Author Archive

ክርስቲያኑ ኢትዮጵያዊ መብቱን ለማስከበር ያልቻለባቸውና የማይችልባቸው ምክንያቶች

Friday, February 15th, 2013

  • ይህ ጽሑፍ የአቅማቸውን ጥቂት ነገር ለማድረግ የሚተጉትን ላይመለከት ይችላል።
(ደጀ ሰላም የካቲት 8/2005፤ ፌብሩዋሪ 15/2012/ PDF)፦ ከቅርብ ዓመታት ወዲህ በአገራችን በኢትዮጵያ እየተስፋፋ በመጣው እምነትን በነጻ የማራመድ መብት ገፈፋ ዋነኛ ተጠቂ ከሆኑት ኢትዮጵያውያን መካከል ኦርቶዶክሱ ክፍል ዋነኛ ተጠቃሽ ነው። በወታደራዊው የደርግ ዘመን የነበረውን ግፍና መከራ እንኳን ለጊዜው ብናቆየው “የሕዝብ ብሶት ወለደኝ” ያለው የኢሕአዴግ መንግሥት ከተመሠረተ ወዲህ ቤተ ክርስቲያናችን በዓይነ ቁራኛ ከመታየት እስከ የ“ነፍጠኛ ጎሬ” እስከመባል ድረስ ብዙ ዘለፋ አስተናግዳለች። ከዚያም ገፋ ሲል በአንዳንድ አክራሪዎች ምእመናኗ ታርደዋል፣ አብያተ ክርስቲያናት ተቃጥለዋል፣ ከየአካባቢው እንዲፈናቀሉ ተደርገዋል። ለዚህም በስልጣን ላይ ያለው ፓርቲ የሚያራምደው ፖሊሲ ሁነኛ ምክንያት ነው።


ከዚህ በፊት የተቻኮለ የፓትርያርክ ምርጫ፣የገበያ ግርግር …’ ይሆናል በሚል ርዕስ ነሐሴ 11/2004 ዓ.ም፤ ኦገስት 17/ 2012/ባቀረብነው ጽሑፍ ላይ እንዳተትነው ኢሕአዴግ ገና በትግል ላይ ከነበረበት ዘመን ጀምሮ ቤተ ክርስቲያናችንን በተመለከተ የያዘው አቋም “ቤተ ክርስቲያኒቱ የጠላት ወገን” እንደሆነች ያስቀመጠ፣ ሌሎች እምነቶችን በተለይም እስልምናን “በተጨቋኝነት” የፈረጀ ስለዚህም ይህንን የተጨቆነ እምነት “በማነቃቃትና ኃይል በመስጠት” ከኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ጋር እንዲገዳደር ያለመ፣ በመጨረሻም ቤተ ክርስቲያኒቱን ቀስ በቀስ በማዳከም የእርሱ አሽከር እንድትሆን በማድረግ ላይ ያተኮረ ነበር። ይህንን ዓላማውን ለማስፈጸምም ከዋናው የቤተ ክህነቱ አስተዳደር የተለየና የፓርቲውን ዓላማ የሚያራምድ ቤተ ክህነት ለመመስረት በመወሰን የረዥም ጊዜ ዓላማና ግብ ይዞ ሲንቀሳቀስ ቆይቷል። (አዲስ አበባን ከመቆጣጠሩ በፊት በትግራይ ፓርቲውን በፓርቲው የሚመራ ሁለተኛ ቤተ ክህነት አቋቁሞ እንደነበር ይታወሳል)።፡የራሱን አባላትም ወደ ታላላቅ ገዳማት በማስገባት በመነኮሳት ስም ዓላማውን እንዲያስፋፉ ሲያደርግ እንደቆየ የፓርቲው መሥራች ዶ/ር አረጋዊ በርሄ በመጽሐፋቸው አስፋፍተው ገልጸዋል።

ይህ መጽሐፍ ያተታቸው ብዙ ሐሳቦች አሁን በተግባር ላይ መዋላቸው በተግባር እየታየ ያለ እውነታ እንጂ መላምታዊ ሐቲት ወይም በአንድ ወቅት ብቅ ብሎ የጠፋ የፓርቲው ሐሳብ እንዳልሆነ ግልጽ ነው። በመነኮሳት ስም ያደራጃቸው አባላቱም በቤተ ክህነቱ የተለያዩ እርከኖች ላይ በመቀመጥ ቤተ ክርስቲያናችን የክርስቶስ ሳይሆን የአንድ የፖለቲካ ፓርቲ ዓላማ ማስፈጸሚያ እንድትሆን አስገድደዋታል። ወታደራዊው መንግሥት እንኳን ያላደረገውን የቤተ ክህነቱን መዋቅር ከዋናው እስከ አጥቢያው ካባ በለበሱ ካድሬዎች በማደራጀት ቤተ ክርስቲያኒቱ የክርስቶስ መንግሥት ሳይሆን የኢሕአዴግ መንግሥት አገልጋይ እንድትሆን አድርገዋታል።

ይህም ሳያንስ በልማትና በዕድገት ስም የቤተ ክርስቲያኒቱ ይዞታ ከመደፈሩም ባሻገር የገዳማት ርዕስ የሆነውን የዋልድባን ድንበር በመጋፋት እና የቅድስና ኑሮውን በመግሰስ አበው ገዳማውያን የመከራ ኑሮ እንዲኖሩ በማስገደድ ላይ ይገኛል። ታዲያ እዚህ ላይ ተያይዞ አብሮ የሚነሣው ነገር “ሃይማኖቱን የሚወደው፣ ለእምነቱና ለማተቡ ሟች የሆነው ክርስቲያን ሕዝብ እንዴት ዝም አለ? መንግሥትስ እንዴት የሕዝቡን ስሜት ከቁብ ሳይቆጥረው ቀረ? ሕዝቡንስ እንዴት እንዲህ ሊንቀው ቻለ? ሙስሊም ኢትዮጵያውያን ‘ድምጻችን ይሰማ’ ሲሉ የክርስቲያኑ ዝምታ ከምን የመነጨ ነው?” ወዘተ የሚለው ጥያቄ ነው።

እንደ እኛ እምነት ከዚህ የበለጠ መከራና ችግር በቤተ ክርስቲያኒቱ ላይ ቢወርድም አብዛኛው ክርስቲያኑ ሕዝብ፣ ካህናቱ እና ሲኖዶሱ ምንም ዓይነት የተቃውሞ ድምጽ ሊያሰሙ አይችሉም። የሚቃወሙ ጥቂት ድምጾች ከተገኙም በርግጠኝነት በውጪ አገር ካለው ክርስቲያን፣ ካህን ወይም ጳጳስ ብቻ ሊሆን ይችላል። እነርሱም ምንም ችግር እንደማይገጥማቸው እርግጠኛ ከሆኑ ብቻ ነው። የሩቁን ጊዜ ብንተወውና አሁን በመደረግ ላይ ያሉትን ሁለት የመብት ጥሰቶች ማለትም የዋልድባን ገዳም ማረስ እና ከሕዝቡ ይሁንታ ውጪ 6ኛ ፓትርያርክ ለመሾም (ለማስቀመጥ) የሚደረገውን ሩጫ እንኳን ለመቃወም ክርስቲያኑ ለምን እንዳልቻለ መጠየቅ እንችላለን። (የተቃወሙና የሚቃወሙ ጥቂት ድምጾች ቢኖሩም እነርሱም ከውጪ አገር የሚሰሙ ብቻ መሆናቸውን ሳንዘነጋ ነው ታዲያ)። ስለዚህም የዚህ ዝምታ ምንጩ የተለያየ ቢሆንም ለመወያያ እንዲሆኑ የሚከተሉትን ሐሳቦች እናቀርባለን።


  1. መብት የሚለውን ቁምነገር በትክክል አለመረዳት፤

ክርስቲያኑ ክፍል እንደማንኛውም ኢትዮጵያዊ ሁሉ “መብት” የሚለውን ቁምነገር በቅጡ ገና አልተረዳም። መብት ጠመንጃ በያዙ ሰዎች ችሮታ የሚታደለው እንደሆነ እንጂ ከእግዚአብሔር ያገኘው ነጻ ሥጦታ መሆኑን አይገነዘብም። ፊደል ያልቆጠረው ማይም ሕዝብ ብቻ ሳይሆን ኮሌጅ የበጠሰው ምሩቅም ቢሆን ተመሳሳይ ሐሳብ የሚያራምድ ሕዝብ ነው። ስለዚህም መንግሥት የሚያደርስበትን የመብት ገፈፋ ሲችል በመለመን፣ ሳይችል ደግሞ ጀርባውን አጉብጦ በመታገስ ወደመቃብር ይወርዳል እንጂ “መብቴ” ብሎ አይጠይቅም።

አንድነት የለውም፤
ከሌላ እምነት ተከታይ ኢትዮጵያውያን በተለየ ክርስቲያኑ ክፍል የተጎዳው አንድነት በማጣቱ ነው። ከሊቃነ ጳጳሳት ጀምሮ እስከ ጥቃቅን ማኅበራት ድረስ አንድነት የሚባል ነገር የለም። ጳጳሳቱ ተከፋፍለው ሁለት ሲኖዶስ አቋቁመናል ብለው ከሚነታረኩ ባሻገር ከእነርሱ በታች ያለውም እዚህ ግባ በማይባል በተለያየ ምክንያት የተከፋፈለ ነው። ይህንን ክፍፍል አንድ ሊያደርግ የሚችል ተአምር ካልተፈጠረ በስተቀር ሊያሰጋው የሚችል ተቃውሞ ሊመጣ እንደማይችል ኢሕአዴግም ጠንቅቆ ያውቃል። ስለዚህ ሕዝቡ ብዙ ቢሆንም፣ ምእመኑን ለእምነቱ ሟች ቢሆንም አንድነት እስከሌለው ድረስ ኃይሉ ከንቱ ይሆናል። ሆኗልም። ሙስሊሙ ሕብረተሰብ ከዚህ የተሻለ አንድነት አለው፤ ይህንንም አንድነቱን በዚህ አንድ ዓመት ባሳየው እልህ አስቆጨራሽ የመብት ትግል በገሃድ አሳይቷል። ፕሮቴስታንቱ ክፍል ሙሉ በሙሉ በሚባል ደረጃ የመንግሥት ቀኝ እጅ በመሆን በማገልገል ላይ በመገኘቱ የሥርዓቱ ዋነኛ ተጠቃሚና የሥርዓቱ ዋነኛ ደጋፊ ሆኗል።

ትክክለኛ መረጃ የለውም፣
ክርስቲያኑ ብቻ ሳይሆን አጠቃላይ ኢትዮጵያዊው ትልቅ የመረጃ እጥረት አለበት። መንግሥት የመገናኛ ብዙኃንን በሙሉ በግል አፍኖ በመያዙ ሕዝቡ የሚያየውም የሚሰማው ነገር የለም። ጋዜጦችና መጽሔቶች አሉ ከሚባሉ ጠፍተዋል የሚለው ይገልጻቸዋል። ያሉትም ቢሆን ውኃ ውኃ የማይል ጽሑፍ ከማንሸራሸር ውጪ መረጃ በመፈንጠቅ ሕዝቡን ከጨለማ ወደ ብርሃን ሊያመጡ የሚችሉ አይደሉም። አገልግሎት እንዲሰጡ የተፈቀደላቸው ሬዲዮኖች “ስፖርት፣ ሙዚቃ፣ ቫለንታይንስ ዴይ አደጋገስ” ወዘተ ካልሆነ ጠለቅ ያለ ሐሳብ ማቅረብ አይችሉም። አይፈረድባቸውም። የተለየ መረጃ ሊገኝበት የሚችለው ነጻ መስኮት (ኢንተርኔቱ) ደግሞ ተቆልፏል። ስለዚህ ይህ መረጃ በማጣት የታወረ ኅብረተሰብ ምኑን ከምኑ ሊያደርገው ይችላል?

“እግዚአብሔር ያውቃል፣ የእግዚአብሔር ፈቃድ” በሚሉ ርዕሶች ዙሪያ ያለው የተሳሳተ የጽድቅ እና የኃጢአት ትምህርት፣
አብዛኛው ክርስቲያን  እምነቱን አፍቃሪና አክባሪ ነው። መምህራኑን ይሰማል፣ ቃላቸውንም ይፈጽማል። ነገር ግን ከሚሰጡት ትምህርቶች አብዛኛዎቹ ሆን ተብሎም ይሁን በሌላ ምክንያት ሕዝቡን የሚያደነዝዙ፣ የጥንት ኦርቶዶክስ አባቶቹ እንዳደረጉት ለአገሩ፣ ለእምነቱና ለቤተሰቡ ከመሞት ይልቅ በቅኝ ግዛት እንደተያዙት ሌሎች አፍሪካውያን መጽሐፍ ቅዱሱን ገልጦ ሰማይ ሰማይ ብቻ የሚያይ ደካማ አድርገውታል። አባቶቹ አድዋ ላይ ታቦቱን ይዘው እንዳልውጡ፣ ሰማዕቱ አቡነ ጴጥሮስ ሰዉንም ምድሪቱንም ለፋሺስቶች እንዳይገዙ ገዝተው እንዳልተሰዉ፣ ብዙዎቹ አበው ለአገራቸውና ለእምነታቸው ደማቸውን እንዳላፈሰሱ አይነገረውም። ስለዚህም በስመ ኦርቶዶክስ የሚመራው ክርስትና ከጥንቱ “አትንኩኝ ባይ” ኦርቶዶክስ ጋር ምንም ግንኙነት ያለው አይደለም።

የተሳሳተ ትርጉም እየተሰጣቸው ሕዝቡ እንዲደነዝዝባቸው ከሚያደርጉት ትምህርቶች መካከል “ሁሉንም ለእግዚአብሔር እንስጠው፣ “እግዚአብሔር ያውቃል፣ እኛ የእርሱን ጊዜ እንጠብቅ” የምትል የራስን ኃላፊነት ሳይወጡ በስንፍና የመቀመጥ አደንዛዥ ትምህርት አንዷ ናት። እግዚአብሔርማ ሁሉን ያውቃል። ምን ጥርጥር አለው። ነገር ግን አዋቂነቱ በዓለም ላይ የሚፈጸመውን ግፍና መከራ ሁሉ እንዲከወን እንደፈቀደ መቁጠር ኑፋቄ ነው።

በዓለም ላይ በየሰከንዱ ብዙ ወንጀሎች ይፈጸማሉ። ያ ሁሉ ወንጀልና ሰቆቃ የእግዚአብሔር ፈቃድ ነውን? በርግጠኝነት አይደለም!!! እግዚአብሔር ያውቀዋል ግን? እንዴታ!! እግዚአብሔር የማያውቀው ምን ነገር አለ? የሰው ልጅ ግን በነጻ ፈቃዱ የሚፈጽመው ወንጀል ነው። ለዚህ ጥፋቱ ደግሞ በእግዚአብሔር ፊት ሲቆም ቅጣቱን ያገኝበታል።

ከዚሁ አያይዘን ስንመለከተው በቤተ ክርስቲያናችን እና በአገራችን ላይ የሚፈጸመውን ግፍ እግዚአብሔር ያውቀዋል። ታዲያ ለምን ዝም አለ ለሚል ግብዝ መልሱ ሰዎች በነጻ ፈቃዳቸው ተጠቅመው ያደረጉት ነገር ነው የሚል ነው። ክፉዎቹ በክፋታቸው ተገፋፍተው ይህንን ሲያደርጉ እኛስ በመልካምነታችን ተጠቅመን የአቅማችንን ለማድረግ ያልቻልነው ለምንድር ነው?

ከመጽሐፍ አንድ ምሳሌ እናንሣ። ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አልአዛርን ከሞት ሊያሥነሣው በሄደ ጊዜ የተፈጸመውን ማወቃችን ከላይ ለመግለጽ የፈለግነውን ሐሳብ ግልጽ ያደርገዋል። ታሪኩ በዮሐንስ ወንጌል ምዕራፍ 11 ላይ ይገኛል። አልአዛር ታመመ፣ ሞተ፣ ተቀበረ። ከተቀበረ ከአራት ቀን በኋላ ጌታ ወደዚያ ሥፍራ ሄደ። ከዚያም ከመቃብሩ ላይ ድንጋዩን አንሱ ብሎ ቤተሰቦቹን አዘዘ። ከዚያም አልአዛርን ከመቃብር አልጋ ከሞት ሸለብታ ቀስቅሶ ሕያው አደረገው። ከሞት ማሥነሣቱ ካልቀረ ድንጋዩን እንዲያነሱ ለምን አዘዛቸው? ለምን ሁሉንም ነገር ራሱ አልፈጸመውም? በዚህ የአልአዛር ድኅነት ውስጥ የሰው ድርሻ በቤተሰቦቹ ተሰርቷል፣ የእግዚአብሔር ድርሻ ደግሞ በራሱ በባለቤቱ ተሠርቷል። የሰው ድርሻ መቃብሩን መክፈት፣ የእግዚአብሐር ድርሻ ሙቱን ሕያው ማድረግ ነው። በዘመናችን ግን እያልን ያለነው “ሁሉንም ነገር አንተ ሥራው!!!” ነው። መቃብሩን አንተው ቆፍር፣ ሙቱንም አንተው አስነሳው፤ እኛ ዝም ብለን እንመለከትሃለን።  

ሥር የሰደደ አድርባይነት መሰልጠኑ፤
ቤተ ክርስቲያን ለረዥም ዘመን ከቤተ መንግሥቱ ጋር ተቀራርባ የኖረች እንደመሆኗ ሥልጣን ላላቸው ሰዎች ማጎብደድ፣ አድርባይነት እና እታይ-እታይ ባይነት ከጥንቱም ሰልጥኖብናል። በዘመናችን ደግሞ ገዝፎና ተስፋፍቶ ቀጥሏል። የጥንቶቹ መሪዎች ፓርቲ ስላልነበራቸው አባላትም አልነበሯቸውም። የአሁኖቹ መሪዎች ባለ ፓርቲ ስለሆኑ አድርባዮቹ የፓርቲዎቻቸው አባላት በመሆን መስቀልና ሽጉጥ ታጣቂ ካህናት አፍርተናል። በደርጉ ዘመን የኢሰፓ፣ በአሁኑ ደግሞ የኢሕአዴግ አባል ደባትር፣ ካህናትና መነኮሳት አያሌ ናቸው። ይህ አባልነትና አድርባይነት ከተራ ካህናት፣ ደባትርና መነኮሳት አልፎ (በዘመነ ኢሕአዴግ) ከጳጳሳቱ ደርሷል። አባል ያልሆኑትም ቢሆኑ ከዝምታ ውጪ ምንም ምርጫ የላቸውም። ስለዚህ አድርባይነቱ በቅርብ መፍትሔ ስለማያገኝ መከራችንም በቅርብ መፍትሔ ይገኝለታል ብሎ ለማሰብ ይከብዳል።

መንግሥታት በፈቃደ እግዚአብሔር ሥልጣን ይይዛል የሚለው ትምህርት፣
ከፍ ብለን ከጠቀስነው ጋር አብሮ የሚሄደው ጉዳይ መንግሥት የሆነ ሁሉ በእግዚአብሔር ፈቃድ ነው ሥልጣኑን ያዘው የሚል ሐሳብና ትምህርት ነው። ቤተ ክርስቲያንን የሚሰቅላትን “እግዚአብሔር ወዶ ፈቅዶ አስቀመጠው” ማለት ድንቁርና ካልሆነ ምን ይሆናል?

ኃላፊነትን ለመቀበል መፍራት፣ ኃላፊነትን አለማወቅ፣ ኃላፊነትን ሁሉንም ለእግዚአብሔር መስጠት፣
እንደተጠቀሰው ከርስቲያኑ ራሱን አቅም እያለው አቅም እንደሌለው፣ ዕውቀት እያለው እንደሌለው ስለቆጠረ ያለበትን ኃላፊነት ለእግዚአብሔር ሰጥቶ “እርሱ ያውቃል” እያለ ተቀምጧል። ኃላፊነቱን አለመወጣቱ ስሕተት መሆኑን የሚገነዘበው ራሱ በጣም ጥቂቱ ነው። ዋልድባ ሲፈርስ፣ አበው አልታረቅ ሲሉ፣ በቆረጣ አዲስ 6ኛ ፓትርያርክ ለማስቀመጥ ሲሯሯጡ “እኔ ምን አቅም አለኝ” ብቻ ነው መልሱ። ይህም ኃላፊነትን ካለማወቅና ኃላፊነትን ለመረከብ ከመስጋት የሚመነጭ ክፉ ደዌ ነው።

ማጠቃለያ፦

በአጠቃላይ ስንመለከተው ክርስቲያኑ ክፍል አሁን ያለበት ይህ እና ሌሎች ምክንያቶችም ተጨማምረውበት ለመብቱ ለመቆም፣ ቤተ ክርስቲያኑን ለመታደግና እምነቱን ለማስከበር የሚችልበት ሁኔታ ላይ እንዳልሆነ እንገነዘባለን። በቅርብ ዓመታትም ይሻሻላል ብሎ መጠበቁ ከባድ ነው። በተአምር ካልሆነ በስተቀር አሁን ባለው የክርስቲያኑ አያያዝ ዋልድባንም ያርሱታል፣ አበውንም እንደጀመሩት በማሰር በማንገላታትና በማሰደድ ይገፉበታል፣ የራሳቸው መጠቀሚያ የሆነ 6ኛ ፓትርያርክ በመሾም ሌላ የመከራ ዘመን ያጸናሉ።

መፍትሔውስ?
መፍትሔው አጭር ነው። ከአሁኑ መሰባሰብ፣ መደራጀት፣ የችግሮቹን ትክክለኛ ምንጭ መረዳት፤ ለማያውቁት ማሳወቅ፣ ለአጭር ጊዜ ሳይሆን ለረዥም ጊዜ መፍትሔ መሥራት። ‘እዛው ሞላ እዛው ፈላ’ እንደሚባለው ተረት ቶሎ መፍትሔ በመፈለግና ለአጭር ጊዜ ሆይ ሆይ በማለት ችግሩ አይፈታም። የቤተ ክርስቲያን የሆኑትን ከአድርባዮቹ፣ ከአስመሳዮቹና ከጥቅመኞቹ ለይቶ በመረዳት የራስን ኃላፊነት መወጣት። የቀደሙት አበው ከመቃብር ተነሥተው ቢመለከቱን እንዳያፍሩብን እኛም በትውልዳችን የራሳችንን ኃላፊነት መወጣት።

ይቀጥላል!!!!

ቸር ወሬ ያሰማን፤ አሜን።   

“አንድ ጥምቀት፣ አንድ ሃይማኖት” የሚል ጥቅስ የያዙ ወጣቶች ታሠሩ

Saturday, January 19th, 2013

(ደጀ ሰላም፤ ጥር 12/2005 ዓ.ም፤ ጃኑዋሪ 20/2013/ PDF)፦ ቅዱስ ጳውሎስ ለኤፌሶን ሰዎች በላከው መልእክቱ ምዕራፍ 4 ቁጥር 5 ላይ ያለውን “አንድ ጌታ፣ አንድ ሃይማኖት፣ አንድ ጥምቀት” የሚል ጥቅስ ያለበት ቆብ ለሰንበት ት/ቤታቸው ገቢ ማስገኛነት በመሸጥ ላይ የነበሩ ወጣቶች በፖሊስ መታሠራቸው ታወቀ።


ጥር 11/2005 ዓ.ም ታቦተ ሕጉን ተከትለው በሞቀና በደመቀ ሃይማኖታዊ መንፈስ በማክበር ላይ እያሉ በፖሊስ የታሠሩት ስድስት ወጣቶች ሲሆኑ ጥቅሱ የተጻፈበትን ቆብ ይሸጡ የነበሩት ደግሞ ለብርሃናተ ዓለም ጴጥሮስ ወጳውሎስ ቤተ ክርስቲያን ሰንበት ት/ቤት ገቢ ለማስገኘት በሚል እንደሆነ ተገልጿል። መንግሥት የሃይማኖት አክራሪነትን እዋጋለኹ በሚለው ዕውቀት የጎደለው ተግባር ‘አንድ ሃይማኖት’ የሚል ቃል የሚናገሩ ክርስቲያኖችን በሙሉ በማሳደድ ላይ ይገኛል። የመጽሐፍ ቅዱስ ኃይለ ቃል እና የቤተ ክርስቲያኒቱ መሠረተ እምነት የሆነውን ቃለ እግዚአብሔርን መናገር፣ ማስተማርም ሆነ በጽሑፍ መያዝ ሌሎች እምነቶችን እንደመዋጋት ተደርጎ እንዲቆጠር በመናገር በፖሊስ ጥብቅ ማዋከብና እንግልት የሚፈጽመው መንግሥት እነዚህን ስድስት ልጆች የያዘው በዚሁ ምክንያት መሆኑን በወቅቱ በቦታው የነበሩ እማኞች ገልጸዋል።

ኢትዮጵያ ውስጥ ከነበሩ ቀደምት መንግሥታት ሁሉ በባሰና በከፋ መንገድ በቤተ ክርስቲያኒቱ የውስጥ ጉዳይ ረዥም እጁን አስገብቶ የሚያምሰው የፖለቲካው መዘውር በቅርቡ በቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤያት ላይ ሳይቀር ባለ ሥልጣኖቹን በመላክ የሲኖዶሱ ተሰብሳቢ ለመሆን በመሞከር ላይ መሆኑን ስንዘግብ መቆየታችን ይታወሳል።

መንግሥት በአገሪቱ ቀደምት እምነቶች ላይ ያለውን አቋም ለካድሬዎቹ በተከታታይ ሥልጠኛ በመስጠት የሚያስጠናበት ሰፊ እንቅስቃሴ ሲያደርግ ቆይቷል። ለዝቅተኛ እስከ ከፍተኛ ባለሥልጣናት ድረስ በቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ እና በሌሎች ኃላፊዎች ሲሰጥ የቆየው ሥልጠና ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን እና እስልምና ላይ ያነጣጠረ ሲሆን በባለሥልጣናት ቁጥር ሰፊ ተሰሚነት ያገኙትን ፖሮቴስታንቶችን ግን ምንም አይነካም። መንግሥት በነባር አገራዊ ቤተ እምነቶች ላይ እያስፋፋ የመጣው ጣልቃ ገብነት ድንበሩን አልፎ የእስልምና መሪዎችን በማሰር፣ የቤተ ክርስቲያናችን ሲኖዶስ በመዘወር መገለጡ ይታወቃል።

መንግሥት ለባለሥልጣኖቹ የሚሰጠውን ሥልጠና ለማወቅ ለምትፈልጉ ወደፊት እንዳስፈላጊነቱ ሙሉ ዶኩመንቱን ለማቅረብ እንሞክራለን።

ቸር ወሬ ያሰማን አሜን

4ኛው ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆርዮስ ስለ በዓለ ጥምቀት እና ወቅታዊ የቤተ ክርስቲያን ጉዳዮች ያስተላለፉት መልእክት

Saturday, January 19th, 2013

4ኛው ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆርዮስ ስለ በዓለ ጥምቀት እና ወቅታዊ የቤተ ክርስቲያን ጉዳዮች ያስተላለፉት መልእክት:: 

በዋልድባ ጉዳይ የተቀሰቀሰው ቁጣ

Thursday, March 29th, 2012

(ደጀ ሰላም፤ መጋቢት 20) — በዋልድባ እና በጠቅላላው የቤተ ክርስቲያን ህልውና ጉዳይ የተቀሰቀሰው ቁጣ በሕዝባዊ ውይይቶች ታጅቦ እየቀጠለ መሆኑን የሰሜን አሜሪካ ምንጮቻችን ገልጸዋል። በመላው የአሜሪካ ግዛቶች የሚኖሩ ኢትዮጵያውያንን በስልክ ኮንፈረንስ ሐሳባቸውን እንዲሰጡ እያደረገ ባለው በዚህ ሕዝባዊ ስብሰባ የምእመናን ቁጥር እየጨመረ መምጣቱ የተገለፀ ሲሆን ተሳታፊዎቹም ስለ ዋልድባ ይዞታ መደፈር ወይም ስለ ዝቋላ እና አሰቦት ገዳማት የእሳት አደጋ ብቻ ሳይሆን “በጠቅላላው ስለ ቤተ ክርስቲያን ህልውና ነው መነጋገር ያለብን” ወደሚለው ገዢ ሐሳብ በመምጣት ላይ ናቸው ተብሏል።

በዚሁ በፈቃደኛ ምእመናን በተጠራው እና በልባቸው በየቤታቸው ሲቃጠሉ የነበሩ ምእመናንን እየቀሰቀሰ በመጣው የስልክ-ጉባኤ አያሌ መሠረታዊ ጥያቄዎች በመነሣት ላይ ናቸው። “እኔ ምንም የሌለኝ አንድ ደካማ ሰው ነኝ” ሲሉ የጀመሩ አንድ ምእመን እንዲህ አሉ። “ስለ ዋልድባ ጉዳይ የአካባቢው ባለሥልጣን ሲናገሩ ሰምቻለኹ። መነኮሳቱም ሲናገሩ ሰምቻለኹ። እንግዲህ ይህ ገዳም ለሁለት ሺህ ዓመት የቆየ ነው። እንዲያው ምንም ችግር ከሌለ እንዴት ገዳማውያኑ እስከ አዲስ አበባ፣ እስከ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ቢሮ ድረስ ለመሔድ ይነሣሉ?” ሲሉ ተጠየቃዊ ሐሳብ አቅርበዋል። አክለውም “እኔ ስለዋልድባ ብቻ አይደለም የምናገረው። ከዚህ በፊት አኩሱም ላይ ችግር ተፈጥሮ ነበር። ከዚያ ሰው ሞተ። የሚገርመው ገዳዩ ማን ነው ሳይባል ሁከቱን የቀሰቀሰው ማን ነው? ይቅርታ ይጠይቅ የሚል ነገር ተነሣ። ይህ መንግሥት (ኢሕአዴግ) ስለ ቤተ ክርስቲያን ያለውን ሀሳብ መጠየቅ አለብን። በዚህ በ20 ዓመት ውስጥ የሌሎች እምነቶች ንብረቶች እንዲህ ሆኑ ሲባል ሰምቼ አላውቅም። የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ብቻ ነው የሚጠፋው። የሚቃጠለው። ይህ እኮ ሕጋዊ ጥያቄም ነው። መንግሥት ለእምነቶች ጥበቃ የማድረግ ግዴታ አለበት። ለዜጎች። የዋልድባ መነኮሳት ከተማን ሸሽተው፣ ዓለምን ንቀው ነው የሄዱት። ለከተማ ለከተማማ በየከተማው ባሉ አብያተ ክርስቲያናት መኖር ይችሉ ነበር እኮ። እነርሱም ዜጋ ናቸው። መንግሥት ጥበቃ ሊያደርግላቸው ይገባል” ሲሉ ልብ የሚነካ ንግግር አድርገዋል።

“ሥር ነቀል የምእመናን እንቅስቃሴ ነው የሚያስፈልገው” ያሉ ሌላ ተናጋሪም ኮፕት ቤተ ክርስቲያንን በአብነት በመጥቀስ ምእመኑ ትልቅ ኃላፊነት እንዳለበት፣ አባቶችን ብቻ በመጠበቅ ጊዜው እንዳያልፍበት፣ እስካሁን ጠብቆ ምንም ያገኘው ነገር አለመኖሩን፣ በመላው ዓለም ያሉ ኦርቶዶክሳውያን በአንድነት በመነሣት ቤተ ክርስቲያናቸውን መጠበቅ እንደሚገባቸው አስረድተዋል።

አክለውም “ሁላችሁንም በእግዚአብሔር ስም አንድ ነገር እለምናችኋለሁ። ከዘረኝነት ራሳችንን እናጽዳ። ዘር ለዱባና ለድንች እንጂ ሁላችን ከአንድ ከክርስቶስ ከማይጠፋው ዘር የተወለድን ነን” ሲሉ በሰሜን አሜሪካ ትልቅ በሽታ የሆነውን የዘረኝነትን ጉዳይ በቀጥታ አንሥተዋል። ሌሎች ተናጋሪዎችም በይዘት ከዚሁ ጋር የሚያያዝ ብዙ ሐሳብ ጠቅሰዋል።

ጉባኤው በዚሁ ቀጥሎ ሰላማዊ ሰልፎችን መቀጠል እንደሚገባ፣ በየአካባቢው የምእመናን አስተባባሪ ኮሚቴዎችን ማቋቋም እንደሚያስፈልግ፣ ይህ ሁሉ ችግር በእግዚአብሔር ቸርነት ይወገድ ዘንድ እና የተጀመረው እንቅስቃሴም ፍሬ እንዲያፈራ የምሕላ ጸሎት መደረግ እንዳለበት፣ ጊዜያዊ ችግር ያለባቸው ለዝቋላ እና ለደብረ አሰቦት ዓይነት ገዳማት የተጀመረው ርዳታ ማስተባበር ተጠናክሮ እንዲቀጥል ከስምምነት ላይ ተደርሷል። በረዥም ጊዜም ዓለም አቀፍ የሆነ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ አማኞች ፋውንዴሽን መቋቋም እንዳለበት የቀረበው ሐሳብ በዓላማነት ተቀምጧል።

ይኸው የምእመናን መነሣሣት እና ሕዝባዊ ውይይት በሌሎች አህጉሮች ማለትም በአውሮፓ፣ በአውስትራሊያ፣ በአፍሪካ እና በአረብ አገሮች ወዘተ ባሉ ምእመናን ዘንድም ይቀጥላል ተብሎ ይጠበቃል።

በዝቋላ የተነሳውን እሳት ለመከላከል የመጡ 3 ተማሪዎችን በፖሊሶች በጥይት አቆሰሉ

Tuesday, March 27th, 2012

(ደጀ ሰላም፤ መጋቢት 11/2004) – በዝቋላ ገዳም የተነሣውን ቃጠሎ ለመከላከል ከተለያዩ አቅጣጫዎች ወደ ስፍራው ከተነቃነቁት አዳማ ዩኒቨርስቲ ተማሪዎች መካከል በፖሊስ ጥይት የቆሰሉት ተማሪዎች ሦስት መሆናቸው ተዘገበ፡፡ በተማሪዎቹ ላይ የደረሰው ጉዳት መንሥኤ በተማሪዎቹ እና በአንድ የኦሮሚያ ቴሌቪዥን ጋዜጠኛ መካከል የተፈጠረ አለመግባባት መሆኑን መዘገባችን ይታወቃል፡፡

እንደ ዐይን እማኞች ገለጻ ተስፋዬ ፈቃዱ ቡራዩ የተባለው ጋዜጠኛ ቃጠሎው በቁጥጥር ሥር እንደ ዋለ የቀጥታ ዘገባ እያስተላለፈ ነበር፡፡ ዘገባውን የሰሙት ተማሪዎች ጋዜጠኛው የተሳሳተ መረጃ እያስተላለፈ በመሆኑ እንዲያስተካክል ያሳስቡታል፤ መታወቂያውን ይጠይቁታል፤ ካሜራውም እንዳይቀርጽ ይከላከሉታል፤ በዚህም አለመግባባቱ በመካረሩ ግርግር ይፈጠራል፡፡

ጋዜጠኛውን አጅበው የመጡት 10 የኦሮሚያ ፖሊስ አባላትም ጥይት ይተኩሳሉ፤ በዚህ መካከል ነው ሦስቱ ተማሪዎች ተመትተው የቆሰሉት፡፡ ሁሉም ተማሪዎች የቆሰሉት ከጉልበታቸው በታች ሲሆን የአንደኛው ተማሪ ከባድ መሆኑ ተገልጧል፡፡ ወጣቶቹ በአዳማ ዩኒቨርስቲ የሦስተኛ እና የአራተኛ ዓመት የኤሌክትሪካል እና መካኒካል ኢንጂነሪንግ ተማሪዎች የሆኑና የግቢ ጉባኤ አባላት ናቸው፡፡

በአሁኑ ወቅት በጥይት ተመትተው የቆሰሉት ተማሪዎች በፖሊሶቹ አማካይነት ወደ ደብረ ዘይት ለሕክምና መወሰዳቸው ተዘግቧል፡፡

የዝቋላ ገዳምን ቃጠሎ አስመልክቶ በትላንትናውና በዛሬው ዕለት በኢ.ቴቪ እና በአንዳንድ የኤፍ.ኤም ሬዲዮኖች የተላለፈው ዘገባ ሐቁን የሚያሳንስ፣ አደጋውን በሚገባ ያልተገናዘበ በመሆኑ በርካቶችን አስቆጥቷል፡፡ ብሔራዊው የቴሌቪዥን ጣቢያ በዛሬ የምሽት ዘገባው፡- ‹‹የዝቋላ ተራራ ቃጠሎ› ከበጋው የአየር ሁኔታ የተነሣ በሌሎችም የኦሮሚያ አካባቢዎች የተነሣው ቃጠሎ አካል መሆኑን፣ በቃጠሎው የአቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ቤተ ክርስቲያን አለመጎዳቱን፣ የክልል እና የፌዴራል ፖሊስ እንዲሁም የኦሮሚያ አደጋ መከላከልና ዝግጁነት ኮሚሽን ቃጠሎውን ለመከላከል የተባበረ ጥረት እያደረጉ ናቸው፤›› በሚል ዘግቧል፡፡

ኢትዮጵያውያን በዋሽንግተን ዲሲ ለዋልድባ ገዳም ሰልፍ አደረጉ (የአሜሪካ ድምጽ)

Monday, March 26th, 2012

የዋልድባ መነኮሳት ህዝብ የማደናገር ዓላማ አላቸው ሲል የአባ ገ/መድህን ጽ/ቤት ከሰሰ

Friday, March 23rd, 2012

(ደጀ ሰላም | PDF) — ሁሉም ሓላፊዎች በዋልድባ ገዳማት፣ በአሰቦት ደብረ ወገግ ቅድስት ሥላሴ ወአባ ሳሙኤል ገዳም እና በዝቋላ ደብረ ከዋክብት አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ገዳም ከተፈጠረው ችግር ጋራ በተያያዘ የጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ምላሽ ተመጣጣኝና ፈጣን እንዳልሆነ በጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ላይ የሚሰነዘረውን ወቀሳ በማጣጣል አስተባብለዋል፡፡

“የምንመሰክርላችሁ ያየነውን ነው” ያሉት የጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ሓላፊዎች በዋልድባ ገዳማት ጉዳይ ከሚመለከታቸው የመንግሥት ባለሥልጣናትና የገዳሙ ማኅበረሰብ ጋራ ከተደረገው ውይይትና በመስክ ከተመለከቱት ‹እውነታ› በመነሣት “ልማቱ በገዳሙ ክልል እንደማይካሄድና ገዳሙን እንደማይነካ አረጋግጠናል፤ ልማቱን እንደ ስጋት የሚያራግቡት ገዳሙን የፖለቲካ መጠቀሚያ ለማድረግና ሕዝበ ክርስቲያኑን የማደናገር ዓላማ ያላቸው መነኰሳት ናቸው፤” ብለዋል፡፡ ይልቁንስ “ግድቡ ለገዳሙ ልማት ዕድል /Opportunity/ በመሆኑ የገዳማት አስተዳደሩ በዚህ ዙሪያ መሥራት አለበት፤” የሚል ማሳሰቢያም ሰጥተዋል፡፡

በብዙ ተፋልሶዎች በተሞላውና ለጋዜጠኞች አሰልቺ በነበረው በዚሁ ጋዜጣዊ ጉባኤ “የዋልድባ ገዳም ትውፊቱን ጠብቆ መሄድ አለበት፤ ”ያሉት ሓላፊዎቹ ከገዳማዊ ሥርዐቱና ትውፊት ጋራ የሚጋጩ ምላሾችን ሲሰጡ ተስተውለዋል፡፡ ‹ልማቱ› ለገዳሙ ዕድል ስለመሆኑ ባብራሩበት ምላሻቸው፡- “ግድቡ ገዳሙን የመክበብ ቅርጽ አለው፤ ይህም የግድቡን ውኃ ለመጠቀም ያስችለዋል፤ በዚህም የዓሣ ርባታና መስኖ ልማት ያካሂዳል፤” ብለዋል፡፡
ከዘላቂ ሥነ ልማት ኀልዮት አኳያ በቂ ወይም ትክክለኛ ትንተና ያልተሠራበት የስኳር ልማቱ ግዙፍነት የአካባቢውን ተፈጥሯዊ ገጽታ፣ ማኅበረ – ኢኮኖሚያዊ ሁኔታ በመሠረቱ በመለወጥ የሚፈጥረው ግዙፍ የከተሜነት ተጽዕኖ ከገዳማውያኑ ጥብቅ የምንኩስና ሥርዐትና ትውፊት ጋራ የዕሴት ግጭትእንደሚፈጥር የገባቸው መነኰሳቱ ግን በደብዳቤያቸው እንደገለጹት፣ በብዙኀን መገናኛም ቀርበው እንደተናገሩት በመንግሥትም ይሁን በቤተ ክህነቱ መግለጫ እንደማይስማሙ ነው – “የተቀደሰችው የዋልድባ
ገዳም ኀጢአት የማይሻገርባት፣ ዘር የማይዘራባት፣ እህል የማይበላባት ናት፡፡”

በጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ሓላፊዎች መግለጫ መሠረት በ‹ልማቱ› ምክንያት የሚነሡት አብያተ ክርስቲያን ቁጥርም ሁለት መሆኑ ተገልጧል፡፡ እኒህም ቢሆኑ የገጠር አብያተ ክርስቲያን እንጂ የገዳሙ አካላት አይደሉም፡፡ በአንጻሩ በመንግሥት ሳይቀር የተነገረውና በገዳማውያኑ መግለጫ የተቀመጡት አብያተ ክርስቲያን ቁጥር አራት ነው፡፡ እኒህ አብያተ ክርስቲያን ምእመኑ ከቦታው ቃል ኪዳን የተነሣ የሚሰጣቸው ከፍተኛ መንፈሳዊ ዋጋ በሓላፊዎቹ መግለጫ ውስጥ ተገቢው ቦታ አልተሰጠውምወይም አልገባቸውም፡፡ ከጀርመንድምጽ ጋር ቃለ ምልልስ ያደረጉ አንድ የመንግሥት ሐላፊ “ተራ አብያተ ክርስቲያናት” በሚል ሲገልጿቸው እንደተሰሙት ማለት ነው።

የዋልድባ ገዳማትን የመጀመሪያ ዜና ከደጀ ሰላም በማግኘት ወደማጣራቱ መግባታቸውን ቢናገሩም ደጀ ሰላምን ጨምሮ፣ የአሜሪካ ድምፅ ሬዲዮን፣ የጀርመን ድምፅ ሬዲዮንና የማኅበረ ቅዱሳን ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣን በ‹አራጋቢነት› እና በ‹ማስጮኽ› ወንጅለዋል፡፡
በምእመናኑ ‹ይግባኝ› የተባለባቸው ሚዲያዎቹ “እነርሱ ናቸው የቤተ ክርስቲያን አሳቢዎች!!” በሚልም ተላግጦባቸዋል፡፡

ሓላፊዎቹ አቤቱታውን ለማቅረብ በመላው የገዳሙ ማኅበር ስምምነት ተወክለው ወደ አዲስ አበባ የመጡትንና በእኒህ ሚዲያዎች ቀርበው ቃላቸውን የሰጡትን ተወካዮችንም “ማንነታቸውን ማወቅ አልቻልንም” ሲሉ ክደዋቸዋል፡፡ የጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ሓላፊዎች የማኅበረ መነኰሳቱን ሙሉ ስምምነት አግኝተው የተላኩትን ተወካዮች እንዲህ ካሏቸው ተነጋግረናል የሚሉት ከማን ጋራ ነው? ፈጣን መልስ የሚሻ ጥያቄ ነው፡፡

ከአቤቱታ አቅራቢዎቹ አንዱ የሆኑትና “እውነተኛ መነኩሴ አይደሉም፤ በገዳሙም አይኖሩም” በሚል የተዘለፉት አባትከቀናት በፊት ለአሜሪካ ድምጽ ሬዲዮ የአማርኛ ቋንቋ አገልግሎት በሰጡት ምላሽ ግን “የእኔ ቆብ ከመርካቶ የተገዛ አይደለም፤ እውነተኛ መነኩሴ ነኝ፤ ያመነኮሱኝም አባት በገዳሙ ይገኛሉ፤ በማኅበሩ የተላኩት ጥያቄውን አድርስ ተብዬ ነው፤ ለሚዲያም የተናገርኹት ሃይማኖቴ አስገድዶኝ ነው፤” ማለታቸው ይታወሳል፡፡ ይህንኑም ቃላቸውንም መምህር አባ ገብረ ክርስቶስ የተባሉ የገዳሙ የቀድሞ አበምኔት አረጋግጠዋል፡፡

በአሰቦት ገዳም በቃጠሎ የደረሰውን ጉዳት የማኅበረ ቅዱሳን ስምዐጽድቅ ጋዜጣ “ተቃጠለ ብሎ በመሥራት አጩኾታል” ያሉት አንድ ሓላፊ “ችግሩን ለመፍታት ቀድመን ወደ ስፍራው ሄደናል፤” ብለዋል፡፡ በቅርቡ በገዳሙ መንፈሳዊ ትምህርት የሚከታተል የሰባት ዓመት ልጅ በአካባቢው ታጣቂ ጎሳዎች መገደሉንም አስታውሰዋል፡፡ ከአፋር፣ ከሶማሌ እና ከኦሮሚያ ክልል ባለሥልጣናት ጋራ በጉዳዩ ላይ መነጋገራቸውንና በአካባቢው የሚታየው የጎሳዎች የርስ-በስ ግጭት ለክልሎቹም አሳሳቢ መሆኑን ጠቅዋል፡፡

ገዳሙን ለቃጠሎም ይሁን ለእንዲህ ዐይነቱ የግፍ ግድያ ያጋለጠው ከዐፄ ኀይለ ሥላሴ ጀምሮ ለገዳሙ ይደረግ የነበረው ቋሚ የፖሊስ ጥበቃ ባለመኖሩ በመሆኑ ወደፊት የጋራ ግብረ ኀይል ተቋቁሞ ለገዳሙ ቋሚ የፖሊስ ኀይል በሚመደብበት ሁኔታ ላይ ከፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽነር ወርቅነህ ገበየሁ ጋራ ንግግር እየተደረገ መሆኑን አስታውቀዋል፡፡

በተያያዘጉዳይ በዕለቱ በተሸጠው መግለጫ ላይነጭ ውሸት ሆኖ የተገኘውና “ለችግሮቹ ሁሉ ቀድመን ተገኝተናል” የሚለውን የቤተ ክህነቱን መቃወሚያ የሚያስተባብለው የዝቋላ ገዳምና አካባቢው እሳት በደጀ ሰላም ቀዳሚ ዜና እንደተገለጸው መጋቢት ስምንት ሳይሆን መጋቢት 10 ነው መባሉ ነው፡፡ በአሰቦት ገዳም የካቲት 20 ቀን የጀመረው ቃጠሎ ለሁለተኛ ጊዜ በተደገመበት የካቲት 23 ቀን በመድረሳቸው “ቀድመን ተገኝተናል” እንዳሉት ሁሉ!!

ቢደርሱስ ይህ ነው የሚባል የገቢ ምንጭ ከሌለው ከዚሁ ገዳም አበል መጠየቅስ በመሠረቱ አግባብ ነውን? እነርሱ አበል ከጠየቁ በበጎ ፈቃድ (በራሳቸው ወጭ) በእግርም በተሽከርካሪም ገስግሰው መጥተው ቃጠሎውን እናጠፋለን ሲሉ የእሳት እና የኢሳዎች ጥይት ራት ሊሆኑ የነበሩት ቀናዒ ኦርቶዶክሳውያን ምን ይከፈላቸዋል?!

ለማንኛውም የዝቋላው ቃጠሎ የተነሣበት ቀን መጋቢት 10 ነው መባሉ የጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ሐላፊዎች መጋቢት 11 መሄዳቸውን ምክንያታዊ ለማድረግና ዘግይታችኋል ከሚለው ተወቃሽነት ለመዳን ታስቦ ይመስላል – ማስተባበያቸው ከእነርሱ ጉዞ አራት ቀናት አንሥቶ የወደመውን ሀብት ባይመልሰውም!!


የዝቋላን ቃጠሎ ለማጥፋት ለአየር ኀይሉ የሄሊኮፕተር ርዳታ ጥያቄ ማቅረባቸውን የተናገሩት ሓላፊዎቹ፡- ሄሊኮፕተሮች ለሌላ ግዳጅ መሰማራታቸው፣ ሄሊኮፕተሮቹ ቢኖሩም ለዚህ ዐይነቱ የቃጠሎ መከላከል ተግባር የተዘጋጁ አለመሆናቸውንና ቃጠሎውን ለማጥፋት የሚያስፈልጉ ማቴሪያሎች አለመኖራቸውን፣ ከዚህ ቀደም የተከሠቱትን ተመሳሳይ ችግሮች ለመከላከል የተቻለው ከደቡብ አፍሪካ መንግሥት በተደረገው እገዛ መሆኑንየጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ሐላፊዎቹ ተናግረዋል፡፡ በመሆኑም ቃጠሎው በሰው ኀይል (በምእመናን፣ በኦሮሚያ ፖሊስ፣ በፌዴራል ፖሊስ) ርብርብ ለመከላከል እንደተቻለ ተናግረዋል፡፡

ማለፊያ! ቃጠሎውን አስመልክቶ ከሓላፊዎቹ ንግግር በእጅጉ የሚነካውና ጆሮን ጭው የሚያደርገው ግን “እሳት በመንደርም ይነሣል፤ በቤተ ክርስቲያን ሲሆን ለምን ይገናል?” የመባሉ እብሪት ነው! አንቶኒዮሙላቱ የተባሉ የፌስቡክ ፀሐፊ እንዳሉት “ታዲያ ይህ ኮሚቴ አጣሪ ወይስ አደናጋሪ” ኮሚቴ?

‘ጳጳሶቹ አይረቡም’ – ስብሐት ነጋ

Friday, July 1st, 2011

(ደጀ ሰላም)፦ የሕወሐት/ኢሕአዴግ የፖለቲካ መሐንዲስ መሆናቸው የሚነገርላቸው አረጋዊው አቶ ስብሐት ነጋ ስለ ቤተ ክህነት በሰጡት ግልጽ አስተያየት ላይ “ጳጳሶቹ አይረቡም”፣ ቤተ ክህነቱም “ወደሞት አፋፍ እየሄደ ነው” ሲሉ ተናገሩ። ዛሬ አርብ ሰኔ 24/2003 ዓ.ም በወጣው “ፍትሕ” ጋዜጣ ላይ ረዥም ጽሑፍ ያስነበቡት አቶ ስብሐት ነጋ (በተለምዶ አቦይ ስብሐት ይባላሉ) ስለ ቤተ ክህነቱ በከፋ አስተዳደራዊ ብልሽት ውስጥ መውደቅ ምክንያቱ “ራሱ ቤተ ክህነቱ” እንጂ መንግሥት አለመሆኑን አብራርተዋል። (To Read in PDF, click HERE).

