም እንኳን ከዚያ በኋላ የተለያዩ የአፍሪካ አገሮችን የመጎብኘት እድል ቢያጋጥመኝም በኢትዮጵያዊነቴ ያገኘሁት ፓስፖርት ላይ በዩጋንዳ መንግስት የተመታው መርገጭ ግን የመጀመሪያውም የመጨረሻውም ሆነ።

ለስደተኛ አለማቀፍ መጓጓዣ አገልግሎት እንዲሆን የሚሰጠውን ሰነድ ስወስድ በወያኔ ኢሚግሬሽን የተሰጠኝን ፓስፖርት መመለስ ቢጠበቅብኝም በዚህ ፓስፖርት ዩጋንዳ ከመምጣቴ ጋር የተያያዙ አንዳንድ አስገራሚ መገጣጠሞችን ያጫወትኳቸው ዩጋንዳውያን ባለስልጣን ወዳጆቼ ፓስፖርቱን በታሪካዊ ሰነድነት እንድይዘው ፈቀዱልኝ። በነገራችን ላይ ይህ በወያኔ አገዛዝ ሙስና ሆኖ በትላቁ ሊያስከስስ ይችላል። ይህን ያነበበ አፍቃሪ ወያኔም ለአሳዳሪዎቹ ነግሮ በዩጋንዳ ባለስልጣናት ሊያሳቅለኝ አይሞክርም አይባልም። ከሆነ ከዩጋንዳዊያን ወዳጆቼ ጋር ሆነን እንደአፍሪካን አሜሪካኑ ተዋናይ ኤዲ መርፊ ሆዳችንን ይዘን እንስቃለን። አሁን ወደመገጣጠሞቹ ልውሰዶት።

ነፍስ ካወቅሁ ለመጀመሪያ ጊዜ በአይኔ ያየሁት የውጭ አገር መሪ ዩጋንዳዊውን ኢዲ አሚንን ነው። በ1967 ሰኔ ወር አካባቢ ይመስለኛል ከታናሼ ታናሽ ጋር ከሆነ ቦታ ቦሌ ሩዋንዳ ኤምባሲ ወደሚገኘው መኖሪያ ቤታችን ለመመለስ በወሎ ሰፈር በኩል ስናቋርጥ ከቦሌ ማተሚያ ቤት ጀርባ/ማተሚያ ቤቱ በዚያን ዘመን አልነበረም/ወደሚገኘው ዩጋንዳ ኤምባሲ አካባቢ ስንቃረብ የሰው ግርግርና በርካታ የታጠቁ ወታደሮች አየን። የታጠቁ ወታደሮች ቢኖሩም ክፉው 1969 ገና ስላልባተ ሲቪሉ ህዝብ ያለምንም መሸበር አንድ ቦታ ተክሎ ወደአንድ አቅጣጫ አተኩሯል።

ሁኔታው የኛንም ትኩረት ስለሳበው በእድሜ እኩዮቻችን የሆኑ የአስር የአስራ አንድ አመት ልጆች ፈልጌ ምን እንደተፈጠረ ጠየቅሁ። ከልጆቹ ቀድሞ አንድ ጎልማሳ ኢዲ አሚን ከጀኔራል ተፈሪ ባንቲ ጋር ኤምባሲውን ለመጎብኘት እንደመጣ ነገረን። ገና በማለዳ ኢዲ አሚን ከአካሉ ግዝፈት በተጨማሪ የዩጋንዳ ንግስናው ታሪኩን አግዝፎት ስለነበር እኔም ወንድሜም ሳንነጋገር በጨረፍታም ቢሆን ሳናየው እንደማንነቃነቅ ተስማማን። አመርቂ ባይሆንም ከነአጃቢዎቻቸው ከኤምባሲው ሲወጡ ጀኔራል ተፈሪንና አሚንን ለማየት ቻልን።