ባለፈው ሳምንት አርብ ሰኔ 17/2003 ዓ.ም ወጥቶ በነበረው የፍትሕ ጋዜጣ ላይ አቶ ተመስገን ደሳለኝ የተባሉ ግለሰብ ለሰጡት አስተያየት መልስ በሆነው በዚህ የአቶ ስብሐት ማብራሪያ ቤተ ክህነት ከጥንት ዘመን ጀምሮ ከመንግሥት ጋር ተጣብቃ እንደኖረች፣ አጼ ኃ/ሥላሴ “ቅዱስ ተብለው ታቦት ተቀርጾላቸው እንደነበር”፣ ለዚህ ደግሞ በዋነኛነት ተጠያቂው ቤተ ክህነቱ ራሱ መሆኑን ዘርዝረዋል። “ኦርቶዶክስ ከመንግሥት ሳይለያይ ለመቆየቱ ዋናው ተጠያቂዎች የቤተ ክህነት ኃላፊዎች የነበሩ ሰዎች ናቸው። መንግሥታቱ በሁለተኛ ደረጃ ይጠየቃሉ። ‘ፕሮፌሰሮቹ (እነ ፕሮፌሰር መስፍንን ለማለት ይመስላል) እና ሌሎች አማኞች ያን ጊዜ ባለመናገራቸውና ባለመጻፋቸው በምን ደረጃ ይጠየቃሉ?’ የሚል ጥያቄም ሊነሣ ይገባዋል” ሲሉ ጽፈዋል።

“ዋናው ነገር ቤተ ክህነት ከመንግሥት ተጣብቆ በመቆየቱ፣ የሃይማኖት ተቋምነቱ እየወደቀ መጥቷል። አሁንስ ሃይማኖትና ፖለቲካ በሕገ መንግሥቱ ደረጃ በጽኑ እምነት ከተለየበት ወዲህ (ቤተክህነቱ) ከደረሰበት ድቀት እያንሰራራ ነው ወይስ በነበረበት ጉዳት ደረጃ ነው ያለው? አሁኑ ፓትርያርክ ሥራ ከጀመሩ ጀምሮ ስለ ቤተ ክህነቱ የሚወራው እጅግ በጣም ዘግናኝና አሳፋሪ የአስተዳደር ጉድለት ተነሥተን ወደ ሞት አፋፍ እየሄደ ነው የሚያሰኝ ነው” ብለዋል።

በመቀጠልም “የቤተ ክህነቱ አስተዳደር ብልሽት የሚባሉ ዘርፈ ብዙ ናቸው። አማኝ ሐቁን የመስማት መብት ያለው ይመስለኛል። ሌሎች ሃይማኖቶች እንደ ቤተ ክህነት ለምን ክፉ ወሬ አይወራባቸውም። በራሱ ውስጣዊ ድክመት እየተጎዳ የመታ ቢሆንም ኦርቶዶክስቤተ ክርስቲያን በታሪኩ የሀገር ፀጋ ሆኖ ነበር የቆየው፤ ፀጋነቱ በዚህ ደረጃ መውደቅ የለበትም ነው የምለው በዚህ አጋጣሚ” ሲሉ አበክረው አሳስበዋል።

ብዙ ጊዜ እንደሚነገረው “የቤተ ክህነቱ አሳዛኝ ቦታ መውደቅ ተጠያቂው መቶ በመቶ ራሱ ነው። ሕገ መንግሥት ከፖለቲካ ነጻ አድርጎት እያለ ለምን?” ሲሊ ይጠይቁና “ባይኖርስ (ከፖለቲካ ነጻ ባይሆንስ?) ለእምነታቸው ለምን አይሠሩም? ጳጳሳቱ አይረቡም ያልኩበት ምንክንያት ከዚህ አጠቃላይ መርሕ ብቻ ተነሥቼ አይደለም። አብዛኞቹ ከድሮ ጀምረው በአቡነ ጳውሎስ አስተዳደር እንደሚያለቅሱ አውቃቸዋለሁኝ። ነገር ግን ትርጉም ያለው ሥራ አልሠሩም። ለዚህ ነው አይረቡም ያልኩበት ምክንያት። አሁንም ልጨምርበትና ለእምነታቸው አልረቡም።” ብለዋል።

ስለ ማ/ቅዱሳንም እግረ መንገዳቸውን ያነሡት አቶ ስብሐት “እኔ እንደሚመስለኝ፣ ባለኝ ቀጥተኛ ትዝብትም፣ ማህበረ ቅዱሳን የቤተ ክህነት እዳ ነው። ቀጥተኛ ትዝብቴ፣ የቤተ ክህነትን አስተዳደር ለማሻሻል መጠነኛ እንቅስቃሴ ሲጀመር ገንቢ ተራ ከመጫወት አፍራሽነት ይበዘበታል። አልፎ አልፎም ብልሽት እያዩ ዝምታ ይበዛል። የተቃዋሚ ፖለቲካ መድረክነትም እንዳለበት ይወራል። ይህ ትክክል ከሆነ እጅግ በጣም የሃይማኖት ብሳ ሳይሆን የሃገር ስርዓት ማለት ህገ መንገስት የመጣስ ክህደት ነው” ሲሉ ተናግረዋል።

“ቤተ ክህነት የራሱን ድክመት እንዳያይ ማድረግ … ቤተ ክህነቱንም በጣም ይጎዳል። …  ቤተ ክህነትን ፖለቲካዊ ጣልቃ ገብነት ነው የመዳከምህ ምክንያት አንበለው። ድክመቱ የራሱ የውስጡ ሁለገብ አስተዳደራዊ ብልሽት ነው። ተደጋግሞ አቤቱታ ቀርቦለት ያላጣራው ከሆነ  አሁንም ብልሽቱ የራሱ ነው።” ሲሉ አብክረው ገልጸዋል።

ጅማ – የሚመለከታቸው በሚገባ ያልተመለከቱት አካባቢ

Tuesday, March 8th, 2011



ማስታወሻ፦ ከዚህ በታች ያለው ጽሑፍ በፀሐፊው ፈቃድ ከፌስ ቡክ ላይ ተወስዶ እዚህ የተለጠፈ ነው። መልካም ንባብ።
++++
ቀሲስ ወንድምስሻ አየለ
(ቀሲስ ወንድምስሻ አየለ):- ጅማ ከ፲፱፻፺፱ ዓም ጀምሮ ስሟ በክፉም መነሣት ጀምሯል፤ የአካባቢውን ነዋሪና አስተዳደር ስሜት ለሚረዳ ይህ ጥሩ አይደለም። መረጃዎችን በግንጥሉ ለሚሰማ ደግሞ ጅማ ላይ ብቻ የተከሠተ አድርጎ ያየዋል። ሌሎችም መታየት ያለባቸውንና የሚመለከታቸው ቢያስቡበት መፍትሔው የማያስቸግረውን ጉዳዮች ብናነሣስ? ደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ በልማቱ ከተዘነጉትና አሁን በመጠኑ በልማቱ ወላፈን ከሚጎበኙት አካባቢዎች አንዱ ነው። ላያቸው ግን ሁሌም የማይረሱና ለመላው ኢትዮጵያም ሆነ ለዓለም የሚበቃ ሀብት እየታፈሰባቸው ነው፡-

(Read More ወደሚቀጥለው ገጽ ይዞራል . . . . .)

የብፁዕ አቡነ ይሥሓቅ የቀብር ሥነ ሥርዐተ ተፈጸመ

Saturday, March 5th, 2011



  • ብፁዕነታቸው ወደ አሜሪካ ለመሄድ ዝግጅታቸውን አጠናቅቀው ነበር
  • ‹‹ብፁዕነታቸው በመንፈሳዊው ትምህርት የተሟላ ሊቅነት ያላቸው፣ በቅድስት ቤተ ክርስቲያን በኩል እግዚአብሔርን በዝማሬ መላእክት፣ ሕዝበ ምእመናንን በትምህርት፣ በስብከተ ወንጌል እና በጸሎተ ቡራኬያቸው ያገለገሉ ያሬዳዊ ቅርስ ነበሩ፡፡›› (ዜና ሕይወታቸው)
  • ‹‹ድጓው፣ ጾመ ድጓው፣ ዝማሬ መዋስዕቱ አልሞተም፤ እዚያው ከዋናው ከቅዱስ ያሬድ ጋራ በሰማይ ያመሰግኑበታል፤ የካቲት 24 ቀን የተክለ ሃይማኖት በዓል ዕለት በመንበረ ፓትርያርክ ቅድስተ ቅዱሳን ማርያም እንዲቀድሱ ተራ ደርሷቸው ነበር፤ ነገር ግን በወዲያኛው ዓለም ከእነ ቅዱስ ያሬድ እና ጻድቁ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ጋራ እንዲቀድሱ ተጠሩ፡፡›› (ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ)
(ደጀ ሰላም፤ ማርች 5/2011)፦ ከትናንት በስቲያ በድንገተኛ ሕመም በተወለዱ በ76 ዓመታቸው ያረፉት የባሌ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ይሥሓቅ ሥርዐተ ቀብር ዛሬ፣ የካቲት 26 ቀን 2003 ዓ.ም በመንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ተፈጽሟል፡፡ የብፁዕነታቸው አስከሬን ትናንት ዓርብ የካቲት 25 ቀን 2003 ዓ.ም በዘጠኝ ሰዓት ወደ ካቴድራሉ ተወስዶ ጸሎተ ፍትሐት ሲደረስለት ያደረ ሲሆን በመላው አህጉረ ስብከትም ጸሎተ ፍትሐቱ ተደርጓል፡፡

(Read More ወደሚቀጥለው ገጽ ይዞራል . . . . .)

የባሌ ሀ/ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ይስሐቅ አረፉ

Friday, March 4th, 2011

(ደጀ ሰላም)፦ ብፁዕ አቡነ ይስሐቅ፣ የባሌ ሀ/ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ ዛሬ የካቲት 24 ቀን 2003 ዓ.ም አረፉ። የባሌ ሀ/ስብከት ሊቀ ጳጳስ እና አሁን ደግሞ በሥራ ላይ የሚገኘው የቋሚ ሲኖዶስ አባል የነበሩት ብፁዕነታቸው ዛሬ በኢትዮጵያ አቆጣጠር ከሰዓት በኋላ ማረፋቸው ታውቋል። በቤተ ክርስቲያን የዕለቱን ሥርዓተ ቅዳሴ ተካፍለው በደህና የተመለሱት ብፁዕነታቸው በድንገት ማረፋቸው የታወቀ ሲሆን መንስዔው ከልብ ጋር የተገናኘ ሳይሆን እንደማይቀር ምንጮቻችን ገልጸዋል። ብፁዕነታቸው ያረፉት በአዲስ አበባ ነው። ዝርዝሩን እንደደረሰልን እናቀርባለን።

በአዋሳ ገብርኤል ምእመናን በድንጋይ ተፈነከቱ

Saturday, January 29th, 2011
  • ፖሊስ ሁከተኞቹን ያሬድ አደመን እና ትዝታው ሳሙኤልን ጨምሮ 12 ሰዎችን በቁጥጥር ሥር አዋለ
  • ምእመናን የክልሉ መንግሥት ሐላፊዎች ችግሩን ለመፍታት ባላቸው ሐቀኝነት ላይ የተፈጠረባቸው ጥርጣሬ እየተጠናከረ ነው
  • ‹‹ፓትርያኩ ውሸታም ናቸው፤ ጉባኤያችንን ከመስቀል አደባባይ ወደ ገብርኤል አመጡብን፤ የማንፈልጋቸውን መምህራን አስመደቡብን፤ የጳጳሱን ግቢ በር እናሽጋለን፤ መኪና ወደ ገዳሙ እንዳይገባ እናግዳለን፤ የተላኩብንን መምህራን እስክንመለስ እና የታሰሩብንን እስክናስፈታ ድረስ ጸልዩልን፡፡›› (ዛሬ ጠዋት የእነ ያሬድ አደመ መናጆዎች በደ/ም/ቅ/ገብርኤል ገዳም ያሰሙት ክስ እና ፉከራ)
(ደጀ ሰላም፤ ጃኑዋሪ 29/2011፤ ጥር 21/2003 ዓ.ም)፦ ንት ማምሻውን በሐዋሳ ደብረ ምሕረት ቅዱስ ገብርኤል ገዳም ለቅዱስ ጊዮርጊስ ሕንፃ ቤተ ክርስቲያን ማሠሪያ ገቢ ለማሰባሰብ በተዘጋጀ ጉባኤ ላይ የሀገረ ስብከቱን ፈቃድ ጥሶ ዐውደ ምሕረቱን በኀይል ለመቆጣጠር በተደረገ ሙከራ ሳቢያ በተቀሰቀሰ ብጥብጥ ምእመናን በድንጋይ የተፈነከቱ ሲሆን ለብጥብጡ መንሥኤ ናቸው የተባሉት የሐዋሳ ቅድስት ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪ አባ ናትናኤል፣ ያሬድ አደመን፣ ዲያቆን ትዝታው ሳሙኤልን ጨምሮ 12 ሁከት ፈጣሪዎች በፖሊስ ቁጥጥር ሥር ውለዋል፡፡

(Read More  . . . . .)

ወ/ሮ እጅጋየሁ በየነ ወደ መንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ቅጽር ግቢ እንዳይገቡ የተጣለባቸው እገዳ እየተከበረ አይደለም

Friday, November 5th, 2010



ወ/ሮዋ በሐውልቱ ምረቃ ዕለት ንግግር ሲያደርጉ
  • ወይዘሮዋ ‹‹ሲኖዶሱ በእኛ ገንዘብ ምን አገባው?›› በሚል የምልአተ ጉባኤውን ውሳኔ አፈጻጸም በመቃወም ተግባራዊነቱን የሚያደናቅፍ ቡድን አደራጅተው ከፍተኛ እንቅስቃሴ እያደረጉ ነው፤
  • በቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ ላይ ጠንካራ ትችት የሰነዘሩባቸውን ብፁዓን አባቶች እየደወሉ በመሳደብ እየዛቱባቸው ነው፤
  • ያሬድ አደመ ‹‹በደረቅ ቼክ ማጭበርበር››፣ በጋሻው ደሳለኝ ‹‹በስም ማጥፋት››  ወንጀሎች ተከሰዋል፤
(ደጀ ሰላም፤ ኖቬምበር 4/2010፤ ጥቅምት 25/2003 ዓ.ም)ጥቅምት 25 ቀን 2003 ዓ.ም፤ የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት የዋና ሥራ አስኪያጁ ጽ/ቤት የአቡነ ጳውሎስን ‹‹ሐውልተ ስምዕ›› በኻያ ቀናት ውስጥ ከቦታው በማንሣት እና በየአብያተ ክርስቲያኑ የተሰቀሉትን የፓትርያርኩን ቢልቦርዶች በመሰብሰብ በመንበረ ፓትርያርኩ ቤተ መጻሕፍት ወመዘክር ውስጥ እንዲያስቀምጥ ያስተላለፈው ውሳኔ አንድ ሳምንት ያህል ሆኖታል፡፡ ለውሳኔው አፈጻጸም የዋና ሥራ አስኪያጁ ብፁዕ አቡነ ፊልጶስ ጽ/ቤት በቁርጠኛነት እየተንቀሳቀሰ ስለመሆኑ ጠርጣሪዎች በርካታ ጥያቄዎችን እያነሡ ይገኛሉ፡፡ ጠርጣሪዎቹ ጥያቄ ለማንሣት የተገደዱት ሐውልቱን በማሠራት እና ቢልቦርዶቹን በመስቀል ግንባር ቀደም ሚና ያላቸው ወ/ሮ እጅጋየሁ በየነ በቤተ ክርስቲያኒቱ የመጨረሻው ሥልጣን ባለቤት የሆነውን የቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ በመጻረር በተገኙት መድረኮች ሁሉ በራሳቸው እና ሌሎች ኀይሎችን በመጠቀም በሚያደርጉት ፀረ – ሲኖዶሳዊ ቅስቀሳ ነው፡፡
እንደ ውስጥ ዐዋቂ ምንጮች ገለጻ ወ/ሮ እጅጋየሁ በየነ ወደ መንበረ ፓትርያርኩ ጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ቅጽር ግቢ እንዳይገቡ በቅዱስ ሲኖዶስ የተጣለባቸውን እገዳ በመተላለፍ ከትናንት በስቲያ ምሽት በብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ ሕንጻ ውስጥ ፌሽታ ሲያደርጉ ቆይተዋል፡፡ እስከ ምሽቱ ሦስት ሰዓት ግድም ‹‹ወደ አባቴ ቤት እንዳልገባ የሚያግደኝ ማነው?›› በማለት ጦር አውርድ ሲሉ የቆዩት ወይዘሮዋ በምልአተ ጉባኤው ስብሰባ ወቅት ጠንካራ ትችት ወደሰነዘሩባቸው አራት ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ስልክ በመደወል፣ ‹‹እርስዎ ነዎት እኔን ‹እንዲህ እና እንዲያ› የሚሉኝ፤ ዶክመንታችሁ’ኮ በእጄ ነው፤. . .›› በማለት በአስነዋሪ ንግግር እንደዘለፏቸው እና እንደዛቱባቸው ተነግሯል፡፡ ወይዘሮዋ በጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ውስጥ በሕግ እና በይፋ የታወቀ ሐላፊነት የሌላቸው ተራ ግለሰብ ከመሆናቸው ጋራ በተያያዘ እርሳቸውን በተመለከተ ቅዱስ ሲኖዶሱ ያስተላለፈውን እገዳ ጠቅላይ ሥራ አስኪያጁ ብፁዕ አቡነ ፊልጶስ ባቀረቡት ሐሳብ መሠረት ለመንበረ ፓትርያርኩ የጥበቃ ሐላፊ በመንገር ተፈጻሚ እንዲሆን ነበር ስምምነት የተደረሰበት፡፡ ይሁንና የወይዘሮዋ ለዚያውም በምሽት ሰዓት እዚያ መገኘት ለስምምነቱ መተግበር ብፁዕ ሥራ አስኪያጁ የቅዱስ ሲኖዶሱ ጽ/ቤት እና የቋሚ ሲኖዶሱ ክትትል ምናልባትም የመንግሥት የጸጥታ ኀይሎች እገዛ ሳያስፈልጋቸው የሚቀር አይመስልም፡፡
በሌላ በኩል ‹‹የአቡነ ጳውሎስ ሐውልት ተነሥቶ እና ቢልቦርዳቸው ተሰብስቦ በመንበረ ፓትርያርክ ቤተ መጻሕፍት ወመዘክር እንዲቀመጥ›› የሚል ውሳኔ የሰፈረበት ቃለ ጉባኤ በጠቅላይ ቤተ ክህነቱ መዝገብ ቤት በኩል ውሳኔውን ለሚያስፈጽመው የጠቅላይ ሥራ አስኪያጁ ቢሮ እስከ አሁን ባልደረሰበት ሁኔታ ወይዘሮ እጅጋየሁ የሲኖዶሱን ውሳኔ የሚቃወም ግርግር በመፍጠር ተግባራዊነቱን እግዳት (deadlock) ውስጥ የሚያስገባ፣ በሂደትም ‹‹ውሳኔውን የሚደግፉ እንዳሉ ሁሉ የሚቃወሙም አሉ›› የሚል ብዥታን በመንግሥትም ዘንድ ሳይቀር ፈጥሮ አፈጻጸሙን አጣብቂኝ ውስጥ በመክተት የሚያስተጓጉል ቡድን አደራጅተው በመንቀሳቀስ ላይ መሆናቸው ተመልክቷል፡፡ ውዥንብሩን በመፍጠር እየተንቀሳቀሱ መሆናቸው የተነገረው ቀሲስ ሳሙኤል እሸቱ፣ መምህር ሰሎሞን በቀለ፣ በጋሻው ደሳለኝ፣ ያሬድ አደመ እና ሊቀ ካህናት ጌታቸው ዶኒ ናቸው፡፡ ከእነዚህ ግለሰቦች በተጨማሪ አንዳንድ የአዲስ አበባ አድባራት እና ገዳማት አስተዳዳሪዎችን ለማነሣሣት ጥረት እየተደረገ እንደሆነም ተገልጧል፡፡
“ሲኖዶሱ በእኛ ገንዘብ ምን አገባው” በሚል አፍቃሬ ሐውልት ዐመፅ ለመቀስቀስ የሚጥሩት ሴትዮዋ ለአቋማቸው ያግዘኛል ያሉትን ማንኛውንም መድረክ እየተጠቀሙ ነው፡፡ ጥቅምት 23 ቀን 2003 ዓ.ም የሐዋሳ እና ዲላ ከተሞች የፍትሕ እና ልማት ኮሚቴ አባላትን እንዲሁም ማኅበረ ቅዱሳንን “በሥልጣን ጥማት፣ በጥቅም አጋባሽነት እና በፀረ ሰላምነት” በመወንጀል፣ አቡነ ፋኑኤልን እና ሥራ አስኪያጃቸውን “የልማት እና የወንጌል አባት” እያሉ በማመሰጋገን ወደ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ለተቃውሞ የመጡት ኀይሎች ከብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ እና ብፁዓን አባቶች ጋራ በተወያዩበት መድረክ ላይ ሐውልቱ እንዲነሣ ቅዱስ ሲኖዶስ ያስተላለፈውን ውሳኔ የሚቃወሙ አስተያየት ሰጪዎች እንዲናገሩ አድርገዋል፡፡ ተቃዋሚዎቹ ከመጡባቸው ዘጠኝ ተሽከርካሪዎች መካከል የአምስቱን መኪኖች ወጪ ስፖንሰር ማድረጋቸው የተነገረላቸው ወ/ሮ እጅጋየሁ፣ ያሬድ አደመ እና በጋሻው ደሳለኝ ቅዱስ ሲኖዶስ አቡነ ፋኑኤልን ያዘዋወረው “በአዋሳ አካባቢ ያሉ መናፍቃን እና የጳጳሱ መኖር ጥቅማቸውን ያሳጣባቸው አንዳንድ ባለሀብት ፀረ ቤተ ክርስቲያኖች በፈጠሩት ጫና፣ ግፊት እና ውዥንብር በመወናበድ በመሆኑ እንዲጣራላቸው” በሚል ተቃዋሚዎቹ ሰጡት የተባለውን አስተያየት እንደሚጋሩ ነው የሚታመነው፡፡
ያሬድ አደመ ስለ “ሐውልቱ” ላደረገው “አስተዋጽዖ” ሲሸለም
በተያያዘ ዜና ያሬድ አደመ በሙስና ባጋበሰው ገንዘብ በሐዋሳ ከተማ በከፈተው “የቅዱስ አትናቴዎስ ዐጸደ ሕፃናት” ልጆቻቸውን የሚያስተምሩ ምእመናን “ልጆቻችን ከሌባ ምን ይማራሉ” በሚል እየሰበሰቡ ሲሆን በተመሳሳይ አኳኋን በከፈተው ዳቦ ቤት ለዕቃ ግዥ ለተስማማቸው አካላት ተቀማጭ ገንዘብ በአካውንቱ የሌለበትን ደረቅ ቼክ በመስጠቱ በማጭበርበር ወንጀል ክስ እንደተመሠረተበት ለማወቅ ተችሏል፡፡ የዓላማ ተጋሪው በጋሻው ደሳለኝ ደግሞ በዐውደ ምሕረት ላይ እንዳይቆም በጠቅላይ ቤተ ክህነት ሥራ አስኪያጅ፣ በስብከተ ወንጌል እና ሐዋርያዊ ተልእኮ መምሪያ የበላይ ሐላፊ ደብዳቤዎች በየደረጃው ከታገደ በኋላ ሚያዚያ 19 ቀን 2002 ዓ.ም በድሬዳዋ ሳባ ደብረ ኀይል ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን ‹‹ንጉሥ በዙፋኑ አለ›› በሚል ርእስ ባሰማው ንግግር ‹‹ብዙ ጋዜጦች ቢጽፉበትም፣ ብዙ ቪሲዲ ቢበተንም ዛሬም በመድረኩ ቆመናል፤ አንድ ማኅበር አለ – ማኅበረ ቅዱሳን የሚባል – ደም መጣጭ ማኅበር፤ የወንድሞችን ደም አፍስሶ ደማቸውን ለመጠጣት በጣሳ የሚቀበል፤ ብዙ አባቶችን ያሳደዱ፣ በጋዜጣቸው ያዋረዱ፤ መንግሥት አዲስ ሕግ አውጥቶ በፖሊቲካ ሲይዛቸው ሃይማኖተኞች ነን የሚሉ፣ በሃይማኖት ሲይዛቸው ደግሞ በፖሊቲካ የሚሄዱ. . . ሌቦች፣ ዘራፊዎች. . .” በሚል በአደባባይ በፈጸመው የስም ማጥፋት ወንጀል ፈጽሞ ነበር፡፡
በጋሻው ስለ “ሐውልቱ” ላደረገው “አስተዋጽዖ” ሲሸለም
ግለሰቡ ራሱ ሕገ ወጥ ሆኖ በፈጸመው የከተማውን ሰላም በሚያደፈርስ ተግባሩ ሳቢያ በማኅበረ ቅዱሳን የድሬዳዋ ማእከል ሚያዝያ 20 ቀን 2002 ዓ.ም ክስ ተመሥርቶበት ነበር፡፡ ይሁንና የድሬዳዋ አስተዳደር ካውንስል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት በጋሻው ከዚህ በፊት በተሰጠው ጊዜ ቀጠሮ ባለመቅረቡ ነገ ጥቅምት 26 ቀን 2003 ዓ.ም ጠዋት በፖሊስ ታስሮ እንዲቀርብ በሰጠው ትእዛዝ መሠረት ጉዳዩ እንደሚታይ ይጠበቃል፡፡

ገብረመድህን (አባ ጳውሎስ) ‹‹ሐውልት ፍለጋ›› ጀመረ

Tuesday, November 2nd, 2010

አቡነ ጳውሎስ ትናንት ጥቅምት 21 ቀን 2003 ዓ.ም በዋለው እሑድ ሰንበት በሰሜን ምዕራብ ሸዋ – ሰላሌ ሀገረ ስብከት የምትገኘዋን የደብር ቅዱስ ደብረ ጽጌ ማርያም ገዳምን ጎበኙ፡፡ የሥሪቷ ጥንታዊነት እስከ መካከለኛው መቶ ክፍለ ዘመን ድረስ ወደኋላ በሚቆጠርላት የደብር ቅዱስ ደብረ ጽጌ ማርያም ገዳም አሁን ቆሞ የሚታየው ሕንጻ ቤተ ክርስቲያን የተሠራው በኢትዮጵያዊው ቀዳማዊ ፓትርያርክ በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ባስልዮስ ዘመን በ1952 ዓ.ም ነው፡፡ በገዳሟ ቤተ መቅደስ ውስጥ ያለውን በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ባስልዮስ መልክእ የተቀረጸውን ምስል የጎበኙት ፓትርያርክ አቡነ ጳውሎስ ምስሉ ፎቶ ግራፍ እንዲነሣ ማዘዛቸውን፣ በቃላቸውም ትእዛዝ መሠረት ምስሉ ፎቶ ግራፍ መነሣቱ ተዘግቧል፡፡ ነዋሪነታቸውን በጀርመን ሀገር ያደረጉ ወገኖች ‹‹ለብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ባስልዮስ ስለነበራቸው ፍቅር›› ከዜና ዕረፍታቸው በኋላ እንዳሠሩት የሚነገርለትን ይህንኑ የቁም ምስል የጎበኙት ፓትርያርኩ ከነገ በስቲያ የሐውልት ማፈላለግ ዑደታቸውን በመቀጠል በግብጽ በርሓ ከሚገኙት ገዳማት የብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ሺኖዳ ሐውልት ይገኛል የሚባልበትን ገዳም እንደሚጎበኙ ተነግሯል፡፡

ባለፈው ዓመት በደብር ቅዱስ ደብረ ጽጌ ማርያም ገዳም ለሚገነባው የአብነት ትምህርት ቤት እና የአረጋውያን መጦርያ እብነ መሠረት እንዲያኖሩ ጥሪ ተደርጎላቸው ያለበቂ ምክንያት ያልሄዱት አቡነ ጳውሎስ፣ ትናንት የእመቤታችን የወር በዓል ከአብነት ት/ቤቱ እና የአረጋውያን መጦርያ ተቋም መጠናቀቅ ጋራ መገጣጠሙን ሰበብ አድርገው ሪባን ቆርጠው ለመመረቅ ተገኝተዋል፡፡ ፓትርያርኩ በገዳሙ ከተገኙ በኋላ ከመቅደሱ በር በስተቀኝ የሚገኘውን የብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ባስልዮስ ሐውልት አብረዋቸው ለተጓዙ ጳጳሳት እያሳዩ ፎቶ ግራፍ እንዲነሣ ማዘዛቸው፣ ቅዱስ ሲኖዶስ በቁማቸው ሳሉ ቀኖና ቤተ ክርስቲያንን ጥሰው ሥርዐተ አበውን ተላልፈው ያሠሩት ሐውልታቸው እንዲፈርስ ያስተላለፈውን ውሳኔ እዚህም እዚያም በግለሰቦች ተፈጸሙ እና መሠረታዊ እውነታውን የማይቀይሩ ስሕተቶችን በልማዳዊ ምልከታዎች ላይ ተመሥርቶ እንደ ማስረጃ በማቅረብ እንዳይፈጸም ለሚያደርጉት ጥረት ጉልሕ ማሳያ መሆኑን ታዛቢዎች ይናገራሉ፡፡
በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የቅዱሳት ሥዕላት ቀኖና እና ትውፊት ሥርዓተ አምልኮን ለመፈጸም፣ የሥዕሉ ባለቤት የሆነውን ቅዱስ ትምህርት፣ ገድል እና ተኣምር ለመዘከር እና ከቃል ኪዳኑ በረከት ለማግኘት እንዲሁም ምእመናንን ለማስተማር አገልግሎት ላይ የሚውሉት የቅብ እና የጭረት ሥዕሎች እንጂ እውናዊ መልክእ ያላቸው ቅርጾች አይደሉም፡፡ እኒህም ተፈጻሚ የሚሆኑባቸው የራሳቸው ጊዜ እና ሥርዓት አላቸው፡፡ አቡነ ጳውሎስ በደብር ቅዱስ ደብረ ጽጌ ማርያም ገዳም ትናንት የጀመሩት ዑደት ይህን ቀኖና ቤተ ክርስቲያን በማፋለስ እና ሥርዓተ አበውን በመጣስ በራሳቸው ምሳሌ ያቆሙት ሐውልት እንዲነሣ ቅዱስ ሲኖዶስ ያሳለፈውን ውሳኔ በተግባር የመገዳደር ውጥን በመሆኑ ብፁዓን አባቶች ሊነቁበት እንደሚገባ ተመልክቷል፡፡
መሠረቱ ሰማያዊ የሆነው ፍጹማዊው ቀኖና ቤተ ክርስቲያን ለኅሊናቸው ከሚያስረግጥላቸው እውነት ይልቅ ከራሳቸው ልባዌ ጋራ የሚጣጣም እና በዳሰሳዊ (ኢምፔሪሲስታዊ) አስረጅ ላይ የተመሠረተ ሐሰሳ ውስጥ የሚዳክሩት ፓትርያርኩ፣ በሕገ ቤተ ክርስቲያን አንቀጽ 15 ንኡስ አንቀጽ 1 – 15 በዝርዝር በተደነገገው መሠረት ‹‹ቅዱስ ሲኖዶስ የወሰነውን በሙሉ ልብ ተቀብሎ ለማስፈጸም›› ካለባቸው ግዴታ ይልቅ የቅዱስ ሲኖዶሱን ተቋማዊ ልዕልና፣ አሠራር እና ውሳኔ ደረጃ በደረጃ በግለሰባዊ ዐምባገነንት በሚተካ ትሮትስካዊ ዘይቤ ራሳቸውን ማሠማራታቸው ከመቼውም ጊዜ በበለጠ እንደ ወርቅ ጠርቶ በሚታይበት ሁኔታ ውስጥ እንገኛለን፡፡

ቅዳሜ፣ ጥቅምት 20 ቀን 2003 ዓ.ም በተጠናቀቀው የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ የሐውልቱን መሠራት ጨምሮ የሲኖዶሱን ማእከላዊ አሠራር ያልጠበቁ አካሄዶች በተመለከተ በተዘረጉት አጀንዳዎች ላይ በመንፈስ ልዕልና እና በሐሳብ የበላይነት አቋማቸውን ፊት ለፊት እያስረገጡ ከመወያየት ይልቅ በዝምታ/ቸልታ ሲያዘናጉ ቆይተዋል፤ በስብሰባው መዳፊያ ላይ ግን እንዲህ ባለው ወሳኝ አካል የሚካሄዱ ውይይቶች እና የሚተላለፉ ውሳኔዎች የሕዝቡን ቀልብ የሚይዙ በመሆናቸው በስተመጨረሻ የሚሰጡ ጋዜጣዊ መግለጫዎች እና የሚዘጋጁ ጋዜጣዊ ጉባኤዎች ከፍተኛ የሕዝብ ግንኙነት ፋይዳ ይኖራቸዋል፡፡ ይህን ለመረዳት ብፁዓን አባቶች የልምድ ውስንነት እንደነበረባቸው ታይቷል፡፡ ፓትርያርክ አቡነ ጳውሎስ ግን የሳምንት አርምሟቸው የአንደበት እንጂ እንደ በቁት አባቶቻችን የጽማዌ እንዳልነበር መድረኩ ያለውን ዋጋ በስተመጨረሻ በብልጣብልጥነት በመጠቀም አሳይተውናል – ብልጥ ያለአንድ ቀን አይበልጥም እንጂ!! ከብፁዓን አባቶች የነበረባቸውን ተግዳሮት ከአንድ ዓመት በፊት እንደነበረው ‹‹በተውሶ ጡንቻ›› ሳይሆን በብልጣብልጥነት ቀጭን ጎዳና የተወጡት የመሰላቸው አቡነ ጳውሎስ፣ አሁን ደግሞ በዳሰሳዊ ዕውቀት ላይ የተመሠረቱ ሙግቶችን (Empirical evidences) በማቅረብ በራሳቸው አስተሳሰብ የክብራቸው ትእምርት የሆነው ሐውልታቸው እንዳይፈርስ በመትጋት ላይ ናቸው፡፡

በመሠረቱ በልማድ ተይዘው የሚፈጸሙ እና የሚደጋገሙ ነገሮች የሚሰጡትን አጠቃላይ መልክእ በመያዝ ላመኑበት አቋም እንደ አስረጅ የሚያቀርበው ዳሰሳዊ ዕውቀት (Empirical Knowledge) መነሻ ቢሆን እንጂ የመጨረሻ ተደርጎ ሊወሰድ አይችልም፡፡ ዳሰሳዊ ዕውቀት በባሕርዩ የነገሮችን መሠረተ እውነት /አመክንዮ ከመመርመር ይልቅ የልማዱን ተቀብሎ የማደር ግዴታን የሚጥል፣ ለጭቆና የተመቸ እና በይዘቱም ጥልቀት የሚጎድለው ነው፡፡ ከዚህ አኳያ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ (በመንበሩ ላይ እስካሉ ድረስ በዚህ ማዕረግ ይጠሩ ዘንድ ሕገ ቤተ ክርስቲያን አንቀጽ 14 ንኡስ አንቀጽ አንድ ያዝዛል) በጀመሩት የእልህ/የቁልቁለት መንገድ እስከ ግብጽ በረሐ ወርደው የሚያፈላልጉት እውነት ቢገኝ እንኳን ፍጽምና የሚጎድለው እና በተሳሳተ መሠረት ላይ የቆመ መሆኑ ግልጽ ነው፡፡

በቤተ ክርስቲያኒቱ ውስጥ የመጨረሻው ከፍተኛ ሥልጣን ባለቤት የሆነው ቅዱስ ሲኖዶስ ስለሚያስተላልፋቸው ውሳኔዎች አፈጻጸም ሕገ ቤተ ክርስቲያኑ የሚለውን የተመለከትን እንደሆነ ግን፣ በአንቀጽ 11 ንኡስ አንቀጽ አንድ ቋሚ ሲኖዶሱ፣ በአንቀጽ 15 ፓትርያርኩ፣ በአንቀጽ 20 ኤጲስ ቆጶሳቱ፣ በአንቀጽ 25 የቅዱስ ሲኖዶስ ጸሐፊው እና በአንቀጽ 30 የቤተ ክህነቱ ጠቅላይ ሥራ አስኪያጅ የመፈጸም እና የማስፈጸም ግዴታ እንደተጣለባቸው ይደነግጋል፡፡ በመሆኑም ስለ ሐውልቱ መፍረስ ብቻ ሳይሆን በሌሎችም አንገብጋቢ አጀንዳዎች ላይ ቅዱስ ሲኖዶስ ያስተላለፋቸው ውሳኔዎች ተፈጻሚነት በተጠቀሱት አካላት የቅርብ ክትትል ሊደረግባቸው ይገባል፡፡ በአፈጻጸሙ ሂደት አስቸኳይ እና ድንገተኛ እክሎች ቢያጋጥሙ በየዓመቱ ጥቅምት 12 እና ትንሣኤ በዋለ በሃያ አምስተኛው ቀን/በርክበ ካህናት/ ከሚደረገው ጉባኤ ውጭ ቅዱስ ፓትርያርኩ ወይም የቋሚ ሲኖዶስ አባላት በሚያደርጉት ጥሪ አልያም ከጠቅላላው አባላት ከሦስት ሁለቱ እጅ የሚሆኑ የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት ምልአተ ጉባኤ እንዲደረግ በጠየቁ ጊዜ ጥሪ ሊደረግ እና ስብሰባው ሊካሄድ ይችላል (አንቀጽ 10 ንኡስ አንቀጽ 1 – 2)፡፡

ገብረመድህን (ጳውሎስ) በቃለ ጉባዔ ላይ አልፈርምም አለ

Saturday, October 30th, 2010

(ደጀ ሰላም፤ ኦክቶበር 30/2010፤ ጥቅምት 20/2003 ዓ.ም):-

አቡነ ጳውሎስ ሐውልቱ እንዲፈርስ የታዘዘበትን እና የሁሉም ሊቃነ ጳጳሳት ስምምነት የተገለጸበትን ውሳኔ በያዘው ቃለ ጉባኤ ላይ ‹‹አልፈርምም›› በማለት እና ሲጠየቁም ዝምታን በመምረጥ ቀድሞ ሲገለጽ በቆየው እምቢታቸው ጸንተዋል፡፡

አቡነ ይሥሐቅ
አቡነ ጎርጎርዮስ

  • ከፓትርያሪኩ ጋራ ሌሎች አራት ሊቃነ ጳጳሳትም በተለያየ ምክንያት የሐውልቱ መፍረስ የተገለጸበትን ቃለ ጉባኤ አልፈረሙም፡፡ ሲኖዶሱ ከ43 ያላነሱ በአገልግሎት ላይ የሚገኙ ጳጳሳት እና ሊቃነ ጳጳሳት በአባልነት ይገኙበታል፡፡
  • የጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ዋና ሥራ አስኪያጅ ብፁዕ አቡነ ፊልጶስ የሐውልቱን ማስፈረስ ውሳኔ እንዲያስፈጽሙ በስማቸው ተለይቶ በመግለጫው ላይ መስፈሩን በመቃወም ለመፈረም ፈቃደኛ አልሆኑም፡፡ ብፁዕነታቸው ‹‹ከእኔ ስም ይልቅ ቢሮው ነው መጠቀስ ያለበት›› የሚል አቋም እንዳላቸው ተነግሯል፡፡
  • አቡነ ይሥሐቅ፣ አቡነ መቃርዮስ እና አቡነ ጎርጎርዮስ (ከዚህ በፊት ሐውልቱን ሲቃወሙ ቆይተዋል) ‹ፓትርያሪኩ ሳይፈርሙ በፊት አንፈርምም› በሚል እና ሌሎች ምክንያቶች ለመፈረም ፈቃደኛ አልሆኑም፡፡
  • በሕገ ቤተ ክርስቲያን ስለ ቅዱስ ሲኖዶስ የስብሰባ ሥነ ሥርዐት አንቀጽ ሁለት ንኡስ አንቀጽ 4/ሀ ሃይማኖትን እና ቀኖና ቤተ ክርስቲያንን በሚመለከት ጉዳይ ከጠቅላላው አባላት ከአራት ሦስቱ እጅ በተገኙበት ሲኖዶስ በማድረግ በሙሉ ድምፅ ውሳኔ ማሳለፍ እንደሚገባ ተደንግጓል፡፡
  • በሕገ ቤተ ክርስቲያኑ አንቀጽ 15 ንኡስ አንቀጽ 1 ፓትርያሪኩ በተሰጠው ሐላፊነት መሠረት ሃይማኖትን እና ቀኖና ቤተ ክርስቲያን የመሠበቅ እና የማስጠበቅ፤ በአንቀጽ 16 ንኡስ አንቀጽ 1 መሠረት ደግሞ የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን ሃይማኖት የሚያፋልስ፣ ቀኖና ቤተ ክርስቲያንን የማይጠብቅ፣ ቤተ ክርስቲያንን የሚያስነቅፍ ተግባር ፈጽሞ ከተገኘ፣ ታማኝነቱ እና ተቀባይነቱ በካህናት እና ምእመናን ዘንድ ተቀባይነት ያጣ ሆኖ ይህም በትክክል ከተረጋገጠ በቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ ከሥልጣን እንደሚወርድ ተደንግጓል፡፡
  • ፓትርያሪኩ ዛሬ ዘጠኝ ሰዓት ላይ በተጠራው ጋዜጣዊ ጉባኤ በቅዱስ ሲኖዶሱ አባላት ስምምነት የተደረሰበትን መግለጫ እንደሚያነቡ ይጠበቃል፡፡ መግለጫውን ለማንበብ ፈቃደኛ ካልሆኑ ብፁዓን አባቶች የወከሉት የሲኖዶሱ አባል እንዲያነቡት ይደረጋል ተብሏል፡፡

“ሐውልቱ” ምን ይሁን?

Thursday, October 28th, 2010



(ደጀ ሰላም፤ ኦክቶበር 27/2010፤ ጥቅምት 17/2003 ዓ.ም):- ቅዱስ ሲኖዶስ በማያሻማ መልኩ ከትምህርተ ተዋሕዶም ሆነ ከ ሥርዓተ አበው ውጪ የሆነው “ሐውልተ ስምዕ” እንዲነሣ ከወሰነ ጀምሮ የተለያዩ ደጀ ሰላማውያን እንዴት እንደሚፈርስ በቀልድ እያዋዛችሁ አስተያየታችሁን ሰጥታችኋል። 

እንግዲህ መፍረሱማ ከሆነ እንዴትና ምን መሆን እንዳለበት ከታሪካችን መጠነኛ አስተያት በመጨመር አጭር ሐሳብ ለማካፈል ወደድን። ሐውልቱ በደህና ቦታ፣ ለምሳሌ ቤተ ክህነቱ ባሠራው ሙዚየም ወይም በሌላ ተገቢ ቦታ አልያም በዚያው በቦሌ መድኃኔ ዓለም “ሙዚየም” (ካላቸው) መቀመጥ አለበት።

አባቶቻችን ቤተ ክርስቲያንን ለ15 ዓመታት ያቃጠላትና ያወደማትን የግራኝን ካባ እና መጎናጸፊያ በመርጡለ ማርያም ገዳም ካስቀመጡ፤ በመረዝ ጋዝ ሕዝባችንን የፈጀውን የጣሊያን ከአየር የሚወረወር ቦንብ በአድዋ  ሥላሴ ካስቀመጡ፤ ይህም ትውልድ ይህንን “ሐውልት” ለመጪው ትውልድ መማሪያ እንዲሆን በተገቢው ቦታ ማስቀመጥ አለበት። 

ስድስት ኪሎ ያለው የማርክስ ሐውልት ላይ ቀለም እንደተደፋው፤ የሌኒን ሐውልት በጭንቅላቱ እንደተገለበጠው፤ ወይም ሩቅ ምሥራቅ የሳዳም ሐውልት መጫወቻ እንደሆነው መደረግ የለበትም። ይህ ታሪካችን ነው። የቅ/ሲኖዶስ ገድል ሲጻፍ አብሮ መጠቀስ ያለበት የአባቶቻችን የመንፈሳዊ አርበኝነት ውጤትም ነውና በሥነ ሥርዓት ይቀመጥ።  

በለንደን በሺዎች የሚቆጠሩ ምዕመናን ቀልብን የሳበው የስብከተ ወንጌል ጉባኤ

Tuesday, September 7th, 2010

(ነጻ አስተያየት ከለንደን – ታምሩ ገዳ):-የለንደን ከተማ ላለፉት ስድስት ሣምንታት በይዘቱ እና በዓይነቱ ታላቅ ትኩረት የሳበ መንፈሳዊ አገልግሎትን በማስተናገድ ተጠምዳ ሰንብታለች። ይህ ማዕከሉን በለንደን ደብረ ገነት ቅድስት ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን በማድረግ በለንደን ከተማ ለሁለተኛ ጊዜ በአውሮፓ ደግሞ ለ13ኛ ጊዜ የተካሄደው የመላው አውሮፓ ዓመታዊ የስብከተ ወንጌል ጉባኤ  ሐምሌ 9 – 11 2002 ዓ.ም  (ጁላይ 16 – 18 2010 ) እንዲሁም 3ኛው የደብረ ገነት ቅድስት ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን ዓመታዊ መንፈሳዊ ጉባኤዎች ጥምረት የአብዛኛው የለንደን ምዕመናን ስሜት የገዛ ነበር። ቁጥራቸው ከ300 በላይ የሚገመቱ ከመላው አውሮፓ የተውጣጡ የተዋሕዶ ልጆችን በጉባኤው ላይ ለመቀበል የቤተ ክርስቲያኒቱ  ሰበካ ጉባኤ ያዋቀረው የዝግጅት አስተባባሪ ኮሚቴ ከምዕመናኑ ጋር በመቀራረብ እንግዶቹን ለመቀበል ወራት የፈጀ ቅድመ ዝግጅት ማድረጉን በፕሮግራሙ ላይ የነበሩት እንቅስቃሴዎች ያስረዳሉ።በዚህ የስብከት ወንጌል ጉባኤ ላይ ከተለያዩ የአለም ማዕዘናት በመምጣት የወንጌል ትምህርት የሰጡ አባቶች መካከል መልአከ ሳሌም አባ ገብረ ኪዳን እጅጉ (ከአሜሪካ ) ፣ አባ ወልደ ትንሣኤ ጫኔ (ከፈረንሣይ ) ፣ ሊቀ ትጉሃን ቀሲስ ጌጡ የኋላሸት (ከስዊድን) ፣ ሊቀ ጉባኤ ጥበበ ሥላሴ  አሰፋ ፣ መልአከ ሰላም ቀሲስ አዲስ አበበ እና መልአከ ገነት ቀሲስ ከፍያለው አስቻለው ( ከለንደን ) ፣ ዲ/ን ብርሃኑ አድማሴ (ከኢትዮጵያ) ፣ መምህር አምሳሉ ተፈራ (ከጣሊያን) ከብዙ በጥቂቱ የሚጠቀሱ ናቸው። በዚህ ጉባኤ ላይ ምዕመናኑ የዘር ፣ የቀለም ፣ የብሔር ፣ የዕድሜ እና የጾታ ልዩነት ሳይገድባቸው ሁሉም በጋራ ከቅዳሴ አንስቶ የስብከተ ወንጌሉ ፕሮግራም እስከሚጠናቀቅበት ምሽት ድረስ የሚዘልቀውን ፕሮግራም ያለ ድካም እና መሰልቸት ሲከታተሉ ለተመለከተ እግዚአብሔር በስደት ላይ ተበታትኖ የሚኖር ሕዝቡን ሊያስተምረው ምን ያህል እንደወደደ መገመት አይከብድም።
የወንጌል መምህራኑ በበኩላቸው በተለያዩ ሃይማኖታዊ እና ማህበራዊ ጉዳዮች ዙሪያ ከመጽሐፍ ቅዱስ ፣ ከነባራዊ ሁኔታ እንዲሁም የራሳቸውን ተሞክሮ እያጣቀሱ በምዕመናኑ ልብ እና  አዕምሮ ውስጥ የወንጌል ዘርን ሲዘሩ ሠንብተዋል። ቤተ ክርስቲያኒቱ ያለ ሕዝበ ክርስቲያን ወይም ሕዝበ ክርስቲያኑ ያለ ቤተ ክርስቲያን መኖር አይችሉም ያሉት አቡነ እንጦንስ የሰሜን ምዕራብ አውሮፓ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ጉባኤው እንዲሳካ ላደረጉ ወገኖች ምስጋናቸውን አቅርበዋል። ለሐዋሪያዊ ተልዕኮ ከምድረ አሜሪካ የመጡት መልአከ ሳሌም አባ ገብረ ኪዳንም በበኩላቸው በለንደኑ ጉባኤ ማስተማር ብቻ ሳይሆን ብዙ ትምህርት መቅሰማቸውን ጭምር ተናግረዋል። በጉባኤው መሣካት መንፈሳዊ ቅናት ያደረባቸው አባ ገብረ ኪዳን አሜሪካ ውስጥ ተመሣሣይ ጉባኤዎች እንዲደረጉ ከወገኖቻቸው ጋር እንደሚመክሩ ተናግረዋል።
ይህን በመላው አውሮፓ የሚገኙ የተዋሕዶ ልጆችን ለ13ኛ ጊዜ ለማሰባሰብ ያስቻለውን ጉባኤ በጽንሠ ሃሳብ ደረጃ ከፈለቁት መካከል በስዊድን የመድኃኒዓለም ቤተ ክርስቲያን የሚያገለግሉት ሊቀ ትጉሃን ጌጡ ዋነኛ ተጠቃሽ ናቸው። እግዚአብሔርን እና ወላዲተ አምላክን በመተማመን ያለ አንዳች የወረቀት ሠነድ እና ፊርማ ከሌሎች የሃይማኖት አባቶች ጋር በመሆን ስዊድን ውስጥ የጠነሰሱት ሃሳብ ዛሬ ከ3000 በላይ ምዕመናንን ለንደን ውስጥ ተሰባስበው በዓይናቸው ለማየት በመብቃታቸው ፈጣሪን በማመስገን ደስታቸውን ገልጸዋል። ከዚህ በተጨማሪ በለንደን ቆይታቸው ወቅት ወደ አንዳንድ የለንደን ቤተ ክርስቲያናት ጎራ በማለት ለሕዝበ ክርስቲያኑ የሰጡት ስብከተ ወንጌል ‘’ የካህን እና የሴት እንግዳ የለውም ‘’ የሚለውን አባባል በተግባር ያስመሰከሩ ሲሆን በክርስቲያኖች ዘንድ ፍቅር ፣ ህብረት ፣ ሰላም ፣ መቻቻል . . . ወዘተ መሠረታዊ ነገሮች ለመሆናቸው ምሳሌ ሆነዋል ሲሉ በወቅቱ በርካታ ምዕመናን ለዚህ ጸሐፊ ነጻ አስተያየታቸውን ሰጥተዋል።
በጉባኤው ማጠናቀቂያ ላይ ሊቀ ትጉሃን ጌጡ ከዚህ ጸሐፊ ጋር አጭር ቃለ ምልልስ አድርገው ነበር። ከቀረቡላቸው ጥያቄዎች መካከል በ አሁኑ ወቅት በቤተ ክርስቲያን አባቶች መካከል ለምን ልዩነት ተፈጠረ? መፍትሔውስ ምንድን ነው ይላሉ? . . . ወዘተ ይገኙበታል። እንደ እርሳቸው እምነት ምዕመናኑ ዘወትር ጥሩ ካህናትን ማየት ይሻል። በቤተ ክርስቲያኒቱ ውስጥ የተፈጠሩት አንዳንድ ያለመግባባቶች ተቀርፈው በምትኩ መቻቻል ፣ አንድነት እና ፍቅር እንዲሠፍን የሁሉም ምዕመናን ፅኑ ፍላጎት መሆኑን ገልጸዋል። ‘’ . . . አንዳንድ በፖለቲካ ይሁን በዘረኝነት ወይም በግል ወዳጅነት ወደ ባለሥልጣናቱ ጠጋ ጠጋ ያሉ ወገኖች የቤተ ክርስቲያኒቱን አንድነት አይፈልጉም። ከእኛ ይልቅ እነርሱ ይሰማሉ ፤ እኛ አቅም አጠረን ፤ አልታመንንም። ይህንን በደንብ እናውቃለን። ችግሩ እዚህ ላይ ነው። ከዚያ ውጪ ምን ይሻላል? ብለን ከማሰብ ከማልቀስ አልቦዘንም። ‘’  ያሉት ሊቀ ትጉሃን ጌጡ ለዚህ ሁሉ ውጥንቅጥ መፍትሔው አዘውትሮ እንደሆነ አስምረውበታል። ‘’ የቃላት ጦርነት ፣ የወረቀት ጋጋታ ፣ የትችት ብዛት ዋጋ የለውም ፤ ይልቁንም የርህራዔ ጸሎት ፣ የአርቆ ማሰብ ጸሎትን እየጸለይን ይህ በኃጢአታችን ያበላሸነውን ሕንጻ ቤተ ክርስቲያን ( አካላችንን ) እግዚአብሔርን በንስሐ ገብተን ብንለምነው እርሱ ችግሩን ይፈታዋል (ሉቃ  21 )።
ይህንን ችግር እና መፍትሔውን በእስራኤል ታሪክ የምናውቀው ነው። እስራኤል እግዚአብሔርን ክደው ጣዖት ሲያመልኩ የመጣባቸውን መከራ የሚቋቋሙት በንስሐ እንጂ በትግል በኃይል አልነበረም። ‘’ እግዚአብሔር የምህረት አምላክ መሆኑን ካህን በመሆኔ ብቻ ሳይሆን በግል ሕይወቴም አይቼዋለሁ። እስቲ ሁላችንም ከራሳችን እንነሳ እና መጀመሪያ እራሳችንን (ሕየወታችንን ) ንጹህ ፣ ቅዱስ ፣ የዋሆች ፣ ትጉህ ፣ ተገዢ . . . ወዘተ እናድርገው በጎደለው እግዚአብሔር ይሞላዋል’’  በማለት ኀዘን እና ቁጭት በተሞላበት መልኩ አስተያየታቸውን ሠጥተዋል። ለተከታታይ ሦስት ቀናት የተካሄደው 13ኛው የመላው አውሮፓ አመታዊ  የስብከተ ወንጌል ጉባኤ የመጠናቀቂያ ዕለት ከአመታዊው የቅድስት ሥላሴ ክብረ በዓል ( አብርሃም ሥላሴዎችን በሰው አምሳል ከድንኳኑ ተቀብሎ ያስተናገደበት ወቅት ዘፍ 18 ፡ 1 – 33 )  መገጣጠሙ ጉባኤውን የተለየ እንዲሆን አድርጎታል። በዚህ ክብረ በዓል ላይ ታቦት በመውጣቱ በኢትዮጵያ የሀገር ባህል ልብስ (ነጠላ ፣ ቀሚስ ፣ሱሪ ) የተዋቡት ሕዝበ ክርስቲያን ከወቅቱ የለንደን የበጋ ጸሐይ ጋር በመደመር በ አካባቢው ለሰዓታት የቆየ ደማቅ ብርሃን እንዲያበራ አድርገውታል። የሰንበት ት/ቤቱ መዘምራን ከሌላ ስፍራ ከመጡ መዘምራን ጋር በመሆን ምዕመናኑን እየመሩ ያሰሙት የነበረው ያሬዳዊ ዜማዎች የመሰጧቸው የአካባቢው ነዋሪዎች እና ቱሪስቶች ይህ በገንዘብ እና በጥበብ የማይገኝ ነገር ግን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ብቸኛ መንፈሳዊ ቅርስ የሆነውን ሥርዓተ ቤተ ከርስቲያን በማስታወሻነት ለመያዝ በምስል መቅረጫዎቻቸው ለማስቀረት ተሯሩጠዋል። አንዳንዶቹም የበዓሉን ምንነት ለማወቅ ሲጠይቁ ተስተውለዋል። በዚህ ክብረ በዓል ላይ በክብር እንግድነት የተገኙት የኢዝልንግተን አካባቢ (ሰሜናዊ ለንደን) ከንቲባ ሚስስ ሙና ስለ ኢትዮጵያ እና የኢትዮጵያን አምልኮተ እግዚአብሔር ያላቸውን እውቀት ፣ ፍቅር እና አክብሮት ለምዕመናኑ ገልጸዋል። ምዕመናኑም በጸሎታቸው እንዲያስቧቸው ተማጽነዋል።
ይህ ‘’ የእግዚአብሔር ድምፅ ከተማይቱን ይጠራታል ‘’ ሚክ 6፡9
በሚል ነቢያዊ ጥቅስ የተከፈተው የስብከተ ወንጌል ጉባኤ ሲጠናቀቅ ለመጪው ዓመት በስዊድን ሀገር ለመገናኘት ቀጠሮ በመያዝ ከእንግሊዝ ውጪ የመጡ ምዕመናን በለንደን ከሚኖሩ ወገኖቻቸው ጋር ተመራርቀው ተሸኛኝተዋል። ከዚያ በመቀጠል በለንደን ፣ በማነችስተር ፣ በበርሚንግሃም ፣ በኒውካስል እና ስቶክ ኦን ትሬንት ከተሞች ለሳምንታት የተሰበከው የ3ኛው የቤተ ክርስቲያኒቱ አመታዊ መንፈሳዊ ጉባኤ በመንፈሳዊ አስተማሪነቱ ከብዙዎች ምዕመናን  አእምሮ የማይጠፋ ትዝታን ጥሏል ተብሎ ይገመታል። ዲ/ን ብርሃኑ አድማሴ በዚህ ጉባኤ ላይ መድረኩን በአመዛኙ ከታላላቅ መምህራን የተረከበበት አጋጣሚ ነበር። ዲ/ን ብርሃኑ አድማሴ አስኳል እውቀቱን ከመንፈሳዊ ተሰጥዖው ጋር እያዋዛ ሕዝበ ክርስቲያኑ በሚገባው ቋንቋ እና አቀራረብ ስለ ‘’ ሰጥቶ መቀበል ፣ አፅዋመ ቤተ ክርስቲያን ፣ ደብረ ታቦር ፣ እና ቅዱስ ጋብቻ ‘’ አስተምሯል። ስለ ቅዱስ ጋብቻ የሰጠው ትምህርት እና ምክር የአብዛኛውን የማህበረሰባችንን መሠረታዊ ችግሮችን የዳሰሰ ነበር። ይህ ትምህርት ለተከታታይ ቀናት በተሰጠበት ወቅት ምዕመናኑ ትምህርቱን ለራሳቸው ለማስቀረት ወይም ለወዳጆቻቸው ለማዳረስ በተለያዩ የድምጽ መቅረጫዎች ለመቅረጽ ሲረባረቡ ተስተውለዋል። በስተኋላ ግን የጉባኤው አስተባባሪዎች ሁሉንም ስብከተ ወንጌል ጥራቱን በጠበቀ መልኩ ቀርጸው በተመጣጣኝ ዋጋ ለምዕመናኑ እንዲዳደረስ እንደሚያደርጉ በድጋሚ ቃል በመግባታቸው ምዕመናኑ ትዕዛዙን በይሁንታ ተቀብሎታል።
ይህ የቅዱስ ጋብቻ ስብከት ምንም እንኳን ሙሉ በሙሉ በመጽሐፍ ቅዱስ እና በገሃዱ አለም የሚታዩ የማህበረሰባችን ውጣ ውረዶች ላይ የተመረኮዘ ቢሆንም የዚህ ጽሑፍ አቅራቢን ጨምሮ በርካታ ምዕመናንን በታዋቂው ኢትዮጵያዊ የስነ ጽሑፍ ሰው ዶ/ር ሃዲስ አለማየሁ ተደርሶ በተራኪው ፍቃዱ ተክለ ማርያም አማካኝነት በአንድ ወቅት በኢትዮጵያ ሬዲዮ ከመፃሕፍት አለም የትረካ ፕሮግራም ከአንድ አመት በላይ አጓጊ በመሆን የተተረከው ‘’ ፍቅር እስከ መቃብርን ‘’ መጽሐፍ አስታውሷል። መጽሐፉ በውስጡ የያዛቸው ገጸ ባሕርያት እና መቸቶች በወቅቱ ሬዲዮኑን በድንገት የከፈተ ማንኛውም የአማርኛ ቋንቋ ሰሚ ቀልብ እና ጆሮዎች ለአፍታም ቢሆን መሳቡ አይካድም።
የብዙዎቹን ምዕመናን ቀልብ በመሳብ ልባቸውን ጭምር ያንኳኳው የዲ/ን ብርሃኑ ስብከትም ቢሆን የደብረ ገነት ቅድስት ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን በኪራይ የምትጠቀምበት ሕንጻ ቤተ ክርስቲያን መያዝ ከነበረበት 500 – 600 መቀመጫዎች ተጠብበው ሁሉም ሕዝበ ክርሰቲያን ፕሮግራሙን በተመስጦ እንዲከታተል አድርጎታል። ስብከተ ወንጌሉን ተከትሎ ምዕመናኑ እንዲብራሩላቸው የሚፈልጉት ጥያቄዎችን በጽሑፍ እና በግንባር እንዲያቀርቡ የተደረገው ፕሮግራም የጉባኤው ሌላኛው ጠንካራ ጎን ነበር። በርካታ ሃይማኖታዊ እና ማህበራዊ የሆኑ ጥያቄዎች ምላሽ አግኝታዋል። ከአንዲት ምዕመን ቀረበ የተባለው ‘’ እጮኛዬን ወደ ቤተ ክርስቲያን ይዤው ብመጣ ችግር አለው . . . ወዘተ ? ‘’ ለሚለው ጥያቄ ‘’ እርሱ ይምጣ እንጂ ችግር የለውም ‘’ የሚለው አጭር ምላሽ ብዙዎቹን በጊዜው ፈገግ ያደረገ ቢሆንም መልዕክቱ ቤተ ክርስቲያን የጠፉ ልጆቿ ሲመለሱ ዘወትር ደስ ይላታል ከሚለው አምላካዊ ቃል ጋር ተዛማጅነት አለው። በሃይማኖት የማይገናኙ ጥንዶች እንኳን ወንዱ በሴቷ ወይም ሴቷ በወንዱ እንዴት እንደሚቀደሱ መለያየት እንደሌለባቸው ( 1ቆሮ 7 ፡ 10 – 12 ) የተሰጠው ትምህርት ቀደም ሲል በዚህ መልኩ ወደ ትዳር የገቡ ወገኖች ምን ማድረግ እንዳለባቸው ያመላከተ ትምህርት ነበር። በስተመጨረሻ ‘’ ነጠላ ዜማዬ ነች . . . ‘’ በማለት ስለ ኢትዮጵያ ፣ ስለ ሕዝቧ አንድነት እንዲሁም ስለ ጎረቤቶቿ ሰላም እና ፍቅር ያዜመው ዲ/ን ብርሃኑ ከምዕመናኑ ሞቅ ያለ የሞራል ድጋፍ እና መንፈሳዊ ምርቃት ተችሮታል።
የስብከተ ወንጌል ጉባኤው ያማረ እና የተዋጣለት እንዲሆን በመቶ የሚቆጠሩ የለንደን ነዋሪዎች ቤታቸውን ለእንግዶች ሙሉ በሙሉ ወይም በከፊል በመልቀቅ ክርስቲያናዊ ተግባር የፈጸሙ ሲሆን በግል ደረጃ አቶ ኃይሌ (በግጥም እና ምስጋና ፣ ዘማሪት ሀረገ ወይን ፣ አቶ ወንደሠን (በመንፋሳዊ ድራማ እና ዝግጅቱን በድምፅ በመቅረጽ ) በኩል ስማቸው ለአብነት ያህል ተጠርተዋል።
ከሁሉም በላይ ስሙ ጎላ ብሎ ሊጠራ የሚገባው ወንድም መዘምር ዲ/ን ምንዳዬ ብርሃኑ ከመንፈሳዊ ወንድሙ ዲ/ን ብርሃኑ ጋር በመሆን በፕሮግራሞቹ ጣልቃ በመግባት ምዕመናኑን በመንፈሳዊ መዝሙሮቹ አስተምሯል፤ ፈጣሪውን በጋራ አመስግኗል። ‘’ ብዙ እንድንዘምር ፣ ፈጣሪን እንድናመሰግን ቦታ እና ጊዜ አገደን . . . ወዘተ ‘’ የሚለው ዲ/ን ምንዳዬ የተዋጣለት እና መለኮታዊ የሆነውን ጣዕመ ዝማሬውን በተሣካ ሁኔታ እንዲያቀርብ አርቲስት ተመስገን የተባሉ የባህላዊ እና ዘመናዊ ሙዚቃ ተጫዋች ከዲ/ን ምንዳዬ እያንዳንዱ ዜማ ጋር የሚሄድ የክራር ቅኝታቸውን በማሰተካከል ያደረጉት ጥረት ምዕመናኑ መዝሙሮቹን በሃይማኖታዊ የምስጋና መሣሪያዎች ( ክራር ፣ በገና ፣ ከበሮ . . . ወዘተ ) አማካኝነት ፈጣሪውን እንዲያመሰግን አድርገዋል። በዲ/ን ምንዳዬ እና አርቲስት ተመስገን መካከል የነበረው ሙያዊ ጥምረት ሁለቱ ወንድሞች ቀደም ሲል አገር ቤት አብረው ያገለገሉ አስመስሏል። ዲ/ን ምንዳዬ በቪሲዲ መልክ ያስቀረጸው ‘’ ደጅሽ ላይ ቆሜ ስለምንሽ ‘’ የሚለው ቁጥር 6 አዲስ መንፈሳዊ አልበሙ ለንደን ላይ እንዲመረቅ አጋጣሚው መፍቀዱ ለንደኖች እድለኞች እና የበረከቱ ተካፋዮች አድርጓቸዋል።  
ጉባኤው ባማረ እና በደመቀ ሁኔታ እንዲከናወን ስፖንሰር የሆኑት የኢትዮጵያ አየር መንገድ ( አንድ ከለንደን አዲስ አበባ ደርሶ መልስ የአየር ቲኬት ) ፣ ስንቄ እና ኮከብ የተባሉ ሁለት ታዋቂ የለንደን ሬስቶራንቶች (ምዕመናኑ ምግብ እንዲቋደሱ በማድረግ ) ፣ አንድ ምዕመን ለሠንበት ት/ቤቱ ተማሪዎች ሙሉ ልብስ በማሰፋት ሌሎችም ስማቸውን መግለጽ ያልፈለጉ ወገኖች ቤተ ክርስቲያኒቱ ለዝግጅቱ አጠቃላይ ወጪነት የያዘችውን 14 ሺህ ፓውንድ ( ወደ 280 ሺህ ብር ) ከሞላ ጎደል እንዲሸፈን ለማድረግ ጥረት ማድረጋቸው የምዕመናኑ እና የቤተ ክርስቲያኑ ጥምረትን ያመለክታል። ወደፊትም በሁሉም ቤተ ክርስቲያን ዘንድ ሊተገበር የሚገባ ተግባር ነው። የዝግጅት ኮሚቴውም አጠቃላይ ወጪ እና ገቢውን በቅርቡ ይፋ እንደሚያደርግ ይጠበቃል።
በበዓሉ ማጠናቀቂያ ዕለት እድሜያቸው በግምት ከ12 ዓመት በታች የሆኑ ታዳጊ ሕፃናት ለወላጆቻቸው እና ለወገኖቻቸው ያሰሙት የግዕዝ እና የአማርኛ መዝሙራት እንሰሳ እንኳን አፍ አውጥታ እንድትናገር ያስቻለ ፈጣሪ በአምሳሉ የተፈጠሩትን የሕፃናት የምስጋና አፍ ለመስማት ምን ያህል እንደሚሻ በገሃድ የታየበት መድረክ ነበር። ሕፃናቱ ላሳዩት ክርስቲያናዊ ጨዋነት እና ዝማሬ ከታዳሚዎቹ በሙሉ ሞቅ ያለ ጭብጨባ እና የእልልታ ምስጋና አግኝተዋል። የፕሮግራሙ ማሣረጊያ የሆነው ‘’ የጥብርያዶስ አሣዎች ‘’ በሚል ርዕስ በሠንበት ት/ቤቱ የተዘጋጀው መንፈሳዊ ድራማ የሁሉንም ቀልብ የሳበ ነበር። ድራማው በተለይ በፈረንጆች የአሻንጉሊት ፊልሞች አእምሯቸው የጦዘውን ታዳጊ ሕፃናትን ሣይቀሩ የተዋኒያኑን ድምፅ እና እንቅስቃሴ በቅርቡ ለመከታተል ያስችላቸው ዘንድ የተዘጋጁላቸውን ወንበሮች ወደ ጎን በመተው ከመድረኩ ፊት ከወለል ላይ ተኰልኩለው በተመስጦ እንዲከታተሉ አድርጓቸዋል። ተውኔቱን በቪዲዮ ካሜራቸው የቀረጹት አያሌ ናቸው።
በቤተክርስቲያኒቱ አስተዳደር የቅርብ እገዛ እና ክትትል እየተደረገለት በሰባት የዝግጅት አስተባባሪ ኮሚቴ አባላት አማካኝነት ሕዝበ ክርስቲያኑ በሙሉ ልቡ ዝግጅቱ የራሱ እንዲሆን አድርጎ ተሣታፊ ያደረገው የስብከት ወንጌል ጉባኤ ሙሉ በሙሉ አልጋ በአልጋ የተጓዘ ነው ማለት አይቻልም። አሣዛኝ ገጠመኞችም አልታጡበትም። ለምሳሌ ያህል ዘማሪያኑ እና ምዕመናኑ ፈጣሪን ለማመስገን ድምፃቸው ከፍ አድርገው ሣለ ‘’ . . . የአካባቢው ነዋሪዎች ለካውንስሉ (መስተዳድሩ) አቤቱታ በማቅረባቸው ድምፃችሁን ቀንሱ ፣ በሮች እና መስኮቶች ይዘጉ፣ የቤተ ክርስቲያኒቱ ባለቤቶች ( ነጮቹ ) ቦታውን ለሌላ አገልግሎት ስለሚፈልጉት ፈጥናችሁ ውጡ ወይም የፕሮግራም መጋጨት ስለተፈጠረ በሚቀጥለው ቀን ስብከተ ወንጌል አይኖርም . . . ወዘተ ‘’ የሚሉት ማስታወቂያዎች እና ምክሮች በርካታ ምዕመናን ስታቸውን ነክቷል። ሁኔታውም ‘’ የሰው ወርቅ አያደምቅ ‘’ መባሉ እውነትነት እንዳለው በተግባር ተስተውሎበታል።
ይህ ጊዜ የማይሰጠው የሕዝበ ክርሰቲያኑ የወንጌል ርሃብ ጥያቄ የቤተ ክርስቲያኒቱ አስተዳደርም ችግር መሆኑ ባይካድም ጉዳዩ በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ የሚመለከታቸው ወገኖች በአዲሱ የኢትዮጵያ ዘመን መለወጫ ( አዲስ አመት ) አንድ አዲስ የሆነ መንፈስን የሚያረጋጋ ሃሣብ ይዘው እንዲመጡ የብዙ ምዕመናን ተስፋ ነው። ከዚህ ጉዳይ ጋር በተያያዘ ለሰላሳ አመታት የራሷ የሆነ ቋሚ ስፍራ ሣይኖራት ከአንዱ ስፍራ ወደ ሌላው ስፍራ ስትንከራተት የቆየቸው የለንደን ርዕሰ አድባራት ደብረ ጽዮን ቅድስት ማርያም  ቤተ ክርስቲያን ሕንፃ ቤተ ክርስቲያን ግዢን ለማጠናቀቅ በለንደን የሚኖሩ ከሰላሳ በላይ ታዋቂ ኢትዮጵያዊያን አርቲስቶች ከሚመለከታቸው  የቤተ ክርስቲያኒቱ ኃላፊዎች እና ምዕመናን ጋር በመሆን  አላማቸውን ግቡን እንዲመታ ማድረጋቸው እና ቤተ ክርስቲያኒቱ በስተመጨረሻ የራሷ የሆነ ቋሚ ሥፍራ ማግኘቷ በመንፈሳዊ አርአያነቱ ሊጠቀስ ይገባል። በጊዜው የነበረውን ሁኔታም ይህ ጸሐፊ በታዋቂው ‘’ የድሬ ቲዩብ ‘’ ድህረ ገጽ አማካኝነት በምስል የተደገፈ ዘገባ አቅርቧል።

የኢትዮጵያ ታሪካዊ ቅርሶች በአደጋ ውስጥ ናቸው ተባለ

Thursday, September 2nd, 2010

(ለደጀ ሰላም መጦመሪያ፤ ታምሩ ገዳ ከለንደን):- ኢትዮጵያን በ

ለም  በታሪክ እና በቅርስ ባለቤትነት ተጠቃሽ ከሆኑት ጥቂት አገሮች መካከል አንዷ እንድትሆን ያደረጓት ታሪካዊ እና ሃይማኖታዊ ቅርሶቿ እጅግ አስጊ በሆነ የመጥፋት አዝማሚያ ውስጥ መሆናቸው ተገለጸ። “የኢትዮጵያ ገዳማት ፣ አድባራት እና የአብነት ት/ቤቶች (የቆሎ ት/ቤቶች) ያሉበት ነባራዊ ሁኔታ” በሚል ርዕስ ዙሪያ አጭር ጥናታዊ ጽሑፍ በማድረግ ለግንዛቤ ያህል ለንደን ውስጥ ለሚገኙ በሺዎች ለሚቆጠሩ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን  አማኞች እና ጥሪ ለተደረገላቸው እንግዶች ባለፈው ሣምንት ገለጻ ያደረጉት
እዚሁ እንግሊዝ አገር ውስጥ በተለዋጭ የተፈጥሮ ሀብት ዙሪያ ከፍተኛ ምርምር በማድረግ ላይ የሚገኙት አቶ በላቸው ጨከነ በአሁኑ ወቅት በርካታ ዓመታት ያስቆጠሩት ሕንፃ አብያተ ክርስቲያናት በእድሳት እጦት ምክንያት በውስጣቸው የሚገኙት ውድ እና ብርቅዬ ቅርሶች መበላሸት፣ ዘራፊዎች እነዚህ ብርቅዬ እና ውድ የሆኑ ንዋየ ቅድሳት ለመስረቅ ማተኮራቸው፣ በተለያዩ ጊዜያት በገዳማት እና በዙሪያቸው በሚገኙ ደኖች ላይ የእሳት አደጋ መድረስ እንዲሁም የቆሎ ተማሪዎች እና መምህራኖቻቸው በምግብ እጦት እና በእርዛት ምክንያት ቀያቸውን እየለቀቁ ወደ ከተሞች መሠደድ በታሪካዊ የኢትዮጵያ ቅርሶች ላይ ካነጣጠሩት ዋነኛ ችግሮች የሚጠቀሱ ናቸው ብለዋል።

አቶ በላቸው ከዚህ ጸሐፊ ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ እነዚህ ታሪካዊ እና ብሔራዊ ቅርሶችን ጠብቆ ለተተኪው ትውልድ ማስረከብ ለአንድ ወገን ብቻ የሚተው ኃላፊነት እንዳልሆነ ይልቁንም አገራችንን ፣ ባህላችን ፣ ቅርሳችንን እንወዳለን የሚሉ ወገኖች በሙሉ በግል ፣ በቤተሰብ እና በቡድን በመሆን በቅርሶች ላይ የተጋረጡትን አደጋዎች ሊታደጉ ይገባቸዋል ሲሉ ጥሪ አቅርበዋል።
ይህንን የማሰባሰብ ዘመቻን በተመለከተ በአሜሪካ የሚገኙ የማኅበረ ቅዱሳን አባላት እያደረጉት ያለውን ጥረት አቶ በላቸው ሳያመሰግኑ አላለፉም። በተለያዩ ወቅቶች ከኢትዮጵያ በድብቅ መጥተው በእንግሊዝ፣ በአሜሪካ፣ በቫቲካን (ኢጣሊያ) . . . ወዘተ በመሳሰሉት አገሮች ከሦስት ሺህ በላይ ብርቅዬ የኢትዮጵያ ንዋየ ቅድሳት እና የብራና መጻሕፍት ለባዕዳኑ ሙዚየሞች ከፍተኛ የገቢ ምንጭ ማስገኛ በመሆን እያገለገሉ ይገኛሉ ሲሉ አቶ በላቸው በቁጭት ተናግረዋል። በየዓመቱ ኢትዮጵያን ለመጎብኘት ወደ ሀገር ቤት ጎራ ከሚሉት ጎብኚዎች መካከል ከ85% በላይ የሚገመቱት አመጣጣቸው እነዚህኑ በመጥፋት ላይ የሚገኙትን ታሪካዊ፣ ሃይማኖታዊ እና ብሔራዊ የኢትዮጵያ አሻራዎች የሆኑትን ቅርሶች ለመመልከት እንደሆነ በጥናታዊ ጽሑፋቸው ላይ አካትተዋል። አቶ በላቸው በቅርቡ ከአማርኛ ወደ እንግሊዝኛ፣ ፈረንሳይኛ እና ጀርመንኛ የተተረጎመ ዘመናዊ የሕፃናት መማሪያ ዲቪዲ በማዘጋጀት የዜግነት ድርሻቸውን መወጣታቸውን የተለያዩ መገናኛ ብዙኃን ዘግበዋል።



“የሐውልቱ ስር ቁማርተኞች”ን ማንበብ ከፈለጉ …

Wednesday, August 18th, 2010

(ደጀ ሰላም፤ ኦገስት 18/2010)፦ የፓትርያርኩና የማፊያው ቡድን “ስውር ፀሐፊ” (Ghost Writer) ዘሪሁን ሙላቱ ስለ ፓትርያርኩ ሐውልትና ተያያዥ ጉዳዮች  ባለ 50 ገጽ መጽሐፍ ማውጣቱን፤ እነ በጋሻው ደሳለኝና ኤልዛቤል የምትባለው ወ/ሮ እጅጋየሁ እንደተጠቀሱበት፤ ዲያቆን ሲባል ቆይቶ በቅርቡ ሊቀ ትጉሃን የሚል የማዕረግ ስም የደረበው Ghost Writer ዘሪሁን ሙላቱ ጊዜውን በቶሎ በማጥናት እና የፓትርያርኩ ሐውልት ብዙ ተቃውሞ እንደበዛበት ሲመለከት፣ የሐውልቱ ተቃዋሚዎች ያሉትን በመሰብሰብና መጽሐፍ አድርጎ በማሳተም ሲያሳዝነው የሰነበተውን ምእመን አሁን ደግሞ ገንዘቡን ሊበላው ይህንን ፓምፍሌት (መጽሐፍ ለማለት ይከብዳል) ማሳተሙን በተከታታይ መዘገባችን ይታወሳል። መጽሐፉን ማንበብ ለፍርድ ይመቻልና እነሆ እንዲህ አዘጋጅተነዋል። ለማንበብ ይህንን (አስነብበኝ) ይጫኑ።



ለሊቀ ማእምራን ፋንታሁን ሙጬ ‹‹የማጽናኛ መዋጮ›› ሊበረክትላቸው ነው

Wednesday, August 18th, 2010
  •     መዋጮውን የአጥቢያ ሰበካ ጉባኤያት ጸሐፊዎች ያስተባብራሉ
    • (ደጀ ሰላም፤ ኦገስት 18/2010፤ ነሐሴ 12/2002 ዓ.ም):- በቁጥር ከስድሳ የማያንሱ እና በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ሥር የሚገኙ የአጥቢያ አብያተ ክርስቲያን ሰበካ ጉባኤያት ጸሐፊዎች እና አንዳንድ የአጥቢያ አብያተ ክርስቲያን አስተዳዳሪዎች ለአወዛጋቢው የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ሥራ አስኪያጅ ሊቀ ማእምራን ፋንታሁን ሙጬ ‹‹የማጽናኛ መዋጮ›› ሊያበረክቱ ማቀዳቸው ተሰማ፡፡ የሀገረ ስብከቱ ምንጮች ለደጀ ሰላም ያደረሱት መረጃ እንደሚጠቁመው፣ ‹‹የማጽናኛውን መዋጮ›› ለማስፈጸም በዋናነት እየተንቀሳቀሱ የሚገኙት የአጥቢያ አብያተ ክርስቲያን ጸሐፊዎች እና አንዳንድ አስተዳዳሪዎች ሲሆኑ ማጽናኛው የሚከናወነው ጸሐፊዎቹ ባሰባሰቡት የገንዘብ አስተዋፅኦ ነው፡፡
      እንደ ምንጮቹ ገለጻ እስከ አሁን ድረስ ሥራ አስኪያጁ በግላዊ እና ማኅበራዊ ኑሯቸው ከደረሰባቸው የሞራል ጉዳት ለማጽናናት ታስቦ እየተደረገ ያለው የገንዘብ አስተዋፅኦ መጠኑ 30‚000 ብር ገደማ መድረሱ የተመለከተ ሲሆን ከነገ በስቲያ ዓርብ ለሥራ አስኪያጁ እንደሚበረክትላቸው ለመረዳት ተችሏል፡፡ ሱባኤውን ምክንያት በማድረግ በድሬዳዋ ሀገረ ስብከት የሚገኙት እና ሕመማቸው እንደጠናባቸው የሚሰማው ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ ወደ አዲስ አበባ ከመመለሳቸው በፊት በጥድፊያ እንዲፈጸም ታስቦ የተደረገውን ይህንኑ ‹‹ገንዘባዊ ማጽናኛ›› በዋናነት የመሩት ፀጋዬ ግደይ (ከመንበረ መንግሥት ቅዱስ ገብርኤል ገዳም – ግቢ ገብርኤል)፣ መልአከ ፀሐይ በቀለ (የፈረንሳይ ደብረ ፀሐይ ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪ)፣ መምህር ሰሎሞን በቀለ (የደብረ ነጓድጓድ ቅዱስ ዮሐንስ ቤተ ክርስቲያን ሰበካ ጉባኤ ጸሐፊ)፣ መንግሥቱ (ከደብረ ብሥራት ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን) መሆናቸው ታውቋል፡፡ የገንዘብ አስተዋፅኦው ምንጭ ከየት እንደ ኾነ እንዲሁም የት እና በምን አኳኋን ለሥራ አስኪያጁ እንደሚበረከትላቸው ለጊዜው ለማረጋገጥ አልተቻለም፡፡ በቁጥራቸው ስድሳ ያህል ይሆናሉ የተባሉት የአጥቢያ አብያተ ክርስቲያን ሰበካ ጉባኤ ጸሐፊዎች በተጠቀሰው አኳኋን ተቆርቋሪነታቸውን ሊያሳዩ የበቁት ከሚበዙት የሀገረ ስብከቱ አድባራት እና ገዳማት አስተዳዳሪዎች በተቃራኒ ከሥራ አስኪያጁ ጋራ በመሠረቱት በጥቅም ላይ የተመሠረተ ልዩ ግንኙነት ምክንያት እንደሆነ ተጠቁሟል፡፡ ይኸውም ሊቀ ማእምራን ፋንታሁን ሙጬ የፀሐፊዎቹን ዘመድ አዝማድ እና ወዳጆች በተለያዩ አጥቢያ አብያተ ክርስቲያን በማስቀጠር እና አግባብነት የሌለው ዕድገት እና ዝውውር በመስጠት የሚገለጽ ሲሆን ፀሐፊዎቹ በበኩላቸው ደግሞ በዋናነት ለሥራ አስኪያጁ ውለታ በሚያበረክቱላቸው በዐሥር ሺሕ ብሮች የሚቆጠር እጅ መንሻ እና ሌሎች የዓይነት ስጦታዎች የሚፈጸም ነው፡፡ ሊቀ ማእምራን ፋንታሁን ሙጩ በመዋጮ ትዳር የመመሥረት፤ የሞባይል፣ የነዳጅ፣ የቤት ቁሳቁሶቻቸውን እና የዕለት ምግባቸውን ወጪዎች በደጅ ጠኚዎች መዋጮ የመሸፈን፣ ይህንንም በአጋፋሪዎቻቸው በኩል በማስፈጸም ገንዘብ የማጋበስ ልማድ ክፉኛ የተጠናወታቸው መሆኑ ይነገራል፡፡ ሥራ አስኪያጁ ከአጥቢያ ሰበካ ጉባኤያት ጸሐፊዎች ጋራ በመሠረቱት ልዩ የጥቅም ግንኙነት ሳቢያ የተማረሩ የአጥቢያዎቹ አስተዳዳሪዎች አቤቱታቸውን ፓትርያርኩ ዘንድ እስከ ማቅረብ ደርሰው እንደ ነበር እኒሁ የሀገረ ስብከቱ ምንጮች ያስረዳሉ፡፡ ለሥራ አስኪያጁ ‹‹የማጽናኛ መዋጮ›› ለማበርከት ሰበብ ሆኖ የተጠቀሰው ‹‹የሐውልቱ ሥር ቁማርተኞች›› በሚል ርእስ በስውሩ ጸሐፊ ‹ሊቀ ትጉሃን› ዘሪሁን ሙላቱ በቅርቡ ‹‹የተጦመረው›› አሸማቃቂ ጽሑፍ የሊቀ ማእምራን ፋንታሁን ሙጩን ግላዊ ሕይወት፣ ማኅበራዊ ግንኙነት እና የሥራ ተነሣሽነት በእጅጉ መጉዳቱ እንደ ሆነ ተገልጧል፡፡ ‹‹ነገረ ፋንታሁን››  በሚለው የጽሑፉ ክፍል(ገጽ 9 – 23) ሊቀ ማእምራን ፋንታሁን ሙጩ በቀደመው ኑሯቸው – ‹‹ጨካኝ የደርግ ኀምሳ አለቃ›› አሁን ደግሞ ‹‹የኢሕአዴግ ዋናው ሰው እኔ ነኝ›› እያሉ በ‹ፖሊቲካ ጫዎታ› የሚያምታቱ፣ ‹‹በትዳር ሕይወታቸው ላይ ባደረሱት ከፍተኛ ደባ፣ ቅሌት እና የወሲብ መዘዝ ብዙዎችን ወደ መቃብር ያሳደዱ፣ የግል ጤንነታቸው የማያሳስባቸው እና በራሳቸው ተስፋ የቆረጡ››፣ በትምህርት ይዞታቸው ‹‹ሰነፍ›› ከመሆናቸው የተነሣ ‹‹3ኤፍ›› የሚል ቅጽል ስም የተሰጣቸው፣ በካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን ባገኙት ነጻ የትምህርት ዕድል መሠረት ከፍተኛ ትምህርታቸውን በሚከታተሉበት ኦስትርያ/ቪዬና ‹‹ወደፊት የካቶሊክ ካህን ለመሆን በመሐላ የተፈጠሙ›› ይኹንና ‹‹የሚያወግዛቸው አጥተው፣ ቅዱስ ነኝ ብለው ከብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት ጋራ የተሰለፉ››፣ በአስተዳደራቸው በገጠማቸው ‹‹የብቃት ግሽበት›› ሀገረ ስብከቱን እንደ ግል ግሮሰሪያቸው በመቁጠር በሥራ ፈላጊ ካህናት ላይ ጭከና እና አረመኔነት የተመላበት የሰብአዊ መብት ረገጣ እየፈጸሙ በሰብአዊ መብት ተሟጓቾች ዘንድ የቤተ ክርስቲያናችንን ገጽታ ያበላሹ – ‹‹መደዴ››፣ በሚልዮኖች የሚቆጠር የቤተ ክርስቲያንን ጥሬ ገንዘብ በዘረፋ በማካበት ብልጽግናን በአቋራጭ የተቆናጠጡ -‹‹ወቅታዊ ባለጸጋ››፣ የአቅም ግንባታ ጥረትዋን የሚያዳክሙ – ‹‹ሙሰኛ››፤ በአጠቃላይ ካለባቸው ከፍተኛ የሥነ ምግባር ግድፈት አኳያ በፍትሕ መንፈሳዊ እንደተደነገገው ከሐላፊነታቸው ተነሥተው እና ከክህነታቸው ተሽረው በሕግ መጠየቅ እንደሚገባቸው እና ይህም ‹‹ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን መታደግ›› መሆኑን ያሳስባል፡፡ በተያያዘ ዜና በትላንትናው ዕለት ተሲዓት በኋላ ከስውሩ ጸሐፊ አዲሱ ‹መጽሐፍ› ሥርጭት ጋራ በተገናኘ አክሊል ዳምጠው የተባለ የቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ ደቀ መዝሙር ፒያሳ አካባቢ ለአጭር ጊዜ በፖሊስ ቁጥጥር ሥር ከዋለ በኋላ ‹‹በስሕተት ነው›› በሚል መለቀቁ ተሰምቷል፡፡ ይኸው ደቀ መዝሙር ቀደም ሲል ከግንቦት 1997ቱ ምርጫ መነሣሣት ጋራ በተያያዘ ከኮሌጁ ታግደው ከነበሩት እና ባለፈው ዓመት ትምህርታቸውን እንዲቀጥሉ በአስተዳደሩ ከተፈቀደላቸው ዐሥራ አንድ ደቀ መዛሙርት አንዱ መሆኑ ተመልክቷል፡፡ በሌላ በኩል በዚሁ ‹መጽሐፍ› ከእነ ሊቀ ማእምራን ፋንታሁን ሙጬ እና በጋሻው ደሳለኝ ጋራ ‹‹ቅዱስ ፓትርያሪኩን ማስፈራሪያ እና የንግድ ምልክት ያደረጉ የዘመናችን አፍኒን እና ፊንሐስ›› የተባሉት ወይዘሮ እጅጋየሁ በየነ የማያባራ ራስ ምታት በሆነባቸው የቀድሞ ወዳጃቸው የአሁኑ ባላንጣቸው ሊቀ ትጉሃን ዘሪሁን ሙላቱ ጉዳይ ላይ ለመምከር የሱባኤውን መጠናቀቅ ሳይታገሡ ፓትርያሪኩ ወደሚገኙበት ድሬዳዋ ለመብረር ተነሥተዋል ቢባልም በርግጥም ይሂዱ አይሂዱ ለማረጋገጥ አልተቻለም፡፡ በድሬዳዋ የሚገኙ ምንጮቻችን ዘግይተው እንደጠቆሙን ወይዘሮዋ በስውሩ ጸሐፊ በተጋለጡበት ጉዳይ የአቡነ ጳውሎስ ኀዘኔታ የተቸራቸው ቢሆንም የፓትርያሪኩ የጤና ይዞታ አሳሳቢ ደረጃ ላይ ነው በመባሉ በአግባቡ ተቀብለው ያስተናግዷቸዋል ተብሎ አይጠበቅም፡፡ ብዙዎች እንደሚናገሩት የስውሩ ጸሐፊ ተግባር በፓትርያሪኩ ቤተሰቦች ዘንድ እንደ መልካም አጋጣሚ ከመታየቱም በላይ በአሁኑ ወቅት የጠቅላይ ቤተ ክህነቱን አስተዳደር መምሪያ በሐላፊነት በሚቆጣጠሩት ሊቀ ኅሩያን ያሬድ ከበደ ሳይቀር ቀድሞ ታውቆ በኅትመቱ እና ሥርጭቱ ረገድ ልዩ ማበረታቻ እና የገንዘብ ድጋፍ ሳይደረግለት አልቀረም፡፡ ለዚሁም ምክንያቱ በተለይም ሊቀ ኅሩያን ያሬድ ከበደ የአቡነ ጳውሎስን ‹‹ሐውልተ ስም›› መተከል በተመለከተ ከወ/ሮ እጅጋየሁ ጋራ የገቡበት እሰጥ አገባ እና የወሰዱት የተቃውሞ አቋም ነው፡፡ ሊቀ ኅሩያን ያሬድ ሐውልቱ እንዳይተከል እና በተገለጠበትም ዕለት በምረቃው ሥነ ሥርዐት ላይ እንዳይገኙ በልቅሶ ጭምር አቡነ ጳውሎስን ቢማፀኗቸውም ፓትርያሪኩ፣ ‹‹እናንተ እንዲህ የምትሉት ለእኔ ክብር ስለማትጨነቁ ነው፤›› በማለት በአቋማቸው ከመጽናታቸውም በላይ በዙርያቸው የሚገኙት ቤተ ዘመዶቻቸው የሐውልት ምረቃውን ማእከል ላደረገው ለ18ኛ ዓመት በዓለ ሢመታቸው ድምቀት በደከሙላቸው እና ‹‹ለክብሬ ይጨነቃሉ›› ባሏቸው በወ/ሮ እጅጋየሁ እና በሊቀ ካህናት ጌታቸው ዶኒ (በዋናነት) በሚመራው የሐውልት እና የበዓል አከባበር ኮሚቴ በኩል የሚጠየቁትን እገዛ እንዲያደርጉ ኀይለ ቃል አዘል ማሳሰቢያ ሰጥተው ነበር፡፡ በዚሁ የፓትርያሪኩ አቋም መከፋታቸው የተነገረላቸው ሊቀ ኅሩያን ያሬድ በሐውልቱ ምረቃ ዕለት ዘግይተውም ቢሆን በስፍራው በመገኘት እነ ወ/ሮ እጅጋየሁ እና በጋሻው ደሳለኝ ያለከልካይ ሊፈነጩበት ያሰቡበትን ‹‹የስብከተ ወንጌል ጉባኤ›› በአጭሩ እንዲቋጭ ለመርሐ ግብሩ አስተባባሪዎች በማሳሰብ (በክርናቸው በመጎሰም ጭምር)፣ አልፎ አልፎም በብቸኝነት ሊቆጣጠሩት ያሰቡትን ድምፅ ማጉያ በመንጠቅ፣ በራት ግብዣው መርሐ ግብር ወቅትም ‹‹እግራቸውን ጎትተው›› እና በፓትርያሪኩ ሳይቀር ተለምነው በመምጣት ቅያሜያቸውን እና ቅዋሜያቸውን በግልጽ አሳይተዋል፡፡ በምሽቱ የራት ግብዣ የ‹‹ሐውልተ ስሙን›› ሥራ ሐሳብ በማመንጨት ስለ ክፉ ቀን ‹ውለታው› ከበጋሻው ደሳለኝ 40‚000 ብር እንደ ተጸበለ የተገለጠበት ስውሩ ጸሐፊ ‹ሊቀ ትጉሃን› ዘሪሁን ሙላቱም ከበዓል አሰናጅ ኮሚቴው የተዘጋጀውን የምስጋና ምስክር ወረቀት ከአቡነ ጳውሎስ እጅ ቢቀበልም ለሌላ ርምጃ እያደባ ነበር፡፡ በራሱ አገላለጽ ሰለባዎቹን ጥሩ አድርጎ ለመለጋት ‹‹በሜዳው ላይ እያመቻቻቸው›› ነበር – ‹‹እነዚህ የዘመኑ አፍኒን እና ፊንሐስ እንዲሁም የመናፍቃን ቅጥረኞች ከቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን የክህነት አገልግሎትም ሆነ ሕዝባዊ አገልግሎት ተለይተው የንስሐ ዘመን ተሰጥቷቸው ስለ ኀጢአታቸው እንዲያለቅሱ እና ከምእመናንም ኅብረት እንዲለዩ ይህ ጦማረ ጽድቅ ተጦመረባቸው›› ይላል የአዲሱ ‹መጽሐፉ› መግቢያ!! የፀሐፊው ወዳጆች እንደሚሉት በመጽሐፉ የቀደመ ረቂቅ ውስጥ ስማቸው ተካትቶ ለጊዜው ከቀረላቸው ከእነ ሊቀ ካህናት ጌታቸው ዶኒ ጋራ የሊቀ ኅሩያን ያሬድ ከበደ ‹ዶሴ›ም አንዱ የነበረ ቢሆንም ግለሰቡ አንድም ከላይ ስለተብራራው ድጋፋቸው አልያም ስውሩ ጸሐፊ ከእነ ወ/ሮ እጅጋየሁ በኩል ይከተለኛል ብሎ ከሚሰጋው ማንኛውም ጥቃት ሊያደርጉለት ከሚችሉት የተጠናከረ ጥበቃ አኳያ የሤራ ስሌቱን ሠርቶ እንዳስቀረው ይታመናል፡፡ ይህም ለስውሩ ጸሐፊ የደኅንነት ዋስትና የሰጠው ከመሆኑም በላይ ‹መጽሐፉ›ን በማሳተም እና በማሠራጨት በኩል የረዱት እና እያገዙት የሚገኙት ባልንጀሮቹ ተነጻጻሪ ነጻነት እንዲሰማቸው ሳያደርግ እንደማይቀር ይገመታል፡፡ ከእነ ወ/ሮ እጅጋየሁ በትይዩ መቆማቸው ግልጽ ሆኖ ከሚታየው የፓትርያሪኩ ዘመዶች መተባበር በመነሣት ባለፈው ሳምንት ዓርብ በሊቀ ትጉሃን ዘሪሁን ሙላቱ ላይ በሀገረ ስብከቱ ጽ/ቤት የወጣው የ‹‹ሪፖርት አድርጉ ማሳሰቢያ›› በስውሩ ጸሐፊ ላይ ያን ያህል አሉታዊ ተጽዕኖ ሊኖረው እንደማይችል የጉዳዩ ታዛቢዎች አስተያየታቸውን ይሰጣሉ፡፡ ለዚህም አስረጅዎቻቸውን ሲጠቅሱ፣ በትላንትናው ዕለት ‹መጽሐፉን› ታሰራጫለህ›› በሚል በቁጥጥር ሥር በዋለ በደቂቃዎች ውስጥ ‹‹በስሕተት ነው›› በሚል የተለቀቀውን የቅድስት ሥላሴውን ደቀ መዝሙር ገጠመኝ ይጠቅሳሉ፡፡ ታዛቢዎቹ አክለው እንደሚያስረዱት ‹መጽሐፉ› ለኅትመት ከመዋሉ ጥቂት ቀናት በፊት የተወሰነው ረቂቅ ተልኮላቸው የነበሩት ወይዘሮ እጅጋየሁ ዘሪሁን ሙላቱን ለማስደብደብ ሁለት ጋሻ ጃግሬዎቻቸውን ይልኩበታል፡፡ ስውሩን ጸሐፊ ሲከታተሉት የቆዩት ጋሻ ጃግሬዎችም አራት ኪሎ አካባቢ ደርሰውበት ለጥቂት ደቂቃ ካሯሯጡት በኋላ ብዙም ሳይገፉበት ይመለሳሉ፡፡ የዚህ ዐይነቱ የፈራ ተባ ክትትል በወይዘሮዋ በኩል ያለውን ‹‹የኀይል ሥሡነት›› እንደሚያሳይ ይታመናል፡፡ ከድብደባው ለጥቂት ያመለጠው ስውሩ ጸሐፊም ስልክ በመደወል ወይዘሮዋን በአጸያፊ ስድብ ከሞለጫቸው በኋላ ብዙም ሳይቆይ ‹መጽሐፉ›ን በገበያ ላይ አውሎታል፡፡ እንግዲህ በዚህ መልኩ የኀይላቸውን ልክ የተረዱት ወይዘሮ እጅጋየሁ ከእነ ሊቀ ማእምራን ፋንታሁን ሙጬ እና ሌሎች ‹‹እማኞቻቸው›› ጋራ ለክስ እየተዘጋጁ ቢሆንም ብዙም እንደማይሰዳቸው በመጠራጠር ይመስላል በጽኑ ሕመም ላይ የሚገኙትን ፓትርያሪክ አጉራህ ጠናኝ ለማለት የተዘጋጁት፡፡  ሌላው የታዛቢዎቹ ተዛማጅ ማስረጃ ደግሞ፣ ሰሞኑን የሐውልት ሥራውን የሚቃወም ጽሑፍ አዘጋጅተው በመንበረ ፓትርያሪክ ቅድስተ ቅዱሳን ማርያም ዐጸድ ዙሪያ ሲለጥፉ በመገኘታቸው ብቻ ‹‹የሕዝብን ሰላም ማደፍረስ›› በሚል በፖሊስ ቁጥጥር ሥር ውለው ከአራት ቀናት እስር በኋላ የተለቀቁትን የድጓውን ሊቅ ሊቀ መዘምራን መንግሥቱ ገብረ አብን ይመለከታል፡፡ ወዳጆቻቸው ‹‹የመንግሥቱ ማኒፌስቶ›› ያሉላቸውን የተቃውሞ መግለጫ ይዘት በትክክል ለማወቅ ባይቻልም ዐቃቤ ሕግ ድርጊቱ ‹‹የሕዝብን ሰላም ማደፍረስ ነው›› በሚል ባለፈው ዓርብ ዕለት ክስ መሥርቶባቸው እንደ ነበር ተሰምቷል፤ ይኹንና ወዲያው ከክሱ በነጻ ተሰናብተዋል፡፡ ታዛቢዎቹ ሁኔታውን እነ ሊቀ ኅሩያን ያሬድ ለሐውልት ሥራው ተቃዋሚዎች ሊኖራቸው ከሚችለው አጋርነት ጋራ ያገናኙታል፡፡ ሊቀ መዘምራን መንግሥቱ ከ1960 ዓ.ም ጀምሮ በትግራይ ሽሬ እና መቐለ ወንበር ዘርግተው ሲያስተምሩ የቆዩ አንጋፋ ምሁር የነበሩ ሲሆኑ በ1988 ዓ.ም በሲኖዶሱ ትእዛዝ ከተዘጋጀ በኋላ የትምህርተ ሃይማኖት ሕጸጽ እንዳለበት ተገልጾ የነበረውን መጽሐፍ እና በሀገረ ስብከቱ ይታይ የነበረውን አስተዳደራዊ በደል በመቃወም ምእመኑን ለሰላማዊ ሰልፍ እስከ ማስተባበር የደረሰ ተደማጭነት ነበራቸው፡፡ በመ/ፓ/ቅ/ቅ/ ማርያም ገዳም የዝማሬ መዋስዕት እና የአቋቋሙ መምህር ሆነው ሲያገልግሉ የቆዩት ሊቀ መዘምራን መንግሥቱ በአሁኑ ወቅት በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ያሬድ ሙዚቃ ት/ቤት የዜማ መምህር ሆነው በመሥራት ላይ ይገኛሉ፡፡



    እነ ወ/ሮ እጅጋየሁ የ “ሐውልቱ ሥር ቁማርተኞች ”መጽሐፍ ደራሲን ለመክሰስ በዝግጅት ላይ ናቸው

    Sunday, August 15th, 2010
    • ሊቀ ትጉሃን ዘሪሁን ሙላቱ በሀገረ ስብከቱ ጽ/ቤት ቀርበው ሪፖርት እንዲያደርጉ ማሳሰቢያ ወጣባቸው፤  

    (ደጀ ሰላም፤ ኦገስት 15/2010፤ ነሐሴ 8/2002 ዓ.ም):- በቅርቡ ‹‹የሐውልቱ ሥር ቁማርተኞች›› በሚል ርእስ፣ ፈታሔ በጽድቅ በሚል የፈጠራ ስም የሊቀ ማእምራን ፋንታሁን ሙጬን፣ የወ/ሮ እጅጋየሁ በየነን፣ የበጋሻው ደሳለኝን እና የያሬድ አደመን “ገመና፣ ኀጢአት እና የሙስና ድርጊቶች” በማጋለጥ ባለ ኀምሳ ገጽ ጽሑፍ ያወጣው ስውሩ ጸሐፊ ዘሪሁን ሙላቱ ከዓርብ ነሐሴ ሰባት ቀን 2002 ዓ.ም (ኦገስት 13/2010) ጀምሮ በሚታሰቡ አምስት ተከታታይ የሥራ ቀናት ውስጥ በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ጽ/ቤት ቀርቦ ሪፖርት እንዲያደርግ የሚያዝዝ ማሳሰቢያ ወጣበት፡፡

    የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ሥራ አስኪያጅ በሆኑት አወዛጋቢው ሊቀ ማእምራን ፋንታሁን ሙጬ ትእዛዝ በቁጥር 8785/2467/02 በቀን 7/12/02 መውጣቱ የተገለጸው ይኸው ማሳሰቢያ “ሊቀ ትጉሃን ዘሪሁን ሙላቱ የሕዝብ ግንኙነት ሐላፊ ኾነው እንዲሠሩ በተመደቡበት የቦሌ ደብረ ሳሌም መጥምቁ ዮሐንስ እና ደብረ መድኃኒት መድኃኔ ዓለም ካቴድራል ለረጅም ጊዜ በሥራ ገበታቸው ላይ እንዳልተገኙ” በመግለጽ አገልግሎቱን ሲበድሉ መቆየታቸውን ያመለክታል፡፡ ስለሆነም ሊቀ ትጉሃን ዘሪሁን ከዓርብ ነሐሴ ሰባት ቀን 2002 ዓ.ም ጀምሮ በሚታሰቡ አምስት ተከታታይ የሥራ ቀናት ውስጥ ወደ ሀገረ ስብከቱ ጽ/ቤት ቀርበው ሪፖርት እንዲያደርጉ፣ በእነዚህ ቀናት ውስጥ ሪፖርት ካላደረጉ ግን ሥራቸውን በገዛ ፈቃዳቸው እንደ ለቀቁ ተቆጥሮ በቦታው ላይ ሌላ ሰው የሚሾም መኾኑ ተገልጧል፡፡ በአድራሻ ለሊቀ ትጉሃን ዘሪሁን ሙላቱ፣ በግልባጭ ለሀገረ ስብከቱ የአስተዳደር መምሪያ እና ለቦሌ ደብረ ሳሌም መጥምቁ ዮሐንስ እና ደብረ መድኃኒት መድኃኔ ዓለም ካቴድራል ሰበካ ጉባኤ ጽ/ቤት ግልባጭ የተደረገው ይኸው ማሳሰቢያ በሀገረ ስብከቱ ጽ/ቤት መግቢያ እና በካቴድራሉ ሰበካ ጉባኤ ጽ/ቤት በትላትናው ዕለት እንዲለጠፍ ተደርጓል፡፡
    በሊቀ ትጉሃን ዘሪሁን ላይ ከተመደበበት ካቴድራል ለሀገረ ስብከቱ ርምጃ መነሻ የሚሆን ውሳኔ ባልተላለፈበት ሁኔታ ይህ ዓይነቱ ማሳሰቢያ መውጣቱ፣ “ተገቢ አካሄዱን ያልጠበቀ እና ለግለሰቦች ቂም በቀል ለማመቻቸት ታስቦ ነው” ሲሉ  ሂደቱን በቅርበት የሚከታተሉ የካቴድራሉ አገልጋዮች ተችተዋል፡፡
    በአንጻሩ ‹ስውሩ› ጸሐፊ ዘሪሁን ሙላቱ ጽሑፉን አሳትሞ ካወጣበት ዕለት ጀምሮ የወትሮ መኖርያውን በመቀያየር እና ዳናውን በማጥፋት የ‹መጽሐፉ›ን ሥርጭት በማጧጧፍ ላይ መሆኑ ታውቋል፡፡ ‹መጽሐፉ› እስከ አሁን ድረስ በ10‚000 ኮፒ እንደ ታተመ የተነገረ ሲሆን በተለይም በሐዋሳ እና በአዲስ አበባ ምእመናን ለሱባኤው በከፍተኛ ቁጥር በተሰባሰቡባቸው እንደ እንጦጦ ኪዳነ ምሕረት ባሉ አብያተ ክርስቲያን እንዲሁም በጠቅላይ ቤተ ክህነቱ እና በሀገረ ስብከቱ ጽ/ቤቶች፣ በቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ በከፍተኛ ቁጥር በመሠራጨት ላይ ይገኛል፡፡ በአንዳንድ ሥፍራዎች ሥርጭቱ በባለሀብቶች የታገዘ ሲኾን 15.00 ብር የኾነውን የሽፋን ዋጋ ከኻያ እስከ ኀምሳ ብር በኾነ ዋጋ የሚሸጡ ነጋዴዎች እና ግለሰቦችም አጋጥመዋል፡፡
    መጽሐፉ በአጭር ጊዜ ባገኘው ከፍተኛ ሥርጭት እና ተነባቢነት በእጅጉ የተደናገጡት እነ ሊቀ ማእምራን ፋንታሁን ሙጩ እና ወ/ሮ እጅጋየሁ በየነ ጽሑፉ በይፋ ታትሞ መውጣቱን ከሰሙበት ካለፈው ማክሰኞ ጀምሮ የ‹ስውሩን› ጸሐፊ መግቢያ እና መውጫ በማጥናት እና በማስፈለግ ሲባዝኑ፣ የሚያሳርፉበትን የበቀል ብትር በተመለከተ ሲመክሩ ሰንብተዋል፡፡ እነ በጋሻው ደሳለኝ በበኩላቸው፣ ‹‹እኛ የጌታ ነን፤ ከጌታ ጋራ የሆነ እንኳን ኀምሳ ገጽ አመስት መቶ ገጽ ቢጻፍበትም አይፈራም፤›› በማለት ካፈርኩ አይመልሰኝ ዓይነት ምላሽ በመስጠት ክሳደ-ልቡናቸውን ማደንደናቸው ተሰምቷል፡፡
    ቀደም ሲል ወይዘሮ እጅጋየሁ እርሳቸውን የሚመለከተው የጽሑፉ ረቂቅ እንዲደርሳቸውና ጽሑፉ እንዳይታተም ከ150‚000 – 200‚000 ብር ጉቦ እንዲሰጡ በጸሐፊው መጠየቃቸው የተነገረ ቢሆንም ጸሐፊውን በማስፈራራት እና “ደፍሮ አያሳትመውም” በሚል ተዘናግተው እንደ ቆዩ ተነግሯል፡፡ ከስድስት ወራት በፊት ስውሩ ጸሐፊ አገር ለቅቆ መሄድ እንደሚፈልግና ይህን የውጭ ጉዞውን ከፓትርያርኩ ጋራ ተነጋግረው እንዲያመቻቹለት ያቀረበላቸውን ተማፅኖ ባለመፈጸም ቂም ያተረፉት ወ/ሮ እጅጋየሁ፣ የአዲሱ ‹መጽሐፍ› ኮፒ ማክሰኞ ዕለት ሲደርሳቸው የጸሐፊውን ‹‹አከርካሪ እንደሚሠብሩ›› አልያም ‹‹ራሳቸውን እንደሚያጠፉ›› በመዛት ጸሐፊውን አድኖ ለመያዝ ወደ ሕዝብ ደኅንነት እና ጸጥታ ቢሮ ያመለክታሉ፡፡ ከቢሮው የተሰጣቸው ምላሽ ግን አፋቸውን የሚያሲዝ፣ ጆሯቸውን ጭው የሚያደርግ ነበር፡፡
    ቢሮው ባለፈው ዓመት በተመሳሳይ ወቅት ዘሪሁን ሙላቱ “ተከሥተ ዘሪሁን” በሚል የፈጠራ ስም፣ ‹‹የጳጳሱ ቅሌት›› በሚል ርእስ በወቅቱ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት እና የፓትርያርኩ ረዳት ሊቀ ጳጳስ በነበሩት እና የአቡነ ጳውሎስን ቅጥ ያጣ ቤተ ዘመዳዊ አስተዳደር ለማረም ሌሎች ብፁዓን አባቶችን በማስተባበር በተጋደሉት ብፁዕ አቡነ ሳሙኤል ላይ አባቶችን የሚያዋርድ ስም አጥፊ ጽሑፍ ባወጣበት ወቅት ወይዘሮዋ በጸሐፊው ላይ የነበራቸውን አቋም አስታውሷቸዋል፡፡
    በወቅቱ ለቤተ ክርስቲያን ሥር የሰደደ አስተዳደራዊ ችግር የሠለጠነ መፍትሔ ለመሻት እና የፓትርያርክ አቡነ ጳውሎስን ዓምባገነናዊነት ለመግራት የተባበረ አቋም የነበራቸውን ብፁዓን አባቶች የማስደብደብ ሙከራ ያደረጉት ወይዘሮ እጅጋየሁ፣ ስም አጥፊው ጸሐፊ በፖሊስ ቁጥጥር ሥር ውሎ በሕግ እንዲጠየቅ በብፁዕ አቡነ ሳሙኤል ፊርማ በወጣ ደብዳቤ በተጠየቀበት ወቅት ‹‹የቤተ ክርስቲያን ልጅ ነው፤ እኔ ዐውቀዋለኹ፤ ለፈጸመው ተግባር ሐላፊነቱን እወስዳለኹ፤›› በማለት ተከላክለውለት(ታድገውት) ነበር፡፡ ‹‹በሰፈሩት ቁና…›› እንዲሉ ‹‹ያ ምስክርነትዎ የት ደረሰ?›› የተባሉት ወይዘሮዋ በብስጭት ለሌላ የበቀል ሙከራ በመዘጋጀት ላይ ናቸው፡፡
    በዚህም መሠረት ሊቀ ትጉሃን ዘሪሁን በቦሌ ደብረ ሳሌም መጥምቁ ዮሐንስ እና ደብረ መድኃኒት መድኃኔ ዓለም ካቴድራል የሕዝብ ግንኙነት ሐላፊ ሆኖ ያለ አንዳች ሥራ በየወሩ የሚያገኘውን 1600.00 ብር በስልክ በሰጡት ትእዛዝ ለማሳገድ ሞክረው በካቴድራሉ አስተዳደር ተቃውሞ ካልተሳካላቸው ሊቀ ማእምራን ፋንታሁን ሙጬ ጋራ ዐርብ ዕለት መምከራቸው የተዘገበው ወይዘሮ እጅጋየሁ በስውሩ ጸሐፊ እና ‹‹ግብረ አበሮቹ ናቸው›› ባሏቸው ሌሎች ግለሰቦች ላይ ክስ ለመመሥረት መወሰናቸው ታውቋል፡፡ በክሱ የማይካተቱትን እና የ‹መጽሐፉ›ን ዝግጅት፣ ኅትመት እና ሥርጭት ረድተዋል በሚል የተጠረጠሩ ሌሎች ሠራተኞችም ከደረጃቸው ዝቅ የማድረግ ወይም ወደማይፈልጉት ቦታ የማዘዋወር ዕጣ ፈንታ እንደሚጠብቃቸው ተሰምቷል፡፡
    የክስ ዶሴ እየተሰናዳባቸው ከሚገኙት ግለሰቦች መካከል ለጸሐፊው ዳጎስ ያለ ገንዘብ አስቀድመው በመስጠታቸው እንደ እነ ወ/ሮ እጅጋየሁ እና በጋሻው ከመጋለጥ ለጊዜው ያመለጡት እና ‹‹መጽሐፉን በማዘጋጀት እና በማሳተም ሂደት መርዳታቸው በእነ ሊቀ ማእምራን ፋንታሁን ተደርሶባቸዋል፤›› የተባሉት ሊቀ ካህናት ጌታቸው ዶኒ ይገኙበታል፡፡ ቀደም ሲል ሊቀ ካህናት ጌታቸው ዶኒ ከሚፈለጉባቸው በርካታ የወንጀል ተግባራት መካከል በአስተዳዳሪነት በሚሠሩባት የሰፋሪ ገነት አቃቂ ደብረ ቁስቋም ቅድስት ማርያም እና ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን ለጠበል ቤት ማሠርያ ተብሎ በምእመናን ገንዘብ የተገዙትን የቤት ክዳን ቆርቆሮዎች መዝረፋቸው እየታወቀ በዝምታ ታልፈው ነበር፡፡ ሊቀ ትጉሃን ዘሪሁን ሙላቱ በብላሽ ሲበላው የቆየው የካቴድራሉ ደሞዝ አሁን እነርሱ ሲነኩ ትዝ ያላቸው ግለሰቦች፣ የቁስቋም ምእመናን በሊቀ ካህናት ጌታቸው ዶኒ ላይ ከዘመን በፊት ያቀረቡት የክስ አቤቱታም የታወሳቸው አሁን ከጀርባ እንደ ተወጉ ሲሰማቸው ነው፡፡ በመሆኑም አቤቱታውን የሚያጣራ ልዑክ ወደ ሥፍራው በመላክ ክሳቸውን ለማጠናቀር ተስማምተዋል፡፡
    እነ ወ/ሮ እጅጋየሁ በጸሐፊው እና ተባባሪዎቹ ናቸው በሚሏቸው ላይ ለመመሥረት ለሚያስቡት ጠቅላላ የክስ ሂደት የሀገረ ስብከቱ የሕዝብ ግንኙነት ሐላፊ ቀሲስ ሳሙኤል እሸቱ፣ የፈረንሳይ ደብረ ሰማዕት ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪ ቀሲስ በቀለ እና የደብረ ነጓድጓድ ቅዱስ ዮሐንስ ቤተ ክርስቲያን ሰበካ ጉባኤ ጽ/ቤት ጸሐፊ መምህር ሰሎሞን በቀለ በእማኝነት መዘጋጀታቸውን እና በምክር በኩል እየረዱ መሆኑ ታውቋል፡፡



    በርግጥ መጋቤ ብሉይ የተናገሩት የእርቁ እንቅፋት ሊሆን ይገባ ነበር?

    Saturday, August 14th, 2010

    (ገብር ሔር ዘመ/መንግሥት እንደጻፈው፤ ኦገስት 14/2010፤ ነሐሴ 8/2002 ዓ.ም)፦ በአንድ ወቅት መጋቤ ብሉይ ሰይፈ ሥላሴ በሰሜን አሜሪካ ለሚሰራጨው የሀገር ፍቅር ሬዲዮ የሰጡት መግለጫ ሰሜን አሜሪካንን ለአስራ ስምንት ዓመታት ላላነሰ ግዜ መኖሪያ ባደረጉት “ስደተኛ አባቶች” ዘንድ አቡዋራ ማስነሳቱን በተባራሪ ወሬ ሰምቼው ነበር። ሳይጀመር ለተጠናቀቀው የሰላምና ዕርቅ መሰናክል የሆነውም ይኸው መግለጫ እነደሆነ ይፋ ሲሆን ሊቁ የተናገሩትን ወይም የሰጡትን መግለጫ ለመስማት ልቡናዬ ተጋ። ግን ከየት አግኝቼ ማድመጥ እችላለሁ? እያልኩ ሳሰላስል የመረጃ ጎተራ የሆነችው ደጀ ሰላም በግራም በቀኝም፤ በድጋፍም በጥላቻም ለተሰለፈው ሁሉ ዕርቀ ሰላሙ ሳይጀመር እንዲያልቅ ምክንያት ሆነ የተባለውን የመጋቤ ብሉይ ሰይፈ ሥላሴን ቃለ መጠይቅ እነሆ ብላ የመረጃ መረብ ሰሌዳዋ ላይ አወጣችውና የመረጃ ፍላጎት ጥማቴን አስታገሰችልኝ፡፡ በዚሁ እግረ መንገዴን ትጉሁን የደጀ ሰላም (የእርሱን አባባል ልጋራና) ጦማሪ (በልቶ ጠጥቶ ጠግቦ ረክቶ ሳያመሰግን ሹልክ ብሎ እንደሚሄድ ሰው እንዳይመስልብኝ) እግዚአብሔር ፀጋውን ያብዛልህ እላለሁ፡፡
    ወደ አስተያየቴ ስገባ፤ መጋቤ ብሉይ ሰይፈ ሥላሴ አንቱ የተባሉ ተጠያቂ የቤተ ክርስቲያን ሊቅ እንደነበሩ እንኳን በኢትዮጵያ ባሉ አባቶች ዘንድ ሰሜን አሜሪካ በከተሙትም አባቶች ዘንድ ሳይቀር የሚታመን ነው፡፡ የሰጡት አስተያትም ሚዛን ደፍቶ በውጭ ባሉት አባቶች ጥርስ ውስጥ እንዲገቡ ያደረጋቸውም ይኸው በእነርሱ ዙሪያ የተኮለኮሉት ሰባክያኑም፣ ቀዳስያኑም፣ ሁሉም “እንደርሱ ያለ ሊቅ ሰባኪና ቅኔ አዋቂ የለም፤ አልነበረምም፤ ለወደፊትም አይኖርምም” ማለት እስኪቀራቸው ድረስ የሚያሞካሿቸው ስለነበሩና፤ በአፍ በመጽሐፍ ያለውን እውነታ ከታሪክ ጋር አጣቅሰው፣ በውጭው ዓለም ያለውን ኦርቶዶክሳዊ ሁሉ አቅፈን እንይዝበታለን ብለው በውጭ ያሉት ስደተኛ አባቶች የጣሉትን “በስደት ያለው ሕጋዊ ሲኖዶስ” የሚለውን ዳስ የቆመበት ምሰሶ መሠረት የሌለው፣ በስልጣን ጥማት፣ በወንዝ በጎጥ የተመሠረተ መሆኑን፣ በፓትርያርክ ላይ ፓትርያርክ በመሾም የቀኖና ጥሰት ተፈጸመ እየተባለ እንደ ሞኝ ለቅሶ ተመላልሶ የሚነገረውም ማደናገሪያ እንጂ እውነታው ምን እንደሆነ፤ ተዋናዮቹ ራሳቸው የተወኑትን ተውኔት ከመድረኩ ርቀው ሲሄዱ ትዕይንቱን ላላየው ሰው በተውኔቱ ውስጥ እንዳልነበሩ አድርገው ያቀረቡት አስቂኝ ድራማ እንደሆነ ፍንትው አድርገው በመግለጻቸው ይመስለኛል፡፡
    “በፓትርያርክ ላይ ፓትርያርክ ተሾመ” የሚለው የሰሜን አሜሪካዎቹ አባቶች ጩኸት ትክክለኛ እንዳልሆነ፣ ፓትርያርክ አቡነ ጳውሎስ ቀኖና ጥሰው፣ መፈንቅለ ፓትርያርክ አድርገው በመንበሩ ላይ እንዳልተሰየሙ፣ ሲመታቸው (ሹመታቸው) በቀኖና ቤተ ክርስቲያን መሠረት የተፈጸመ፣ ከሲመቱ ማግስት ሀገር ጥለው በመውጣት “በአዲስ ስልት ድንገት ያጣነውን ስልጣን መልሰን በእጃችን ማስገባት አለብን” በማለት በሰሜን አሜሪካ የከተሙትን  ጨምሮ ሁሉም “ይደልዎ” (ይገባዋል) ብሎ የተቀበለው መሆኑን ብዙዎች የመሠከሩት ሆኖ ሳለ የመጋቤ ብሉይን ምሥክርነት እነዚህ ወገኖች ልዩና አዲስ ምስጢር ያወጣ ያክል አምርረው ሊይዙበት የቻሉበት ምክንያት ምንድር ነው? የሚለው የብዙዎች ጥያቄ እንደሚሆን እገምታለሁ፡፡
    እንደኔ አመለካከት የመጋቤ ብሉይ መድፍ የጠላትን ወረዳ አሸብሮታል ባይ ነኝ፡፡ በዚያ ወገን ከተሰለፉት ብዙዎች  መጋቤ ብሉይ ሰይፈ ሥላሴን አርዓያ የደርጋሉ መባሉን ልብ በሉ፡፡ በአቡነ መልከ ጸዴቅ (አባ ሀብተ ማርያም) ዘንድ አሁን ያሉት የሲኖዶስ አባላት ሲናገሩ እንደተሰሙት “ሁሉ ደናቁርት ናቸው፣ መጋቤ ብሉይ ሰይፈ ሥላሴ ግን ሊቅ” ናቸው፡፡ ስለዚህ ሊቅነታቸውን በተቀበሉትና በመሠከሩላቸው ሰው አንደበት “አቡሀ ለሀሰት” መሆናቸውና ዉጉዛን መባላቸውን ከመስማት የበለጠ ቅስም የሚሰብር፣ ተስፋ የሚያስቆርጥና የሚያንገበግብ ነገር ያለ ይመስላችሁዋል? እኔ አይመስለኝም፡፡
    በእኔ ዕይታ በእርቁ ላይ መጋቤ ብሉይ ሰይፈ ሥላሴ እንዲገኙ የአሜሪካው ወገን ያልፈለገበት ምክንያት ይህ ጥላቻ ያመጣውና የፈጠረው ፍርሃትም ይመስላል። በውይይቱ ላይ የ“ቀኖና ተጣሰ” ጉዳይ የአሜሪካው ወገን መጫወቻ ካርታ ስለሆነ ይህን በዜሮ የሚያባዛና ከጨዋታ ውጭ የሚያደርግን ሰው ማግለል ካልተቻለ ትርፉ ኪሳራ መሆኑን በአግባቡ የተረዱት ይመስላል። እንዲህ ካልሆነማ በየትኛው የድርድር መርሕና ደንብ ነው ተደራዳሪ ወገን የሚደራደረውን ወገን የሚመርጠው? ሁሉም በየፊናው ውጤት ያመጣልኛል፣ እውነታውን ያስረዳልኛል ብሎ የሚያምነውን በራሱ ይመድባል እንጂ “እገሌን ለድርድር እንዳትመድብ” እያለ በአንጻር ላለው ተደራዳሪ አስተያየት መስጠት አይችልም።
    መጋቤ ብሉይ ሰይፈ ከተደራዳሪነት እንዲወጡ/እንዲቀሩ የቀረበባቸው ምክንያት ግራ የሚያጋባ ነው። ቃለ ምልልሱን እንዳደመጥነው መጋቤ ብሉይ የሦስተኛውና የአራተኛው ፓትርያርኮች ፓትርያርክነት በቤተ ክርስቲያኒቱ ተቀባይነት የለውም የሚል ቃል አልሰነዘሩም። ዳሩ ግን  በግብጽ ቤተ ክርስቲያን ዘንድ ግን ተቀባይነት እንደሌላቸው ገልጸዋል። ይኼ ደግሞ በብዙዋቻችን ዘንድ የሚታወቅና የማይካድ ነው። የግብጽ ቤተ ክርስቲያን መሪዎችንም ጠይቆ መረዳት፣ እርሳቸው እንደጠቀሱትም መዛግብትን ማገላበጥም ይቻላል፡፡ይህኮ ከልሒቅ እስከ ደቂቅ በቤተ ክርስቲያኒቱ አገልጋዮች ዘንድ የሚታወቅ እውነታ ነው፡፡ የግብጽ ቤተ ክርስቲያን  ተቀብላቸዋለች የሚሉ ከሆነ መከራከሪያቸውና ማስረጃቸውን ማቅረብ ነው። ከዚያ አልፎ ግን ቲፎዞን ለማሰባሰብ ታስቦና በሌላው ወገን ያለውንም ለመሳብና አጋር ለማድረግ ያልተባለን እንደተባለ አድርጎ የሦስተኛውንና የአራተኛውን ፓትርያርኮች ሕጋዊነት እንደሰረዘ አድርጎ ማቅረብ፤ በዚህ የተነሳም “የሁለት አሥርት ዓመታትን ታሪክ ሰርዟል፤ በእነዚህ ዓመታት የተደረጉ የቤተ ክርስቲያን ምሥጢራት ሁሉ እንዳልተፈጸሙ ተቆጥረዋል” ማለት ከሰማነው የመጋቤ ብሉይ ሠይፈ መግለጫ አንጻር ማሩን አምርሮ ወተቱን አጥቁሮ መናገር ነው፡፡
    የግብጽ ቤተ ክርስቲያን አልተቀበለችም ማለት የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን አልተቀበለችም ማለት ነው የሚል ድምዳሜ ላይ እስካልተደረሰ ድረስና የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ሉዓላዊነት እስከታመነ ድረስ የመጋቤ ብሉይ አስተያየት በእኔ በኩል የአምስተኛውን ፓትርያርክ ሕጋዊነት በሁሉም ወገኖች ዘንድ ተቀባይነት ያገኘ ቀኖናን ያልጣሰ መሆኑን ለማስጨበጥና ለማረጋገጥ የተናገሩት መሆኑን ነው፡፡ ስለሆነም የአሜሪካው ወገን ራሱ ለራሱ በሚመስለው መንገድ በተረጎመው ለሰላም ድርድሩ እንቅፋት ሆኗል ነው የምለው፡፡
    ቅዱስ ሲኖዶስ የወከላቸው አራቱም የሰላም ልዑካን እዚህ ያሉትን ያወገዙ ወይም በውግዘቱ መሠረት ከእነርሱ ጋር ሕብረት የሌላቸው ናቸው፡፡ ሁሉም በቃልም ሆነ በተግባር የእነርሱን ሕገ ወጥነት በአንድም በሌላ ያንጸባረቀ ነው። እውነታው ይህ ሆኖ ሳለ ከሁሉም ለይቶ አንዱን ጠላት አድርጎ መፈረጅና ከድርድር ውጭ እንዲሆን መጠየቅ ምክንያታዊ ነው ትላላችሁ? አይመስለኝም።
    ቸር ወሬ ያሰማን፣
    አሜን



    የጀርመን ድምጽ ሬዲዮ ዘገባ ስለ አባቶች የሰላም ድርድር

    Friday, August 13th, 2010
    width="320" height="266" bgcolor="#FFFFFF"
    flashvars="flvurl=http%3A%2F%2Fv10.nonxt6.googlevideo.com%2Fvideoplayback%3Fid%3D7e67cc229bf224e1%26itag%3D5%26app%3Dblogger%26ip%3D0.0.0.0%26ipbits%3D0%26expire%3D1283887338%26sparams%3Did%252Citag%252Cip%252Cipbits%252Cexpire%26signature%3D4CBE81F7885CD90A7BBC1918DA5CDB04E2BEEF3B.28D3B064CE55D0C2E639B6BA6E86C25752BC6A9D%26key%3Dck1&iurl=http%3A%2F%2Fvideo.google.com%2FThumbnailServer2%3Fapp%3Dblogger%26contentid%3D7e67cc229bf224e1%26offsetms%3D5000%26itag%3Dw160%26sigh%3DPUNgHPGza_KmnQNIzJOYC-GQ5RU&autoplay=0&ps=blogger"
    allowFullScreen="true" />



    የመጋቤ ብሉይ ሰይፈ ሥላሴ ቃለ ምልልስ “ስለ ፓትርያርክ ከሥልጣን መውረድ እና መሻር”

    Thursday, August 12th, 2010

    ለአባቶች ድርድር መሰናከል ምክንያት ሆኗል የተባለው የመጋቤ ብሉይ ሰይፈ ሥላሴ ቃለ ምልልስ “ስለ ፓትርያርክ ከሥልጣን መውረድ እና መሻር”

    M.B Seife Silassie Yohannes about Patriarch Change in Ethiopian Orthodox Church from Deje Selam on Vimeo.



    የመጋቤ ብሉይ ሰይፈ ሥላሴ ዮሐንስ የቀብር ሥነ ሥርዐት ሪፖርታዥ

    Tuesday, August 10th, 2010

    • . ‹‹ማወቅ ትርጉም ያገኘው በመጋቤ ብሉይ ሰይፈ ሥላሴ ነው፤ ከካባቸው በላይ ሊቅነታቸው ጎልቶ ይታይ ነበር፤ ሊቅነት ብቻ ሳይኾን ይህ ጎደለህ የማይባል መልካም ጠባይዕ ነበራቸው፤ ለእርሳቸው እንዲህ ያለ አቋራጭ ጊዜ ይመጣል ብለን አልጠበቅንም፤ ሰላምን ለማምጣት በመፋጠን ላይ እንዳሉ ከረጅም መንገድ መጥተው ወደ ረጅም መንገድ ሄዱ – የሰላም መልእክተኛ ኾነው ሁሉንም በፍቅር እና በትዕግሥት እያዩ ነው የሄዱት፤ ይኼ ራሱ ትልቅ ምስክርነት ነው እኮ!!›› (ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ)    
    • . ‹‹በቅንነት እና በታማኝነት ያገለገሏት ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችንም ከፍተኛ ጉዳት ደርሶባታል፡፡›› (የኀዘን መግለጫው)

    (ደጀ ሰላም፤ ኦገስት 10/2010፤ ነሐሴ 4/2002 ዓ.ም) ነሐሴ አንድ ቀን 2002 ዓ.ም ጠዋት በድንገተኛ ሕመም በተወለዱ በስድሳ ሰባት ዓመታቸው ያረፉት እና በመ/ፓ/ጠቅ/ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት የሊቃውንት ጉባኤ መምሪያ ሐላፊ የኾኑት የመጋቤ ብሉይ ሰይፈ ሥላሴ ዮሐንስ የቀብር ሥነ ሥርዐት በትናንትናው ዕለት ከጠዋቱ 3፡00 – 9፡00 ሰዓት በመንበረ ጸባኦት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል በተካሄደ የጸሎተ ፍትሐት እና ጸሎተ ቅዳሴ ሥነ ሥርዐት ተፈጸመ፡፡

    ከዚህ ቀደም ብሎ አስከሬኑ ከነበረበት ሆስፒታል መኖርያቸው ወደ ኾነው እና ሲያገለግሉበት ወደ ነበረው የቀጨኔ ደብረ ሰላም መድኃኔ ዓለም ቤተ ክርስቲያን ተወስዶ ጸሎተ ፍትሐት እና ሙሉ አደራረስ ሲደረግ አድሯል፤ በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ መመሪያ ሰጭነት በሌሎች የአዲስ አበባ ገዳማት እና አድባራትም ጸሎተ ፍትሐት ተደርጓል፡፡

    - ‹‹ጋሻ መመኪያዬ ሰይፈ ሆይ የእኔ አባት፣
    ድንገተኛው ሞትህ ፈጀኝ እንደ እሳት፤
    ላፍታ ተነሣና ምስጢሩን ተናገር፣
    አይቃጠል ወገን አንጀቱም አይረር፤
    …..
    ድንቁርና ንገሥ ዛሬ ተሳካልህ፣
    የዕውቀት ሁሉ ቁንጮ ሰይፈ ታሰረልህ፤››(ባለቅኔው)

    -‹‹ለሰይፈ ሥላሴ ዮሐንስ
          እንተ ልማዱ ትሕትና
          ለቤተ ክህነት ዓይና፣
    ለገብረ ሥላሴ ዐወቀ
          እንተ ንብረቱ ጽሙና
          ለባሕረ ምስጢር ወሰና፣
    እስኪ ንገሪኝ እማማ
    ትወልጅዋለሽ እንደገና
    ያን የቅኔ ጎዳና
    ያን የትርጓሜ ሳተና
    ያነን የምስጢር ድንቅ ጀግና
    ታገኝዋለሽ እንደገና?
    እስኪ በይ ይኹና!!››(ባለቅኔው)

    ሰኞ ነሐሴ ሦስት ቀን ከጠዋቱ ሦስት ሰዓት ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያሪኩ፣ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፣ የመ/ፓ/ጠ/ቤ/ክ የየመምሪያ ሐላፊዎች እና ሠራተኞች፣ ቤተሰብ፣ ወዳጅ ዘመድ እና በርካታ ምእመናን በተገኙበት ወደ መንበረ ጸባኦት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ተወስዶ ጸሎተ ፍትሐት ሲደረግ አርፍዷል፡፡ ከቀኑ አምስት ሰዓት በኋላ ባለቦታዎቹን የቀጨኔ ደብረ ሰላም መድኃኔ ዓለም ቤተ ክርስቲያን ካህናት ጨምሮ ከተለያዩ የአዲስ አበባ ገዳማት እና አድባራት በመጡ ሊቃውንት፡-      
    ‹‹በአምሳለ ወፍ ርግበ ጸዐዳ ትመስል
        ይእቲኬ ማርያም፣ ማርያም ይእቲ›› የሚለው የአርያም ድርሰት ተወርቧል፡፡ ወረቡ እንደ ተጠናቀቀ በመምህር ቀጸላ፣ በመምህር ዘአማን፣ በመምህር ዲበኵሉ፣ በሊቀ ኅሩያን በላይ መኰነን እና በመጋቤ ምስጢር ወልደ ሩፋኤል ፈታሒ የተዘጋጁ ሙሉ አርያም እና ሥላሴ ቅኔያት ቀርበዋል፡፡ ቅኔያቸውን ለማበርከት ጓጉተው በዙርያው ከነበሩት በርካታ ሊቃውንት መካከል በሰዓት መጣበብ ምክንያት ተመርጠው የተሰሙት የመምህራኑ ቅኔዎች ብዙዎቹ ለ75 ዓመታት አራቱን ጉባኤት እና ቅኔ ከነአገባቡ ሲያስተምሩ ኖረው ግንቦት 22 ቀን 2002 ዓ.ም በ102 ዓመታቸው ካረፉት መልአከ ገነት ገብረ ሥላሴ ዐወቀ ጋራ የተሰናሰሉ እና የመጋቤ ብሉይ ሰይፈ ሥላሴን የቅኔ፣ የትርጓሜ፣ የጽሕፈት እና የስብከት ዐዋቂነት፣ የሥራ ትጋት፣ ትሑት ሰብእና እና የመግባባት ችሎታ የሚመሰክሩ ናቸው፤ አንዳንዶቹም፣ የሞተ ዕረፍታቸው ድንገተኛነት ያጫረባቸውን ቁጭት እና ጥርጣሬ የሚገልጡ ነበሩ፡፡ በተለይም ለመጋቤ ብሉይ የረጅም ጊዜ የሥራ ባልደረባቸው የኾኑት የዜና ቤተ ክርስቲያን ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ መጋቤ ምሥጢር ወልደ ሩፋኤል ፈታሒ ከቅኔያቸው በፊት እምባ ቀድሟቸው ‹‹እንግዲህ መስቀልን ማን ይጽፈዋል? ጥምቀትን ማን ይጽፈዋል?. . .›› በማለት መንሥኤው በውል ያልታወቀው የሊቁ በድንገት መለየት ያሳደረባቸውን ልባዊ ኀዘን በቅኔያቸው ገልጸዋል፡፡ በግእዝ እና አማርኛ የተነገሩትን ቅኔያት ምስጢር በመረዳት፣ ‹‹እውነት ነው!›› እያሉ ሳግ እየተናነቃቸው አሰምተው የሚያልቅሱ፣ እጃቸውን በቁጭት የሚጸፉ የሊቁ ወዳጆች በዐውደ ምሕረቱ ዙሪያ ተስተውለዋል፡፡

    መጀመርያ ታመም ዘመድ ይጠይቅህ
    ምንህን እንዳመምህ ይወቀው ወገንህ
    በምን ተቀየምህን ምንስ አስቀየምንህ
    ሹልክ ብለህ ወጥተህ ወገንህን ትተህ
    ከቶ ላትመለስ በመቅረትህ ወሰንህ፤
    ምንድነው ነገሩ እንዲህ ያስጨቀነህ
    ምንድነው ምስጢሩ እንደዚህ ያስከፋህ
    ሰይፈ ሆይ ተናገር ወገንህ ይካስህ
    እንደወጣህ አትቅር ዐይን ዐይን ስናይህ፤
    ድንቁርና ንገሥ ዛሬ ተሳካልህ፣
    የዕውቀት ሁሉ ቁንጮ ሰይፈ ታሰረልህ፡፡

    ከዚህ በመቀጠል የሊቁ ዜና ሕይወት እና ሥራዎች በትንሣኤ ማሳተሚያ ድርጅት ዋና ሥራ አስኪያጅ ሊቀ ካህናት ብርሃኑ ገብረ አማኑኤል አማካይነት በንባብ ተሰምቷል፡፡ በሕይወት ታሪካቸው ሊቁ ከልደት እስከ ዕረፍት የነበራቸው የትምህርት አድማስ፣ የአገልግሎት ትጋት፣ የሥራ ፍሬ፣ ቤተሰባዊ ሕይወት እና መገለጫ ጠባዕያት በስፋት ተዘርዝረዋል፡፡ የድንገተኛ ዕረፍታቸው መንሥኤ ስለሆነው ሕመማቸው ምንም ያልተባለበት ይህው የሕይወት ታሪክ፣ ‹‹በክቡር መጋቤ ብሉይ ሰይፈ ሥላሴ ዮሐንስ ዕረፍት መሪር ኀዘን የደረሰባቸው ቤተ ሰቦቻቸው እና ወዳጅ ዘመዶቻቸው ብቻ ሳይኾኑ በቅንነት እና በታማኝነት ያገለገሏት ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችንም ከፍተኛ ጉዳት ደርሶባታል፤›› ብሏል፡፡

    ከጸሎተ ቅዳሴው በፊት የመጨረሻ መርሐ ግብር የነበረው የብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያሪኩ ቃለ ምዕዳን ነበር፡፡ ‹‹መጋቤ ብሉይ ሰይፈ ሥላሴ ሁሉንም በአክብሮት የሚቀበሉ፣ ይህ ቀረህ የማይባሉ መልካም ጠባይ የነበራቸው ሊቅ እና ወንድም ነበሩ፡፡ ብዙ ምሁራን እንዳሉ ይነገረናል፤ እናያለን፤ የእርሳቸው ግን የተለየ ነበር፤ በካባ እና ባማረ ልብስ የተደበቀ አልነበረም፤ ከካባቸው በላይ ሊቅነታቸው ጎልቶ ይታያል፤ ለሚጠየቁት ሁሉ ‹እሺ፣ ይኹን› ባይ ነበሩ፤ ፍጥነት፣ ጥራት እና ታማኝነት የሚያስፈልገው ተግባር ለመጋቤ ብሉይ ነበር የሚሰጠው፤›› ያሉት አቡነ ጳውሎስ የሊቁ መዋዕለ ዘመን እንዲህ ባጭሩ ይቋረጣል ብሎ የሚያስብ እንዳልነበር በመጥቀስ የመለየታቸውን አስደንጋጭነት አመልክተዋል፡፡ አያይዘውም፣ ‹‹እንደ ባሕር ጥልቅነት ያለው መልካም ጠባይ ያላቸው እና ደከመኝ ማለትን የማያውቁ ነበሩ፤ ይህው አሁን እንኳ ሰላምን ለማምጣት በመፋጠን ላይ እንዳሉ ነው ከረጅም መንገድ መጥተው ወደ ረጅም መንገድ የሄዱት – የሰላም መልእክተኛ ኾነው፣ በአውሮፕላን ማረፊያ ጎንበስ ቀና ብለው አብረዋቸው የነበሩትን እየረዱ፣ ሁሉንም በፍቅር እና በትዕግሥት እያዩ ነው የሄዱት፤ ይኼ ራሱ ትልቅ ምስክርነት ነው እኮ!!›› በማለት አንክሯቸውን ገልጸዋል፡፡

    በቃለ ምዕዳናቸው መጨረሻ፣ ‹‹ማወቅ ትርጉም ያገኘው በመጋቤ ብሉይ ነው፤ በሰው መተካት ለእግዚአብሔር ልማዱ ስለሆነ ለዚህ ጸሎት ያስፈልገናል፤ ከዚህ በቀር ወደኋላ መመለስ አንችልም፤ እግዚአብሔር ነፍሳቸውን ከማኅበረ መላእክት፣ ከማኅበረ ቅዱሳን ይጨምርልን፡፡›› በማለት ካሳረጉ በኋላ ሥርዐተ ቅዳሴውን መርተው ከድርገት በኋላ፣ ከሠርሆተ ሕዝብ በፊት አስከሬኑን በተዘጋጀለት መካን(ፉካ) በማሳረፍ የቀብር ሥነ ሥርዐቱ እንዲፈጸም አድርገዋል፡፡ ሥርዐተ ቀብሩ በተጣደፈ አኳኋን እንደተፈጸመ የሚገልጹ የአንዳንድ የቤተሰብ አባላት እና ሌሎች ኀዘንተኞች ቅሬታ የተሰማ ሲኾን ከቅዳሴው በፊት የተከናወነው ሥነ ሥርዐት ከቅዳሴ በኋላ እንደሚኾን ጠብቀው ለመጡት ኀዘንተኞችም ኹኔታው ግርታን ፈጥሯል፡፡ ጥድፊያው ምናልባትም ፓትርያሪኩ  ለሱባኤው እና ለጤንነታቸው ወቅታዊ ተስማሚነት ወዳለው ወደ ድሬዳዋ ዕለቱኑ ያደርጉታል ተብሎ ከሚታሰበው የመልስ ጉዞ ጋራ ሳይያዝ እንደማይቀር አንዳንድ ተመልካቾች ግምት ወስደዋል፤ ሌሎችም ከቅዳሴው በፊት የተከናወነው መርሐ ግብር በቂ እንደ ኾነና ግብአተ መሬቱ ከድርገት በኋላ መፈጸሙ ሥርዐታዊ መኾኑን በአዎንታ በመጥቀስ ቅሬታውን ያጣጥሉታል፡፡
    ከዚህ በመቀጠል ለሊቁ መጋቤ ብሉይ ሰይፈ ሥላሴ ዮሐንስ ዕረፍት ከተበረከቱ ቅኔዎች መካከል የቀረቡትን እና በአማርኛም በግእዝም ከተነገሩት አንዳንዶቹን ለዝክረ ነገር መርጠን አቅርበንላችኋል፡፡

    ሀ) ‹‹ሕያው ልሳን›› የተባለው የግእዝ-አማርኛ መዝገበ ቃላት አዘጋጅ ሊቀ ኅሩያን በላይ መኰንን ያቀረቡት፤

                      ጉባኤ ቃና     
    ፩.እፎኑመ ሞት ለሰይፈ ሥላሴ ዘፈርሆ

    እስመ በፍኖት ተኃብዐ ከመ ይማኦ ጸኒሖ፡፡

    ፪.መኰንነ አቤል ቃየን ለሰይፈ ሥላሴ ተወክፎ

    እምዕራፈ መቅሰፍት አየር ጽጌ ሞተ ግብት ሐቂፎ፡፡

                     
    ሥላሴ ቅኔ

    በገባዖን መቃብር
    እመ ተዐየኑ ሠራዊት፣
    ንግሥተ ሃይማኖት አዜብ
    አሐቲ በዘታጸንዕ ሥርዐተ፣
    ፈነወቶ ለገብረ ሥላሴ ዘሰይፈ ቀነተ፡፡
    ወቤተ ትርጓሜ ተኀሥሥ እም ልባ
    ዘይመርሐ ፍኖተ፤
    እስመ ክልኤሙ አዕይንተ፣
    ፍጡነ ኀጥአት አሐተ ዓመተ
    ወትበኪ ኵለሄ ዕለተ፡፡
    ኦ ሰይፈ ሥላሴ የቅኔው ገበሬ
    የወልደ ማርቆስ የአክሊሉ ፍሬ
    በቅድስት ሥላሴ መካነ ኁባሬ
    መወድስ ሲዘርፉ ሊቃውንተ ኀሬ
    ፍታሕ ሊተ አትልም ምኑ ነካህ ዛሬ፡፡
    ወጋ ወጉ እንዳይቀር እያልን ዲማ ሞጣ
    መወድስ ልንቀኝ ስንዘርፍ አገኝ አጣ
    ቅኔ ብናበላሽ የምስጢሩን ጣጣ
    አደራህ ሰይፍዬ በእኛ እንዳትቆጣ፡፡
    ነገሩስ ሰይፍዬ!
    ከወልደ ማርቆስ በመንፈስ ተወልደህ
    የደንቢያው አክሊሉ ኮትኩቶ አሳድጎህ
    ከገብረ ሥላሴ ከማዕዱ በልተህ
    እኛም እናውቃለን
    ትዕቢትና ቁጣ አይደለም ገንዘብህ፡፡
    ኦ መጋቤ ብሉይ ዘልብከ ብሩህ
    ወከመ ስምከ ልሳንከ በሊህ
    በዚያ በጣፋጩ ለስላሳ አንደበትህ
    በደስታው ባዘኑ
    መወድስ ስትዘርፍ ቀስ ረጋ ብለህ
    ታሪክ ስትነግረን በዘጋቢ ፊልምህ
    ይበል! መልካም ብለን አጨበጨብንልህ
    የዛሬ ሁለት ወር ይዘህ በትረ ሙሴ
    ለመልአከ ገነት ለገብረ ሥላሴ
    ተቀኝተህ ነበር መውድስ ሥላሴ፡፡
    ዛሬ ድንገት ስትበር ልብህ ሀገር ናፍቆ
    ነጣቂ ተኩላ ሞት መንገድ ላይ ሸምቆ
    የምሥጢሩን ለዛ አንደበትህን አንቆ
    ከመንጋው ለይቶ አልጋ ላይ ቢያውልህ
    በመጽሐፈ ግንዘት ስንፈታህ ላንፈታህ
    ቅኔ ምትዘርፍበት አንተ አንደበት ካጣህ
    እባክህ ንገረን ምን እንቀኝልህ?
    እየሰማሽ ነው እማማ!
    ድንቅ ቅኔያቸው ሲፈታ
    የዲማው ቅኔ ዘራፊ
            ሰይፈ ሥላሴ ቱማታ
    መልአከ ገነት ገብረ ሥላሴ
            የኒያ የሞጣው ዬኔታ
    የቅዱስ ጳውሎስ ኮሌጅ
            ሰዋስወ ብርሃን ማኅቶታ
    የብሉይ ኪዳን ምሰሶ
            የሐዲስ ኪዳን ዋልታ
    እስኪ ንገሪኝ አንድ አፍታ
    ጎዳና ቅኔው ሲፈታ፡፡
    ብሥራተ አብ ረድእ ትሩፍ
    ብሎ ጀምሮ ሐዲስ ምዕራፍ
    በእእምሮው ወንጌል ሲጽፍ
    በትርጓሜው ሲረቅ ሲገዝፍ
    በቅኔ ምሥጢር ሲፈላሰፍ
    እንደ ስሙ ነበረ ሰይፍ፡፡
    በቀዳሚ ገብረ ብሎ
    ብሉያትን አደላድሎ
    እምከርሰ እሙ አእሚሮ
    እንዘ ይተግህ ለምህሮ
    ቃል ሥጋ ኮነን ፈክሮ
    በአንድምታ ተርትሮ
    ሐዲሳትን አመሳክሮ
    በራእየ ዮሐንስ ዘለቀ
    ገብረ ሥላሴ ዐወቀ፡፡
    ለሰይፈ ሥላሴ ዮሐንስ
    እንተ ልማዱ ትሕትና
    ለቤተ ክህነት ዓይና፣
    ለገብረ ሥላሴ ዐወቀ
     እንተ ንብረቱ ጽሙና
     ለባሕረ ምስጢር ወሰና፣
    እስኪ ንገሪኝ እማማ
    ትወልጅዋለሽ እንደገና
    ያን የቅኔ ጎዳና
    ያን የትርጓሜ ሳተና
    ያነን የምስጢር ድንቅ ጀግና
    ታገኝዋለሽ እንደገና?
    እስኪ በይ ይኹና!!

    የመምህር ዲበኵሉ ግጥም እና ቅኔ

             

    ምንድን ነው ነገሩ?
    የተላኩበትን ወሬ ሳያበሥሩ
    ሪፖርቱ ሳይቀርብ ዜና ሳያወሩ
    እንደወጡ መቅረት ምንድን ነው ነገሩ፤
    የተላኩበትን እግዚአብሔር ይርዳዎት
    በሰላም ይምጡልን ብለን ሸኝተንዎት
    ደኅና ኹኑ ብለው በመሰነባበት
    ምንድን ነው ነገሩ እንደወጡ መቅረት፡፡
    ጋሻ መመኪያዬ ሰይፈ ሆይ የእኔ አባት፣
    ድንገተኛው ሞትህ ፈጀኝ እንደ እሳት፤
    ላፍታ ተነሣና ምስጢሩን ተናገር፣
    አይቃጠል ወገን አንጀቱም አይረር፤
    አፈር አፈር ማለት የሰው ዐይን መጥላቱ
    ታይቶበት አያውቅም ሰይፈ በሕይወቱ
    ታዲያ ወገን መጥላት ከሩቅ መሰወሩ
    ምንድነው ነገሩ፣ ምንድነው ምስጢሩ
    መጀመርያ ታመም ዘመድ ይጠይቅህ
    ምንህን እንዳመምህ ይወቀው ወገንህ
    በምን ተቀየምህን ምንስ አስቀየምንህ
    ሹልክ ብለህ ወጥተህ ወገንህን ትተህ
    ከቶ ላትመለስ በመቅረትህ ወሰንህ፤
    ምንድነው ነገሩ እንዲህ ያስጨቀነህ
    ምንድነው ምስጢሩ እንደዚህ ያስከፋህ
    ሰይፈ ሆይ ተናገር ወገንህ ይካስህ
    እንደወጣህ አትቅር ዐይን ዐይን ስናይህ፤
    ድንቁርና ንገሥ ዛሬ ተሳካልህ፣
    የዕውቀት ሁሉ ቁንጮ ሰይፈ ታሰረልህ፡፡
    ሞት የሚሉት ጠላት ይንሁሉ እያወቀ
    በቅኔው ባለቤት በሰይፈ ላይ ሣቀ
    በብሉያቱ ሊቅ በሰይፈ ላይ ሣቀ፡፡
    ቅኔ ማን ይቀኝህ
    መጽሐፍ ማን ይጻፍህ
    ሰም እና ወርቅህን ማንስ ያራቅልህ
    መጽሐፍ አንድምታን ማን ይተርጉምልህ
    ታላቁ ዐይናማ ሊቅ ሰይፈ ተጋዘልህ፡፡
    ወርቅ እና አልማዝ ዕንቈ ጽጌሬዳ
    እንደ ቀላል ነገር ገባህ ከሞት ጓዳ፤
    ያን ሁሉ ዕውቀትህን ለልጅ ላታወርሰው
    ታላቁ ሊቅ ጀግና መድከምህ ለምነው?
    ቅዱስ አባታችን እግዚአብሔር ያጽናዎት
    ፈጣኑ ልጅዎን ሞት ወሰደብዎት
    የሰይፈማ ነገር አከተመ በቃ
    ሰው ይፈልጉልን ሰይፈን የሚተካ
    ታላቋ እናትዎን ወራሪ እንዳይደፍራት
    ቅዱስ አባታችን ሰው ይፈልጉላት፤
    የዋህ እናትዎ ታሳዝነኛለች
    ታላቁን ልጅ ቀብራ ትንሹን ደገመች፤
    ታላቋ እናትዎን የልጆችን እናት
    ሾተላይ ናት መሰል እስኪ ያስመርምሯት፤
    የመጀመርያው ልጅ ወጣ ወጣ ሲባል
    በአጭር ርቀት እንዲቆም ተገዷል
    ለአካለ መጠን ሳይደርስላት ቀርቷል
    በሞትም ማሰርያ ታስሮ ተለይቷል፤
    ያ ታላቁ ልጇ በሞት ቢለያትም
    በልጅ ልጅ ተክሳ ትኖር ነበር ጎጃም
    በዚያ ሁሉ መከራ ከዐይኗ እምባ ሳይጠራ
    የመጨረሻው ልጅ ሰይፈ ከዐይኗ ጠፋ፤
    የሞት ቀስቶች ሁሉ በእሷ አነጣጠሩ
    በደጋን መሎጊያው ሹሎች ተቀሰሩ፤
    ምንድነው ነገሩ ምንድነው ምሥጢሩ
    በአበባ እየታዩ መቅረት ሳያፈሩ፤
    አለኝታችን ሰይፈ ተጠያቂው አባት
    የትምህርት መሠረት የዕውቀት አብነት
    እግዚአብሔር ነፍስህን በገነት ያኑራት፡፡

    ጉባኤ ቃና

    ፩. ሊቀ ሐዋርያት ጴጥሮስ

       ሞተ ፍጡራን አእላፍ
       ኀበ ውስተ ቤቱ አብዖ
        ለበዓለ ቅኔከ ሰይፈ፡፡
    ፪. ጎጃም ተከዘት ዘኢተከዘት እምጥንታ
       አኮኑ ማሰና ክልኤቲ
       አንቅዕት ብርሃን አዕይንታ
    ፫. ጎጃም ወላድ ለቅኔያት
       ዉሉደ ሰይፈ ክብር ይባቤ
       እጓለማውታ ትኩኑ ኢያኀድገክሙ ትቤ፡፡

                   ሥላሴ

    ሰይፈ ኢትአንሥዑ ዕፄያተ አልዓዛር አልዓዛር
    በከመ አንበብነ ቅድመ ዘሊቃውንተ መጽሐፈ
    እስመ ሰይፍ እለያነሥኡ ይመውቱ ሰይፈ. . .