ከአመታት በኋላ የቪዲዮ ቴክኖሎጂ ሲመጣ ቴክኖሎጂውን በማስገባት ግምባር ቀደም ከሆኑ የቦሌ ዲታዎች ቤት በአንዱ በልጃቸው አማካኝነት Raise & fall of Idi Amin Dada የተሰኘው ፊልም በመጀመሪያ በቪዲዮ ያየሁት ለመሆን በቃ። ይባስ ብሎ በኢንግሊዚኛ ንባብ ከልብወለድ ኢልብወለድ መጽሐፍ ስሸጋገር እጄ የገባው የመጀመሪያ መጽሐፍ በአሚን ዘመነመንግስት የጤና ጥበቃ ሚኒስትር የነበረው ሄንሪ ኪምባ የተባለው ሰው ስለአሚን አገዛዝ ጨካኝነት ከተሰደደ በኋላ የጻፈው A State of Blood ሆነ። እንደነገርኩዎ መሰደዴ ሐቅ ሲሆን ለውጭ አገር ጉዞ በመጀመሪያ መርገጭ ያስመታሁባት ዩጋንዳ እህል ውሃዬ ከመሆን አልፋ በአጋጣሚ ከህይወቴ ጋር የሚገጣጠመው ታሪኳ እየመሰጠኝ ይሄድ ገባ።

ከሁሉም በላይ እስከዛሬ የሚያስደምምኝ ዩጋንዳ ከመምጣቴ በፊት በቅኝ ስለተገዙ አገሮች የነበረኝ ግምት እዚህ ከመጣሁ በኋላ እጅጉን ሲፋለስ ልጽፍበት ይገባል ብዬ አንዳንድ መረጃዎች ሳሰባስብ በፊት ያላጤንኩት ሌላ አጋጣሚ ከዩጋንዳ አመጣጤ ጋር መገጣጠሙ ነው። ዩጋንዳ ከመምጣቴ በፊት ሁሉም ባይሆንም አብዛኞቹ በቅኝ የነበሩ አገሮች ከእኛ በተሻለ ዘመናዊነት ላይ ይገኛሉ የሚል ግምት ነበረኝ። በሚያሳዝን ሁኔታ ኢንቴቤ አርፌ ወደካምፓላ ጉዞ የጀመርኩ የመጀመሪያውኑ ቀን ይህ ግምቴ ያላንዳች የችሮታ ዘመን ወዲያውኑ ተንኮታኮተ። አንዳችም የዘመናዊ ከተማ እቅድ አይታ የማታውቅ የምትመስለው ካምፓላ ካፒቴን አረፋይኔን ሁሉ እንድጠረጥር አደረገችኝ።

አንጋፋው ካፒቴን በናቪጌሺን ስህተት አርባ ምንጭ ጥሎኝ የሄደ እስኪመስለኝ ድረስ እንግሊዝ ያቀናው አገር መሆኔን ተጠራጠርኩት። መንገዳቸው ሁሉም ቦታ እንደክፉ ገላ የፈራረሰ ቀኑን ሙሉ የሚቆየው የትራፊክ ጭንቅንቅ በየቦታው ከሚወጣው ልክየለሽ ሙዚቃና የሽያጭ ማስታወቂያ ጋር ተዳምሮ ከፍተኛ የአእምሮ ጭንቀት የምትፈጥር ከተማ ነው የጠበቀችኝ። ሳይደግስ አይጣላም እንዲሉ ዩጋንዳውያንን ግን ቄጠማ/ከተስፋዬ ገ/አብ የኮረጅኩት ሌላ ቃል መሆኑ ነው/ሆነው ነው ያገኘኋቸው። እናም በገዛ አገራቸው ሳይጠሩኝ ልሸሸግ መጥቼባቸው አገራቸውን ሳማርርና ስነጫነጭባቸው እኔኑ መልሰው ከማጽናናትና በሆደሰፊነት የምለውን ሁሉ በቅንልቦና ከማዳመጥ ውጪ ‘አገርህ አይደለም ስትሮጥ መጥተህ ምን ታላዝናለህ’በሚል ስደተኝነቴን ሊያስታውሰኝ የሚሞክር ዩጋንዳዊ አጋጥሞኝ አያውቅም። በተቃራኒው በአገራቸው ፖሊቲካዊ ማህበራዊና ኢኮኖሚ ነክ ጉዳዮች ሁሉ የሚመስለኝን በአደባባይ በፈለኩት የመገናኛ ብዙሃን እንድተች በየጊዜው የሚጋብዙኝ ከመሆኑም ባሻገር ትንሽ ፍራንክም ካለኝ መሬት ገዝቼ ኑሮዬን እዚሁ እንዳደላድል ይመክሩኛል። እግረመንገዳቸውንም ስለእኛ በቅኝ አለመገዛትና ኮሎኒያሊዝምን አፈርድሜ ስላስጋጥንበት ታሪክ የተማሩት ዛሬ ከሚያዩን አሜሪካና ካናዳ ናፋቂ ኢትዮጵያዊያኖች ጋር እንደሚጋጭባቸው ሳያለዝቡ ይነግሩኛል።