                  መወድስ

    ቤተ ክርስቲያን ወላድ ወላደ አእምሮ
    ብካያ ትበኪ በለቢሰ ልብስ ጸልይ
    በሞተ ፍጡራን ሞት ሠረገላ ዛቲ ዓለም፤
    ቅኔያት ዉሉደ ሥጋሃ
    እስመ አንቊ ዮም፤
    ወለሞት ሠረገላ ዘያረውፆ
    ጠቢብ ሰይፈ ሥላሴ መስተቀውም
    ድኅረ ወድቀሂ ሞተ ገንጰለ
    ጽድቀ ሐቅለ አቤሮን ሴም
    ሞት ሠረገላ ዘተንሥኣ በሰላም
    ለነሢኣ ብዙኅ ሕዝብ ለሰይፈ ሥላሴ ሥዩም
    ኢያትረፈ ዘርዐ ሰብእ ወኢክፍልተ ዐፅም፡፡
    ሀገረ ቴዎፍሎስ አብ መቃብረ ሥጋ
    ሰይፈ ሥላሴ ነገደ በኀዲገ ብዙኅ ምሕረቱ
    ወቅኔያቲሁ በዛኂት ሕፃናቲሁ እሙንቱ
    እንዘ እንዘኀድግ በበክፍሉ
    ቴውፍሎስ አምጣነ ጸውዖ ይትረከብ በቤቱ
    ወቃለ ቴዎፍሎስ ዘያከብር ሰይፈ ሥላሴ ሰማዕት
    ለቴዎፍሎስ አረፍቱ
    ቴዎፍሎስሂ መሠረትነ
    ወለክብረ ጳውሎስ ጥንቱ
    ለሰይፈ ሥላሴ ከመ ንርአዮ
    ፈንዎ በሕይወቱ
    ድኅረ ነጸርኖሂ ኵልነ
    ወጠየቅናሁ ለዝንቱ
    ይትመየጥ መንገሌከ ወትገብር ዘትፈቱ፡፡



    የሐውልቱ ሥር ቁማርተኞች

    Monday, August 9th, 2010

    (ደጀ ሰላም፤ ኦገስት 8/2010) — የፓትርያርኩና የማፊያው ቡድን “ስውር ፀሐፊ” (Ghost Writer) ዘሪሁን ሙላቱ ስለ ፓትርያርኩ ሐውልትና ተያያዥ ጉዳዮች  ባለ 50 ገጽ መጽሐፍ አወጣ፤ እነ በጋሻው ደሳለኝና ኤልዛቤል የምትባለው ወ/ሮ እጅጋየሁ ተጠቅሰውበታል። ዲያቆን ሲባል ቆይቶ በቅርቡ ሊቀ ትጉሃን የሚል የማዕረግ ስም የደረበው Ghost Writer ዘሪሁን ሙላቱ ጊዜውን በቶሎ በማጥናት እና የፓትርያርኩ ሐውልት ብዙ ተቃውሞ እንደበዛበት ሲመለከት፣ የሐውልቱ ተቃዋሚዎች ያሉትን በመሰብሰብና መጽሐፍ አድርጎ በማሳተም ሲያሳዝነው የሰነበተውን ምእመን አሁን ደግሞ ገንዘቡን ሊበላው ይህንን ፓምፍሌት (መጽሐፍ ለማለት ይከብዳል) አሳትሟል። መታሰቢያነቱንም በቅርቡ ከዚህ ዓለም በሞት ለተለዩት ለብፁዕ አቡነ መልከ ጼዴቅ በማድረግ መጽሐፉ ተቀባይነት እንዲያገኝ ለማድረግ ሞክሯል። ርእሱን ደግሞ በቅርቡ እኛም ካወጣነው (በአዲስ አበባ በጋዜጣ ከወጣ) አንድ ጽሑፍ ላይ የወሰደው ነው።

    በዚህ መጽሐፍ ስማቸው የተጠቀሱት ሰዎች በርግጥም ቤተ ክርስቲያንን በሚጎዳ ሥራ ላይ የተሰማሩ መሆናቸውን በተደጋጋሚ መዘገባችን ይታወቃል። ነገር ግን ሰዎቹ ስሕተተኛ መሆናቸውን መጥቀሳችን አሁን ዘሪሁን የጻፈውን አስነዋሪ ጽሑፍ እንድንቀበለው አያደርገንም። ብዙ ጊዜ እንዳልነው “ለገንዘብ ብሎ ስለ እግዚአብሔር የሚሰብክ፣ ገንዘብ ከተሰጠው ለሰይጣንም መስበኩ የተረጋገጠ ነው። ዘሪሁን በዚህ ጽሑፉ የሚያዋርዳቸው ሰዎች በዓላማም በግብ አንድ የሆኑትን ሰዎች ነው።

    ዘሪሁን “የሚታወቅባቸው ሥራዎቹ” በሙሉ የሰዎችን ስም የሚያንቋሽሹ ሲሆኑ ከነዚህም ውስጥ ሁለቱ ዋነኛ መጽሐፎቹ ለዲ/ን በጋሻው “የመስቀሉ ሥር ቁማርተኞች” መልስ የሰጠበት “የስድብ አፍ” እና ብፁዕ አቡነ ሳሙኤልን “የሚያዋርድ” ስድብ ያሳተመበት መጽሐፉ ናቸው። የመጀመሪያውን መጽሐፉን በጻፈበት ወቅት ቅ/ፓትርያርኩ 60 ሺህ ብር ጥሬ ገንዘብ እንደሰጡት ውስጥ አዋቂዎች ይናገራሉ። መጽሐፉንም እያንዳንዱ ቤተ ክርስቲያን በግድ እየወሰደ እንዲያከፋፍል፣ ካህናቱም በነፍስ ወከፍ እያንዳንዳቸው አምስት አምስት እንዲወስዱና እንዲሸጡ፣ ገንዘቡ ግን ከደሞዛቸው በግድ እንዲቆረጥ ተደርጎ ነበር።  ይህ ግለሰብ ባለፈው ሐምሌ በተደረገው ሽልማት ላይ ስለዚሁ ስውር ሥራው (ከነ ዲ/ን በጋሻው ጋር) ከቅዱስ ፓትርያርኩ እጅ በአደባባይ ሽልማት ተበርክቶት ነበር።

    የመጽሐፉ ርዕስ፦ የሐውልቱ ሥር ቁማርተኞች፣
    ዋጋው፦ 15 ብር
    የገጽ ብዛት፦ 50 ብቻ
    ደራሲ፦ ፈታሒ በጽድቅ (የብዕር ስም)፣
    መታሰቢያነቱ፦ ለአቡነ መልከ ጼዴቅ
    ማተሚያ ቤት፦ አልተጠቀሰም፣
    ምእመናን እንዲህ ዓይነቱን ርካሽ መጽሐፍ እየገዙ አጽራረ ቤተ ክርስቲያንን በተዘዋዋሪ እንዳይጠቅሙ እናስታውሳለን።

    የመጋቤ ብሉይ ሰይፈ ሥላሴ ዮሐንስ የቀብር ሥነ ሥርዐት ሰኞ ይፈጸማል

    Sunday, August 8th, 2010

    (ደጀ ሰላም፤ ኦገስት 8/2010) — በትላንት ዕለት በድንገተኛ ሕመም ሕይወታቸው ያለፈው የመጋቤ ብሉይ ሰይፈ ሥላሴ ዮሐንስ የቀብር ሥነ ሥርዐት ነገ ሰኞ፣ ነሐሴ ሦስት ቀን 2002 ዓ.ም በስምንት ሰዓት በመንበረ ጸባኦት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ይፈጸማል፡፡

    በትላንትናው ዕለት ረፋድ ላይ ለእርቅ እና ድርድር ጉባኤ የሄዱበትን የአሜሪካ ተልእኮ አጠናቀው አዲስ አበባ ቦሌ ዓለም ዓቀፍ አየር ማረፊያ እንደ ደረሱ ራሳቸውን የማቃጠል እና ልባቸውን የመውጋት ስሜት እንደተሰማቸው አብረዋቸው ለተጓዙት የልኡካን ቡድኑ አባላት የተናገሩት መጋቤ ብሉይ ሰይፈ፣ አስቸኳይ ሕክምና ሊያገኙ ይችሉ ከነበረበት ስፍራ ርቆ እና ከጊዜው ዘግይቶ አራት ኪሎ አካባቢ ቀድሞ ‹‹ጉድሸፐርድ›› አሁን ‹‹አዲስ የሕፃናት እና እናቶች ሆስፒታል›› በሚባለው የሕክምና ተቋም ውስጥ የመጀመርያ ደረጃ ምርመራ እየተደረገላቸው ሳለ ነበር ሕይወታቸው ያለፈው፡፡ ወዲያኑ አስከሬናቸው በቅዱስ ገብርኤል እና በዳግማዊ ምኒልክ ሆስፒታሎች ከፍተኛ ምርመራ ከተካሄደለት በኋላ ዛሬ ቀትር ላይ ሰበካቸው በሚገኝበት እና በአገልግሎት ብዙ በደከሙበት በቀጨኔ ደብረ ሰላም መድኃኔዓለም ቤተ ክርስቲያን እንዲያርፍ ተደርጓል፡፡

    የመጋቤ ብሉይ ሰይፈን ድንገተኛ ሞት በመስማት ለሱባኤው እና ለግል ጤንነታቸው ካለው ወቅታዊ ተስማሚነት ጋራ በተያያዘ ከሄዱበት ድሬዳዋ በትላንትናው ዕለት የተመለሱት ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ፣ ማምሻውን በመጋቤ ብሉይ መኖርያ ቤት ተገኝተው ቤተሰቡን በአባታዊ ቃል አጽናንተዋል፡፡ ከዚሁ ጋራ በተያያዘ ከቤተሰቡ አባላት ጋራ በተደረገ ምክክር የቀብር ሥነ ሥርዐቱ በቀጨኔ ደብረ ሰላም መድኃኔዓለም ቤተ ክርስቲያን እንዲፈጸም ፍላጎቱ የነበረ ቢኾንም ከብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያሪኩ ቀርቧል በተባለው ሐሳብ በመንበረ ጸባኦት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል እንዲፈጸም ተወስኗል፡፡

    ዛሬ ከቀትር በኋላ አስከሬኑ ባረፈበት በቀጨኔ ደብረ ሰላም መድኃኔዓለም ቤተ ክርስቲያን ሙሉ ጸሎተ ፍትሐት የተደረሰ ሲኾን በነገው ዕለት ጠዋት ሦስት ሰዓት ላይ ወደ መንበረ ጸባኦት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ተጓጉዞ በዚያም ጸሎተ ፍትሐት እና ጸሎተ ቅዳሴ ከተደረሰ በኋላ ከስምንት ሰዓት ጀምሮ የቀብር ሥነ ሥርዐቱ እንደሚከናወን ተገልጧል፡፡

    በተያያዘ ዜና መጋቤ ብሉይ ሰይፈ በእርቅ እና ድርድር ጉባኤው ላይ በሚሳተፈው የልኡካን ቡድን ውስጥ እንዳይካተቱ እና በቅድመ ጉባኤ ውይይቱ ወቅትም ከድርድሩ እንዲወጡ በስደት የሚገኘው ወገን ጫና ከመፍጠሩ አስቀድሞ የልኡካን ቡድኑ አባል ኾነው ለመሄድ ፍላጎቱ እንዳልነበራቸው ለቤተሰቦቻቸው እና ለፓትርያሪኩ ተናግረው እንደ ነበር ተሰምቷል፡፡ የልኡካን ቡድኑ ከአገር ቤት ከመነሣቱ አስቀድሞ የስደተኛው ወገን ዒላማ መኾናቸውን ያልወደዱት መጋቤ ብሉይ፣ ‹‹እኔ ባልሄድ፣ ቢቀርብኝ፤ ሌላ ሰው ይተካ›› በማለት በተደጋጋሚ ቢያሳስቡም በአቡነ ጳውሎስ ጫና ለመሄድ እንደ ተገደዱ ለመረዳት ተችሏል፡፡

    በድርድሩ ስፍራም በተለይ በስደት ከሚገኙት ተወያዮች አንዱ ከኾኑት አቡነ መልከ ጼዴቅ ጋራ ከፍተኛ አተካራ ውስጥ መግባታቸው ተገልጧል፡፡ ኹኔታው በመጋቤ ብሉይ ልቡና ላይ ከፍተኛ ኀዘኔታ እና ጭንቀት እንደ ፈጠረ ወደ ሀገር ቤት መመለሳቸውን ነው የጉዳዩ ታዛቢዎች የሚገልጹት፡፡ እኒሁ ታዛቢዎች አክለውም በርግጥም ውይይቱ እንዲሳካ ልባዊ ፍላጎቱ ከነበረ እንዲህ ያሉትን መለስተኛ ችግሮች ቀድሞ መቅረፍ ይቻል እንደ ነበር እና ይህ ዐይነቱ ውዝግብ አስቀድሞም ውይይቱ እንዳይሳካ ሥር የሰደደ ፍላጎት ያላቸው ወገኖች ሤራ ሊኾን እንደሚችል ሁለቱንም ወገኖች በመውቀስ ይናገራሉ፡፡

    ለቀብር ሥነ ሥርዐቱ የተሰናዳውን የመጋቤ ብሉይ ሰይፈን ዜና ሕይወት እና ሥራ እንደደረሰን የምናቀርብ መኾኑን እየገለጽን አምላከ ቅዱሳን ለመጋቤ ብሉይ ዕረፍተ ነፍስን ለቤተሰቦቻቸውም መጽናናትን እንዲሰጥልን እንመኛለን፡፡

    መጋቤ ብሉይ ሰይፈ ሥላሴ ዮሐንስ አረፉ

    Saturday, August 7th, 2010

    (ደጀ ሰላም፤ ኦገስት 7/2010) — ሰሞኑን ለአባቶች ድርድር አሜሪካ የሰነበቱትና አርብ ወደ ኢትዮጵያ ለመመለስ ተነሥተው ቅዳሜ ጠዋት አዲስ አበባ የደረሱት መጋቤ ብሉይ ሰይፈ፣ ቤታቸው እንኳን ሳይደርሱ በድንገት ከዚህ ዓለም በሞት ተለዩ። መጋቤ ብሉይ ሰይፈ ሥላሴ በዚህ ጊዜ አሉ ከሚባሉት ሊቃውንት መካከል ተጠቃሽ ሲሆኑ በአንደበት ርቱዕነታቸው፣ በቅኔ አዋቂነታቸው፣ በሰባኪነታቸው የተመሰገኑና የተከበሩ ነበሩ።

    መጋቤ ብሉይ ሰይፈ ሥላሴ ሰሞኑን በተካሄደው የአባቶች የሰላምና የእርቅ ድርድር በተለይም ከአሜሪካኖቹ አበው ወገን “ይቅርታ ካልጠየቁን” በሚል ስሞታ ሲቀርብባቸው እንደነበር እና በዚህም ምክንያት ጉባዔው ሳይካሄድ መቅረቱ ይታወሳል።

    ካልተሳካው የእርቅ ውይይት በኋላ የልኡካን ቡድኑ ወደ ኢትዮጵያ ተመልሶ ዛሬ ረፋድ ላይ በአዲስ አበባ ቦሌ ዓለም አቀፍ አየር ማረፊያ እንደ ደረሰ ልባቸውን የመውጋት እና ብርድ ብርድ የማለት ስሜት እንደሚሰማቸው አብረዋቸው ለነበሩት አባቶች የተናገሩት መጋቤ ብሉይ ሰይፈ የሐኪም ርዳታ እንዲያገኙ ወደ አንድ ክሊኒክ ከደረሱ በኋላ ነበር ሕይወታቸው ያለፈው፡፡ በቀድሞው ሥርዐተ መንግሥት በአንድ ወቅት ክፉኛ ይሠቃዩበት ከነበረው የሳምባ ሕመም ወደ ኢየሩሳሌም ተልከው ባገኙት ከፍተኛ ሕክምና ሙሉ በሙሉ የዳኑት መጋቤ ብሉይ ሰይፈ በሰዋስወ ብርሃን ቅዱስ ጳውሎስ ከፍተኛ መንፈሳዊ ት/ቤት በብሉይ ኪዳን መምህርነታቸው፣ ከ1950ዎቹ እስከ 1970ዎቹ አጋማሽ ድረስ በኅትመት ላይ በነበረው ‹‹ትንሣኤ›› መጽሔት በአዘጋጅነት በሌሎቹም የቤተ ክርስቲያኒቱ ብዙኀን መገናኛዎች በጽሑፋቸው እና በሚያበረክቷቸው ደገኛ ቅኔዎች ይታወቃሉ፡፡

    በአሁኑ ወቅት አስከሬናቸው በቅዱስ ገብርኤል ሆስፒታል ገብቶ ምርመራ የተደረገለት ሲኾን ጸሎተ ፍትሐቱ እና የቀብር ሥነ ሥርዐቱ በመንበረ ጸባኦት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ወይም መጋቤ ብሉይ ሰይፈ በኑሮ እና በአገልግሎት ብዙ እንደ ደከሙበት በሚታወቀው በቀጨኔ ደብረ ሰላም መድኃኔዓለም ቤተ ክርስቲያን እንደሚፈጸም ይጠበቃል፡፡ ለቀብር ሥነ ሥርዐቱ በውጭ የሚገኙት የመጋቤ ብሉይ ሰይፈ ሁለት ልጆች እስከሚደርሱ ሊጠበቅ እንደሚችል የተነገረ ሲኾን በመንበረ ፓትርያሪኩ ጽ/ቤት ምንጮች ግን ቀብሩ በነገው ዕለት በመንበረ ጸባኦት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል እንዲከናወን የታሰበ መኾኑ ተገልጧል፡፡

    የሊቃውንት ጉባኤ መምሪያ ሐላፊ የነበሩት የመጋቤ ብሉይ ሰይፈ ሥላሴ ድንገተኛ ሞት በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ሠራተኞች በተለይም በሊቃውንት ጉባኤ መምሪያ አባላት ዘንድ ከፍተኛ ድንጋጤ እና ኀዘን እንደ ፈጠረ ተዘግቧል፡፡ የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን ፍልሰት እና ዕርገት በማሰብ በየዓመቱ ከነሐሴ አንድ እስከ ዐሥራ አምስት ቀን የሚጾመውን ጾም(ጾመ ማርያም፣ ጾመ ፍልሰታ) ምክንያት በማድረግ በድሬዳዋ ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን የሚገኙት ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ በቀብር ሥነ ሥርዐቱ ላይ ለመገኘት ወደ አዲስ አበባ በመመለስ ላይ እንደ ኾኑ ለማወቅ ተችሏል፡፡

    ዝርዝር ታሪካቸውንና ተያያዥ ጉዳዮች እንደደረሰን እናቀርባለን።

    መግለጫዎቹ መግጫ፣ መገጫ፣ መገጫጫ ባይሆኑ

    Saturday, August 7th, 2010

    (ደጀ ሰላም፤ ኦገስት 6/2010):- እነሆ አባቶችን ለማስታረቅ የተደረገው ሙከራ የተፈለገውን ያህል ሳይራመድ መቅረቱን ስንዘግብ ቆይተናል፤ አሁን ደግሞ አሸማጋዩ ክፍል “መግለጫ”ውን አውጥቶ የሄደበትን ሒደት እና የደረሰበትን፣ እንዲሁም ድርድሩ የፈረሰበትን ምክንያት ነግሮናል። ከዚህኛው ጋር በድምሩ ሦስት መግለጫ አንብበናል ማለት ነው። ነገ ደግሞ ሌላ መግለጫ ሊመጣ፣ ለዚያ መልስ የሚሰጥ ሌላ መግለጫ እንዳይወጣ፣ ያንን የሚያስተባብል ሌላ መግለጫ እንዳይከተል እና መግለጫዎቹ መግለጫነታቸው ተረስቶ “መግጫ፣ መገጫ እና መገጫጫ” እንዳይሆኑ ከወዲሁ ለመጠቆም ወደድን።
    መግለጫ 1፦ የአሜሪካ አባቶች መግለጫ
    በዚህ መግለጫ በዋነኝነት ድርድሩን ያፈረሱበትን ምክንያት ዘርዝረዋል። ለዚህም በምክንያትነት ያቀረቡት “አንድ ግለሰብ” መሆኑን ሲሆን ያ አንድ ግለሰብ “መጋቤ ብሉይ ሰይፈ ሥላሴ ዮሐንስ” መሆናቸውን፤ “ጥፋታቸውም” በሬዲዮ የሰጡት ቃለ ምልልስ መሆኑን ተረድተናል። ይኸው የድምጽ ቅጂ ከዝግጅት ክፍላችን ስለደረሰ እንደ አስፈላጊነቱ እናቀርበዋለን። እዚህ ላይ ልንጠይቀው የምንፈልገው አንድ ጥያቄ ግን “መጋቤ ብሉይ ሰይፈ ምንም ይበሉ ምን ቅ/ሲኖዶስን ወክለው እስከተገኙ ድረስ መቀበል አይገባም ነበር?” የሚል ይሆናል።
    መግለጫ 2፦ ከአዲስ አበባ የመጣው ልዑክ መግለጫ
    ይህ መግለጫ የአሁኑ ድርድር የፈረሰበትን ምክንያት ለማስረዳት ከመሞከሩም በላይ ቀድሞውኑ ይህ መለያየት የተፈጠረበት ታሪካዊ ዳራ እና ምክንያት ለማብራራት ጊዜ ወስዷል። 

    • አራተኛው ፓትርያርክ እንዴት እንደወረዱና በወቅቱም አሁን የተለዩት አባቶች እንደተስማሙ፤ 
    • አሁን የተለዩት አባቶች የተቆጩት በ4ኛው ፓትርያርክ መውረድ ሳይሆን እነርሱ ቦታውን ባለመያዛቸው እንደሆነ፤ 
    • ይህም ባለመሳካቱ ቀኖና ጥሰው አዳዲስ ኤጲስ ቆጶሳትን እንደሾሙ፤ 
    • እነዚህ አባቶች ሕዝቡን ለማቃቃር “በፖለቲካ ዓለም እየገቡ የተሸከሙትን የቤተ ክርስቲያን ክቡር ሥልጣን” ማዋረዳቸውን፤ 
    • ይህንን ልዩነት ለመፍታት ቤተ ክርስቲያን ብዙ እንደደከመች፤ 
    • አሁን የተጀመረው ጥረት በብፁዕ አቡነ ዜና ማርቆስ ሞት ማግስት የተጀመረ እንደነበረ፤  
    • በሰሜን አሜሪካ የሚገኙት አባቶች የሚፈጥሩት የሰላም እንቅፋት ብዙ መሆኑን ወዘተ አትተዋል። 

    በየመካከሉም መብራራት የሚገባቸው ሌሎች ጥያቄዎች አጭሮ አልፏል። ለምሳሌ በዚሁ መግለጫ ገጽ 3 ሁለተኛው አንቀጽ ላይ በውጪ የሚገኙት አባቶች ሕዝቡን ለማቃቃር “በፖለቲካ ዓለም እየገቡ የተሸከሙትን የቤተ ክርስቲያን ክቡር ሥልጣን” ማዋረዳቸውን አትተዋል። ትክክል ነው። ይሁን እንጂ በዚህ የፖለቲካ አባዜ ተጠምደው ቤተ ክርስቲያኒቱን በማስደፈር በኩል አዲስ አበባ ያሉት አባቶች እኩል ተጠያቂዎች ናቸው። ልዩነቱ ሰሜን አሜሪካ ያሉት የተቃዋሚዎች ፖለቲካ አራማጅ መሆናቸው፤ አገር ቤት ያሉት ደግሞ የኢሕአዴግ ፖለቲካ ደጋፊና አራማጆች መሆናቸው ብቻ ነው። ዋናው ቁም ነገር እርሱ አይደለም። ለዚህ ለዚህማ ሁለቱንም ክፍል የምንጠይቅበት ዘመን ይመጣ ይሆናል። ይህ መግለጫ በመጨረሻ የቤተ ክርስቲያን የሰላም በር አለመዘጋቱን በማስረዳት ይፈጽማል። ይህ ጥሩ ማጠቃለያ ነው። ለሰላም የሚዘጋ ምንም በር መኖር የለበትም። ለሰላም ምንም ቅድመ ሁኔታ እና ጊዜ ገደብ መኖርም የለበትም። ያውም ለቤተ ክርስቲያን ሰላም።

    መግለጫ 3፦ “የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሰላምና አንድነት ጉባዔ መግለጫ”
    መግለጫው ባለ 3 ገጽ ሲሆን ጉባዔው የሄደበትን ሒደት በአጭሩ ከዘረዘረ በኋላ የአሁኑ ሙከራ ያልተሳካበትን ምክንያት ያብራራል። ሙከራ ያልተሳካበት ምክንያትንም ሲያትት በአሜሪካ አባቶች መግለጫ በተጠቀሰው ይስማማና የአዲስ አበባው ክፍል ይህንን ጉዳይ ቀድሞ ቢያውቅም መፍትሔ ፈልጎ አለመምጣቱን ያትታል። ልዑካኑን “ፊት ለፊት ቀርቦ ለማነጋገር ያላስቻለው ዕንቅፋት … ከአዲስ አበባ ከተመደቡት ልዑካን መካከል በአንዱ ላይ ከፍተኛ ቅሬታ” መነሣቱ መሆኑን፣ “የሰላም ጉባኤውም ከልዑካኑ መካከል እንዳይሆኑ በደብዳቤም ሆነ በስልክ ያደረገው ጥረት” እንዳልተሳካ ይገልጻል። ይህ መግለጫ የአሸማጋዮችን ስምና ማንነት፣ አስታራቂዎቹ እነማን እንደነበሩ ሳያስረዳን አልፏል። አሁንም በደፈናው “ሽማግሌዎች” እንላቸዋለን እንጂ ማንነታቸውን አልገለፁም። ይህንን የሚያክል ታላቅ ተግባር አሁንም ተደብቀውና ደብቀው መሥራት የመረጡ ይመስላሉ። ወይም ስማቸው ቢታወቅ “እንዴ? እነርሱ ናቸው እንዴ?” እንዳይባሉ የፈሩ ይመስላሉ።
    መግለጫዎቹ ሲገጫጩ
    አሁን እንደሚባለው ሁሉም ቡድን በየትኛውም መግለጫ አልተደሰተም። ከተሠራው ሥራ ይልቅ ለመግለጫዎቹ ትልቅ ትኩረት የሰጠ ይመስላል። ሁሉም ጣቱን ለመጠቆምና ራሱን ለማዳን የሚሞክርም ይመስላል። እርቁ ተጀመረ እንጂ አልተፈጸመም። በአንድ ዙር ይፈጸማል ተብሎም አልተጠበቀም። ለሚቀጥለው ሥራ እንቅፋት ላለማስቀመጥ ግን ቢሞክር ጥሩ ነው። በመግለጫ ጋጋታ መገጫጨቱ ምንም አይፈይድም። ያለፈው አለፈ። እስቲ በተሻለ ጥራት ለመሥራት ቢሞክር። ለዚህም ከሽማግሌዎቹ ይጀመር። ከማጀት ወደ አደባባይ ውጡ። እንወቃችሁ። ሕዝብ የማይፈልጋቸው ካሉ መንገዱን ለሚታመኑ ሰዎች ይልቀቁ። ራሳቸው ሳይታረቁ ማስታረቅ የሚፈልጉም ካሉ በመጀመሪያ ይስተካከሉ። ሦስት ወይም አራት ወር ብዙ አይደለም። ትንሽም አይደለም። አስታራቂዎቹ አሁን በገጠማቸው ነገር ተስፋ ሳይቆርጡ ሥራውን ይቀጥሉ። ይህንንም ቢሆን ያደረጉት እነርሱ ናቸው። ሌላው ቁጭ ብሎ ድንጋይ ያቀብል የለ? እንደ እብድ ገላጋይ! ስለዚህ የተጀመረው ይጠናከር። የተበላሸው ይስተካከል። ሽማግሌዎቹ ሸምግለው ይሸምግሉ። ታርቀው ያስታርቁ።
    የሰላም አምላክ ሰላሙን ይስጠን፣

    አሜን



    “የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሰላምና አንድነት ጉባዔ” መግለጫውን አወጣ፤ ድርድሩ በሦስት/አራት ወራት ውስጥ ይቀጥላል

    Friday, August 6th, 2010

    (ደጀ ሰላም፤ ኦገስት 6/2010):- በቤተ ክርስቲያን አባቶች መካከል ያለውን መለያየት ለማስወገድ የማሸማገል ተግባር ሲፈጽም የነበረው የሰላምና የአንድነት ጉባዔ መግለጫውን አውጥቷል፤ ድርድሩ ከሦስት እስከ አራት ወራት ውስጥ እንደሚቀጥል አስታውቋል። የመግለጫውን ሙሉ ቃል ለማንበብ ይህንን ይጫኑ።
    ቸር ወሬ ያሰማን፣
    አሜን




    በሐዋሳ የአጥቢያ ሰበካ ጉባኤያት እና የሀገረ ስብከቱ ‹ልኡካን› ውዝግብ

    Monday, August 2nd, 2010
    • ‹‹ከእኛ ወገን አልያም ከዐመፀኛ ኀይሎች ጋራ ለመኾናችሁ ሚናችኹን ለዩ! በእንጀራችኹ ፍረዱ!! ፓትርያሪኩም ቢኾኑ አያድኗችኹም!!›› (አቡነ ፋኑኤል)
    • ‹‹በእንጀራችሁ ፍረዱ!›› (ሥራ አስኪያጁ)

    (ደጀ ሰላም፣ ኦገስት 2/2010)፦ በሲዳማ፣ ጌዲኦ፣ አማሮ እና ቡርጂ ዞኖች እና ልዩ ወረዳዎች ሀገረ ስብከት በሐዋሳ ከተማ በሚገኙ ሦስት አጥቢያ አብያተ ክርስቲያን ከቃለ ዐዋዲው ውጭ የሰበካ ጉባኤ አባላትን እንዲያስመርጡ ከሀገረ ስብከቱ በተላኩ ግለሰቦች ሳቢያ ውዝግብ ተቀሰቀሰ፤ በውዝግቡ የተልእኮው አስፈጻሚ እና ተባባሪ ኾነው የመጡ ራሱን ‹‹ተስፋ ኪዳነ ምሕረት ፀረ – ኤድስ ማኅበር›› እያለ የሚጠራው ቡድን አባላት በተቃወሟቸው የሰንበት ት/ቤት ተማሪዎች ላይ አካላዊ ጥቃት አድርሰዋል፡፡
    የሀገረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጅ በመንበረ ጵጵስናው ትእዛዝ እና ራሳቸው በማስፈራራት የሰበሰቧቸውን ካህናት በሁለት መኪና ጭነው ወደ ፓትርያሪኩ ለመግባት እየተንቀሳቀሱ ነው፤ ድርጊቱ የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ ሐምሌ 12 ቀን 2002 ዓ.ም የሀገረ ስብከቱን አጥቢያ አብያተ ክርስቲያን አለቆች እና ካህናትን በመንበረ ጵጵስናው ሰብስበው፣ ‹‹በሀገረ ስብከቱ ወሳኙ እኔ ነኝ፤ አላያችኹም እንዴ አለቃውን [አባ ገብረ ዋሕድን] መንቅሬ እንዳስወጣኹት፤ በጠቅላይ ቤተ ክህነቱም ቢኾን በሲኖዶሱ ያለኹት እኔው ነኝ፤… ከእኛ ወገን ናችሁ ወይስ ከዐመፀኛ ኀይሎች ጋራ? አቋማችኹን ለዩ! ፓትርያሪኩም ቢኾኑ አያድኗችኹም!!›› ማለታቸውን ተከትሎ የተፈጸመ መኾኑን የደጀ ሰላም ምንጮች ተናግረዋል፡፡
    - – - – - – - – - – - – - – - – - – - – - – - – - – - – - – - – - – - – - – - – - – -
    ትላንት ሐምሌ 25 ቀን 2002 ዓ.ም በሐዋሳ ከተማ በሚገኙት የደብረ ምሕረት ቅዱስ ገብርኤል ገዳም፣ የኆኅተ ሰማይ በዓለ ወልድ እና የዳቶ ኪዳነ ምሕረት አብያተ ክርስቲያን፣ ‹‹የቀድሞውን የሰበካ ጉባኤ አስተዳደር በመለወጥ አዲስ የሰበካ ጉባኤ ምርጫ እናካሂዳለን፤›› በሚሉ ከሀገረ ስብከት በመጡ ልኡካን እና ድርጊቱ የሰበካ ጉባኤውን ቃለ ዐዋዲ አንቀጽ ስምንት እና ዘጠኝ እንደሚጥስ በተቃወሙ የየአጥቢያዎቹ ምእመናን መካከል ውዝግብ ተቀስቅሶ እንደ ነበር የደጀ ሰላም ምንጮች ገለጹ፡፡ መልእክተኞቹ ለሕገ ወጥ ተልእኳቸው መሠረት ያደረጉት በተለይም ለሀገረ ስብከቱ ብልሹ አሠራር አልመች ባሉት ሦስቱ አጥቢያ አብያተ ክርስቲያን ሐምሌ 12 ቀን 2002 ዓ.ም አዲስ የሰበካ ጉባኤ ምርጫ እንዲካሄድ በሀገረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጅ ፊርማ የታዘዘበትን ደብዳቤ በመያዝ ነው፡፡ ድርጊቱ ሐምሌ 22 ቀን 2002 ዓ.ም የሐዋሳ ምእመናን ተወካዮች ከብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያሪኩ ጋራ ባደረጉት ውይይት የአጣሪ ኮሚቴው ተግባር እስኪጠናቀቅ ድረስ የሰበካ ጉባኤ አባላት ምርጫ እንዳይካሄድ የተደረሰውን ስምምነት የሚፃረር እንደ ኾነ አስተያየታቸውን ለደጀ ሰላም የሰጡ ምእመናን ተናግረዋል፡፡

    የሕገ ወጡ ምርጫ አስፈጻሚ ኾነው የተላኩት ግለሰቦች፣ በኆኅተ ሰማይ በዓለ ወልድ – በኩረ ትጉሃን አማረ ግርማ እና መጋቤ ልኡካን አንዳርጋቸው፣ በዳቶ ኪዳነ ምሕረት ቀሲስ አስረስ እና መጋቤ አእላፍ ኀይለ ጽዮን፣ በደብረ ምሕረት ቅዱስ ገብርኤል ደግሞ በአቡነ ፋኑኤል ‹መጋቤ ልኡካን› የተባለው ያሬድ አደመ፣ ጌራ ወርቅ እና መጋቤ ሐዲስ ፍሥሐ ለማ የሚባሉ ናቸው፡፡ አሁን በሐላፊነት የሚገኙ የየአጥቢያው ሰበካ ጉባኤ ሊቃነ መናብርት ዕድል አግኝተው አንዳችም ሐሳብ እንዳይሰጡ መድረክ እንዲነፈጉ፣ የየአድባራቱ አስተዳዳሪዎች እና አገልጋይ ካህናት፣ ‹‹ከእኛ ወገን ናችሁ ወይስ ከሌላ – አቋማችኹን ለዩ!›› እየተባለ ከሊቀ ጳጳሱ የተሰጠው ትእዛዝ ግልጽ ወጥቶ በልኡካኑ ይነገርበት የነበረው ይኸው ተልእኮ ከምእመናን ጠንካራ ተቃውሞ ገጥሞታል፡፡ በተለይም በኆኅተ ሰማይ በዓለ ወልድ ምእመናኑ የሰበካ ጉባኤው ቃለ ዐዋዲ አንቀጽ ስምንት እና ዘጠኝ ወጥቶ እንዲነበብ በማድረግ ልኡካኑን ፊት ለፊት ‹‹አንቀበላችኹም!›› ብለዋቸዋል፡፡ በደብረ ምሕረት ቅዱስ ገብርኤል ገዳም ደግሞ የሕገ ወጡ ተልእኮ አስፈጻሚ ቡድን መሪ ኾኖ የመጣው ያሬድ አደመ፣ ‹‹አንተ ከዚህ በፊት የፈጸምኸው የሙስና ተግባር ሳያንስህ አሁን ዳግመኛ ተመልሰኽ ለምን ትበጠብጠናለኽ?›› የሚል ጠንካራ ተቃውሞ ከምእመናኑ ሲገጥመው እርሱን ተከትለው የመጡ የ‹‹ተስፋ ኪዳነ ምሕረት ፀረ-ኤድስ ማኅበር›› አባላት ውዝግቡን በማባባስ የተቃወሟቸውን እስከ መደብደብ መድረሳቸውን ትዕይንቱን በምስል ወድምፅ ያስቀሩ የደጀ ሰላም ምንጮች ገልጸዋል፡፡

    በተመሳሳይ መልኩ እነዚሁ የማፊያ ቡድን አባላት ከቀትር በኋላ በመደበኛው የገዳሙ ሰንበት ት/ቤት መርሐ ግብር ሰዓት በስፍራው በመገኘት ‹‹አዲስ የሰንበት ት/ቤት አመራር እናስመርጣለን፤›› በሚል ተጨማሪ ሁከት መቀስቀሳቸውን ለመረዳት ተችሏል፡፡ በዚሁ ሁከት በያሬድ አደመ የተደራጁ የ‹‹ተስፋ ኪዳነ ምሕረት ፀረ-ኤድስ ማኅበር›› ወጣቶች የሰንበት ት/ቤቱን አባላት ደብደበዋል፤ በድብደባው መኳንንት አየለ የተባለ የሰንበት ት/ቤቱ አባል ጥርስ መጎዳቱን ተያይዞ የደረሰን መረጃ ያመለክታል፡፡ እነ ያሬድ አደመ ቀደም ሲል በሀገረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጅ ደብዳቤ እና በሕገ ወጥ መንገድ በተሾሙት የደብሩ አስተዳዳሪ አባ ኀይለ ጊዮርጊስ አብርሃም አይዞህ ባይነት የሰንበት ት/ቤቱን ቁልፍ ሠብረው በሌላ ቁልፍ በመለወጥ ከቃለ ዐዋዲው እና ከጠቅላላ ጉባኤው ዕውቅና ውጭ አዲስ አመራር በመተካታቸው በሕጋዊው የሰንበት ት/ቤቱ አመራር መከሰሳቸውን መግለጻችን ይታወሳል፡፡

    በተያያዘ ዜና፣ ለዓመታት ባደረሱት አስተዳደራዊ በደል እና ዐይን ባወጣ ሙሰኛነታቸው ከሐላፊነታቸው እንዲነሡ የምእመናን አቤቱታ የቀረበባቸው የሀገረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጅ መልአከ ምሕረት ፀሐይ መልአኩ በሀገረ ስብከቱ የሚገኙትን አድባራት አለቆች እና የሰበካ ጉባኤ ጸሐፊዎች በማስፈራራት የሀገረ ስብከቱን ችግር በሚያጣራው ኮሚቴ ላይ ከወዲሁ ተጽዕኖ ለመፍጠር እየተንቀሳቀሱ መኾኑን ውስጥ ዐዋቂ ደጀ ሰላማውያን ገለጹ፡፡

    ምንጮች ለደጀ ሰላም እንዳደረሱት ነገሩ ባጭሩ እንዲህ ነው፤ ሐምሌ 23 ቀን 2002 ዓ.ም ሥራ አስኪያጁ የደብር አለቆች እና ጸሐፊዎች የየሰበካ ጉባኤያቸውን ማኅተም በመያዝ እንዲመጡ ያዝዛሉ፡፡ የታዘዙትን ከማድረግ በቀር ምርጫ የሌላቸው አስተዳዳሪዎች እና ጸሐፊዎችም፣ ‹‹ሥራ አስኪያጁ ትጉህ አገልጋይ ናቸው፤ ለአጭር ጊዜ የታሰሩት በፀረ ሰላም እና አሸባሪ ኀይሎች ተንኮል ነው፤ ይኹንና በቅዱስ ፓትርያሪኩ ጥረት ሊፈቱ ችለዋል፤…›› የመሳሰለው ይዘት ባዘለው እና ራሳቸው ሥራ አስኪያጁ ባዘጋጁት ደብዳቤ ላይ እንዲፈርሙ ያስገድዷቸዋል፡፡ እነርሱ ይህን ሲቃወሙ አጅሬ ወዲያው የእያንዳንዳቸውን ማኅተም እየተቀበሉ ባዘጋጁት ጽሑፍ ላይ ያትሙበታል፡፡

    በዚህ አሳፋሪ አካሄድ ያልተገቱት ሥራ አስኪያጅ ወደ ሀገረ ስብከቱ ሠራተኞች ተመልሰው እንደለመዱት እነርሱንም ፈርሙ ይሏቸዋል፤ ካህናት አባቶች ጭምር የሚገኙባቸው የሀገረ ስብከቱ ሠራተኞችም፣ ‹‹እንዴት ተደርጎ! ፀረ ሰላም የምንላቸውኮ የንስሐ ልጆቻችን የኾኑ ምእመናን ናቸው፤ እናውቃቸዋለን፤ እንደምን በእነርሱ ላይ እንፈርማለን? ስለ እርስዎ በጎነት መፈረም እንችላለን፤›› ይሏቸዋል፡፡ በዚህ የተበሳጩት ሥራ አስኪያጅም ‹‹በእንጀራችኹ ፍረዱ!!›› እንዳሏቸው እነዚሁ ምንጮች ጨምረው ገልጸዋል፡፡ የዚህ ሁሉ ጫና ዓላማ ካህናቱን አስፈራርተው እና ይዘው ሄደው ወደ ፓትርያሪኩ በመግባት ሥልጣናቸውን ለማስጠበቅ፣ በአጣሪ ኮሚቴው ምርመራ ሂደት እና ውጤት ላይ ተጽዕኖ ለመፍጠር በማሰብ እንደ ኾነ ኹኔታውን በቅርበት የሚከታተሉ ምእመናን ስጋታቸውን ገልጸዋል፡፡ ይህ እንቅስቃሴ በአድባራት አለቆች እና አገልጋይ ካህናት እንዲሁም በሀገረ ስብከቱ ሠራተኞች መካከል ከፍተኛ ግራ መጋባትን የፈጠረ መኾኑን ለመረዳት ተችሏል፡፡



    ውይይቱና ሽምግልናው በምን ዙሪያ?

    Monday, August 2nd, 2010

    (ደጀ ሰላም፤ ኦገስት 1/2010)፦ በጉጉት ሲጠበቅ የነበረው የአባቶች የሰላምና የዕርቅ ድርድር በነገው ዕለት ማለትም ሰኞ ኦገስት 2/2010 (ሐምሌ 26/2002 ዓ.ም) ይጀመራል ተብሎ ይጠበቃል። ከሁለቱም በኩል ያሉ ተወካይ “የሰላም ልዑካን” ዋሺንግተን ዲሲ አካባቢ ተሰባስበዋል። እንደተለመደው ውይይቱ እንደሚደረግ በደፈናው ከመታወቁ ውጪ በምን ዙሪያ፣ እንዴት የሚለው ጉዳይ “በምስጢር” ስለተያዘ ብዙም ለማለት አያስደፍርም። ቤተ ክህነቱን የብልሹ አሠራር ምንጭ ያደረገውና ለዚህ ሁሉ ውድቀት ያበቃን ዋነኛው ምክንያት ነገሮችን ከሚመለከተው አካልና ምእመን ደብቆ የመሥራት አባዜ ስለሆነ ይህ ብልሹ አመለካከት ይሰበር ዘንድ ዝምታው ይሰበር፣ መጋረጃው ይቀደድ እንላለን፤ ስለዚህም እንጽፋለን።
    የወቅቱ ዋነኛ አጀንዳ ወደሆነው ጉባዔ ስንመለስ፣ ይህ ጉባዔ ሊነጋገርባቸው/ ሊመለከታቸው ይገባል የምንላቸውን ነጥቦች ለማቅረብ እንወዳለን። እነዚህም፦
    ·    በነዚህ 18 የልዩነት ዓመታት ውስጥ የተፈጠሩ ስሕተቶች ከቀኖና ቤተ ክርስቲያን አንጻር እንዴት ሊታረሙ ይችላሉ?
    ·    የሁለቱ ፓትርያርኮች የወደፊት ዕጣ ፈንታ ምን ይሆናል፣
    ·    አሜሪካ ባሉት አባቶች ክፍሎች የተሾሙ ኤጲስ ቆጶሳት ዕጣ ፈንታና ጉዳይ እንዴት ይፈታል?
    ·    ከልዩነቱ በኋላ የተሠሩ ሥራዎች፣ የተደነገጉ ድንጋጌዎች ወዘተ እንዴት ይስተካከላሉ?
    ·    በሁለቱም በኩል የተላለፉ ውግዘቶች እንዴት ይታያሉ፣ ይፈታሉ?
    ·    ዕርቁ የጳጳሳት ብቻ እንዳይሆን፣ በእነርሱ ምክንያት የተለያዩት (በልዩነቱ ውስጥ ተዋናይ የነበሩ) የተለያዩ አካላት ዕጣ ፈንታስ?
    ·    ውይይቱና እርቁ በሕዝብ ዘንድ ተቀባይነት እንዲኖረው ምን ማድረግ ይገባል?
    ·    እርቁ ከተፈጸመም በኋላ ቢሆን ስምምነቱ ሊመጣበት ከሚችለው ተቃውሞ (ካለ) በተለይም ከኢትዮጵያ የፖለቲካ ዘዋሪዎች (አሽከርካሪዎች) ከሆኑት (በሀገር ቤት ከኢህአዴግ፣ በውጪ ደግሞ ከተቃዋሚዎች) ተጽዕኖ እንዴት ነጻ ማድረግ ይቻላል?

     

    የሚሉት እና ሌሎችም ተያያዥ ጉዳዮች ናቸው። 

    የአባቶች ሽምግልና እና እርቅ ከየት ይነሣ፣ የት ይድረስ?

    (ደጀ ሰላም፣ ጁን 26/2010)፦ በግንቦቱ የቅ/ሲኖዶስ ጉባዔ ላይ እንደተገለፀው ከአምስተኛው ፓትርያርክ ከብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ሲመት ማግስት ጀምሮ በቤተ ክርስቲያኒቱ የተነሣውን መከፋፈል ለማቆምና በአባቶች መካከልም የተፈጠረውን እስከ መወጋገዝ የሚያደርስ ልዩነት በእርቅ ለመጨረስ እንቅስቃሴ ተጀምሯል። ይኸው ከአበው ካህናት፣ ከምእመናንና ከታዋቂ ግለሰቦች በአባልነት የተውጣጡ ሰዎች የሚሳተፉበት ነው የተባለው አንቀሳቃሽ ቡድን በግንቦት ወር ወደ ጠቅላይ ቤተ ክህነት (አዲስ አበባ) እንዲሁም ወደ ኒውዮርክ ልዑካንን በመላክ እርቁ እንዲጀመር አግባብቷል።

    በዚህም ከሁለቱም በኩል ቀና ምላሽ አግኝቷል። ቀጣዩ ሁለቱንም ወገኖች ፊት-ለፊት፣ መሳ-ለመሳ ማገናኘትና ማወያየት ይሆናል። ሁሉ ነገር ምሥጢር፣ ሁሉ ነገር ከመጋረጃ ጀርባ ተጀምሮ ከመጋረጃ ጀርባ በሚያልቅበት “የምሥጢር ማኅበረሰብ” መካከል ስለምንኖር ልናውቀው የሚገባንን ሳናውቅ፣ የበኩላችንን ድርሻ ልንወጣበት የሚገባው ነገር ላይ ምንም ሳናከናውን ጊዜው እንዳያልፍ ግን አስግቶናል። ከመጋረጃ ጀርባ የሚደረጉ ቲያትሮች ታዲያ ጦሳቸው ጥንቡሳታቸው ዘግይቶ ይደርሰንና “ለምን የመጣ ለምን ይተርፋል” ይሆናል። በፖለቲካችንም፣ በቤተ ክህነታችንም፣ በሃይማኖታችንም ሁሉ ከጀርባ እያለቀ የሚመጣው ነገር አገሪቱንም፣ ቤተ ክርስቲያኒቱንም ሲያምሳት እነሆ የአንድ ሰው ዕድሜ በላይ ሆኖናል። ወደ ቀደመ ነገራችን እንመለስና “የእርቁ ነገር” ላይ ለመወያየት እንሞክር።

    ጥንተ ታሪክ

    ኢሕአዴግ ስልጣን በያዘ ማግስት “ከደርግ ጋር አብረዋል” ያላቸውን አራተኛውን ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስን “እንደማንኛውም ደርግ/ ደርጌ” በመቁጠር አብሯቸው ሊሠራ እንደማይችል በወቅቱ አዛዥ ናዛዥ በነበሩት በጠቅላይ ሚኒስትር ታምራት ላይኔ በኩል ግልጽ አደረገ። እርሳቸውን ከስልጣን ለማውረድ ከቤተ ክህነቱም ከቤተ መንግሥቱም ስምምነት ላይ ተደረሰ። እርሳቸው ፓትርያርኩም አልተቃወሙም። ጥያቄው ከወረዱ በኋላ ስለሚኖሩት የኑሮ ዓይነት ነበር። በምትካቸውም አፈር ይቅለላቸውና በቅርቡ ከዚህ ዓለም በሞት የተለዩት ብፁዕ አቡነ ዜና ማርቆስ አቃቤ መንበር (መንበር/ ወንበር/ ዙፋን ጠባቂ) ሆነው ተሾሙ። ከዚያም ጊዜውን ጠብቆ አዲስ ፓትርያርክ እንዲመረጥ ተወሰነ። ለእጩነት የቀረቡት ብፁዕ አቡነ ጳውሎስ ተመረጡ እና አምስተኛው ፓትርያርክ ሆኑ። በወቅቱ “ብፌ እንኳን ለማንሳት ዕውቀት ያልነበራቸው አባቶች አልፈው እንግሊዝኛ ተናጋሪ፣ ዶክተር፣ ዓለምን ጠንቅቆ ያወቀ አባት ተገኘ” ተባለና ሁሉም አባት ደስ አለው። “ይደልዎ”!!! እያለ በቪዲዮ ተቀረፀ። ትንሽ ቆይቶ ደግሞ በኬንያም፣ በባሌም፣ በቦሌም ወደ አሜሪካ መጡ እና “ሕጋዊ ቅዱስ ሲኖዶስ” ተመሠረተ ተባለ። አራተኛውም ፓትርያርክ ተቀላቀሏቸው”። ከዚያም “ስደተኞቹ አባቶች” የዚህኛው ቡድን ፖለቲካ አቀንቃኝ፣ አምስተኛው ፓትርያርክ ደግሞ አዲስ አበባ ተቀምጠው የሚኒሊክ ቤተ መንግሥትን የተቆጣጠረው ቡድን አቀንቃኝ ሆነው በሬዲዮም፣ በጋዜጣም፣ በእንቁላልም ሲደባበደቡ 20 ዓመት ሊሞላ አንድ ፈሪ (ማለትም 19 ዓመት) ሆነው።

    ዛሬ አሜሪካ የተሰበሰቡት ስዱዳን አባቶች ቅ/ሲኖዶሱን ጥለው ከወጡ ጀምሮ ከአሜሪካ ወደ ኢትዮጵያ የገቡ ሰሞን አንገታቸውን ደፍተው በትህትና ሲመላለሱ የነበሩት ብፁዕ አቡነ ጳውሎስ አንገታቸው ቀና አደረጉና ሌሎችን አንገት አስደፉ። ስደተኞቹ ከአሜሪካ እንቁላላቸውን በወረወሩ መጠን አቡነ ጳውሎስም ከመንገዳቸው ወደ ኋላ ከመመለስ ይልቅ የበለጠ ገፉበት። ከዚያም በውጪ ያሉት አባቶች “ጳጳሳት ሾምን” ብለው የበለጠ ልዩነቱን አስፍተው ቀኖና እስከመጣስ ድረስ ሄዱ። ከዚያም ውግዘት ተከተለ እና አራተኛው ፓትርያርክ እና አብረዋቸው ያሉት አባቶች በሙሉ በየስማቸው ተወገዙ። እነርሱም በፈንታቸው ሌላውን አወገዙ። እንዲህ እንዲህ ቆይቶ አሁን የእርቅ ዜና ተሰማ። ተመስገን። ነገር ግን እርቁ በየትኛው ላይ ይሆን? ውይይቱና ሽምግልናውስ እስከምን ድረስ?

    ለእርቅና ለሽምግልና የሚያስፈልጉ አራት ነጥቦች
     
    ይህንን የመሰሉ አገራዊ አጀንዳዎችን ይዞ የሚነሣ አካል ሊያውቃቸው የሚገባ አራት ነጥቦች አሉ። የመጀመሪያው አብረውት የሚሠሩ የቴክኒክ እና የምክር ኮሚቴዎች ሊኖሩት እንደሚገባ ነው። አንድ ሰው ተሰሚነት ያለው ሰው በመሆኑ ብቻ ሽማግሌ ይሆናል፣ ለማስታረቅ የሚያስችሉ ዲፕሎማሲያዊ፣ ታሪካዊ እና ንግግራዊ ክህሎቶች አሉት ማለት አይደለም። የሁለቱን ወገኖች ታሪካዊ ሽግግር፣ የልዩነት ምክንያቶች፣ የሌሎች አገሮች ተሞክሮ (ልምድ)፣ ከዚህ በፊት የነበሩ የእርቅ-ድርድሮች ሊከሽፉ/ሊሳኩ የቻሉበት ምክንያት፣ የታራቂዎቹ ጠባይ ወዘተ የሚለውን የሚያጠና፣ ስልት የሚጠቁም እና ሙያዊ እገዛ የሚያደርግ አካል ያስፈልጋል። አንዳንድ ጊዜ ታራቂዎቹ የሃይማኖት ሰዎች ሆነው አስታራቂዎቹ ግን የሃይማኖቱን ቀኖና እና መሠረተ ሐሳብ ያልተረዱ አልያም ታራቂዎቹ ፖለቲከኞች ሆነው አስታራቂዎቹ የፖለቲካን አካሄድ ጭራሽ ያልተረዱ ከሆኑ እርቁ በደፈናው “አንተም ተው፣ አንተም ተው” ዓይነት ይሆናል። በዚህ ጊዜ አካሄዶችን አጥንተው መንገድ የሚያሳዩ ባለሙያዎች ያስፈልጋሉ።

    ሁለተኛው ነጥብ ደግሞ የሕዝብ ይሁንታ ነው። አገራዊ የሆኑ እርቆች ሲደረጉ ሕዝቡ ስለጉዳዩ ሐሳብ እየሰጠ፣ አቅጣጫ እየጠቆመ. ከመነሻው ይሁንታውን እየሰጠ መሆን አለበት። የሕዝብ ጉዳይ ለሕዝብ ዱብ ዕዳ መሆን የለበትም። እንዲህ ዓይነቱ ዱብ ዕዳ ሲከሰት ሕዝቡ ስለ እርቁ የራሱን ምክንያት እና አንድምታ ይሰጥና ከእርቁ መንፈስ ይወጣል። የሰዎቹን እርቅ ቅቡልነት (ተቀባይ መሆን) ጥርጣሬ ላይ ይጥለዋል። በርግጥ በእርቁ ሒደት ምስጢራዊ ሊሆኑ የሚገባቸው አንዳንድ ነገሮች ይኖራሉ። ይህ ማለት ግን ሁሉም ነገር ምስጢራዊ ይሆናል ማለት አይደለም። ልዑል እግዚአብሔር እንኳን ከሰዎች ልጆች ጋር እርቅን ሲመሰርት መንገዱን፣ አመጣጡን፣ አሠራሩን ከመጀመሪያው ጀምሮ ሱባዔ አስቆጥሮ እና በኦሪት እና በነቢያት አናግሮ ነው። መቼ ከዚ ምስጢር (ከምስጢረ ሥጋዌ) የበለጠ ምንም ምስጢር የለም።

    ሦስተኛው ነጥብ ደግሞ የሽማግሌዎቹ ለእርቁ ተገቢ መሆን እና በሰዎች ዘንድ ያላቸው ተቀባይነት ነው። ሽምግልናው ተቀባይነት የሚኖረው ሕዝቡ ሲቀበለው፣ ሽምግልናው ውጤት ሲያመጣ እና ለሌሎችም ምሳሌ መሆን ሲችል ነውና ይህንን ለማድረግ አደራዳሪዎቹ ራሳቸው በሌላው ዘንድ ተቀባይነት ያላቸው፣ ወገንተኝነት ያላጠቃቸው መሆን አለባቸው። አሁን በተጀመረው ሽምግልና ማን ሽማግሌ እንደሆነ፣ ሽማግሌዎቹ በምን መመዘኛ እንደተመረጡ፣ ዓላማቸው ምን እንደሆነ በትክክል ለሕዝብ አልተገለጸም። ይህ ደግሞ ውሎ አድሮ ጥያቄ ማስነሣቱ አይቀርም። ነገሩ የሃይማኖት መሆኑን ስናውቅ ደግሞ ይበልጥ አሳሳቢ ያደርገዋል።

    የተሸምጋዮቹ ሽምግልናውን እና የእርቅ ጥያቄውን መቀበላቸው ብቻ ጅምሩን የተሳካ አያደርገውም። ለምሳሌ የቀድሞ የቅንጅት አመራሮችን የተፈቱበትን ሒደት እንመልከት። በሽማግሌዎቹ አማካይነት የታሠሩት ተፈቱ ተባለ። ይህ መልካም ነው። የሽምግልናው ሒደት ግን ምስጢራዊነቱ እጅግ የበዛ እና ሽማግሌዎቹ እንዴት ሊሸመግሉ እንደበቁ ባለመገለጡ ውጤቱ እስካሁን በሕዝቡ ዘንድ ጥያቄ እንዳስነሣ ነው። እንኳን ሕዝቡ ራሳቸው ተሸምጋዮቹ ጥያቄ የሚያነሡበት ሒደት ሆኗል።

    አራተኛው ነጥብ የሽምግልናው ግብ በግልጽ መቀመጥ መቻሉ ነው። ሽማግሌዎቹ ዓላማቸው ምንድርነው? የሚጠብቁት ውጤትስ ምንድርነው? ሽምግልናው ተሳካ/አልተሳካም የሚሉት የት ጋር ሲደርሱ ነው? እነዚህ እና እነዚህን መሰል ጥያቄዎች በግልጽ ተነሥተው በግልጽ መልስ ማግኘት አለባቸው። “አለባብሰው ቢያርሱ ባረም ይመለሱ” እንደሚባለው እንዳይሆን።

    ከዚህ አንጻር አሁን የተጀመረው መልካም የእርቅ እና የሽምግልና ሒደት ግቡን እንዲመታ የሽማግሌዎቹ ቡድን እነዚህን ጉዳዮች ለመፈተሽ ሃይማኖታዊም፣ ባህላዊም፣ ሞራላዊው ግዴታ አለበትና በዝርዝር ሊመለስበት፣ ጋዜጣዊ መግለጫ በመስጠትም ሆነ ሕዝቡን ይወክላሉ የሚባሉ አካላትን በማማከር ገለልተኛነቱን እና ብቃቱን ማሳየት አለበት እንላለን። አለበለዚያ ግን እንደ አልጀርሱ የኢትዮ-ኤርትራ ሽምግልና “ተፈፀመ፣ ታረቁ” የሚለው ፊርማ ሳይደርቅ “አልታረቅንም” የሚል መግለጫ እንደማይወጣ ማስተማመኛ አይኖረንም።

    በመጨረሻ
     
    ይህንን ሁሉ ማለት የፈለግነው እንዲያው በደፈናው “ጨለምተኞች” (ፔሲሚስት) ስለሆንን፣ ወይም ይህ እርቅ እንዳይሳካ ስለምንፈልግ፣ ወይም እንዲያው ነገር ለማዳመቅ ከመሻት አለመሆኑን ማንም አስተዋይ ልቡና ያለው ሁሉ ይረዳዋል ብለን እንገምታለን። ሽማግሌዎች እና ተደራዳሪዎቹም ጭምር።

    ቸር ወሬ ያሰማን፣
    አሜን



    የሊ/ካህናት ጌታቸው ዶኒ እና የአባ ሰረቀ ምስጢራዊ ደብዳቤ

    Friday, July 30th, 2010

    • . ‹‹ወጣቱን በተሐድሶአውያን ኅብረት አዲስ ጥምቀት በማድረግ በ‹ቅን ልቦና የመንፈሳዊ የፈውስ አገልግሎት› ሥር መሰብሰብ፤››
    • . ‹‹ሐሳባችንን የሚያደናቅፉ የአቡነ ሳሙኤል ደጋፊዎችን ተቋቁመን ልንጥላቸው ይገባል፤››
    • . ‹‹ወላጅ በሌላቸው ሕፃናት ስም የገንዘብ እና አልባሳት ርዳታን ከሙሉ ወንጌል አማኞች ማኅበር በመቀበል እና የቤት ለቤት ማጥመቅ ተግባራትን በመፈጸም እንቅስቃሴውን ማጠናከር፤››

    (ደጀ ሰላም፤ ጁላይ 30/2010)፦ ራሳቸውን ‹‹የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት ሕጋዊ ወኪል›› በማለት በይፋ የሚጠሩት እና የሰፋሪ ገነት አቃቂ ደብረ ቁስቋም ቅድስት ማርያም እና ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪ ሊቀ ካህናት ጌታቸው ዶኒ፣ ቤተ ክርስቲያንን ‹‹በተሐድሶአውያን ኅብረት›› ለማጥመቅ በሚል ያቀዱበት፣ ለዚህም እንቅስቃሴያቸው ማጠናከርያ የአቡነ ጳውሎስን ሐውልት በአጥቢያቸው ከማሠራት ጀምሮ ሌሎች የገንዘብ
    ማሰባሰቢያ ስልቶችን የነደፉበት እና ይህንኑ ውጥናቸውንም በመንበረ ፓትርያሪክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት የሰንበት ት/ቤቶች ማ/መ ሐላፊ ከሆኑት ከአባ ሠረቀ ብርሃን ወልደ ሳሙኤል ጋራ በሐሳብ የተስማሙበት እና የመከሩበት መሆኑን የሚገልጽ በእጃቸው የተጻፈ ደብዳቤ ለደጀ ሰላም ደርሶ ተመልክተነዋል፡፡
    በቀን 05/02/2002 ዓ.ም እንደ ተጻፈ የተመለከተበት ይኸው ደብዳቤ የሊቀ ካህናት ጌታቸው ዶኒ የግል ማኅተም እና ፊርማ ያረፈበት ነው፡፡ የደብዳቤውን ሙሉ ቃል ዳግመኛ ታይፕ በማድረግ ከእጅ ጽሑፉ ጋራ አባሪ በማድረግ ያቀረብንላችኹ ሲኾን በይዘቱ ላይ የተመሠረተ ዝርዝር ሐተታ በቀጣዮቹ ቀናት የምናስነብብ መኾኑን እንገልጻለን፡፡
                                                         ቀን፡- 05/03/2002

    ለአባ ሠረቀ ብርሃን
    ለሰንበት ት/ቤቶች መምሪያ ሐላፊ፤

           የማክበር ሰላምታዬን እያቀረብኹ፣ እንደሚታወቀው ባለፈው በተነጋገርነው መሠረት ጉዳዩን እየሄድኩበት እገኛለሁ፡፡
    እንደሚታወቀው አንዳንድ የአቡነ ሳሙኤል ደጋፊዎች የግል ማኅደሬን ለማበላሸት የፓትርያሪኩን ሕጋዊ ወኪልነቴን ለመሻር ደብዳቤ ጽፈውብኝ ነበር፡፡ ነገር ግን ይህን ሐሳባቸውን አክሽፌባቸዋለሁ፡፡ በመሆኑም አቡነ ይስሐቅ እንድነሣ ሊያደርጉኝ ቢያስቡም በአቡነ ገሪማ ጸሐፊነት ደብዳቤው እንዲመለስልኝ ተደርጓል፡፡ ምክንያቱም ጋዜጣ ላይ የጻፍኹት ራሴን ለማስተዋወቅ አይደለም፡፡ የፀረ ሰላም ኀይሎችን ምስጢር ነው ያወጣሁት፡፡ አባ ሠረቀ ብርሃን በእርስዎ በኩል ይጠበቅብዎታል፣ ምክንያቱም በርካታ ሰንበት ት/ቤቶችን በመምሪያው ሥር ማግኘት ስለምትችሉ፣ ቤተ ክርስቲያንን በወጣት ኀይል ነውና ማደስ የሚቻለው ጠንክረን መሥራት እንችላለን፡፡
    እኛ ሣራ የወለደችን በመሆኑ እናታችንን ከኋላ ቀር አሠራር እና ባህል አላቀን፣ ወጣቱን በተሐድሶአውያን ኅብረት አዲስ ጥምቀት በማድረግ ‹‹ቅን ልቦና የመንፈሳዊ የፈውስ አገልግሎት›› ሥር ልንሰበስባቸው እንችላለን፡፡
    የካናቴራ አልባሳት ማሠርያ ለማሠራት በጎ ፈቃደኞችን እየጠቆሙኝ ነው፡፡ ስለዚህ እኔም የማጥመቅ ሥራ በየቤቱ እየዞርኹኝ እያጠናከርኩኝ ነው፡፡ እርስዎም ይህን መንገድ በተሻለ መንገድ አጠናክረው ሊቀጥሉበት ይገባል፤ ስለ ገንዘቡ ሊጨነቁ አይገባም፡፡ 170 ሺሕ የሚያወጣ ሐውልት በእኛ ደብር ስለምናሠራ ከዚያ ላይ በሚገኘው ገንዘብ ልናጠናክረው እንችላለን፡፡ በዙሪያው ያሉ የአቡነ ሳሙኤል ደጋፊዎች ይህን ሐሳባችንን ሊያደናቅፉ ቢችሉ እንኳን ተቋቁመን ልንጥላቸው ይገባል፡፡

    በመጨረሻም የሙሉ ወንጌል አማኞች ወላጅ ለሌላቸው ሕፃናት የገንዘብ እና የልብስ ድጋፍ ስለሚያደርጉልን ሕፃናትን መመዝገብ አለብን፡፡ በዚህ እኔ ባለሁበት ደብር አባ ገብረ ሥላሴ የተባሉት በስማቸው የመሠረቱት የሕፃናት ማሳደጊያ በርካታ ልጆች ስላሉ፣ በዚህ ማሳደጊያ ስም ልናገኝ እንችላለን፡፡ ስለዚህ በገንዘቡ በኩል በእንዲህ ዐይነት ኹኔታ ላይ ስለሆንን እርስዎ ወጣቱን በማነሣሣት ትልቅ ሥራ ሊሠሩ ይገባል፡፡ በተረፈ አዳዲስ ነገር ሲኖር በስልክ በመደዋወል እንጨርሰዋለን፡፡
                                           
     ‹‹ከመንፈሳዊ ሰላምታ ጋር››
                                             ሊቀ ካህናት ጌታቸው ዶኒ
                                       የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን መንበረ ፓትርያርክ ሕጋዊ   ወኪል               



    የቅዱስነታቸውን ሐውልት በማቆም የቅድስት ማርያም ስብከተ ወንጌል ማኅበር ከፍ ያለ አስተዋፅኦ አድርጓል›› (ብፁዕ አቡነ ፋኑኤል)

    Friday, July 30th, 2010
    •  ፓትርያርኩ ቁልቢ አልሄዱም፣

    (ደጀ ሰላም፤ ጁላይ 29/2010)፦ የብፁዕ ወቅዱስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ አቡነ ጳውሎስን 18ኛ ዓመት በዓለ ሢመት ‹‹በልዩ ሁኔታ ለማክበር›› በሚል በተቋቋመው የበዓል አከባበር ኮሚቴ፣ ከ300‚000 ብር በላይ ወጪ በማድረግ በቦሌ ደብረ ሳሌም መድኃኔ ዓለም ቤተ ክርስቲያን ደጃፍ ዐጸድ ውስጥ የቆመውን እና ሐምሌ አራት ቀን 2002 ዓ.ም ፓትርያሪኩ እና ዐሥራ አንድ ብፁዓን አባቶች (ብፁዕ አቡነ ገሪማ፣ ብፁዕ አቡነ አረጋዊ፣ ብፁዕ አቡነ ኤፍሬም፣ ብፁዕ አቡነ ኤርሚያስ፣ ብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ፣ ብፁዕ አቡነ ያሬድ፣ ብፁዕ አቡነ ዳንኤል፣ ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ፣ ብፁዕ አቡነ ስምዖን፣ ብፁዕ አቡነ ኢሳይያስ፣ ብፁዕ አቡነ ፋኑኤል) በተገኙበት የተገለጠውን የፓትርያርኩን የ‹ምስክርነት ሐውልት› ለማሠራት ‹‹የቅድስት ማርያም ስብከተ ወንጌል ማስፋፊያ ማኅበር››  ‹‹ከፍ ያለ አስተዋፅኦ ያደረገ የቤተ ክርስቲያን ማኅበር›› መሆኑን ብፁዕ አቡነ ፋኑኤል ተናገሩ፡፡

    አቡነ ፋኑኤል ይህን የተናገሩት ሐምሌ 19 ቀን 2002 ዓ.ም ፓትርያርክ አቡነ ጳውሎስ አለወትሯቸው በተገኙበት በአዋሳ ደብረ ምሕረት ቅዱስ ገብርኤል ገዳም በተከበረው የቅዱስ ገብርኤል ዓመታዊ ክብረ በዓል ላይ ነው፡፡ ‹‹ማኅበሩ በቅዱስነታቸው ዕውቅና የተሰጠው የእነ በጋሻው ማኅበር ነው፤››  ያሉት አቡነ ፋኑኤል ማኅበሩ በፓትርያርኩ ሐውልት ሥራ እና ተከላ ላይ ግንባር ቀደም አስተዋፅኦ ማድረጉን ግልጽ አድርገዋል፡፡ አቡኑ ከጥቂት ጊዜያት ወዲህ ስለነበጋሻው ቡድን የሚያሰሙትን የድፍረት መወድስ እና የምእመናኑን ሚና የሚያናንቅ አሰልቺ ንግግራቸውን የተከታተሉ በበዓሉ ላይ የተገኙ የደጀ ሰላም ምንጮች ኹኔታውን ‹‹የዐዋጁን በጆሮ›› ብለውታል፡፡

    ከ‹ምስክርነት› ሐውልቱ መገለጥ በኋላ የሚወጡ መረጃዎች እንደሚጠቁሙት፣ የሐውልቱን ሐሳብ የማመንጨት ቅድምናው የማፊያው ቡድን ‹‹ስውሩ ጸሐፊ›› ዘሪሁን ሙላቱ ሲኾን ምክንያቱ ደግሞ የዲያቆን በጋሻው ደሳለኝ ውትወታ መኾኑ እየተነገረ ነው፡፡ ይኸውም ዲያቆን በጋሻው እውነተኛ ማንነቱ በተለያዩ ቀናዒያን ምእመናን ከተጋለጠ፣ በጠቅላይ ቤተ ክህነቱ የስብከተ ወንጌል እና ሐዋርያዊ ተልእኮ መምሪያ እና በዋና ሥራ አስኪያጁ በወጣ ደብዳቤ ከታገደ እንዲሁም ‹መጋቤ ሐዲስ› በተሰኘው ያልተገባ ሹመቱ ሳቢያ በፓትርያርኩ ሳይቀር በጉባኤ ከተገሠጸ በኋላ የገጠመውን ክስረት በአቋራጭ ለመቀልበስ የቀድሞ ባላጋራውን ምንደኛውን ዘሪሁን ሙላቱን ‹‹ከጉድ አውጣኝ›› ይለዋል፡፡ ጥቅም ላሳዩት ሁሉ(ለመሐመዳውያን ሳይቀር) የጥፋት ብዕሩን ከመምዘዝ፣ ፓትርያርኩን እና ብፁዓን አባቶችን የሚያዋርድ ተግባር ከመፈጸም ወደ ኋላ የማይለው ይኸው ቅጥረኛ ግለሰብም ቀን እንዲሰጠው ጠይቆ ሲያስብበት ይቆያል፡፡ በመጨረሻም ዲያቆን በጋሻው የፓትርያርኩን አፍቃሬ ርእስ(መወድስ) የመኾን ከልክ ያለፈ ፈቲው ተጠቅሞ ‹ከጎጉል ጎልጉዬ አገኘኹት› ያለውን የሐውልት ሥራ ዐይነቶች በመዘርዘር ለአቡነ ጳውሎስ ‹የምስክርነት› ሐውልት እንዲሠራላቸው ሐሳብ እንዲያቀርብ፣ ለአፈጻጸሙም ራሱ ዘሪሁን ከሊቀ ካህናት ጌታቸው ዶኒ ጋራ፣ ዲያቆን በጋሻው ደግሞ ከወ/ሮ እጅጋየሁ ጋራ ተመካክረው ለማስወሰን ይስማማሉ፡፡

    የፓትርያርኩን 18ኛ ዓመት በዓለ ሢመት ‹‹በልዩ ኹኔታ እናከብራለን፤›› በሚል ሽር ጉድ ሲሉ የነበሩት፣ በተለይም ቀደም ብሎ በወንጀል ከሚፈለጉበት የሕግ ተጠያቂነት ተሰውረው የቆዩት ሊቀ ካህናት ጌታቸው ዶኒም በሚያስተዳድሯት ቁጥጥር የሌለባት አጥቢያ ቅጽር ውስጥ የአቡነ ጳውሎስን ምስል በ170‚000 ብር (እርሳቸው 400‚000 ብር ነው ያወጣኹት ብለው ሪፖርት ቢያቀርቡም) አሠርተው በማስመረቅ መሥዋዕተ እርያ የማቅረብ ‹ልምድ› ያገኙ በመኾናቸው የፓትርያርኩን ሐውልት እስከ በዓለ ሢመቱ መዳረሻ ቀን ድረስ ሰውረው በድብቅ በማሠራት እና በዋዜማው በመግለጥ ከተጠያቂነት ለመሸሽ ተጠቅመውበታል፡፡

    ዲያቆን በጋሻውም በተጋለጠው እውነተኛ ማንነቱ የተነሣ የደረሰበትን ክስረት ለመሸፈን፣ በአበው ጳጳሳት ጉባኤ ፊት ኦርቶዶክሳዊነትን በመፃረር ሲፈጽማቸው ለቆዩት ድርጊቶቹ ገሥጸው፣ ‹መጋቤ ሐዲስ› የተባለበትን ቀድሞም በአቡነ ፋኑኤል አለግባብ የተሰጠውን ማዕርግ ገፍፈው ‹አቶ› አሰኝተው ባስለቀሱት እና ባዋረዱት አቡነ ጳውሎስ ፊት ‹ሞገስ› ለማግኘት፣ ስለ ድካሙ ‹‹ፍሬም›› በበዓለ ሢመታቸው የራት ግብዣ ምሽት በበዓል አከባበር ኮሚቴ መዘጋጀቱ የተገለጸለትን የምስክር ወረቀት ከግብር አበሮቹ ጋራ መቀበሉ ይታወሳል፡፡

    በተያያዘ ዜና በርእሰ አድባራት ቁሉቢ ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን በየዓመቱ እየተገኙ በዓሉን የሚያከብሩት ፓትርያሪኩ የዚህን ዓመት የቅዱስ ገብርኤል በዓል ለማክበር ያመሩት ግን ወደ አዋሳ ደብረ ምሕረት ቅዱስ ገብርኤል ገዳም ነበር፡፡ ቅዱስነታቸው በጉዟቸው ሻሸመኔን አልፈው ልዩ ስሙ ጥቁር ውኃ  እየተባለ በሚታወቀው የአዋሳ ከተማ መግቢያ ላይ ሲደርሱ በእነ ሊቀ ካህናት ጌታቸው ዶኒ፣ ወ/ሮ እጅጋየሁ በየነ እና በተለይም የማፊያው ቡድን ተባባሪ በመኾን የሀገረ ስብከቱን የስብከተ ወንጌል እንቅስቃሴ በተሐድሷዊ ስልት ለመቆጣጠር እና የግለሰቦችን ኪስ ለማደለብ በሚሠራው ‹‹ማኅበረ ተስፋ ኪዳነ ምሕረት›› እየተባለ በሚጠራው አካል ተቀስቅሰው የተሰለፉ ወጣቶች ከሌላው ጊዜ በበለጠ በአቡነ ጳውሎስ ዘመነ ፕትርክና የተለየ ሥራ መሠራቱን የሚያወሱ መፈክሮችን በማንገብ ተቀብለዋቸዋል፡፡ ሐምሌ አራት ቀን በቦሌ ደብረ ሳሌም መድኃኔ ዓለም ቤተ ክርስቲያን በተከናወነው የፓትርያርኩ ‹የምስክርነት ሐውልት› መገለጥ ወቅት ራሱን ‹‹የቅድስት ማርያም ስብከተ ወንጌል ማስፋፊያ ማኅበር›› እያለ የሚጠራው የእነ በጋሻው  ቡድን ባዘጋጀው መድረክ ላይ ወ/ሮ እጅጋየሁ በየነ ባቀረቡት የበዓል አከባበር ኮሚቴ ‹ሪፖርት› ተመሳሳይ ሐሳቦችን ያዘሉ የቅስቀሳ ንግግሮችን በማሰማት ፓትርያርኩን ለጉባኤ ወደ አዋሳ መጋበዛቸው ይታወሳል፡፡

    በማግሥቱ በገዳሙ በተከናወነው ሥነ በዓል ላይ ‹‹ማኅበረ ተስፋ ኪዳነ ምሕረት›› ለፓትርያርኩ የወላይታን ባህላዊ ቡሉኮ አልብሷል፡፡ ስለ ተደረገላቸው ስጦታ ምስጋና ያቀረቡት አቡነ ጳውሎስ፣ ‹‹እኛ የእንጀራ ልጅ የለንም፤ ሁላችኹም ታስፈልጉናላችኹ፤. . . ሁሉም ማኅበራት ለቤተ ክርስቲያን ይጠቅማሉ፤ የማይጠቅም የለም፡›› በማለት ለአክብሮ በዓል የተሰበሰበውን ምእመን ግራ ያጋባ ንግግር አሰምተዋል፡፡ የፓትርያርኩን አነጋገር የተከታተሉ በርካታ ምእመናን፣ ‹‹እኛ እዚህ የተገኘነው ከመልአኩ በረከት ለመካፈል እንጂ እርሳቸውን እና አጋፋሪዎቻቸውን ብለን አይደለም፤ ለምንድን ነው በዓሉን የተመለከተ ትምህርተ ወንጌል የማይሰጡት?›› በማለት በኀዘን ሲናገሩ ተደምጠዋል፡፡ ከዚህ በተፃራሪ በዐውደ ምሕረቱ በፓትርያርኩ ዙሪያ የተኮለኮሉ የ‹‹ማኅበረ ተስፋ ኪዳነ ምሕረት›› ጥቂት ወጣቶች ፓትርያሪኩ በተናገሩ ቁጥጥር በኾነው ባልኾነው ቅጥ ያጣ ጭብጨባ ያሰሙ እንደ ነበር ተመልክቷል፡፡

    ከዚሁ ጋር በተያያዘ ሌላ ዜና የአዋሳ ደብረ ምሕረት ቅዱስ ገብርኤል ገዳም ቤተ ክርስቲያን ሰንበት ትምህርት ቤት፣ ሐምሌ 17 ቀን 2002 ዓ.ም፣ ‹‹የሰበካ ጉባኤውን ቃለ ዐዋዲ በመፃረር በጠቅላላ ጉባኤ የተመረጡ የሰንበት ት/ቤቱን አመራሮች ለማገድ እና ሰንበት ት/ቤቱን አላግባብ ለመቆጣጠር በማሰብ የሰንበት ት/ቤቱን ቁልፍ በመሥበር በሌላ ቁልፍ ቀይረዋል፤›› ባላቸው ሦስት ግለሰቦች ላይ ክስ መሠረተ፡፡፡-

    1) በኩረ ትጉሃን ዓለምነህ ሽጉጤ – የሲዳማ ሀገረ ስብከት የመጽሐፍ ቅዱስ ማኅበር አስተባባሪ፣ ‹‹ማኅበረ ተስፋ ኪዳነ ምሕረት›› እያለ በሚጠራው ማኅበር ውስጥ የሚንቀሳቀሱ፣

    2) መጋቤ ሐዲስ ፍሥሓ ለማ – የሲዳማ ሀገረ ስብከት ሰንበት ት/ቤቶች ማ/መ ሐላፊ እንዲሁም በልማት እና ክርስቲያናዊ ተራድኦ  ኮሚሽን የሀገረ ስብከቱ ፀረ-ኤች.አይ.ቪ/ኤድስ መከላከያ እና መቆጣጠርያ አስተባባሪ፣

    3) ላእከ ወንጌል ያሬድ አደመ – የፓትርያርኩን ሐውልት አወራው ‹‹የቅድስት ማርያም ስብከተ ወንጌል ማስፋፊያ ማኅበር››  አባል ናቸው።



    ሐምሌ 22፦ የሰማዕቱ የብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ እና የታላቁ ሐዋርያ የብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ ዕለተ እረፍት

    Thursday, July 29th, 2010




    በአዋሳ የምእመኑ ተቃውሞ፣ የፓትርያርኩ ምላሽ እና የብፁዕ አቡነ ፋኑኤል ማስፈራሪያ

    Thursday, July 29th, 2010

    (ደጀ ሰላም፤ ጁላይ 29/2010):- የቅዱስ ሲኖዶስን ውሳኔ ለማስፈጸም እነበጋሻውንና ቡድኑን እንዳያስተምሩ የከለከሉት የአዋሳ ቅ/ገብርኤል የቀድሞ አስተዳዳሪ በፓትርያርኩ ቀጥተኛ ጣልቃ ገብነት ከቦታቸው ከተነሱ ጀምሮ ምእመኑ ይህንኑ በመቃወም የተለያዩ እርምጃዎች ወስዷል። የገዳሙ አስተዳዳሪ መልአከ ምሕረት አባ ገብረ ዋሕድ ወልደ ሳሙኤል ወደ ቦታቸው እንዲመለሱ ለሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ፋኑኤል ያቀረቡት ጥያቄ ተቀባይነት ባለማግኘቱ ወደ መንበረ ፓትርያርክ  ጠቅላይ ቤተ ክህነት በመምጣት ጉዳዩን ለጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ዋና ሥራ አስኪያጅ ብፁዕ አቡነ ፊልጶስ አመልክተው ነበር፡፡ የምእመናኑን ማመልከቻ የተቀበሉት ብፁዕነታቸው ምእመናኑን በማስከተል ወደ ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ ዘንድ ቀርበው ጉዳዩን ለማስረዳት ጥረት ቢያደርጉም ምእመናኑ ከሥፍራው በማይጠበቅ መንፈሳዊነት የጎደለው አኳኋን በመገፋታቸው እና በጎ ምላሽ በማጣታቸው አዲሱን የገዳሙን አስተዳዳሪ የአባ ኀይለ ጊዮርጊስን ሹመት እንደማይቀበሉት በመግለጽ፣ ያለምንም ውጤት በከፍተኛ ኀዘን ተውጠው ወደ ሀገረ ስብከታቸው ለመመለስ ተገደዋል፡፡

    የቀድሞው የገዳሙ አስተዳዳሪ ከፍተኛ የልማት ተግባራትን ያከናወኑ በመኾናቸው ከቦታቸው ያለአግባብ መነሣት እንደሌለባቸው እንዲሁም ከቦታቸው ከተነሡ በኋላ ያለምንም አገልግሎት እየደረሰባቸው ያለውን እንግልት በመቃወም ለፓትርያርኩ ባቀረቡት ጥያቄ በጎ ምላሽ ያላገኙት ተወካዮቹ፣ የበርካታ ምእመናንን ፊርማ በማሰባሰብ ሐምሌ አራት ቀን 2002 ዓ.ም ለጠቅላይ ሚኒስትሩ እና ለሌሎች ከፍተኛ የመንግሥት ባለሥልጣናት ባለስምንት ገጽ ደብዳቤ ጽፈዋል፡፡ በዚህ ጥያቄቸው መሠረት በፌዴራል ጉዳዮች ሚኒስቴር የሃይማኖት ጉዳዮች ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር የኾኑት አቶ መረሳ ረዳ ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያሪኩን ማነጋገራቸው ተመልክቷል፡፡
    ሐምሌ 19 ቀን 2002 ዓ.ም በአዋሳ በተከበረው የቅዱስ ገብርኤል በዓል ላይ ከዋዜማው ጀምሮ የተገኙት ፓትርያርኩ ለዚህ የምእመናኑ ጠንካራ ግፊት ምላሽ እንደ ኾነ በተገመተው ንግግራቸው፣ ‹‹አዋሳ ብሔር ብሔረሰቦች ተቻችለው የሚኖሩበት ከተማ ነው፤ መቻቻል ያስፈልጋል፤. . . በራችን ለውይይት ክፍት ነው፤ መክሰስ መከሰስ ለማንም አይጠቅምም፤ የቤተ ክርስቲያን ጉዳይ የሚፈታው በራሳችን እንጂ ሌላ ማንም ሊፈታው አይችልም፤ ላይ ታች ማለት ተገቢ አይደለም፤›› በማለት ኀይለ ቃል አዘል ማሳሰቢያ መስጠታቸውን በበዓሉ ላይ የተገኙ ደጀ ሰላማውያን ተናግረዋል፡፡ ከዚህ ቀደም ሲል የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ፋኑኤል ሐምሌ ሰባት ቀን በተከበረው የቅድስት ሥላሴ በዓል በአዋሳ ቅድስት ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን በመገኘት ባሰሙት ተግሣጽ አዘል ንግግር፣ ‹‹የአጥቢያ አስተዳዳሪዎች ለተቀመጡበት ቦታ ብቁ ኾነው ሳይገኙ ሲቀሩ እነርሱን መሻር፣ ማዘዋወር እና በምትካቸው ሌላ መሾም የሀገረ ስብከቱ ብቸኛ ሥልጣን ነው፤ ምእመናን በዚህ ውስጥ ድርሻ የላችሁም፤ በቃ፣ ለእኔ ተመችቶኛል፤ የሾምኩላችኹን ተቀብላችኹ መኖር ነው፤›› ሲሉ ተደምጠዋል።
    በሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ እና በሥራ አስኪያጁ መካከል በቤተ ክርስቲያንን ንብረት እና ሀብት ላይ የተመሠረተ ከፍ ያለ የጥቅም ትስስር መኖሩን የሚናገሩት አንዳንድ ምእመናን ጉዳዩ ሊጋለጥ እንደሚገባው አሳስበዋል፡፡
    ውዝግቡ ያሳሰበው የክልሉ ጸጥታ ቢሮ፣ ‹‹ችግሩ ማን ጋራ እንዳለ ተረድተነዋል፡፡ ጉዳዩ የጸጥታ ጉዳይ ነው፤ ሰዎቹ ይኹነን ብለው ችግር ለመፍጠር የሚፈልጉ ናቸው፤. . . ፓትርያሪኩ ለውይይት በራችን ክፍት ነው ካሉ መንገድ መዝጋት አያስፈልግም፤ ውይይቱ ውጤት የማያመጣ ከኾነ ግን ጣልቃ ለመግባት እንገደዳለን፤›› በማለቱ የምእመናኑ ተወካዮች በዛሬው ዕለት ጠዋት ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩን ለማነጋገር ቀጠሮ በተያዘላቸው መሠረት ማነጋገራቸውን እነዚሁ ደጀ ሰላማውያን ጨምረው ገልጸዋል፡፡

    ይህ በእንዲህ እንዳለ የሲዳማ ሀገረ ስብከት ሥራ አስኪያጅ መልአከ ሕይወት ፀሐይ መልአኩ ትናንትና ሐምሌ 21 ቀን 2002 ዓ.ም ከስም ማጥፋት እና ‹‹ለአዋሳ ከተማ ጸጥታ ስጋት ኾነዋል፤›› በሚል በፖሊስ ቁጥጥር ሥር ውለው ማምሻውን መፈታታቸውን  የደጀ ሰላም ምንጮች አመለከቱ፡፡ የእስራቸው ምክንያት በሀገረ ስብከቱ የሚገኘው የአዋሳ ደብረ ምሕረት ቅዱስ ገብርኤል ገዳም አስተዳዳሪን ያለአግባብ መነሣት እና በሕገ ወጥ ሰባክያን የሚካሄዱ ጉባኤያትን በመቃወም ለብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ  አቡነ ጳውሎስ አቤቱታ ያቀረቡትን ቁጥራቸው 39 የሚደርሱ ምእመናንን፣ ‹‹አሸባሪዎች እና ፀረ ሰላም ኀይሎች ናቸው፤›› ብለው በመወንጀላቸው መኾኑ ታውቋል፡፡
    በሥራ አስኪያጁ ስማቸው ተጠቅሶ ለፌዴራል ጉዳዮች ሚኒስቴር እና ለክልሉ ፖሊስ ውንጀላ የቀረበባቸው ሠላሳ ዘጠኙ ምእመናን ታዋቂ ግለሰቦች፣ የአገር ሽማግሌዎች እና ባለሀብቶች ናቸው፡፡ በሀገረ ስብከቱ በተለያዩ የልማት ሥራዎች እየተሳተፉ የሚገኙ ከመኾናቸውም በላይ፣ የሐዋሳ ቅዱስ ገብርኤልን፣ በዓለ ወልድን፣ ኪዳነ ምሕረትን፣ ቅዱስ ሩፋኤልን እና የቅዱስ ጊዮርጊስ አብያተ ክርስቲያናትን በማነፅ ከፍተኛ አስተዋፅኦ ማበርከታቸውን የደጀ ሰላም ምንጮች ይናገራሉ፡፡



    አባቶችን የማደራደሩ ውይይት ይጀመራል

    Wednesday, July 28th, 2010

    (ደጀ ሰላም፤ ጁላይ 28/2010)፦ ከአምስተኛው ፓትርያርክ ከብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ሲመት ማግስት ጀምሮ በቤተ ክርስቲያኒቱ የተነሣውን መከፋፈል ለማቆምና በአባቶች መካከልም የተፈጠረውን እስከ መወጋገዝ የሚያደርስ ልዩነት በእርቅ ለመጨረስ በተጀመረው እንቅስቃሴ ቅ/ሲኖዶስን ወክለው የሚወያዩት ልዑካን ከዚህ በፊት የዘገብናቸው ብፁዕ አቡነ በርተሎሜዎስ፣ ብፁዕ አቡነ ቀውስጦስ፣ ብፁዕ አቡነ ናትናኤል፣  ብፁዕ አቡነ አትናቴዎስና ብፁዕ አቡነ ኤልሳዕ ሳይሆኑ ከሐምሌ ስድስቱ የቅ/ሲኖዶስ ጉባዔ ማግስት ስማቸው በየጋዜጣው የተጠቀሰው ብፁዕ አቡነ ገሪማ፣ ብፁዕ አቡነ አትናቴዎስ፣  ንቡረ ዕድ ኤልያስ አብርሃ እና መጋቤ ብሉይ ሰይፈ ሥላሴ ዮሐንስ ናቸው። የአሜሪካን አባቶችን ወክለው ደግሞ ብፁዕ አቡነ መልከ ጼዴቅ፣ ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ እና ብፁዕ አቡነ ኤልያስ ይደራደራሉ ተብሏል።



    ብፁዕ አቡነ ቄርሎስ ወደ ሀገር ቤት ተመለሱ

    Tuesday, July 27th, 2010

    (ደጀ ሰላም፤ ጁላይ 27/2010)፦ በጀርመን ሀገር ሕክምና ሲከታተሉ የነበሩት ብፁዕ አቡነ ቄርሎስ ሕክምናቸውን ፈጽመው ወደ ሀገር ቤት ተመለሱ።

     ብፁዕነታቸው ለሚያሰቃያቸው የጀርባ ሕመም መፍትሔ ለማግኘት ቀደም ብሎ በግሪክ ከዚያም ደግሞ በጀርመን ሲታከሙ ቆይተው ባለፈው ሐሙስ ወደ ኢትዮጵያ ለመመለስ በቅተዋል። ብፁዕነታቸው አሁን በተሻለ ጤንነት ላይ የሚገኙ ሲሆን ምርኩዛቸውን ተደግፈው ለመንቀሳቀስም ችለዋል።

    የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን በአሁኑ ወቅት ካሏት በሐዋርያነታቸው ከሚሰከርላቸው ደጋግ ሊቃነ ጳጳሳት መካከል አረጋዊ አባት የሆኑት ብፁዕ አቡነ ቄርሎስ በግሪክ እና በጀርመን የሚገኙ ክርስቲያኖች ባደረጉላቸው ርዳታ ከጥሩ ጤንነት ላይ ለመድረስ ችለዋል።

    እንደሚታወቀው በቤተ ክህነታችን የሕክምናም ሆነ የጤና ኢንሹራንስ ስለሌለ አባቶች (በተለይም ከቅርብ ዓመታት ወዲህ) በሚያሳዝን መልኩ እያለቁ ነው። ለምሳሌ በቅርብ ጊዜ ያረፉትን አቡነ መልከ ጼዴቅን ማንሳት ይቻላል።

    ብፁዕነታቸውን ሳይታክቱ  ያገለገሉት ክርስቲያኖች የእግዚአብሔር ሰው ስለሆኑ ከብፁዕነታቸው ትልቅ በረከት እና ረድኤት እንደሚያገኙ ብታውቅም “ደጀ ሰላም” በግሪክ እና በጀርመን ያሉትን ክርስቲያኖች በሙሉ ከልብ ታመሰግናቸዋለች።

    ይህንን  ፎቶግራፍ  የላኩልንንም ከልብ እናመሰግናለን።
    ቸር ወሬ ያሰማን፣
    አሜን



    የአራቱ ጉባኤያት ሊቅ ዐረፉ

    Sunday, July 25th, 2010

    (ማኅበረ ቅዱሳን):- የአራቱ ጉባኤያት አብነት መልአከ ገነት ገብረ ሥላሴ አወቀ በተወለዱ በአንድ መቶ ሁለት ዓመታቸው ግንቦት 28 ቀን 2002 ዓ.ም ለ29 አጥቢያ ከዚህ ዓለም በሞተ ሥጋ ተለይተዋል፡፡ ሥርዓተ ቀብራቸውም በትውልድ ሀገራቸው ባሠሩት ቤተክርስቲያን ተፈጽሟል፡፡

    መልአከ ገነት ገብረ ሥላሴ እንዳረፉ አስከሬናቸው ወደ ሰዋስወ ብርሃን ቅዱስ ጳውሎስ ቤተክርስቲያን ተወስዶ ጸሎተ ቅዳሴ ከተደረገበት በኋላ በትምህርት ቤቱ የስብከተ ወንጌል አዳራሽ ሙሉ ጸሎተ ፍትሐትና አደራረስ ሲደረግበት ውሏል፡፡
    አስከሬናቸው ጉባኤ ዘርግተው ያስተምሩበት ከነበረው ሰዋስወ ብርሃን ቅዱስ ጳውሎስ መንፈሳዊ ኮሌጅ በዓታቸው ወደ መንበረ ጸባኦት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ተወስዷል፡፡

    በካቴድራሉም ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት የዓለም አብያተ ክርስቲያናት ምክር ቤት ፕሬዚዳንትና የዓለም ሃይማኖቶች ለሰላም የክብር ፕሬዚዳንት፤ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፣ የአዲስ አበባ አድባራት አስተዳዳሪዎችና የገዳማት አበ ምኔቶች፣ የጠቅላይ ቤተ ክህነት ሹማምንትና የየመምሪያው ሓላፊዎች በተገኙበት ጸሎተ ፍትሐት ተደርጎላቸዋል፡፡

    በዚህም ወቅት የሕይወት ታሪካቸው ከተነበበ በኋላ ቅዱስነታቸው ባስተላለፉት ቃለ በረከተ፤ «በሊቁ በመምህር ገብረ ሥላሴ ሞት ቅድስት ቤተክርስቲያን ከፍተኛ ሐዘንና ጉዳት የደረሰባት መሆኑን ጠቅሰው፤ ይሁን እንጂ እንደ ሊቁ መምህር ገብረሥላሴ ያሉት የትምህርት አብነቶች አያሌ ተተኪ መምህራንንና ደቀመዛሙርትን በማፍራት ራሳቸውን ተክተው ያለፉ በመሆናቸው እንደሞቱ አይቆጠርም፡፡ ቸር አምላክ በቸርነቱ ለኒህ ታላቅ ሊቅ ለነፍሳቸው ዕረፍት መንግሥተ ሰማያትን እንዲሰጥና ለቤተክርስቲያናችን እንደሳቸው ያለ ሊቅ እንዲተካ እንጸልያለን በማለት ጸሎተ ቡራኬ አድርገዋል፡፡

    የመምህር ገብረ ሥላሴ አስከሬን ወደ ጎጃም ተወስዶ በትውልድ ሀገራቸው ራሳቸው ባሠሩት በሞጣ ደብረ መድኃኒት መድኃኔዓለም ቤተክርስቲያን ሊቃነ ጳጳሳቱ በተገኙበት ሥርዓተ ፍትሐት ተከናውኖ ሰኔ 1 ቀን 2002 ዓ.ም ሥርዓተ ቀብራቸው ተከናውኗል፡፡

    በሥርዓተ ቀብራቸው ላይ ሊቃነ ጳጳሳት የአካባቢው አድባራት አስተዳዳሪዎች፣ የገዳማት አበምኔቶች፣ በርካታ ካህናትና ሊቃውንተ ቤተክርስቲያን ተገኝተዋል፡፡

    የመምህር ገብረ ሥላሴ አጭር የሕይወት ታሪክ

    የኔታ ገብረ ሥላሴ አወቀ በቆላ ደጋ ዳሞት አውራጃ በደጋ ዳሞት ወረዳ ወይም ፈረስ ቤት ልዩ ስሙ ወገም ቅዱስ ጊዮርጊስ በተባለው ታሪካዊ ቤተክርስቲያን ጳጉሜ 3 ቀን በ1900 ዓ.ም ከአቶ ደርሰህ ወንድሁነኝና ከወ/ሮ ማዘንጊያ ገብረ ሰንበት ተወልደዋል፡፡

    ታላቁ ሊቅ የኔታ ገብረ ሥላሴ አወቀ የትውልድ ሐረጋቸው ከቤተ ሌዊ /ቤተክህነት/ የተያያዘ እንደ ነበረ ታሪካዊ አመጣጣቸው ይገልጣል፡፡ በዚህም መሠረት የኔታ ገብረ ሥላሴ አወቀ ዕድሜያቸው ለትምህርት እንደደረሰ ወደ አብነቱ ትምህርት ቤት ገብተው ድጓና ጸዋትወ ዜማ ወገም ቅዱስ ጊዮርጊስ ከመሪጌታ ገላው ደስታና ከመሪጌታ ተገኝ የቁም ዜማ ተምረዋል፡፡

    ከዚያም ጾመ ድጓ፣ ድጓ፣ ምዕራፍ ከዘለቁ በኋላ ወደ ቅኔ ቤት አምርተዋል፡፡

    የኔታ ገብረ ሥላሴ አወቀን ቅኔ ያስተማሯቸው መምህራን መምህር ገብረ ሥላሴ ዘደብረ ኤልያስ፤ መምህር ማዕበል ፈንቴ ዘዋሸራ፤ መምህር ገሠሠ ዘአቸፈር ናቸው፡፡

    በቅኔ ቤት ደግሞ አራት ዓመት ቆይተው ለአንድ ዓመት የቅኔ ዘረፋ ከተቀበሉ በኋላ ተመልሰው ወደ ድጓ ቤት ገብተዋል፡፡ ድጓን ከዘለቁ በኋላ የተክሌ አቋቋምን ተምረው በመምህርነት ተመርቀዋል፡፡ በመቀጠልም ለሦስት ዓመታት ቅኔ ቤት ቆይተው የቅኔ አገባብን በመቀጸል ወደ ጌቴ ገሞራ አዴት ሰበካ የቅኔ አገባብን ከነ እርባ ቅምሩ ለሁለት ዓመታት ተምረዋል፤ አስመርቀዋልም፡፡

    በአጠቃላይ የኔታ ገብረ ሥላሴ አወቀ በቅኔ ትምህርት ብቻ ለዐሥር ዓመታት ከደከሙ በኋላ የቅኔ ጉባኤ ዘርግተው አስተምረዋል፤ ብዙ መምህራንንም አፍርተዋል፡፡

    የኔታ ገብረ ሥላሴ መጀመሪያ ጣሊያን ኢትዮጵያን ሳይወር አዲስ አበባ መጥተው ከእነ አለቃ አየለና አለቃ ኅሩይ በደብረ ልዑል ቅዱስ ማርቆስና በታዕካ ነገሥት በአታ ለማርያም በእግር ጉዞ እየተመላለሱ መጻሕፍተ ሐዲሳቱን ዘልቀዋል፡፡

    የኔታ ገብረ ሥላሴ አወቀ በመማር ብቻ የተወሰኑ ሳይሆን እየተማሩም አስተማሪ እና አገልጋይ ነበሩ፡፡ የኔታ በዚህ ሁኔታ አዲስ አበባ ለዐሥር ዓመታት እንደቆዩ ጣሊያን በ1928 ዓ.ም ሀገሪቱን ሲወር ከአዲስ አበባ ተነሥተው መምህር አባ ጽሕማ ዘጐንድ ተክለሃይማኖት ጋር በጎሐ ጽዮን አድርገው ጉዟቸውን ቀጠሉ፤ በዚያን ጊዜ ጣሊያንን ሊወጉ በአርበኝነት የተሰለፉት አበበ አረጋይ በኋላ ራስ አበበ የዓባይን ወንዝ በዋና አሻግረዋቸው ወደ ሞጣ ቅዱስ ጊዮርጊስ ሔደዋል፡፡

    ታላቁ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ሊቅ የኔታ ገብረ ሥላሴ አወቀ የትምህርት ጥማታቸው ገና ስላልረካ ከአለቃ ጌታሁን የላይ ቤቱን መጻሕፍተ ሐዲሳት ትርጓሜ፣ ከመምህር ጽሕማ ዘጐንድ ተክለሃይማኖት ደግሞ ፍትሐ ነገሥቱን፣ ትርጓሜ ዳዊቱን፣ መጽሐፈ አስቴርን፣ መጽሐፈ ኢሳይያስን፣ መጽሐፈ ኤርምያስን አሂደዋል፡፡

    በመቀጠልም በ1933 ዓ.ም የድሮ መምህራቸው አለቃ አየለ ዓለሙ ወደ ጎንደር መመለሳቸውን ሰምተው መጻሕፍተ ብሉያቱንና መጻሕፍተ ሊቃውንቱን አጠናቅቀዋል፡፡

    የኔታ ገብረ ሥላሴ የተማሩትን ትምህርት ለማስተማር ወደ ደንበጫ ለመሔድ በዝግጅት ላይ እንዳሉ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ቴዎፍሎስ በአስቸኳይ አዲስ አበባ እንዲመጡ ላኩባቸው፡፡ እሳቸውም ጥሪውን አክብረው አዲስ አበባ እንደመጡ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ቴዎፍሎስ ከግርማዊነታቸው ዘንድ አቅርበው የሞጣ ደብረ ገነት ቅዱስ ጊዮርጊስ መልአከ ገነት ሆነው እንዲያስተምሩ ተሹመዋል፡፡

    ታላቁ ሊቅ መልአከ ገነት ገብረ ሥላሴ አወቀ የሞጣ ቅዱስ ጊዮርጊስ አስተዳዳሪ ሆነው ለ15 ዓመታት አገልግለዋል፡፡ ከዚያ በኋላ በማስተማር ብቻ ተወስነው እያሉ ብፁዕ አቡነ ተክለሃይማኖት የሰዋስወ ብርሃን ቅዱስ ጳውሎስ ከፍተኛ መንፈሳዊ ትምህርት ቤት የአራቱ ጉባኤያት መምህር ሆነው እንዲያስተምሩ በቅዱስ ሲኖዶስ አስወስነዋል፡፡

    በውሳኔውም መሠረት በ1979 ዓ.ም ከወርኃ ኅዳር እስከ ግንቦት 4 ቀን 2002 ዓ.ም ድረስ የሰዋስወ ብርሃን ቅዱስ ጳውሎስ ኮሌጅ ለ24 ዓመታት ደከመኝ ስለቸኝ ሳይሉ እስከ መጨረሻ የእስትንፋስ ሕቅታ ድረስ ቃለ እግዚአብሔር በመናገር በልማደ ሰብእ ከዚህ ዓለም በሞት ተለይተዋል፡፡



    Ethiopia: Thousands of EOC believers wave London

    Saturday, July 24th, 2010

    By NewsDire Contributor, Tamiru Geda
    (NewsDire):- Thousands of Members of the Ethiopian Orthodox Tewahedo Church, EOTC, gathered in London ,to attend and celebrate annual spiritual conference and event respectively that took place between 16 to 18, July,2010 . EOTC in Sweden are elected to host the next spiritual conference. 