ይህኛው ራሱን የቻለ ታሪክ ስለሚወጣው በይደር አቆይቼ ዩጋንዳ እያደር እየሰነበትኩ በሄድኩ መጠን በአስተናጋጄ አገር ህዝብ ላይ እንዲሁም ዩጋንዳ ኗሪ በሆኑ የገዛ ራሴ ወገኖች ላይ የማየው በፍጹም ተቃርኖ የተሞላ ህይወት ይበልጥ እንድጽፍበት ይጎነትለኝ ገባ። በዩጋንዳውያኑ መመሰጥና መደመም ሲበዛብኝ ጉንተላውንም ለማስታገስ ዩጋንዳ በገባሁ በሁለተኛው አመት የሆነ ነገር በፈረንጅኛ ልጽፍ ተነሳሁ። ለጽሁፌ የሚሆኑ አንዳንድ መረጃዎች ሳሰባስብ ታዲያ ኢዲ አሚን በመፈንቅለ መንግስት ስልጣን የያዘው እ.ኤ.አ ጃኑዋሪ 25,1971 እንደነበር ተረዳሁ። ይገርምዎታል እኔም ዩጋንዳ እግሬ የረገጠው በዚያኑ ቀን አሚን ከእሱ በፊት የነበረውን ሚልተን ኦቦቴን በገለበጠበት ሰላሳ ስድስተኛ አመት እ.ኤ.አ በ2007 ነው።

ዩጋንዳ በገባሁ ሁለተኛው አመት ማለትም እ.ኤ.አ በ2009 ከምኖረው ኑሮ ከማየውና ከምታዘበው ጋር ተጨማምሮ በዚያን ጊዜ አርባ ሰባተኛ የነጻነት በአሏን ለማክበር በዝግጅት ላይ በነበረችው ዩጋንዳ ላይ “Two years in a nation only two years older than me” በሚል ርእስ የሆነ ስንክሳር ጀምሬ ከስንፍናዬ ጋር አንድ ፋታ የማይሰጥ የኑሮ ጣጣ ሲያጋጥመኝ ተውኩት። ፌሎውሺፕ በሚሉት ስታይል እንድጽፍ ብቻ እዚሁ ዩጋንዳ ኑሮ የሚባለውን ጣጣ የሚሸክፍልኝ ባገኝ ማን ያውቃል ያኔ ከጀመርኩት በበለጠ ልጽፈው እችላለሁ። ተተመኙ አይቀር እንዲህ ነው። ገሃዱ አለም ለምኞት ብዙም በር ስለማይከፍት ምኞቱን ትቼ በአምስት አመት የስደት ኑሮ ውስጥ አምስት የመኖሪያ ሰፈር የቀያየርኩባት ዩጋንዳ ሃምሳኛ የወርቅ ኢዮቤልዩ የነጻነት በአሏን ለማክበር በዝግጅት ላይ ስለሆነች ጀምሬ ከተውኩት ስንክሳር የበለጠ የማውጣት እድል እንደመጣልኝ ይሰማኛል። ደበበ ሰይፉ “አንቺ ልጅ ኩሪባቸው፤በእንግሊዝ አናግሪያቸው”በሚል ዘፈን የዘፈነውንና ያዘፈነውን ትውልድ “ረግረጋማ”ሲል በብርሃን ፍቅር ቅጽ 1 መግቢያ ላይ የዠለጠበት ሊመለከተኝ ቢችልም የምጽፈው ከሆነ እየጎለደፍኩም ቢሆን በእንግሊዝ አፍ ይሆናል። ስለምን ዩጋንዳውያንም እንዲያነቡኝ።