    The thirteenth European EOTC gospel conference held at the Debre Genet Holy Trinity Church preached by famous and inspirational gospel preachers, who came from Ethiopia, US America, Italy, France, Sweden and the like. It is said that all participants rejoiced by the program. Fortunately, the Conference coincides with the annual festive of Kidist Selassie (Holy Trinity), the feast about the hosting of Abraham the Three people in his tent. That event believed where God expressed Himself to Abraham in Trinity: God the Father, God the Son and God the Holy Spirit.

    .

    After the mass service, the Covent (Tabbott ) was taken out side the church. It was accompanied by Priests, Deacons , Spiritual singers and Mayor of Islington Borough and by more than three thousand Ethiopians who wear traditional and colorful Clothes. .Though all roads , around the Church, were closed from traffic ,for about one hour, several drivers showed their respect to the Ethiopians .Some local residents also joined the crowed , by taking pictures ,clapping and cheering .Among them was Mouna Hamitouche, Mayor of the London Borough of Islington, who spoken her gratitude for the EOTC and its worshipers .Mouna said:” I am privileged to attend this wonderful event . I would like to congratulate you.” She requests Ethiopians to pray for her.

    In an exclusive interview with this writer and Lucy Radio, the latter is Leeds – based Ethiopian community radio ,His Grace Abune Enthons, Archbishop of ETOC in North Western Europe, appreciated the warm welcome and good relationship made by and with the host communities. He said it is vital for the church to deal its routine spiritual work, peacefully . He also urged all Ethiopian spiritual leaders to narrow their differences instead to work together . “I’m grateful to see more than three thousand Ethiopians here , celebrating our festive and listening the gospels. We should be concerned about our faith and our people as well” Abune Enthons said.
     
    Likee Teguhanne Getu, Yehuwaleshit , one of the founding members of the conference with in Europe, said if there is unity and solidarity among Ethiopians a lot could be done. ”We started the conference just with some friends .we had no written documents or paper work. We just left every thing for the Holy Spirit, to full fill our ambition .Now you could be an eye witness that how we are surrounded with thousands of EOC’s worshipers. I’m happy to be here and to see my own people who gathered here for common cause .”

    Abba Gebre Kidane Ejigu , gospel preacher from America , also impressed with the whole event and the mass. He plans to do something similar in the US ,when he returns to his church located in , Las Vegas. He said: We have large number of Ethiopian communities in different parts of America .I wish if we could organize similar conference there. “Deacon Berhanu Admassie , who came from Addis Ababa to preach . gospel also expressed his impression about the number of worshipers ,who spent more than 13 hours with him. Memihere Tebebe Selassie, one of the preachers from Debre Genet Holy Trinity Church , London based, revealed how Ethiopians are not poor in Faith ,but in Technology. He also mentioned about the role of the EOTC to intervene in tackling social and economical problems .

    Welette Maryam, from Oslo ,Norway, said she spent memorable time with her Christian friends in London and has gained important things for her soul. She also thanks for Londoners, who provided her free shelter for the past three days . It is said more than 100 members of the EOC in London made similar contribution , to host their Christian brothers and sisters , who came from different parts of Europe . The organizers thanked all worshipers for their support. Ethiopian (The New Sprit of Africa) has also got special blessed for its keen interest to offer a return ticket for any lucky Tombola’s winner that would be disclosed on August 22,2010.A six week long gospels’ program (July 19 2010 –August 22,2010 ) has already started in different parts of England namely Birmingham, New Castle Manchester, Stoke on Trent . London hosts this conference for the Second time. Five years ago, St. Virgin Mary Church organized similar spiritual conference.



    ‘ከቤተ ክርስቲያኒቱ ልጆች ለቅዱስ ሲኖዶስ አባላት" ከሚል መልእክት የተገኘ

    Friday, July 23rd, 2010

    በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን።
    ቀን 29/10/2002

    ከቤተ ክርስቲያኒቱ ልጆች  

    ለኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን
    ቅዱስ ሲኖዶስ አባላት
    አዲስ አበባ
    ብፁዓን አባቶች ሆይ፦
    ·         በቤተ ክርስቲያናችን ቅዱስ ሲኖዶስ እየተባለ የሚታወቀውና የሃይማኖታችን ሞገስ የሆነው ቅዱስ ጉባዔ አለ ወይስ ጠፍቷል?
    ·         ቤተ ክርስቲያኒቱ የአቡነ ጳውሎስ የግል ንብረት ሆናለች ወይስ የጋራችን?
    ·         በአሁኑ ጊዜ ቤተ ክርስቲያናችን ተቆርቋሪ የሌላትና የግል ማላገጫ ስትሆን ብፁዐን አባቶች እያያችሁ ታዝኑላታላችሁ ወይስ አያገባንም ብላችሁ በግድየለሽነት እየተመለከታችሁ ነው?
    የሚሉ ጥያቄዎች ስላሉን ከአባቶቻችን መልስ የምንጠብቅ መሆናችንን እየገለጽን የበኩላችንን ሐሳብ ከዚህ ቀጥሎ በመመዝገብ አቅርበናል። እናንተም ስለ ቤተ ክርስቲያናችንና ስለ እግዚአብሔር ብላችሁ እስከ መጨረሻው ድረስ በጥሞና እንድታነቡት በእግዚአብሔር ስም እንጠይቃል።
    በመጀመሪያ ደረጃ ሃይማኖታችንና ቤተ ክርስቲያናችንን እንጠብቃለን ብላችሁ በሕዝበ ከርስቲያኑና በእግዚአብሔር ፊት ቆማችሁ ቃል ገብታችሁ፤ ምላችሁ በቤተ ክርስቲያኑ ላይ የተሾማችሁ ጳጳሳት ፣ ሊቃነ ጳጳሳት፣ የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት እየተባላችሁ መኖራችሁን እኛም እናውቃለን፤ እንኮራባችኋለንም። ቅዱስ ሲኖዶስ የሚባለው ጉባዔ ግን አለ ብለን በጭራሽ አናምንም፤ ቤተ ክርስቲያኒቷም ተቆርቋሪ የሌላት መሆኗንም ሙሉ በሙሉ እየተከሰቱ ካሉ ጉዳዮች በመነሳት ማረጋገጥ ችለናል። ዝርዝር ምክንያቱንም ከዚህ ቀጥለን የመዘገብነው ስለሆነ መመልከት ይቻላል።

    ክፍል አንድ ሕገ ወጥ አሠራር
    1.      ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ከቤተ ክርስቲያኒቱ ቀኖና ውጭ በሆነ መንገድ በየቤተ ክርስቲያኑ ሥዕላቸውን እያቆሙ በመሆናቸው ወደ ቤተ ክርስቲያን ስንመጣ የምንሰግደው ለእግዚአብሔር ነው ወይስ ለአቡነ ጳውሎስ ሥዕል በማለት እየተሳቀቁና እያዘኑ የሚኖሩ የቤተ ክርስቲያናችን አባላት እጅግ ብዙ ከመሆናቸውም በላይ በተለይ በአሁኑ ጊዜ ቃልቲ አካባቢ በምትገኘው በቁስቋም ቤተ ክርስቲያን በዐውደ ምሕረት ፊት ለፊት ማለትም ታቦት ሲቆም ሊቃውነቱ ከሚያስረግጡበት አጠገብ በአደባባዩ ላይ በልዩ ብረት ታጥሮ የአቡነ ጳውሎስ ሥዕል ቆሟል። በሥዕሉ ራስ ላይ ‘ስምከ ሕያው ዘኢይመውት’ የሚልና ከሥዕሉ በታች ‘ሰማዕት ዘእንበለ ደም ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ’ የሚል ጽሑፍ አለበት። በቦሌ መድኃኔዓለም ቤተክርስቲያን ደግሞ በልዩ ሁኔታ በሲሚንቶና በአርማታ ሐውልታቸው ተሰርቶ ቆሟል። በሐውልቱ ላይ ‘ስምከ ሕያው ዘኢይመውት’ የሚለውና ‘ሰማዕት ዘእንበለ ደም’ የሚለው ቃል አለበት።
    ይህንኑ ሐውልትም የሙዚቀኛው የመሐሙድ ሚስት የነበሩት ወ/ሮ እጅጋየሁ እና ‘የመስቀሉ ስር ቁማርተኞች’ የሚለውን መጽሐፍ የጻፈው ከሌሎች ጓደኞቻቸው ጋር በመሆን እንዳሰሩት እየተነገረ ነው። በመሆኑም የአቡነ ጳውሎስ ሥዕልና ሐውልት ቀኖና ቤተ ክርስቲያናችንን በእጅጉ የሚፈታተን ከመሆኑም በላይ ወ/ሮ እጅጋየሁ የተባሉት ሴት ዘፋኝ ባላቸውን ከፈቱ በኋላ የአቡነ ጳውሎስ ጉዳይ አስፈጻሚ እንዲሆኑ የሾማቸው ማነው? ከአቡነ ጳውሎስ ጋር ያላቸው ግንኝነትስ ምንድነው? የሚሉ አጠራጣሪ ጥያቄዎችን የሚያስነሳና ስሙ ራሱ የቤተ ክርስቲያናችንን ክብር የሚነካ ስለሆነ ተገቢነት የሌለውና ቅጥ ያጣ ግኑኝነታቸው አሳፋሪ አካሄድ ነው።
    እኒሁ ወ/ሮ እጅጋየሁ ከአሁን በፊትም በ2000 ዓ.ም. የሚሊኒየሙ በዓል በሚከበርበት ጊዜ በአንገት የሚጠለቅ ወርቅ ለአቡነ ጳውሎስ የግል ሽልማት ሲሰጡ “ሰማዕት ዘእንበለ ደም”’ ብዬ ሰይሜዋለሁ ብለው የቤተ ክርስቲያኒቱን ቀኖና በመጋፋት የተናገሩ ሰው ናቸው። በመሠረቱ አንድ ቅዱስ ፓትርያርክ እንደዚህ ባለው ቅሌታዊ አካሄድ ተሰማርቶ መገኘት መረገም እንጂ የጤንነት አይመስለንም። ቤተ ክርስቲያኒቱንም የሚያሳስብ ጉዳይ ነው።

    2.    የአቡነ ጳውሎስን የግል ታሪክ በሐሰት አጉልቶ የሚያሳይ የሚያወድስ ዶክመንተሪ ፊልም በራሳቸው ተዘጋጅቶ የአዲስ አበባ ካህናት እየተገደዱ እየገዙ ናቸው።

    ከመሰረቱም ቢሆን የአቡነ ጳውሎስን ታሪክ መመስከር ያለባት ራሷ ቤተ ክርስቲያኒቱ እንጂ ራሳቸውን በራሳቸው ታላቅ መንፈሳዊ አባት አስመስለው ማቅረብ ፈጽሞ ነውር ነው። ምክንያቱም የክርስቲያኖች መንፈሳዊ ሕይወት የሚመራው ራስን ዝቅ በማድረግና በትሕትና ብቻ መሆኑን ምዕመናን ሁሉ የሚያውቁት ጉዳይ ነው።

    እኒህ ሰው ግን መጥፎው ታሪካቸውና ጉዳቸው ራሳቸው ባዘጋጁት ፊልምና በአቆሙት ሐውልት ተደብቆ (ተሸፍኖ) ካህናቱም ትክክለኛውን እና እውነተኛውን ታሪክ ሳይሆን ተገደው የገዙትን ፊልምና የቆመውን ሐውልት ውበት እየተመለከቱ ቅዱስ ናቸው እያሉ ሲያመሰግኗቸው እንዲኖሩ የተደረገ የብልጥነት ተግባር ነውና ሙሉ በሙሉ ጥፋት ነው።

    3.    በራሳቸው በአቡነ ጳውሎስ ስም የተዘጋጀው መጽሐፍም የሃይማኖታችንን አቋም የነካ ሆኖ እያለ በፁዓን አባቶች እያያችሁና እየሰማችሁ ዝም ማለታችሁ ካህናቱንም ሆነ ምዕመናኑን የሚያሳፍር ሆኗል።

    4.    ከቅዱስ ፓትርያርኩ ጀምሮ ማንኛውንም ቤተ ክርስቲያኒቱን ወክሎ ወደ ውጭ የሚላክ (የሚመጣ) የቤተ ክርስቲያኒቱ አባል ሁሉ በመጀመሪያ በቅዱስ ሲኖዶስ ሊፈቀድለት እንደሚገባ በሕገ ቤተክርስቲያን መደንገጉ ይታወቃል።

    አሁን ጳውሎስ ግን ከሕግ በላይ የሆኑ ወይም የቤተ ክርስቲያኒቱን ሕግ እርሳቸውን የማያውቃቸው ይመስል ስራዬ ሙያዬ ብለው የያዙት ወደ ተለያዩ አገሮች መሄድ፣ መምጣት፣ መዞር፣ መንከራተት፣ መዝናናት ነው። በተለይ ደቡብ አፍሪካ የናት ቤት ሆኗል።

    ለመሆኑ ግን አቡነ ጳውሎስ ደቡብ አፍሪካ ምን አስቀምጣል? ምን አላችው? በአጠቃላይ ነጋ ጠባ ደቡብ አፍሪካ የሚሉበት ምክንያት አጠያያቂ ስለሆነ ሊታሰብበት ይገባል እንላለን።

    5.    አምና የዛሬ ዓመት ብፁዓን ጳጳሳት በጸሎት ቤታቸው እንዳሉ ተደብድቧል። በዚህም ቤተ ክርስቲያናችን ራሷ ከራሷ ጋር ስትደበደብ የመጀመሪያ ጊዜዋ መሆኑ ነው። ምንም እንኳ በአቡነ ጳውሎስ ዘመነ ስልጣን ቤተ ክርስቲያናችን ለውርደት የተጋለጠች ዘመን መሆኑ በዓለም አደባባይ የታወቀ ቢሆንም በዚሁ በብፁዓን ጳጳሳት ላይ በተፈመው የድብደባ ወንጀል የሃይማኖታችን ክብርና ታሪክ ተደፍሯል። የሕዝበ ክርስቲያኑ ሞራልም ተነክቷል።
    “ይህ ጉዳይ ይጣራና ወንጀሎች ለሕግ ይቅረቡ ወደፊትም በቤተ ክርስቲያናችን እንዲህ ዓይነቱ አሳፋሪ ተግባር እንዳይታይ ይሁን”ተብሎ ሲጠየቅ አቡነ ጳውሎስና በወቅቱ ጠቅላይ ሥራ አስኪያጅ የነበሩት አቡነ ይስሐቅ ጉዳዩን አፍነው አስቀርተውታል። ከዚህ ጋር በተያያዘ ሁኔታ የሚያስገርመው ደግሞ፣ ስም መጥቀስ አያስፈልግም እንጅ፣ በዚህ ወንጀል መፈጸም ምክንያት ይደሰቱ፤ ይዘፍኑ የነበሩ ግለሰቦች እየተፈለጉ በየመምሪያውና በየቁልፍ ቦታው እንደዚሁም በየታላላቅ አድባራቱ መሐይምነታቸውን እንደተጎናጸፉ እየተሾሙ የስልጣን ባለቤቶች መሆናቸው ነው። በተለይ ዱርየና ስርዓተ አልበኛ የሆኑት ባለጌዎች በመብራት እየተፈለጉ ነው ባለስልጣናት የሆኑት፤ እንዲህ አይነቱ አሰራር ደግሞ ነውረኛነት ነው። ለቤተ ክርስቲያኒቱም ከፍተኛ ውድቀት ለመሆኑ አጠራጣሪ ነገር የለውም።

    ክፍል ሁለተ፡ ሕገ ወጥ ብዝበዛዎች
    1.    ከዚህ በላይ በተጠቀሰው በአንቀጽ 1/4/ ላይ በገለጥነው መሰረት አቡነ ጳውሎስ ወደ ውጭ አገር እሄዳለሁ እያሉ ከአንጋቻቸውና ከአጨብጫቢዎቻቸው ጋር በተመላለሱ ቁጥር ለትራንስፖርት፤ ለአበል፣ ለክብር መጠበቂያ እየተባለ የሚጨፈጨፈው የቤተ ክርስቲያናችን ገንዘብ በእጅጉ የሚያሳዝን ነው። ለቤተ ክርስቲያናችን አላችሁላት ተብሎ የሚታመንባችሁ እናንተ ብፁዓን አባቶችም ዝም ብላኋችል። ምን ይሻላል?

    2.    አቡነ ጳውሎስ በደቡብ አፍሪካና በጋምቤላ ስራ እሰራለሁ በሚል ቅዱስ ሲኖዶስ የማያውቀው የገንዘብ መበዝበዣ ዘዴ ፈጥረው ቅዱስ ሲኖዶሱም በቤተ ክርስቲያኒቱ ምንም ምን እንደማያገባውና ለቤተ ክርስቲያኒቱ ብቸኛ አሳቢ እርሳቸው ብቻ በማስመሰል አሳምነው ከአዲስ አበባ አድባራትና ገዳማት ያለ ታዛቢ ገንዘብ እየሰበሰቡ ናቸው። ይህ አሰራራቸውም “የነቃ የለም፣ ማንም አያውቅብኝም” በሚል የንቀት መንፈስ ተሞልቶ ጠያቂ በሌለበት ሁኔታ የተዘረጋ የብዝበዛ መረብ ስለሆነ አደገኛ ብልጥነት ነው።

    3.    አቡነ ጳውሎስ “ኤልሻዳይ” የሚል አዲስ ፕሮግራም ፈጥረው ከአዲስ አበባ አድባራት ገንዘብ እየበዘበዙ መሆናቸውንም ከቅዱስ ሲኖዶስ አባላት መካከል ብዙዎቻችሁ እያወቃችሁ የእግዚአብሔር ገንዘብ የጠላት ገንዘብ የሆነ ይመስል በዝምታ ማየታችሁ የሚያሳዝን ጉዳይ ነው። እርሳቸው ግን በገንዘብ ብዝበዛ በኩል ክፉኛ የተመረዙና በአጠቃላይ ከመንፈሳዊ አባትነት ባህርይ አጥብቀው የራቁ አሳፋሪ ሰው ናቸው። “ተዉ አይገባም ” የሚል ተቆርቋሪም ጠፍቷል። ሁሉም ነገር ክፉውን ተግባር ለማከናወን በሚመች መልኩ ጨለማ ሆኗል። ብቻ እግዚአብሔር ይሁነን።

    ክፍል 3 ቤተ ክርስቲያናችን የቤተሰብ ብቻ መጠቀሚያ ስለመሆኗ
    አቡነ ጳውሎስ ቤተ ክርስቲያኒቱ በሀብቷ፣ በንብረቷና በቀኖናዋ ላይ ሁሉ ከንቀት ጋር እየተጫወቱበትና እየረገጧት ከመሆናችውም በላይ ለቤተሰብ መጠቀሚያ እያደረጓት እንደሆነ በተደጋጋሚ የገለጥነውና የታወቀ ጉዳይ ቢሆንም በአሁኑ ጊዜ እየተደረገ ያለውን ብቻ ጥቂቶቹን ለመጠቆም እንሞክራለን።
    1.    የአንጋቻቸው የሙሉጌታ በቀለ ወንድም አሰፋ በቀለ የተባለ ሰው ያለምንም ውድድር የቤተክርስቲያኒቱ ሊቃውንት ቁጭ ብለው እየተመለከቱ በከፍተኛ ደመወዝ በልማት መምሪያ እንዲቀጠር አደርገዋል፤
    2.    አሁንም ሊቃውንቱ ተመልካቾች ሆነው እየሳሱና እየጓጉ አቡነ ጳውሎስ አንድ ዘመዳቸውን አምጥተው ያለምንም ውድድር በከፍተኛ ደመወዝ በልማት መምሪያው እንዲቀጠር አድርገዋል፤
    3.    ተክሉ የተባለው የቅርብ ዘመዳቸውና አንጋቻቸው በልማት መምሪያው እየሰራ ያለ ቢሆንም ከማንም ጋር ሳይወዳደር ከፍተኛ እድገትና ከፍተኛ ደመወዝ እንዲያገኝ ተደርጓል፤
    4.    በልዩ ጽ/ቤት አካባቢ የቤተ ክርስቲያኒቱ መዋቅር በማያውቀው ሁኔታ አንዱ ተርጓሚ፣ አንዱ አጥኚ ወዘተ በሚል የውሸት የስራ መደብ እየተፈጠረ ምንም ነገር ሳይሰሩ አራት ሺ፤ ስድስት ሺ ፤ ስምንት ሺ፤ የሚከፈላቸው ዘመዶቻቸውም እየተፈለፈሉ ናቸው። በአጠቃላይ ግን ስለ ቤተ ክርስቲያናቸን ጉዳይ መልስ ያላገኘንላቸው ብዙ ቢሆንም መሰረታዊ የሆኑ ሁለት ጥያቄዎችም አሉን። ማለትም፦
    ሀ.  እግዚአብሔር ይችን ቤተ ክርስቲያን በእኒህ ሰው አማካይነት እየቀጣ ነው?   ወይስ ሰውየው ከሌላ የተሰጣቸውን ተልዕኮ እያከናወኑ ነው?
    ለ. ቤተ ክርስቲያኒቱ እንደዚህ ባለ በከፋ ውድቀት ላይ እያለች መሆኗን ብፁዓን አባቶች እያዩ ምንም አያገባንም ብለው ዝም እንዲሉ እግዚአብሔር ልቦናቸውን አደነደነው ወይስ የግል ችግር ያለባቸው አባቶች በዙ
    የሚሉ ናቸው።

    በበኩላችን ግን በቤተ ክርስቲያናችን ውስጥ ያለው ጭካኔ ስላሳዘነን ለዋናው ዳኛ ለእግዚአብሔር አቤቱታችንን እያቀረብን መሆናችንን እየገለጥን ምናልባት ብፁዐን አባቶቻችን የቤተ ክርስቲያኒቱን ጉዳይ ለማየትና ለመዳኘት የምትፈቅዱ ከሆነ ሊፈጸም ይገባል ብለን ያቀረብነውን የማጠቃለያ ሀሳባችንን ከዚህ ቀጥለን መዝግበነዋል።

    ክፍል አራት የውሳኔ ሐሳብ
    1.    ‘ስምከ ሕያው ዘኢይመውት’ እየተባለ እግዚአብሔር የሚከብርበትና የሚቀደስበትን ቅዱስ ቃል አቡነ ጳውሎስ ዘርፈው ወስደው ለራሳቸው ማድረጋቸውና በስለት ወይም በእሳት ወይም በውግረተ ዕብን ወይም በሌላ ሁኔታ መከራና ስቃይ ሳይቀበሉ ደምም ሳይፈሳቸው፣ የሰማዕትነት ማዕረግም ከቤተ ክርስቲያኒቱ ሳይፈቀድላቸው እንዲሁ በንጥቂያ እና በጉልበት ሰማዕት ሆኛለሁ ማለታቸው የቀኖና ጥሰት ስለሆን ራሳቸውም ተባባሪዎቻቸውም ሊቀጡ ሊወገዙ ይገባል እንላለን። ምክንያቱም ጤናማ እና የተደላደለ አእምሮ ያለው መንፈሳዊ ነኝ ባይ ሰው ያልሆነውን ነገር ሆኛለሁ በማለት ሰውን ግራ ለማጋባት እና ሥርዓትን ለማፋለስ ሙከራ ካደረገ የተሟላ ጥፋት ፈጽሟል ማለት ነውና ይህ ከግምት ገብቶ ሐውልቱም ጭምር መፍረስ እንዳለበት እናሳስባለን። በየቤተ ክርስቲያኒቱ የቆሙ ፎቶዎቻቸውችም ተነስተው መውረድ አለባቸው እንላለን፤

    2.    ታሪካቸውን በውሸት የሚያንጸባርቀውና በአዲስ አበባ ካህናት እንዲገዙት የሚገደዱት ፊልም እንዲታገድ፤

    3.    ቅዱስ ሲኖዶስ በማያውቀው ሁኔታ በደቡብ አፍሪካ እና በጋምቤላ ሥራ እሰራለሁ እያሉ የሚያካሂዱት የገንዘብ ዘረፋ እንዲቆም፣

    4.    በጠቅላይ ቤተ ክህነቱ የአስተዳደር ኃላፊ ተብሎ ከተሾመው ከአቶ ያሬድ ጀምሮ በልዩ ጽ/ቤትም ሆነ በልማት መምሪያው ያለ አግባብ የተሾሙትና አዲስ ተቀጣሪዎችም እንዲታገዱና እንዲጣራ፤

    5.    ከአሁን በፊት ሚያዝያ 19 እና ሰኔ 24 ቀን 2002 ዓ.ም. ጽፈን በአቀረብነው መግለጫ መሰረት ብፁዕ አቡነ ይስሐቅም በቤተ ክርስቲያናችን ላይ ከፍተኛ የአስተዳደር በደልና የገንዘብ ብዝበዛ የፈጸሙ ስለሆን የአቡነ ጳውሎስንና የአቡነ ይስሐቅን ጥፋት የሚያጣራ ኮሚቴ በቅዱስ ሲኖዶስ እንዲቋቋምና የኮሚቴው ውጤት እስኪገለጥ ድረስም አቡነ ጳውሎስ በአስተዳደር ሥራ እንዳይገቡ እንዲታገዱ እየጠየቅን ከዚህ ጋር የምንገልጠው ከአሁን በፊት ቅዱስ ሲኖዶሱ የቤተ ክርስቲያኒቱን ጉዳይ ማጣራት አይችልም፤ በገለልተኛ አጣሪ ኮሚቴ ነው መታየት ያለበት በሚል ሐሳብ ስራ ተከናውኖ የቤተ ክርስቲያኒቱን ቀኖና የማያውቁ ግለሰቦች በኮሚቴ ደረጃ ተቋቁመው በቤ ተክርስቲያኒቱ ሀብት ያለ አግባብ የተጠቀሙ መሆናቸውን ማንም ሰው ያውቃል። እንደ እውነቱ ከሆነ ግን በተለያዩ የሀገር መንግስታት መካከል የተፈጠረ የድንበር ጥያቄ ወይም ጦርነት ቢሆን ኖሮ ወይም በአንድ ሀገር መንግስትና የፖለቲካ ድርጅት መካከል የሚፈጠር የአገዛዝ ጥያቄ ያለበት ቢሆን በእርግጥ ገለልተኛ ያጣራ ማለት ይገባ ነበር። ከዚህ ውጭ ግን አንድ መንግስት የራሱ አስተዳደርና የሀገሩን ሀብት መቆጣጠርና ማጣራት አይችልም? ቤተ ክርስቲያኗም በበኩሏ ቀኖናዋን፣ ሃይማኖቷን፣ የቤተ መቅደሷን አሰራርን፣ ሀብቷን፣ ንብረቷን መቆጣጠርና ማጣራት አትችልም ተብሎ የተደነገገ ሕግ በሀገራችን በጭራሽ የለም። ብቻ ‘ያይዘጌን ቤት ውሻ ታውቀዋለች’ እንደሚባለው ሁሉ የተለያየ ምክንያት ተፈጥሮላቸው ግለሰቦች እናጣራለን ብለው ገብተው በቤተ ክርስቲያኒቱ ሀብት ተረዳጅተውበታል። የሆነ ይሁንና ያለፈው እንደ ታሪክ ተቆጥሮ ለዚህች ቤተ ክርስቲያን ከእናንተ ከብፁዓን አባቶች የሚቀርባት የለምና እባካችሁ ዳኝነት እዩላት፤ ፍትህም ስጡ በማለት በቤተ ክርስቲያን ስም እንማጸናችኋለን።

    ከቤተክርስቲያኒቱ ልጆች
     



    ትንቢቱ ሲፈጸም

    Thursday, July 22nd, 2010

    (ደጀ ሰላም፤ ጁላይ 22/2010)፦
    (አግናጢዎስ ዘጋስጫ)
    ትንቢቱ ሲፈጸም በመጽሐፍ ያለው፣
    ወገኔ አትደንግጡ ይህ ሊሆን ግድ ነው።
    ቅዱሳን ሳይቀሩ የተመረጡቱ፣
    በመጨረሻው ቀን በዓለም እንዲስቱ፣
    ቀድሞ በመጽሐፍ ተነግሯል ትንቢቱ።

    የእውነት ደብዛ ጠፍቶ ሐሰት መሰልጠኑ፣
    ሥርዓት ተጥሶ ነውሩ ጌጥ መሆኑ፣
    አይቀሬ ነውና ወገን አትደንግጡ፣
    ከመጣብን ቁጣ በጸሎት አምልጡ።

    የእግዚአብሔር ሰገነት ሲቀየር በጣዖት፣
    በቅዱሱ ሥፍራ ሲፈጸም እርኩሰት፣
    በአደባባይ ሲታይ ሰይጣን አካል ነሥቶ፣
    ከዚህ የበለጠ ምን ይመጣል ከቶ?

    ቅዱሳን ተናቁ አፈኞች ተሾሙ፣
    ንጹሐን ተዋርደው ሌቦች ተሸለሙ።

    በቅዱስ መስቀሉ በድኅነት ምልክት፣
    የእብነ በረድ ሐውልት ጣዖት ባረኩበት፣
    ጸጋ ቢሰጣቸው መንጋ እንዲጠብቁ፣
    በውዳሴ ከንቱ በገንዘብ ወደቁ።

    ብዙ ፈርኦኖች በኢትዮጵያ ነገሱ፣
    የአባቶችን ድንበር ሥርዓት አፈረሱ፣
    በውል ሳይታወቅ ማን እንደሾማቸው፣
    በቤቱ ቀለዱ እነርሱ እንዳሻቸው፣
    አየ የጥፋት ቀን የዓለም መጨረሻ፣
    የሐሳዊ መሲህ የአውሬው መንገሻ፣
    እጅግ ያሳዝናል ኢትዮጵያ መሆኗ፣
    ትንሽ ሳታገግም ከትናንት ሀዘኗ።
    በገንዘብ ተገዝተው ሀሰት ቢናገሩ፣
    በውዳሴ ከንቱ በዓለም ቢኖሩ፣
    ሁዋላ አይጠቅምም ከቶ በሞት ስንጠራ፣
    እግዚአብሔር ፊት ሲቀርብ የሠራነው ሥራ፣
    መሳሳት ያለ ነው መውደቅ መነሳቱ፣
    ፍጹም ስላልሆነ ሰው በሰውነቱ፣
    ነገር ግን ትልቁ ሊያድን የሚችለው፣
    ሰው ስህተቱን አውቆ ሲመለስ ብቻ ነው፣
    ስለዚህ ኤልዛቤል አክዓቦችም ሁሉ፣
    የናቡቴን ርስት እንቀማ ስትሉ፣
    አምላክ ተቆጥቶ እንዳያጠፋችሁ፣
    መመለስ ይሻላል ከክፉ ሥራችሁ።

    እናንተም አባቶች አበው ቅዱሳኑ
    መከራን ሳትፈሩ በእምነታችሁ



    አባቶችን ወክለው የሚደራደሩት ተደራዳሪዎች ታወቁ

    Thursday, July 22nd, 2010

    (ደጀ ሰላም፤ ጁላይ 21/2010)፦ ከአምስተኛው ፓትርያርክ ከብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ሲመት ማግስት ጀምሮ በቤተ ክርስቲያኒቱ የተነሣውን መከፋፈል ለማቆምና በአባቶች መካከልም የተፈጠረውን እስከ መወጋገዝ የሚያደርስ ልዩነት በእርቅ ለመጨረስ በተጀመረው እንቅስቃሴ ቅ/ሲኖዶስ ተወካዮቹን መምረጡ ታወቀ። ከዚህ በፊት መርጧቸው የነበሩትን ሻረ።

    ዛሬ ረቡዕ በተካሄደው ስብሰባ ላይ ከዚህ በፊት መርጧቸው የነበሩትንና አሜሪካ ያሉት አባቶች ያልተቀበሏቸውን ልዑካን በመተው አረጋውያን አባቶችን ተክቷል። በዚህም መሠረት ብፁዕ አቡነ በርተሎሜዎስ፣ ብፁዕ አቡነ ቀውስጦስ፣ ብፁዕ አቡነ ናትናኤል፣  ብፁዕ አቡነ አትናቴዎስና ብፁዕ አቡነ ኤልሳዕ ይሸመግሉ ዘንድ ተመርጠዋል። ከእነርሱም ጋር ንቡረ ዕድ ኤልያስ አብርሃ እና መጋቤ ብሉይ ሰይፈ ሥላሴ ዮሐንስ አብረው ይሄዳሉ ተብሎ ይጠበቃል።

    ይህ በእንዲህ እንዳለ የአሜሪካን አባቶችን ወክለው ብፁዕ አቡነ መልከ ጼዴቅ፣ ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ እና ብፁዕ አቡነ ኤልያስ ይደራደራሉ ተብሏል። የቀድሞውን ፓትርያርክም ሆኑ የአሁኑ በድርድሩ ውስጥ እንደማይገቡ ታውቋል።

    ከዚህ በፊት በተደረገው ምርጫ ቅዱስ ሲኖዶስ ወክሏቸው የነበሩትን ተደራዳሪዎች እንደማይቀበሏቸው የአሜሪካዎቹ አባቶች በተናገሩት መሠረት እነዚህ አረጋውያን አባቶች ሊመረጡ ችለዋል ተብሏል።



    ሐውልት ሰሪው የማፊያ ቡድን ጋዜጠኞችን እያስፈራራ ነው፣ አምና የ“አዲስ ነገር ጋዜጣ” ሪፖርተር ተደብድቦ ነበር

    Wednesday, July 21st, 2010

    (ደጀ ሰላም፤ ጁላይ 20/2010)፦ የፓትርያርኩን ሐውልት በማሠራትና የዝርፊያ ዕድሜውን ለማራዘም በመጣር ላይ ያለው የማፊያ ቡድን ይህንን ዜና የዘገቡትን ጋዜጠኖች ማስፈራራት መጀመሩ ታውቋል።

    “ስማችን በጋዜጦቹ እና በመጽሔቶቹ ተነሥቷል” የሚሉት ሊቀ ካህናት ጌታቸው ዶኒ፣ ዲ/ን በጋሻው ደሳለኝ እና ዲ/ን ዘሪሁን ሙላት “አውራምባ” ጋዜጣን፣ “ነጋድራስ” ጋዜጣንና “ሐምራዊ’ መጽሔትን “እንከሳችኋለን” በሚል ለማስፈራራት እየሞከሩ ነው።

    ከዚህ ማስፈራሪያ ጀርባ ግን አምና እንዳደረጉት ወደ አካላዊ ጥቃት የማይሄዱበት ምክንያት የላቸውም። በጥቅማቸው የመጣውን ማንንም ቢሆን ከማጥፋት ወደ ኋላ አይሉም። ይህ ተቃዋሚዎቻቸው ላይ አደጋ የመጣል ቁርጠኝነታቸው የብፁዓን አባቶችን ቤት በመሰባበርና በማስፈራራት የተገለጸ ነው። በሐምሌ ስድስቱ የቅ/ሲኖዶስ ስብሰባ ላይ ብፁዓን አባቶች ምንም ነገር ሳይተነፍሱ የወጡት ለሕይወታቸውም ስለሚሰጉ ሳይሆን አይቀርም። በወቅቱ ተቃውሞ ሲያቀርቡ የነበሩት ብፁዕ አቡነ ሳሙኤል አንድም ደጋፊ ሳያገኙ ሊቀሩ ችለዋል።

      ብዙዎችም “አቡነ መልከ ጼዴቅን ያየህ ተቀጣ” ያሉ ይመስላሉ። በቅርቡ ከዚህ ዓለም በሞት የተለዩት ብፁዕ አቡነ መልከ ጼዴቅ የሞቱበት ምክንያት በይፋ እንደሚነገረው “ተፈጥሯዊ” በሆነ ምክንያት ብቻ ሳይሆን ሌላ እጅ አለበት የሚለውን ብዙዎች ይስማሙበታል። ብፁዕነታቸው ቀደም ብሎ “ሳይመረዙ” እንዳልቀረ ነው የሚነገረው። (ታሪኩ የራሺያ መንግሥት ተቃዋሚዎቹን ከሚያጠፋበት መንገድ ጋር ይመሳሰላል።)

    የማፊያው ቡድን ወዶ ገባ አባል ዲ/ን በጋሻው እንዲህ ባለ መልኩ ከማስፈራራቱ ውጪ ይፋዊ በሆነ መንገድ አስተያየቱን ለመስጠት አልደፈረም። ይህንን የምትናገረውን ቃል ለምን ጽፈህ አትሰጠንም ሲባል ያንን ለማድረግ አልፈቀደም።



    የጀርመን ድምጽ ራዲዮ የሕዝብ አስተየየት ስለ ሐውልቱ

    Tuesday, July 20th, 2010
    width="320" height="266" bgcolor="#FFFFFF"
    flashvars="flvurl=http%3A%2F%2Fv13.nonxt5.googlevideo.com%2Fvideoplayback%3Fid%3D410b305150db21a7%26itag%3D5%26app%3Dblogger%26ip%3D0.0.0.0%26ipbits%3D0%26expire%3D1283047088%26sparams%3Did%252Citag%252Cip%252Cipbits%252Cexpire%26signature%3D20CD16874DEDE9F4D91EEA1F8DD15A4461B8EC0C.501970145678D38B5222BEC213F067CF3BFBCFCB%26key%3Dck1&iurl=http%3A%2F%2Fvideo.google.com%2FThumbnailServer2%3Fapp%3Dblogger%26contentid%3D410b305150db21a7%26offsetms%3D5000%26itag%3Dw160%26sigh%3Dhq9MccDuk4XidWOm6MKzgj9__qo&autoplay=0&ps=blogger"
    allowFullScreen="true" />

    (ደጀ ሰላም፣ ጁላይ 20/2010)፦ ይህ ዝግጅት የጀርመን ድምጽ ሬዲዮ (ዶይቸ ቨለ) ያዘጋጀው ነው። ሐውልቱን አስመልክቶ ኦርቶዶክሳውያን ምን እንደተሰማቸው መጠነኛ ገለጻ ነው። እንዲህ የሚናገር ቁርጠኛ ሰው አያሳጣን።

    ቸር ወሬ ያሰማን፣ አሜን



    Mass allows Ethiopian community to come together in Lebanon

    Monday, July 19th, 2010

    The Daily Star:-BEIRUT: Lebanon is widely known to be home to 18 official religious sects, but with the steadily growing numbers of foreign workers in the country, several other religions and sects now have a critical mass, requiring places to come together for worship and fellowship.

    The current center of the Ethiopian Orthodox community is located at the church of the Convent of the Franciscaines in Badaro, where Ethiopian expatriates have been able to maintain their rich cultural and religious heritage every Sunday.

    Akin to Lebanon, Ethiopia’s major religions are Christianity and Islam. It is estimated that approximately 60,000 to 70,000 Ethiopians are currently working in Lebanon. Many have been here for several years and don’t intend to return home to Ethiopia soon due to dismal economic and financial conditions. Overwhelmingly female, most are employed in household labor and are paid a wage that most Lebanese could never survive on. As of now, attending church on Sundays is one of the ways for the community to come together.

    The service is in Amharic, Ethiopia’s official language. Worship typically begins at 8:00 am and concludes between 12:30 pm and 1:00 pm.

    Most of the service entails the priest singing a capella canon to the congregation as they respond back in song, often bowing their heads. The inside of the church is impressive in its austere simplicity. The harsh white walls are unadorned and the wooden pews are worn, but worshipers brave the heat and humidity without air-conditioning.

    The church-goers come from all over Lebanon by bus or taxi, from as close as Beirut’s suburbs to as far away as villages on the Lebanese-Israeli border. They remove their shoes before entering the church and loosely drape themselves in a matala, a thin, transparent white cloth that is symbolic of the purity and cleanliness necessary to enter the house of God. Women must wear long, modest clothing that covers their shoulders. Trousers and long skirts must cover the legs to at least the ankle.

    Not all of Lebanon’s Ethiopian workers can always make it to church.

    “I am lucky to be able to come worship today, my Madame doesn’t let me come always because she needs me to work on Sundays in the kitchen. Many other Ethiopians can’t come to our church at all because their Madame won’t let them have a day off,” said one attendee, who preferred to remain anonymous.

    Until recently, Ethiopians lacked a church of their own, as they have been renting the Convent of the Franciscaines for the past decade, and before that, services used to be held at a church in Gemmayzeh. Finally, an Ethiopian Orthodox church was built two years ago in Ain Aar, above Bikfaya.

    Ethiopian workers and ordinary Lebanese citizens who wished for the community to have their own place of worship funded Lebanon’s first official Ethiopian Orthodox church. However the new church is slated to be used only during special festivities and holidays, due to its location; hence regular church services are held in Badaro. The Ethiopian Orthodox calendar, which begins on the September 11, sees 150 festivities per year.

    Ethiopians continue to remain wary of the media, amid the spotlight on less-than-adequate treatment by their employers, a rash of suicides by domestics, and the workers’ fear of being deported.

    Photographers and journalists are asked to keep their distance, and for now, the church in Badaro is a place where the Ethiopians of Lebanon can come together, but not a place where Ethiopians can interact with the rest of their host society.

    Source:- The Daily Star



    “ ለጊዜው ተስማምተናል "

    Sunday, July 18th, 2010
    (ደጀ ሰላም፤ ጁላይ 18/2010)፦
    ክርስቲያን ተብለው የተጠሩ ሁሉ
    ኧረ ምን ነካቸው አበዱ ይላሉ
    ሞኞች ናቸው ጅሎች ቢዝነስ የማያውቁ
    ያልኖረን ቃል ፈጥረው “ተጣሉ ታረቁ
    ተወጋግዘው ነበር ዛሬ ግን ተስማሙ“
    ብለው የሚያወሩ ሚያቦኩ የሚያሙ።
    ድሮም አልተጣላን ክስም አልነበረን
    በታክቲክ፡ነው፡እንጂ፡በዓላማ፡አንድ፡ነን::

    እርግጥ በተሰለፍንበት ተመሳሳይ ሜዳ
    በአጨዋወት ስልታችን አንዱ አንዱን ሲጎዳ
    መኖሩን አንክድም ነበረን ተቃርኖ
    ደጋፊም ተጣልቷል ሁለት ጎራ ሆኖ፡
    አሁን ግን ተግባባን በጋራ ለመብላት
    ለሰላም መግለጫም አቁመናል ሐውልት
    ዓለም ባደነቀው በgive & take ስልት
    እንደተሰጠን ስም – “ቅዱስ“ : “አቶ“ ሆነን
    “ለእኔ“ “ለእኔ“ ክብር ልንሰራ ተስማማን
    ወዮ ለእናንተ ውጪ ለቆማችሁ
    ማልያ ቀይሮ መግባት ላልቻላችሁ
    ለራሳችሁ አስቡ አንድ መልክ ላላችሁ
    ዓለም ላይ ኖራችሁ “ዓለም“ ላልገባችሁ



    ሁለት ጽሑፎች ስለ ሐውልቱ ጉዳይ:- ባሮክ እና ገብር ሔር እንደጻፉት

    Saturday, July 17th, 2010

    (ደጀ ሰላም፤ ጁላይ 16/2010)፦  ትናንት እንደዘገብነው፣ “ስውሩ ፀሐፊ” ዘሪሁን ሙላቱ ያዘጋጀውና በፓትርያርኩ “የተባረከው” ጽሑፍ በሊቀ ካህናት ጌታቸው ዶኒ ስም “ነጋድራስ ጋዜጣ” ላይ ታትሞ ወጥቷል። ይህ ኢ-ኦርቶዶክሳዊ ትምህርት በኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ ይሁንታ መውጣቱ እጅግ አሳዛኝ እና ዘመነ-ንስጥሮስን የሚያስታውስ ነው። አምስተኛው ፓትርያርክ አቡነ ጳውሎስ ሞት ሥልጣናቸውን እስኪነጥቃቸው ድረስ ሳይወገዙ ቢቆዩም እንኳን ከዚያ በኋላ እግዚአብሔር ጥሩ ቅን አባት ሲሰጠን ቀኖና ቤተ ክርስቲያንን የጣሱ ፓትርያርክ ናቸውና እንኳን በሕይወት እያሉ ከሞቱም በኋላ ቢሆን ስማቸውና ተግባራቸው ሊወገዝ ይገባዋል።
    የእስክንድርያ ቤተ ክርስቲያን የኑፋቄ ትምህርት ሲያስተምር የነበረውን አርጌንስ ከሞተ ከ300 ዓመት በኋላ እርሱንም የጻፋቸውን ስፍር ቁጥር የሌላቸውን መጻሕፍቱንም ማውገዟ ትምህርት ሊሆነን ይገባል። አቡነ ጳውሎስም አሁን የሚያወግዛቸው ሲኖዶስ ባናገኝ እንኳን ለዚህ ሥራቸው ከሞቱም በኋላ ውግዘቱ አይቀርላቸውም፤ ንስሐ እስካልገቡበትድረስ። ለጊዜው ግን ይህንን ካቶሊካዊ ሥራቸውን የሚሞግቱ ሁለት ጽሑፎችን ከዚህ በታች ተመልክቱ። አትማችሁ ላላነበቡ አድርሱ፤ ለታሪክም አስቀምጡት።

    ቸር ወሬ ያሰማን፣ አሜን

    የሐውልቱ ሥር «ቁማርተኞች»


    (ባሮክ ዘሣልሳይ ሽሕ)


    ሐምሌ አራት ቀን 2002 ዓ.ም በቦሌ ደብረ ሳሌም መድኃኔዓለም ቤተ ክርስተያን ደጃፍ ዐጸድ ላይ የብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ «የምስክርነት» ሐውልት ቆሟል፡፡ ሐውልቱ ከመቆሙ በፊትም ሆነ ከቆመ በኋላ ሁለት ተቃራኒ ሐሳቦች እየተንጸባረቁ ናቸው፡፡ የመጀሪያው እና በአሠሪ ኮሚቴዎቹና በዙሪያቸው ካሉ ጥቂት ግለሰቦች የተደመጠው ሐሳብ፣ «ሐውልት ማቆም የቤተ ክርስቲያኗ ሥርዐት ነው» የሚል ነው፡፡ የዚህ ተፃራሪ የሆነውና አብዛኛውን ሕዝበ ክርስቲያንና የቅዱስ ሲኖዶሱ አባላት፣ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንና የመንፈሳዊ ኮሌጅ ደቀመዛሙርት ያካተተው ሁለተኛው ሐሳብ ደግሞ፣ «ሐውልት ማቆም በቤተ ክርስቲያኗ ሕግ፣ ቀኖና ሥርዐት የተወገዘ እና መጽሐፍ ቅዱሳዊ መሠረት የሌለው ነው» የሚለው ነው፡፡

    ከዚህ አንጻር ለሕዝበ ክርስቲያኑ እውነታውን ከመግለጽ አኳያ መጽሐፍ ቅዱስ፣ የቅዱስ ሲኖዶስ እና ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ውሳኔ እንዲሁም በጥቅሉ የቤተ ክርስቲያኗ አስተምህሮ እና ሊቃውንት ምን ይላሉ? የሚለውን በጥንቃቄ መመርመር ለሁሉም ማለፊያ በመሆኑ የሚከተሉት ትንታኔዎች ቀርበዋል፡፡

    1.    ጥንተ ሐውልተ

    መስከረም 1987 ዓ.ም በቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ፣ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ልዩ ትእዛዝ፣ በብፁዕ አቡነ መቃርዮስ በወቅቱ የትግራይ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ሰብሳቢነት፤ በመልአከ ሰላም ዳኛቸው ካሣሁን፣ በሊቀ ካህናት ክንፈ ገብርኤል አልታዬ በመጋቤ ምስጢር ወልደ ሩፋኤል ፈታሒ፣ በመጋቤ ብሉይ ሠይፈ ሥላሴ ዮሐንስ አዘጋጅነት፣ «ሃይማኖት የለየንን መቃብር አንድ አያደርገንም» በሚል ርእስ የተዘጋጀው መጽሐፍ ስለ ሐውልት ምንነት እና አጀማመር ሲያስረዳ እንደሚከተለው ይላል፡፡

    ሐውልት አንድ ወጥ የሆነ ክብነት ወይም ማእዘንነት ያለው፤ ከድንጊያ ተጠርቦ፣ ከኖራ እና አሸዋ፣ ከሲሚንቶ እና ከተፈጨ ደንጊያ ተሠርቶ ለመታሰቢያ የሚተከል፣ እንደ ዐምድ /እንደ ምሰሶ/ የሚቆም መዘክር ነው፡፡ ሐውልት- የሚያመለክተው በአንድ ዘመን በአንድ ቦታ ላይ የተፈጸመን ድርጊት ስለሆነ ከብዙ የድንጋይ ቁልል /ጉር/ ሊሠራ ይችላል፡፡ በቀድሞ ጊዜ ሐውልት የሚቆመው በጦር ሜዳ ወድቀው ለሚቀሩ ጀግኖች፤ በስደትና በሽሽት ጊዜ በጉዞ ላይ በሚደርስ ድንገተኛ ሞት፣ ከቤተሰብ ተለይተው በመንገድ ዳር ለሚቀበሩ ወገኖች መታሰቢያ ነበር፡፡» /ገጽ-32/

    በዚህ ምክንያት ሐውልት የመቆሙም ጥቅም «ይኽ መቃብር የእገሌ ወይም የእገሊት መቃብር» ነው ተብሎ ለመታወቂያና ለመታሰቢያ ነው እንጂ መንግስተ ሰማያት የሚያወርስ፣ ሰማያዊ ጥቅምን የሚያስገኝ አይደለም፡፡ በዚህ መልኩ እና ዐውድ /Context/ ለሙታን ሐውልት ማቆም በያዕቆብ ወልደ ይስሐቅ ዘመን የተጀመረ ልማድ መሆኑን ቅዱስ መጽሐፍ ሲገልጥ፣ «ወአቀመ ያዕቆብ ሐውልተ ላዕለ መቃብረ ራሄል፤ ወይእቲ ተሰምየት ሐውልተ ራሄል፤ ያዕቆብ በራሄል መቃብር ላይ ሐውልትን አቆመ፤ እስከ ዛሬም የራሄል ሐውልት ተብሎ ተሰየመ፤» በማለት ነው፡፡ /ዘፍ. 35.20/