ይሁንና ዩጋንዳንና ዩጋንዳውያንን ያስተዋወቀኝ ስደት ግን ከመጀመሪያው ጀምሮ ቀናኢ ስለነበር ይበልጥ በስደት በራሴ ስደተኝነትና በኔ ቢጤ ስደተኞች ላይ ብቻ እንደቆዝም አስገደደኝ። ሃ ብዬ ቁዘማውን ስጀምር ታዲያ ትዝ ያለኝ በልጅነቴ ያነበብኩት በቅርቡ ህይወታቸው ባለፈው ማሞ ውድነህ የተደረሰው “ካርቱም ሄዶ ቀረና ዲግሪ ያሳበደው”በሚል የተለያየ ርእስ ሁለት አጫጭር ታሪኮችን በአንድ ላይ ያሳተሙበት መጽሐፍ ነው። ያነበብኩት የአራተኛ ወይም የአምስተኛ ክፍል ተማሪ በነበርኩበት 1966 ወይም 1967 ስለነበር በአብዛኛው ተረስቶኛል። የሁለቱም አጫጭር ልብወለዶች ጭብጥ ግን በድንግዝግዝም ቢሆን ይታወሰኛል።

ከኔ ጋር የሚያያዘው “ካርቱም ሄዶ ቀረ”ታሪክ የሚያጠነጥነው በኤርትራ ፌዴሬሽን መፍረስ ወይም በመሃል አገር አገዛዝ ቅሬታ የተሰማቸው የኤርትራ ተወላጆች በመናኛ ብስጭት አኩርፈው ወደ ሱዳን ከተሰደዱ በኋላ ኑሮ ሳይመቻቸው ቀርቶ ለመመለስ እየፈለጉ ካፈርኩ አይመልሰኝ አባዜ የተነሳ እዚያው ካርቱም እየማቀቁ እንደቀሩ የሚያሳይ ነበር። በነገራችን ላይ መጽሀፉ የታተመው በሃምሳዎቹ መጀመሪያ ገደማ ነበር። እና እኔንም ስደት ካምፓላ ጎትቶ ካመጣኝ በኋላ በዚያን ጊዜ በጥጋብ መልክ የተጀመረው የኤርትራዊያን ክህደትና ስደት እንዴት ከአስር እጅ እጥፍ በላይ አድጎ አሁን የሚያሰድድ ተጨባጭ ምክንያት ኖረም አልኖረ እንዴት የኑሮ መላ እንደሆነ ሳይና ይህንኑም በሽታ እንዴት ወደኛ እንዳጋቡብን ስመለከት እኔስ ለምን “ካምፓላ ሄዶ ተቀረቀረ”በሚል አልጽፍም ብዬ ብዙ ጊዜ ተነስቼ ነበር። ከመጻፌ በፊት ግን “ካርቱም ሄዶ ቀረ”ን መከለስ እንዳለብኝ ተገንዝቤ እስከዛሬ በይደር አቆይቼዋለሁ። ነፍሳቸውን ይማርና የማሞ ውድነህን ይህን መጽሐፍ የት አገኝ ይመስልዎታል?ለመሆኑ እኔ Literary vintage ብዬ የምጠራቸውን እንዲህ ያሉ የቆዩ የጥበብ ስራ በድጋሚ ለማሳተም የሚያስብ ተቋም ወይም በጎአድራጊ ግለሰብ ሰምተው ያውቃሉ?

(አስተያየት ሊሰጡኝ ቢሹ kiflukam@yahoo.com)