    እንግዲህ ከዚህ የሙታን ጥንተ ሐውልት ታሪክ መረዳት እንደሚቻለው አንድ ወጥ የሆነ የቆመ ድንጊያ /ትክል/ ምልክት እንጂ ዛሬ በዘመናችን የአቡነ ጳውሎስን የ«ምስክርነት ሐውልት» ጨምሮ/ በተለያየ ቅርጽና መልክ እንደሚሠራው ያለ ጥርብ ድንጋይና የእምነ በረድ፤ የአሸዋና ሲሚንቶ፣ የኖራና የጠጠር ክምር አይደለም፡፡ ያዕቆብም ለራሔል የመታሰቢያ ሐውልት ያቆመበት ምክንያት ወደሀገሯ ሳትገባ በድንገት በመንገድ ዳር አርፋ ከወገኖቿ ጋራ ለመቀበር ዕድል ሳታገኝ በመቅረቷ ለመታሰቢያ ነው፡፡ በመስከረም 1987 ዓ.ም በቅዱስ ፓትርያርኩ ልዩ ትእዛዝ የተዘጋጀውም መጽሐፍ ይኽ የራሄል የመታሰቢያ ሐውልት አሁን በዘመናችን ከሚቆሙት ሐውልቶች በእጅጉ መለየቱን ሲገልጽ፣ «… አሠራሩም ሆነ አፈጻጸሙ በዘመናችን እንደሚታየው ያለ ሁኔታ አልነበረም፤ ሊሆንም አይገባም፡፡» ይላል፡፡ /ገጽ. 34/

    ስለዚህ ከዚህ መረዳት የሚቻለው የሐውልትን ታሪካዊ ዕድገት እንጂ ሥርዐተ አበው እና ሕገ ሃይማኖት ኾኖ መሥራቱን እና መደንገጉን አይደለም፡፡ ግን ልማድ ነው፡፡ ከገድለ ቅዱሳን እንደምንረዳው፤ እንኳን በሕይወት ያሉ ይቅርና ሃይማኖታቸውን ጠብቀው፣ ሥነ ምግባራቸውን አሳምረው በሞት ዕረፍት የተለዩን ደጋግ አባቶችና እናቶች በመካነ መቃብራቸው ተአምራት እየተደረገ እንኳን ምልክት /ትክል ድንጋይ/ ይቆማል እንጂ ሐውልት አይሠራም፡፡ የቀደሙት ክርስቲያኖች አባቶቻችን የሙታንን መታሰቢያ አስመልክቶ በመካነ መቃብር ላይ የሚያደርጓቸው ምልክቶች ልዩ ልዩ ዐጸዶችን /ዛባቸነ/  መትከል ነው፡፡ /ገጽ 36/

    ከዚህ ጋር በተያያዘም የሚነሣው ሌላ ነጥብ «የሐውልት ምረቃ» ነው፡፡ እንኳን በሕይወት ያለ ሰው ሐውልት ይቅርና ከዚህ ዓለም በሞት ለተለየ ሰው ሐውልት አቆሞ ማስመረቅ በቀኖና ቤተ ክርስቲያን ያልተፈቀደ መሆኑን የቤተ ክርስቲያኗ አቋም የተገለጸበት ይኸው በቅዱስነታቸው ልዩ ትእዛዝ የተዘጋጀው መጽሐፍ ያስረዳል፤ እንዲህ በማለት፡- «የሐውልት ምረቃ» የሚባለው ከቤተ ክርስቲያን ያልተሰጠ እንግዳ ልማድና ከመንፈሳዊ ሥርዐት ውጭ የሚፈጸም ነው፡፡ ለሞቱ ሰዎች ለሥጋቸው ትንሣኤን፣ ለነፍሳቸው በጎ ዕረፍት ስጥ ለማለት ለምሕረትና ለይቅርታ በመካነ መቃብር ላይ ጸሎት ይደረጋል፡፡ በሐውልት ዙሪያ ሕዝብ ሰብስቦ ሐውልቱን ግምጃ አልብሶ ጸሎተ አኰቴት ማድረስ ግን በቀኖና ቤተ ክርስቲያን የታዘዘም የተፈቀደም አይደለም፡፡» /ገጽ-37/

    2.   የሐውልት ክልከላ ምክንያት

    ከጥንት ጀምሮ እንደሚታወቀውም ሆነ በባዛንታይ በ787 ዓ.ም በተወሰነው ውሳኔ መሠረት ቤተ ክርስቲያን የቅብ ወይም የጭረት ሥዕልን እንጂ ቅርጽን ወይም ሐውልትን አትጠቀምም፡፡ በሮማውያምኑ ዘንድ ቢኾን የጣዖት አምልኮ ከጥንቱ በተወረሰ ልማድ ካልሆነ በቀር በቤተ ክርስቲያን ትውፊት ቅርጽ /ሐውልት/ ማቆም የተፈቀደ አይደለም፡፡ በቤተ ክርስቲያን ትምህርት፣ ታሪክና ትውፊት ሐውልት ሳይሆን ሥዕል የተፈቀደ፣ የተለመደና ሥርዐታዊ ነው፡፡ ይኽም አምስት ነገርን መሠረት በማድረግ ነው፡፡

    2.1 መጽሐፍ ቅዱስ

    እግዚአብሔር አምላክ ለሙሴ ከሰጣቸው ዐሥርቱ ትእዛዛት አንዱ «በላይ በሰማይ በታችም በምድር ካለው፤ ከምድርም በታች በውሃ ካለው ነገር የማናቸውንም ምሳሌ የተቀረጸውን ምስል ለአንተ አታድርግ፤ የሚለው ነው፡፡ /ዘጸ. 20.4-5/ በዚህ መሠረት የተቀረጸ ምሳሌ /ሐውልት/ ቁጥሩ ከአምልኰ ባዕድ ስለሆነ ቤተ ክርስቲያን ትቃወማለች፡፡

    2.2 የታሪክ መዛግብት እና መረጃዎች ምስክርነት

    ቀደምት የቤተ ክርስቲያን አበውና የታሪክ ጸሐፊዎች በቤተ ክርስቲያን ሥዕል እንጂ ሐውልት የተፈቀደ መሆኑን አልገለጹም፤ አላስተማሩም፡፡ አውሳብዮስ በቤተ ክርስቲያን ታሪክ መጽሐፉ፣ «ታላላቅ ሥዕላትን አይቻለሁ፤ የመድኃኔ ዓለም፣ የቅዱስ ጴጥሮስና የቅዱስ ጳውሎስ ሥዕላት እስከ ዘመናችን ድረስ አሉ፡፡» አለ እንጂ ሐውልትን አልጠቀሰም፡፡ /Eusabius, History of the church, Book III, page 20/

    በቤዛንታይን መንግሥት የቅዱሳት ሥዕላት ክርክር በተካሄደ ጊዜ ቅዱሳት ሥዕላትን በተመለከተ ሦስት መጻሕፍትን የጻፈው ታላቁ ሊቅ ዮሐንስ ዘደማስቆ፣ «ሥዕል በቤተ ክርስቲያን ሁለት ዐይነት ጥቅም አለው፡፡ ከእነዚህም አንዱ በዋሻ እንደነበሩት ክርስቲያኖች ተአምራት ነክ የቅዱሳት መጻሕፍትን ታሪክ ማነበብ ለማይችሉ ሰዎች ለማስረዳት ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ ሃይማኖቱን ሳይፈራ፣ ሳያፍር መስክሮ በሰማዕትነት የሞተ ወይም ስለ ዓለም እና ስለራሱ በመጸለይ መላ ሕይወቱን ከፍትወታት፣ ከእኩያት፣ ከአጋንንት ጋር በመጋደል ያሳለፈውን ሰማዕት ወይም ጻድቅ በሥዕል ለመዘከር፣ በሥዕሉም አማካይነት እያንዳንዱ ምእመን ለሥዕሉ ባለቤት ክብርና ፍቅር ለመግለጥ ነው፤» በማለት ጻፈ እንጂ ሐውልትን አልጠቀሰም፡፡ /አባ ጎርጎርዮስ፣ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ታሪክ፣ ገጽ 99/ ከዚህ ሊቅ በተጨማሪም እነጎርጎርዮስ ዘዐቢይ እና ባስልዮስ ዘቂሣርያ በየድርሳኖቻቸው ስለቅዱሳት ሥዕላት አስፈላጊነት እንጂ ስለ ሐውልት ተከላ እና ምረቃ አልጻፉም፡፡

    2.3 የኦሪየንታል አብያተ ክርስቲያን ትውፊት /Oriental Church tradition/

    የነገረ እግዚአብሔር ሊቃውንት ስለምዕራብና ምሥራቅ አብያተ ክርስቲያናት ሲያስተምሩ «East is Iconic, west is pictorial» /ምሥራቅ ሥዕላዊ፣ ምዕራብ ባለ ምስል ናቸው/ ይላሉ፡፡ የምሥራቅ አብያተ ክርስቲያናት ሥዕል ሲሉ ሦስት ማእዘናዊ /three dimensional/  የሆነውን ሐውልትን በመተው ወካይ ትርጉማዊ እውነታን የሚያስፍረውን ሥዕልን ይጠቀማሉ፡፡ /Coptic Encyclopedia Vol. 4 -1276/

    በዚህም መሠረት በምሥራቃውያን ትውፊት ሥዕል ሊታይ ወይም ሊዳሰስ የሚችል ቅርጽ የሌለው ሁለት ማእዘናዊ /two-dimensional/ የሆነ በቀለም የሚሠራ ነው፡፡ በኢትዮጵያ፣ በግብጽ፣ በሶርያም ሆነ በአርመን ገዳማት ቅዱሳት ሥዕላት እንጂ ሐውልቶች አይገኙም፡፡ ሌላው ቀርቶ መለካውያን ኦርቶዶክሶችም /Chalcedonian/ Byzantine Orthodox Churches/ በሥርዐታቸው ሐውልትን አይጠቀሙም፡፡ /2ኛው የኒቂያ ጉባኤ ውሳኔ 787 ዓ. ም/

    2.4 የቤተ ክርስቲያን መጻሕፍት ምስክርነት

    በቤተ ክርስቲያናችን የተጻፉ መጻሕፍት ሥዕል እንጂ ሐውልት የቤተ ክርስቲያን መሆኑን አይገልጹም፤ እንዲያውም ይከለክላሉ፡፡ ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ ካልዕ «የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ታሪክ» በተባለው የታወቀ መጽሐፋቸው፣ «በምሥራቅ አብያተ ክርስቲያናት ትውፊት መሠረት ሥዕል የሚሣለው በቀለም ነው፡፡ ላቲኖች ግን ቅርጽን /ሐውልትን/ ይጠቀማሉ፡፡» በማለት ገልጠዋል፡፡ /ገጽ 114/ ይኽም የሚያመላክተን ትውፊታችን የቀለም ሥዕል እንጂ የቅርጽ ሐውልት ያለመሆኑንን ነው፡፡

    በ1970 ዓ.ም የታተመው «The Ethiopian Orthodox Church» የተሰኘው የአእምሮ ወንድማገኘሁ መጽሐፍም፣ «ኦርቶዶክሳውያን የሚያከብሩት ዝርግ /flat/፣ ሁለት ማእዘናዊ /two dimension/ ቅዱሳት ሥዕላትን ነው፡፡ ለሦስት ማእዘናዊ ሐውልት /Statue/ አይጸልዩም፡፡ ምክንያቱም ዕውናዊ ጠባይ ሰላለውና በራሱም ጣዖትን ማክበር ስለሆነ ነው፡፡» ይላል፡፡ /ገጽ 91/

    «የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን እምነት፣ ሥርዐተ አምልኮና የውጭ ግንኙነት» በሚል ርእስ ቅዱስ ሲኖዶስ ያሳተመው መጽሐፍም ቅዱሳት ሥዕላት በቤተ ክርስቲያን ስላላቸው ክብር ይዘረዝራል እንጂ «ሐውልት የቤተ ክርስቲያን ትውፊት ነው» ብሎ አልጠቀሰም፡፡ /ገጽ-95/

    «ሃይማኖት የለየንን መቃብር አንድ አያደርገንም» በሚል ርእስ በ1987 ዓ.ም የተዘጋጀው መጽሐፍም፣ «የክርስቲያኖች ሐውልት ቤተ ክርስቲያን ናት፤ አማንያን በአርባ በሰማኒያ ቀን እየተጠመቁ ከአብራከ መንፈስ ቅዱስ ከማሕፀነ ዮርዳኖስ በመወለድ ከሥላሴ ልጅነትን ይቀበሉባታል፡፡ ከዚህ ዓለም በሞተ ሥጋ በሚለዩበትም ጊዜ የዕረፍት ቦታቸው ናት፡፡ ቤተ ክርስቲያን የጸሎት የመሥዋዕት ቦታ ከመሆኗም በላይ በተስፋ ትንሣኤ የሚታረፍባት ስለሆነች ሲያዩት ደስ በሚያሰኝ፣ ሲመላለሱበት ኅሊናን በሚስብ ንጽሕና መጠበቅ ይኖርባታል እንጂ የሐውልት መከማቻ ልትሆን አይገባም፡፡ ሐውልት… ትንሣኤን ስለሚያስረሳ አፍአዊ ምልክት /ከንቱ መታለያ/ ነው፡፡ … ልምዱም የመጣው ከሌሎች እንጂ ከአባቶቻችን የመጣ ባህልና ትውፊት ስላልሆነ እንዳይቀጥል የሚደረግበት መንገድ መፈለግ ይኖርበታል፡፡» በማለት አስፍሯል፡፡ /ገጽ፣ 35 እና 38/

    2.5 የቤተ ክርስቲያን ጸሎት ምስክርነት /Liturgical witness/

    የቤተ ክርስቲያን ትምህርትና ሥርዐተ አምልኰ ከሚገለጽባቸው መንገዶች አንዱ ሥርዐተ ጸሎት ነው፡፡ በዚህ ውስጥም ዶግማዋ፣ ታሪኳና ሥርዐቷ ተካትቶ ይገኛል፡፡

    ቅዱሳት ሥዕላት ቤተ ክርስቲያናዊ ሥርዐትና ትውፊት በመሆኑ «መልክእ ሥዕል» የተሰኘ ጸሎት አለው፡፡ «መልክአ ሐውልት» ግን የለም፡፡ ይኽንንም መልክአ ሥዕል ሲገልጽ «ሰላም ለሥዕልኪ እንተ ሠዓላ በእዱ፣ ሉቃስ ጠቢቡ እም አርባዕቱ /ወንጌላውያን/ አሐዱ፤ ቅድመ ሥዕልኪ እሰግድ ወለሥዕለ ወልድኪ እገኒ፤ ማርያም ድንግል ማርያም እመ አዶኒ» በማለት ነው፡፡ /መልክአ ሥዕል/

    በመቅድመ ተኣምረ ማርያምም «ለሥዕሏ ያልሰገደ ስም አጠራሩ ይጥፋ» ይላል እንጂ “ለሐውልቷ ያልሰገደ” አይልም፡፡ እነዚህ ሁሉ የቤተ ክርስቲያን ጸሎት ክፍሎች የሥዕልን ሥርዐታዊነትና ትውፊታዊነት እንጂ የሐውልትን ኦርቶዶክሳዊነት አይመሰክሩም፡፡

    እንግዲህ ከላይ በቅደም ተከተል የጠቀስናቸውን ማስረጃዎች «የሐውልቱ ሥር ቁማርተኞች» እንደሚሉት ሳይሆን ቅዱሳት ሥዕላት እንጂ ሐውልት ኦርቶዶክሳዊ አለመሆኑንን የሚያመለክቱ ናቸው፡፡ ለጊዜያዊ ስምና ዝና እንዲሁም ለገንዘብ ተብሎ እውነተኛውን የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት አጣምሞ ማቅረብ በእግዚአብሔርም በታሪክም፣ በሕግም ከማስጠየቁም በላይ በቅዱስነታቸው ክብርና ስም በመቆመር ለሃይማኖታችን መዘባበቻን ለምእመናንም ኀፍረትን ማትረፍ ነው፡፡

    ለሥርዐተ ቤተ ክርስቲያን ተፃራሪ የኾነው የዚህ ሕገ ወጥ ድርጊት ፊታውራሪዎች፣ አባሪ እና ተባባሪዎች የፓትርያርኩን 18ኛ ዓመት በዓለ ሢመት ምክንያት በማድረግ በተቋቋመ ኮሚቴ ሽፋን የሚንቀሳቀሱ ናቸው፡፡ እንደ እውነቱ ከኾነ በየዓመቱ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ለሢመተ ፕትርክና በተመረጡበት ቀን የሚከበረው ይህ በዓል ለታሪካዊቷ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን የነጻነት በዓል ነው፤ ከኮፕት ቤተ ክርስቲያን ሞግዚትነት ተላቃ ከራስዋ አበው መነኮሳት እና ሊቃውንት በተመረጡ አባቶች ለመመራት የበቃችበት ነውና፡፡ ይኹንና በዘንድሮው በዓለ ሢመት ዝግጅት ስም የፓትርያርኩን የ«ምስክርነት ሐውልት» በማን አለብኝነት እና ግልጽነት በጎደለው የጥቅም ትስስር ሠርተው ያስመረቁት ግለሰቦች የቤተ ክርስቲያኒቱን የነጻነት በዓል በባዕዳን ትምህርት እና ልማድ በመለወጥ በቤተ ክርስቲያኒቱ ውስጥ የሽፍትነት እና የቁማርተኝነት ተግባር በመፈጸም የግል እና የቡድን ጥቅማቸውን እያዳበሩ ከመኾናቸውም በላይ ከሌሎች ቤተ እምነቶች የቅልውጥ ድርጊቶችን በመውሰድ ጥንታዊትና ስንዱ እመቤት በኾነችው ቤተ ክርስቲያን ውስጥ የባርነት መንፈስ ለማስፈን እየማሰኑ ይገኛሉ፡፡

    ከፓትርያርኩ ሽልማት ኮሚቴ አባላት አንዳንዶቹ የቤተ ክርስቲያኒቱን ቆብ እና ቀሚስ ለብሰው፣ መስቀል ጨብጠው ሲያበቁ ከፕሮቴስታንት አብያተ እምነት ለአንዱ ክፍል ማደራቸውን በጻፉት ደብዳቤያቸው ያረጋገጡ፣ በረከት ሞልቶ ከተረፋት እናት ቤተ ክርስቲያን ይልቅ የሌሎችን ገፈራ ለመቀላወጥ በደጃቸው የተለጎሙ፣ በሄዱበት ሁሉ የቤተ ክርስቲያኒቱን ፍሬ በልተው እና አራቁተው እብስ የሚሉ ናቸው፡፡ አንዳንዶቹም በጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ውስጥ አንዳችም በይፋ የታወቀ ሥልጣን እና ተግባር ሳይኖራቸው፣ ቤተ ክርስቲያኒቱ በሠራቻቸው የኪራይ ቤቶች በነጻ እየኖሩ፣ ቅዱስ ፓትርያርኩን ያሻቸውን በማስወሰን ግፈኛ ኤልዛቤላዊ ተግባር የሚፈጽሙ፣ ሐውልተ ስም አቁመው መስዋእተ እርያ የሚያቀርቡ ናቸው፡፡

    አንዳንዶቹም በቤተ ክርስቲያኒቱ ከፍተኛ የትምህርት ተቋም የሚሰጠው ነገረ መለኮት የብረት ቆሎ ሲኾንባቸው በፕሮቴስታንት «ሐሊበ – ቃል» ተዘርተው የበቀሉ፣ ተኮትኩተው ያደጉ፣ ኦርቶዶክሳዊ ሥርዐትን እና ካህናትን የሚነቅፉ እና የሚዘልፉ፣ ፕሮቴስታንታዊ ፓስተሮችን የሚያሞጋግሱ እና በፕሮቴስታንታዊ ዘይቤዎች የተጠመዱ፣ ትላንት «የመስቀሉ ሥር ቁማርተኞች» ብለው በተናገሩበት አንደበታቸው ዛሬ የተለወጡ ኹኔታዎች በሌሉበት የውዳሴ ከንቱ ዶፍ የሚያወርዱ፣ የእኛ ያልሆነ እንግዳ ልማድ አስርገው ኢየሩሳሌም ዘሞዐብ ሊያደርጉን የሚርመሰመሱ ክልኤ ባሕርይ ናቸው፡፡ ሌሎቹም ከድመት ጠጉር ልመው ወደ ቤተ ክርስቲያን ሰርገው የገቡ እና በጭንቅ የተገኘን የቤተ ክርስቲያን ንዋይ እርም የበሉ ናቸው፡፡ ሌሎቹም ቀደም ሲል ፓትርያርኩን ሲዘልፉ የነበሩትን ተፃርረው ለ«ስድብ አፋቸው» ምላሽ የሰነዘሩ፣ ዛሬ ግን እነዚያኑ ዘላፊዎች ሕገ ወጥ በኾነ እና በአፈሳ በተገኘ ሹመታቸው እየጠሩ የሚያወድሱ፣ የብር ቀፈታቸውን ለሚሞላቸው ሁሉ የጥፋት ብዕራቸውን የሚመዙ ምንደኞች እና ቅጥረኞች /Ghost writers/ ናቸው፡፡ እንግዲያስ ያላወቀ ይወቃቸው፤ ያወቀም ይጠንቀቃችው። እግዚኦ ቦኡ አሕዛብ ውስተ ርስትከ፣ ወአርኰሱ ጽርሐ መቅደሰከ፣ ወረሰይዋ ለኢየሩሳሌም ከመ ልገተ ዐቃቤ ቀምሕ፡፡

       +++++


    ምስል ማቆም የኦርቶዶክስ አብያተ ክርስቲያናት ባህል ነውን?
    (ገብር ሔር ዘመ/መንግሥት)

    “ጌታቸው ዶኒ የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ሕጋዊ ወኪል” በሚል ስም የወጣውን በሐሰት የተሞላ መጣጥፍ ባነበብኩ ጌዜ “ጠላቶችሽ ሁሉ አፋቸውን አላቀቁብሽ እያፍዋጩና ጥርሳቸውን እያፋጩ ውጠናታል ተስፋ ያደረግናት ቀን ይህች ኛት አግኝተናታል አይተናታልም ይላሉ” በማለት ነቢየ እግዚአብሔር ኤርምያስ ስለ ኢየሩሳሌም የተናገረው ኃይለ ቃል ነበር ትዝ ያለኝ (ሰቆ.ኤር.216)፡፡

    በሊቃውንት ተሞልታ የነበረችው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን እነሆ እነዚያ ትንታግ የሆኑ ሊቃውንቶችዋ አልቀው በላይዋ ላይ ወልደ ዶኒን የመሰሉ አራሙቻዎች በቅለውባታል እንኩዋን ሊቀ ካህናት የሚለውን የቤተ ክርስቲያኒቱን ታላቅ የማዕረግ ስም የያዘ ቀርቶ ጨዋ የሚባለው ተራው ምዕመን አሳምሮ የሚያውቀውን የቤተ ክርስቲያኒቱን እምነትና ሥርዓት በማን አለብኝነት ግዚያችን ዛሬ ነው የቤተ ክርስቲያኒቱ ጠበቆች እነ አለቃ አያሌው አረፍተ ዘመን ገትቱዋቸዋል የቤተ ክርስቲያኒቱን ቁንጮም ተቆጣጥረነዋል በማለት ዓለም ያወቀው ፀሐይ የሞቀው የካቶሊክ ና የኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ከሚለያዩበት አንዱ የሆነውን ምስልን ቀርጾ በቤተ ክርስቲያን ማቆምና ለጸሎትና ለሥርዓተአምልኮ መጠቀምን ኦርቶዶክሳዊ ሥርኣት አስመስለው ለመሾም ለመሸለም ብለው በቤተ ክርስቲያኒቱ ቅጽር  አቁመዋል፡፡ያቆሙት የፓትርያርኩ ምስል የቤተ ክርስቲያኒቱን እምነትና ሥርዓት የማይፈቅደው መሆኑን የሚያውቁ የቤተ ክርስቲያኒቱ ልጆች በመቃወማቸውም ይህን የምእመናኑን ተቃውሞ ለማስቆም አስበው ድርጊቱን መጽሐፍ ቅዱሳዊ ለማስመሰል ያልተጻፈውን እንደተጻፈ በማስመሰል ልክ በጥንቆላ ተግባሩ እንደሚያጭበርብረው ሁሉ አሁንም ምዕመኑን በመጽሐፍ ቅዱስ ያልተጻፈን እንደተጻፈ በማድረግ ለማደናገር የሞከረበት ትብታቡ እውነተኛ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን ልጆችን ከእምነታቸው ጋት ያህል ፈቀቅ እንደማያደርጋቸው እምነቴ ቢሆንም ይህ መሳቲና ግብር አበሮቹ የቤተ ክርስቲያኒቱ አስተምህሮ ያልሆነውን እንደሆነ አድርገው በቤተ ክርስቲያኒቱም ውክልናሳይኖራቸው ያላቸው አስመስለው እያቀረቡ ያሉትን የቅሰታ ተግባር በዝምታ ማለፍ የቤተ ክርስቲያን ልጅነቴ ስለማይፈቅድልኝ ይህን ጦማር ልጽፍ ተገድጃለሁ፡፡በቀይ ቀለም የቀለመው ጌታቸው ዶኔ ከተበተበው ትብታብ የተወሰደ መሆኑን ለአንባብያን ማሳወቅ እወዳለሁ፡-

    ዳሩ ግን የቅዱስ ፓትርያርኩ ሐውልት መተከል ከቤተ-ክርስቲያን ሥርዓትና ከመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት አንጻር ተቀባይነት ያለውና ፈጣሪ ያዘዘው መሆኑን ቅዱሳት መጻሕፍት በአንድነት የሚመሰክሩት ነው:: ለእመቤታችን ድንግል ማርያያ ስዕል ፊት ድንግል ማርያምን ያከብራል ይጸልያል ይማጸናል አበው ሊቃነ ጳጳሳት በድንግል ማርያም መልክ ያስቀረጹትን በአንገታቸው ያጠለቁትንም የምስል ውጤት (አይከን) ይስማል ይሳለማል::  የስዕልና የምስል መንፈሳዊ አገልግሎቶች በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን በሰፊው ይታወቃል:: የመስቀል አይነቶች ሁሉ መጠናቸውና ይዘታቸው ይለያይ እንጂ ሁሉም የተቀረጹ የቅርጻ ቅርጽ ውጤቶችና የምስል ዓይነቶች ናቸው::


    የትኛው የኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን የሥርዓት መጽሐፍ ነው ምስልን ለጸሎት ለስርዓተ አምልኮ እንድንጠቀም የሚያስተምረው?በኦርቶዶክስ ካባ ተሰውራችሁ ወደ ቤተ ክርስቲያኒቱ የገባችሁ ካቶሊካውያን ከሆናችሁ ያስኬዳችሁዋል ታጣቂው ካህንና የሥራ ባልደረቦቹ እያተቱልን ያሉት ለቅሰጣ ስለገቡባት ቤተ ክርስቲያን እምነትና ስርዓት ሳይሆን ስለሚያምኑበት የካቶሊክ እምነት ነው፡፡ ታላቁ ሊቅ አለቃ አያሌው የጸሎታቸው በረከት ትድረሰንና አቡነ ጳውሎስን የካቶሊክ እምነት አራማጅ ናቸው በማለት አዘውትረው ይከስዋቸው የነበረው በይሆናል ሳይሆን  በእውነት እንደሆነ በእናንተ በሎሌዎቻቸው አማካይነት የቤተ ክርስቲያንዋ ጠበቃዎች አልቀዋል አሁን ቤተ ክርስቲያንዋ ባድማ ሆናለች በሚል እሳቤ የቤተክርስቲያኒቱን እምነትና ሥርዓት ካቶሊካዊ የማድርግ ተልዕኮአቸውን በአደባባይ እየፈጸሙ ያሉበት ይህ ድርጊታቸው ያረጋግጣል፡፡

    በዚሁ አንጻር የብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስም ሐውልት የሚያሳየው አንድ የስልጣኔ ጮራ እንዳለ ያመላክተናል:: ይህም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ-ክርስቲያን አስተዳደርን ዘመናዊ ለማድረግ በምትሄደው መንገድና አስተዳደራዊ ሥራዎቻቸው ሁሉ ኮምፒተራይዝድ መሆነቸው የሥልጣኔው ተቀዳሚም ተከታይም መሆናቸውን ያመለክተናል::

    በዚሁ አንጻር የቅዱስ ፓትርያርኩን ሐውልት ብናየው ቅዱስ ጳትርያርኩ ገና ብላቴና ሳሉ ለዚህ ቅዱስ መንበርና ኃላፊነት ሲጠሩ የገቡት ቃል በዚህ የዓለምና ዓለማዊ ጥበብና አካሄድ የሞቱ ለጽድቅ ግን ሕያው የሆኑ አካሄዳቸውን ከፈጣሪ ጋር ያደረጉ በመሆናቸው:: የቆመው ሐውልታቸው መታሰቢያነቱ ለሞቱለት የጽድቅና የድንግልና ህይወት ብሎም ለተጠሩለት የፕትርክና አገልግሎት መሆኑ ቅቡል የሆነ ቀኖናዊ ትንታኔ ነው::


    ይህ የለበጣ አነጋገር መሆኑ መቼም ከፓትርያርኩ ይሰወራል ብዬ አላምንም አባብ ለእባብ ይተያያል ካብ ለካብ ነው፡፡ምክንያቱም የቤተ ክርስቲያኒቱ አስተዳደር ከግዜ ግዜ እየባሰበት ሙስና የሰፈነበት ኮምፒውተራይዝድ ሊሆን ቀርቶ ስለ ኮምፒውተር ምንነት አስፈላጊነት ገና እየተወተወተ ያለ መሆኑን ውስጥ አዋቂ ሁሉ የሚያውቀው ነው፡፡ ጌታቸው ዶኔም ሆነ የሥራ ባልደረቦቹ እነ በጋሻው የጥቅም ሰዎች በመሆናቸው አይደለም የነቁ የበቁ ቅዱስ ማለት ውዳሴ ከንቱ እንዳይሆንባቸው ነው እንጂ እርሳቸው እኮ ከኪሩቤል የበለጠ ክንፍ አላቸው ከማለት ወደኋላ የማይሉ ይህን ድርጊታቸውን የቤተ ክርስቲያኒቱ አባቶች ካልተቃወሙ ነገ “ሰው በሕይወት ሳለ ነው እንጂ ማመስገንና ክብሩን መግለጽ ከሞተ በኋላ ምን ጥቅም አለው ብለዋል ቅዱስነታቸው” በማለት ኑ ለቅዱስ አባታችን በሕይወት ሳሉ ጽላት እናስቀርጽላቸው ቤተ ክርስቲያንም በስማቸው እንትከልላቸው ባይሉ ታዘቡኝ፡፡ መቼም አንድ ግዜ ኅሊናው በጥቅም የታወረ ሰው የሚሠራውንም የሚናገረውንም አያውቀውም፡፡

    ሀ. የእሥራኤል ሁሉ አባት ያዕቆብ ገና በህይወት ሳለ ሐውልቱን አቁሟል::


    ያዕቆብ እግዚአብሔር በሕልሙ ተገልጾለት ከነግገረውና ከባረከው በኋላ ሥሙን ቀይሮለታል:: እሥራኤል ብሎ ጠርቶታል ያዕቆብም ሕልሙን ባየበት ሥፍራ ተንተርሶት የነበረውን ደንጊያ መሠረት ባለማድረግ የምስክርነት ሐውልት አስቀምጧል:: (ዘፍ 28÷18′ 31÷45-54)


    ያዕቆብ በሕይወት ሳለ ሐውልቱን አቁJል የሚል ከውሸትም ያለፈ ነጭ ውሸት ማስቀመጥህ መጽሐፍ ቅዱስን ገልጦ የሚያይ የለም ብለህ ይሆን? ያንተንና የመሰሎችህን የርክሰት ስራ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ለማስመሰል አበው ያላለፉበትን የትዕቢት ራስን የማምለክ ሕይወት እንደፈጸሙት አድርጎ ማቅረብ የርክሰት ተግባር ነው፡፡ለነገሩ ዋሽቶ መኖርን የሕይወትህ ዕጣ ክፍል ካደረግህ ካንተ የእወነት ፍሬን መጠበቅ ጌታ ከኩርንችት በለስ አይለቀምም እንዳለው ነው፡፡

    ክርስቶስ በከበረ ደሙ ፈሳሽነት የገዛችሁ ምዕመናን ሆይ የዚህን መሳቲ አጭበርባሪነት የጠቀሳቸውን ጥቆሶች አንብባችሁ ማንነቱን ትረዱ ዘንድ እተወዋለሁ፡፡

    አባታችን ያእቆብ ግን ለምሥክርነት የሚሆን ድንጋይ ሃውልት አድርጎ ማቆሙ ከመገለጹ ውጭ የራሱን ምስል ሐውልት አድርጎ አቆመ የሚል ከቶ በዘፍጥረትም ሆነ በሌላው የመጸሐፍ ቅዱስ ክፍል አልሰፈረም ዘፍ.31፤45፡፡

    በፍኖተ ሎዛም ተንተርሶት የነበረውን ድንጋይ ወስዶ ሐውልት አድርጎ አቆመው ይላል እንጂ የረሱን ምስል ቀርጾ አቆመ የሚል ከቶም አልተጻፈም፡፡ዘፍ.28፤18፡፡

    “የሚያናውጡአችሁ የክርስቶስንም ወንጌል ሊያጣምሙ የሚወዱ አንዳንዶች አሉ”ገላ.1፤7፡፡እንደተባለው ጌታቸው ዶኒና ባልደረቦቹ የመጸሐፍ ቅዱስን ቃል ለገዛ ጥቅማቸው ሲሉ እንዴት እያጣመሙ እንደሚጠቅሱ ከራሳቸው ጽሁፍ ተገንዝበናል፡፡

     በቅዱስ መጽሀፍ ሐውልት ለምልክትነት፣ ለምስክርነትና ለመታወቂያነት ተጠቅሱዋል፡፡በእኛም ሆነ በሌላው ዓለም በሞቱት ምዕመናን መቃብር ላይ ሐውልተ እብን ይቆማል ይህም በያዕቆብ የተጀመረ እንደሆነ ይነገራል ያዕቆብ ለሚሽቱ ለራሄል በመቃብርዋ ላይ ሐውልት እንዳቆመ በመጽሀፍ ተጽፉአል፡፡ዘፍ.35፤20፡፡ጠቀሜታው ይህ የእገሌ መቃብር ነው ተብሎ ለመታወቂያና ለመታሰቢያ እንጂ ሰማያዊ ጥቅምን ያስገኛል ተብሎ አይደለም፡፡ዳሩ ግን በአሁን ዘመን በኢትዮጵያ በአንዳንዳንድ ሙታን መቃብር ላይ እንደሚሰሩት ያለ ጌታ እናንተ ግብዞች ጻፎችና ፈሪሳውያን የነቢያትን መቃብር ስለምትሠሩ የጻድቀንንም መቃብር ስለምታስጌጡ ወዮላችሁ (ማቴ 23÷29) እንዳለ ያለ የቅንጦት ሳይሆን ለምልክትነት ያህል የሚቆም ነው፡፡

    በመሠረቱ በሐውልት፣ በምስልና በሥዕል መካከል ትልቅ ልዩነት መኖሩን መገንዘብ ያሻል አለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌ መጽሐፈ ሰዋሰው ወግስ ወመዝገበ ቃላት ሐዲስ በሚለው መጽሐፋቸው ላይ የሦስቱን ትርጉም በሚከተለው መልክ ገልጸውታል፡-

    ሐውልት፤በቁሙ ትክል ድንጊያ እንደ ዐምድ እንደ ምሶሶ የቆመ ክብነት ምእዙንነት ያለው ለመታሰቢያ የሚተከል የሚነደቀ ወይም ከኖራ ካሸዋ ከስሚንቶ ከድንጊያ ዱቄት ቀላቅለው ደባልቀው እያፈሰሱ የሚሠሩት ፍስ ደንጊያ፡፡(ኪዳነ ወልድ ገጽ436)

    ምስል፤በቁሙ ጣዖት መታሰቢያ ግልፎ ቅርጽ ተመሳሳይ መልክ ያለው የነገር ምሳሌ(ኪዳነ ወልድ ገጽ 613)

    ሥዕል፤በቁሙ መልክ የመልክ ጥላ አምሳል ንድፍ ቢጋር በውሃ በመጽሔት በጥልፍ በስፌት ወይም በቀለም በወረቀት ገዝፎ ተጥፎ ከጽቡር ከእብን ከዕፅ ከማዕድን ታንጦ ተቀርጦ ተሸልሞ አጊጦ የሚታይ የሚዳሰስ ነገር(ኪዳነ ወልድ ገጽ 673)

    ከላይ በተገለጸው መሰረት ምስል ማቆምና ሐውልት ማቆም የተለያዪ ናቸው። ቤተ ክርስቲያናችን ለጸሎት፣ ለትምህርትና ለሥርዓተ አምልኮ ደግሞ ሥዕላትን ትጠቀማለች፡፡

    የኢትዮጵያ ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን እንደ ሌሎቹ አኃት አብያተ ክርስቲያናት ምስልን (three dimensional) የሆነን ቅርጽ ለሥርዓተ አምልኮ አትጠቀምም። በቤተ ክርስቲያን ቅጽርም እንዲቆም አትፈቅድም። ይህ አስተምህሮ ኦርቶዶክሳውያን ከካቶሊካውያን የሚለዩበት አንዱ መለያ ነው፡፡

    ባለ ሽጉጡ ሊቀ ካሕናትና እነዲያቆን በጋሻው በፓትርያርኩ አይዙአችሁ ባይነት በቤተ ክርስቲያቱ ላይ እያነገሱ ያሉት የካቶሊክን ባህል ነው፡፡

    የሚከተለውን ዓይን ያወጣ የጌታቸው ዶኔን ውሸት ትመለከቱ ዘንድ እጋብዛችሁዋለሁ፦      

    ሐ. ከሙሴ ቀጥሎ የእሥረኤልን ሕዝብ ይመራ የነበረው ኢያሱ 12ቱን የእሥራኤል መሪዎች ጠርቶ ገና በሕይወት እያሉ ሐውልት በስማቸውና በቅርጻቸው አቁሞላቸዋል ኢያሱ ይህንን ያደረገበት ምክንያት እግዚአብሔር ጠላቶቹን መትቶለት የዮርዳኖስን ባህር እንደመሬት እየረገጡት በመሻገራቸው ይህ የፈጣሪ እርዳታ ለምስክርነት ይሆን ዘንድ የመሪዎቹን ሐውልት በቦታው ላይ ማለትም በዮርዳኖስ ባሕር ዳርቻ በስማቸውና በቅርጻቸው አቁሞላቸዋል:: (ኢያሱ 4÷1-9)

    መ. የኢያሱ የምስክርነት ሐውልት (ኢያሱ 24÷26) ይህ ብልሁ የእስራኤል መሪ ኢያሱ አገልግሎቱን የሕጉንና የአስተዳደር ሥርዐቱን ለሕዝቡ ሊሰጥና ከሕዝቡ ጋር ቃል ኪዳን ሲያደርግ እርሱ ገና በሕይወት እያለ በራሱ ስምና ምስል ሐውልት አሠርቶ በእግዚአብሔር ቤት ደጅ ለምስክርነት አቁሞታል::


     የእንጀራ ከፋቻችሁን የአቡነ ጳውሎስን ምስል ለማቆም ኢያሱ ያላቆመውን ምስሉንና የመሪዎቹን ምስል ሐውልት አድርጎ አቆመ ብላችሁ መዋሸት ምን ይባላል?

    ስለሆነም ይህንን የመጽሐፍ ቅዱስ መመሪያንና ትምህርትን መሠረት በማድረግ ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ-ክርስቲያን ጋር ሕብረት ያላቸው አሐት አብያተ ክርስቲያነት ግብፅ ሕንድ አርመንና ሶርያ የሃይማኖት መሪያቸውን መልክ በሰውነታቸው በመነቀስ በመቀለምና በመወቀር ብሎም ገና በሕይወታቸው እያሉ ሐውልታቸውን በማቆም በታሪክ ቀዳሚዎች ናቸው::

     እስቲ የየትኛቸው አብያተ ክርስቲያናት መሪዎች ምስል ነው በሕይወት ሳሉ በቤተ ክርስቲያናቸው ተቀርጾ የቆመላቸው? የአንዳቸውን ስም ሊጠቅሱልን እንኳን አልቻሉም ከላይ በመጽሐፍ ቅዱስ እንደተጻፈ በማስመሰል ሊያታልሉ እንደሞከሩት ያለ ነጭ ውሸት በመሆኑ ነው፡፡ከእነዚህ አብያተ ክርስቲያናት ግን የአንዳቸውም መሪ በህይወት ሳሉ ምሳላቸውን እንዳቆሙ ከጌታቸው ዶኒ በስተቀር ቆመላቸው የተባሉትም ጭምር አንዳች የሚያውቅ ሰው የለም፡፡



    ዘሪሁን ሙላቱ፦ የፓትርያርኩና የማፊያው ቡድን “ስውር ፀሐፊ” (Ghost Writer)

    Friday, July 16th, 2010

    (ደጀ ሰላም፤ ጁላይ 15/2010)፦ Ghost Writer የሚለው የእንግሊዝኛ ቃል “ስውር ፀሐፊ” የሚለው ቃል ሙሉ በሙሉ አይተካውም። ነገር ግን በደምሳሳው(A ghostwriter is a professional writer who is paid to write books, articles, stories, reports, or other texts that are officially credited to another person. Celebrities, executives, and political leaders often hire ghostwriters to draft or edit autobiographies, magazine articles, or other written material.)  (Ghost Writer) ማለት በሌላ ሰው ስም ለሚታተም ነገር ገንዘብ እየተቀበለ ክሽን ያለ ጽሑፍ የሚጽፍ ሰው ማለት ነው። “ስውር ፀሐፊነት” ሙያ እንጂ ወንጀል አይደለም። በአገራችን ይህ “ስውር ፀሐፊነት” የተለመደ ባይሆንም ቤተ ክህነቱ አሁን እየተጠቀመበት ነው። ችግሩ ለበጎ ተግባር ሳይሆን ለጥፋት መሆኑ ነው። ቤተ ክህነቱ የሚጠቀምበት ግንባር ቀደም “Ghost Writer” ዘሪሁን ሙላቱ ይባላል።
    ዲያቆን ሲባል ቆይቶ በቅርቡ ሊቀ ትጉሃን የሚል የማዕረግ ስም ደርቧል። ለዚህ “ኢትዮጵያዊ Ghost Writer” ጠቀም ያለ ብር የሚከፍሉት ደግሞ ቅዱስ ፓትርያርኩ እና “የማፊያው ቡድን” የሚባለው በቤተ ክህነቱ ውስጥ የተወሸቀው የዝርፊያ  ቡድን ነው።Ghost Writer ዘሪሁን ሙላቱ “የሚታወቅባቸው ሥራዎቹ” በሙሉ ፓትርያርኩን የሚያጸድቁ እና ሌሎችን የሚያንቋሽሹ ሲሆኑ ከነዚህም ውስጥ ሁለቱ ዋነኛ መጽሐፎቹ ለዲ/ን በጋሻው “የመስቀሉ ሥር ቁማርተኞች” መልስ የሰጠበት “የስድብ አፍ” እና ብፁዕ አቡነ ሳሙኤልን “የሚያዋርድ” ስድብ ያሳተመበት መጽሐፉ ናቸው። የመጀመሪያውን መጽሐፉን በጻፈበት ወቅት ቅ/ፓትርያርኩ 60 ሺህ ብር ጥሬ ገንዘብ እንደሰጡት ውስጥ አዋቂዎች ይናገራሉ። መጽሐፉንም እያንዳንዱ ቤተ ክርስቲያን በግድ እየወሰደ እንዲያከፋፍል፣ ካህናቱም በነፍስ ወከፍ እያንዳንዳቸው አምስት አምስት እንዲወስዱና እንዲሸጡ፣ ገንዘቡ ግን ከደሞዛቸው በግድ እንዲቆረጥ ተደርጎ ነበር።  ይህ ግለሰብ በቀደም ዕለት በተደረገው ሽልማት ላይ ስለዚሁ ስውር ሥራው (ከነ ዲ/ን በጋሻው ጋር) ከቅዱስ ፓትርያርኩ እጅ በአደባባይ ሽልማት ተበርክቶለታል።

    Ghost Writer ዘሪሁን ሙላቱ የሚጽፋቸው ጽሑፎች ተጠቃሚ ከሆኑት ግለሰቦች አንዱ በስሙ በየጋዜጣው ጽሑፍ የሚያሳትመው “ባለ ሽጉጡ ቄስ” ሊቀ ካህናት ጌታቸው ዶኒ ነው። ሊቀ ካህናት ጌታቸው “የመንበረ ፓትርያርክ የጠቅላይ ቤተ ክህነት ሕጋዊ ወኪል” በሚለው ማዕረጉ ይታወቃል። በየጋዜጣው የሚጽፋቸው ጽሑፎች ግን የዘሪሁን ሙላት ናቸው። ሊቀ ካህናት ጌታቸው በፓትርያርኩ የሐውልት ምረቃ ወቅት ባቀረበው ሪፖርት ላይ በየመካከሉ የተጠቀሱትን የእንግሊዝኛ ቃላት ለማነበብ ሲቸገር ላየ ሰው ጽሑፉ የእርሱ አለመሆኑን ይረዳል። ጽሑፉማ የዘሪሁን ነው። ይኸው አሳዛኝ ግለሰብ በሰሞኑ በፓትርያርኩ ላይ የተነሣውን ተቃውሞ ለማብረድ ከዘሪሁን እየተዘጋጁ የሚመጡለትን ጽሑፎች በየጋዜጣው ለማሳተም በዝግጅት ላይ ነው። የደጀ ሰላም ውስጥ አዋቂዎች ከሰሞኑ በየጋዜጣው ሊወጡ ከተዘጋጁት ጽሑፎች መካከል ባለ 14 ገጽ የሆነ አንድ ጽሑፍ አግኝቶ ለመመልከት ችሎ ነበር። የዚህ ጽሑፍ ምንጭ “ከኮምፒውተር አድራሻው” ላይ እንደሚያመለክተው “Zer8.doc” በሚል ከዘሪሁን ዶኩመንቶች መካከል የወጣ ሆኖ ተገኝቷል። ዘሪሁን “የፋይሉን ስም (File Name)” ሳያስተካክል ነበር የላከው። ፀሐፊው ተብሎ የተጠቀሰው ግን “ሊቀ ካህናት ጌታቸው የመንበረ ፓትርያርክ የጠቅላይ ቤተ ክህነት ሕጋዊ ወኪል” ተብሎ ነው።

    ጽሑፉ በአጭሩ ፓትያርኩን የሚያሞግስ፣ ሐውልት አስፈላጊ ብቻ ሳይሆን መጽሐፍ ቅዱሳዊ እና ኦርቶዶክሳዊ መሆኑን ለማስረዳት የሚሞክር፣ የዚህ የሐውልት ሥራ ተቃዋሚዎች ናቸው የሚላቸውን ሰዎች “ሰይጣኖች” ብሎ የሚያወግዝ፣ ዲ/ን በጋሻውን ከፍ ከፍ የሚያደርግ ነው። ትናንት በጋሻውን እንዳይሸጥ እንዳይለወጥ አድርጎ በሰደበበት ብዕሩ አሁን ደግሞ ሰማየ ሰማያት ያደርሰዋል። ሰሞኑን እንዳልነው “ገንዘብ ተቀብሎ ስለ እግዚአብሔር የሚሰብክ የበለጠ ገንዘብ ከተሰጠው ስለ ሰይጣንም ይሰብካል” ነው ነገሩ።

    የፖለቲካ ልሒቃን “በፖለቲካ ውስጥ ዘላቂ ወዳጅነት እና ዘላቂ ጠላትነት የለም” እንደሚሉት አሁን ደግሞ ቤተ ክርስቲያንን በመዝረፉ ውድድር ውስጥ ዘላቂ ጠላትም፣ ዘላቂ ወዳጅም የለም። በጋሻው ትናንት ስለ ፓትርያርኩ ሲጽፍ “በፕትርክና ዘመንዎ ሁሉ፣ አልታዘዝ ባሉት አብያተ ክርስቲያናትና ገዳማት ላይ እንደ ጦር ጄኔራል ጦር ዚያዘምቱ፣ ቆመጥና ጥይት የያዙ ወታደሮች ሲበትኑ ሰነበቱ” ብሎ ነበር። ዛሬ ደግሞ ኢ-ኦርቶዶክሳዊ ይትባህል ይዞ ሐውልት ያስገነባላቸዋል። ምክንያቱም በዝርፊያ ውስጥ “ዘላቂ ወዳጅነትም፣ ዘላቂ ጠላትነትም” የለማ። ዘሪሁን በብዕሩ ያሞግሰዋል፣ ፓትርያርኩም በሽልማት ያምነሸንሹታል። በዚህ ሁሉ መካከል የሚጎዳው ግን የዋሁ ምዕመን፣ እያንዳንዳችን የመንፈሳዊነት ሕይወት እና እናት ቤተ ክርስቲያን ናት።

    “ስውሩ ፀሐፊ” ዘሪሁን በሊቀ ካህናት ጌታቸው ዶኒ ስም፣ በፓትርያርኩ ቡራኬ የሐውልትን ትምህርት፣ የምስልን ኦርቶዶክሳዊነት እየሰበኩ ነው። ሊቃውንቱስ ምን ይሉ ይሆን? ነው ወይስ ሳናውቀው እምነታችን ተቀይሮ ይሆን?



    ቅን የተዋሕዶ መሪ

    Friday, July 16th, 2010

    (ደጀ ሰላም፤ ጁላይ 15/2010)፦

    አንተ ኖላዊ ሰው ትጉሁ እረኛ
    በበር የገባኸው ያልሆንከው ቀማኛ
    እግዚአብሔር የላከህ አንተ ደግ እረኛ
    እውነተኛ ፈራጅ አንት የፍቅር ዳኛ፤
    ከበረት ለወጡት ለጠፉት በጎችህ
    ፈጥነህ ድረስልን ታደገን በበትርህ።

    አንተ ደግ ዳኛ ባለ ቀጭን ዘንጉ
    ዘመንህ መቼ ይሆን የምትመጣበቱ
    እግዚአብሔር የላከህ አንተ ደግ እረኛ
    እውነተኛ ፈራጅ አንት የፍቅር ዳኛ?
    ላክልን ጌታችን ተክለ ሃይማኖትን
    በወንጌሉ ያጽናን በጸሎት ያድነን፤
    ላክልን ጌታችን አባ ጊዮርጊስን
    ሰዓሊ ለነ ብሎ ከጌታ ያስታርቀን፤
    ላክልን ጌታችን ቅዱስ ያሬድን
    “ፍቅር ሰሐቦ” ብሎ እንዲያስተምረን፤
    ላክልን ጌታችን ፍሬምናጦስን
    የሰላሙን አባት ከሳቴ ብርሃን፤
    ላክልን ጌታችን ተክለ ሃይማኖትን
    ቀጭኑን ፓትርያርክ ጫማ ‘ማያውቀውን፤
    ላክልን ጌታችን ጎርጎርዮስ ካልዕን
    የዝዋዩን መናኝ ባህታዊ ምሁሩን፤
    ተዋሕዶ ተጣራች ተጋልጣ እርቃኗን
    ልጇ ቢቀድባት ቀሚስ ነጠላዋን፤
    አትናቴዎስ ተነሥ ቁም ተሟገትላት
    ቄርሎስም ተነሣ ጥብቅና ቁምላት፤
    ዮሐንስ አፈወርቅ ድርሳኑን ጻፍላት
    ዲዮስቆሮስ ተነሥ ጥርስህ ይርገፍላት፤
    ጊዮርጊስ ተቀበል ሰማዕትነቱን
    በመጋዝ መሰንጠቅ በጦር መወጋቱን፤
    ባስልዮስም ጥራው ቅዱስ ኤፍሬምን
    ለተዋሕዶ ያልቅስ ይዝጋ በዓቱን፤
    ማኅበረ ሥላሴ ዋልድባም ተናገር
    ጣና ቂርቆስ ፈክር የተዋሕዶን ነገር፤
    አክሊላችን ወድቋል ከራሳችን ወርዶ
    ክብርም ሸሽታለች ከጽድቅ ወዲያ ማዶ፤
    ያን ደግ ኖላዊ ቅን የተዋሕዶ መሪ
    ያን ደግ እረኛ ላክልን ፈጣሪ።