ኢትዮጵያን ለማጥፋት የሚደረግ ደባ፣


መረጃ ቲቪ አባል በመሆን የሳተላይት ቲቪውን ቀጥታ ስርጭት፣ ወቅታዊ ዜናዎችን እና ትንተናዎችን፣ የመዝናኛ ፕሮግራሞችን፣ ስፖርት እና ሌሎችንም ዝግጅቶቻችንን በፍጥነት እና ጥራት ስልክዎ፣ ኮምፒዩተርዎ ወይም ቲቪዎ ላይ ማየት ይችላሉ። እዚህ ሊንክ ላይ በመጫን አባል ይሁኑ


ከፕሮፌሰር አለማየሁ ገብረማርያም 

ትርጉም በነጻነት ለሀገሬ

ለአራት አስርት ዓመታት እራሱን ህዝባዊ ወያኔ ሀርነት ትግራይ (ህወሀት) እያለ የሚጠራው እና በአሁኑ ጊዜ በኢትዮጵያ ህዝብ ጫንቃ ላይ ከህዝብ ፍላጎት ውጭ በኃይል በስልጣን ወንበር ላይ ተፈናጥጦ የሚገኘው የወሮበላ የማፊያ ቡድን ኢትዮጵያን ለማጥፋት ቀጣይነት ያለው እና የማያቋርጥ የፖለቲካ፣ የማህበራዊ እና የባህል ጦርነት በመክፈት ዕቅድ አውጥቶ በመንቀሳቀስ ላይ ይገኛል፡፡ የህወሀት ኢትዮጵያን የማጥፋት ተልዕኮው እና ፍልስፍናው የተመሰረተው በተወሰኑ የአፈጻጸም ስልቶች፣ ፖሊሲዎች፣ የድርጊት መርሀ ግብሮች እና ተሞክሮዎች ላይ ሲሆን በዋናነት የሚከተሉትን የአፈጻጸም ስልቶች ያካትታል፣ 1ኛ) የኢትዮጵያውያንን/ትን ብሄራዊ ማንነት በጠባብ እና በጎሳዊ አመላካከት ተክቶ በመከፋፈል ኢትዮጵያውያን/ት ያሏቸውን የማህበራዊ የጋራ ልምዶች፣ የህዝቡን የተከበሩ እሴቶች፣ እምነቶች እና ልማዶች ፍጹም በሆነ መልኩ እንዲወገዱ አበርትቶ መስራት፣ 2ኛ) የተለያዩ ዕኩይ የተግባር ስልቶችን እና ዕቅዶችን በማዘጋጀት ሀገሪቱን መከፋፈል፣ መሸጥ፣ መገንጠል እና መገነጣጠል፣ የወያኔ ኢትዮጵያን የማጥፋት ፍልስፍና እና ዕቅዶች ዓላማ አድርገው የተነሱት ኢትዮጵያ ተብላ የምትጠራዋን የአንጸባራቂ ታሪክ ባለቤት የሆነች ሀገር በማስወገድ ጭራቃዊነት በሆነ መልኩ በተጸነሱ፣ ለእኩይ ምግባር ፍጻሜው በጥንቃቄ በታቀዱ እና እነዚህን መሰሪ ዕቅዶች ስልታዊ በሆነ መልኩ ተግባራዊ በማድረግ በመጨረሻ በወያኔ ምናብ የተፈበረከች በጎሳ ተበጣጥሳ እና ተጣማ በተሰራች ደካማ ሀገር ለመተካት ነው፡፡ ወያኔ ኢትዮጵያን የማጥፋት ተልዕኮውን እ.ኤ.አ ከ1991 ጀምሮ በይፋ እና ግልጽ በሆነ መልኩ መተግበር ጀመረ፡፡    

የወያኔ ኢትዮጵያን የማጥፋት ፍልስፍና፣

ወያኔ ኢትዮጵያን ለማጥፋት የሚጠቀምበት ዋናው ፍልስፍናው ምንድን ነው?

ለዚህ ጥያቄ መልሱ ከቀድሞው የህወሀት የገንዘብ ኃላፊ እና ቁልፍ አመራር ሰጭ ከነበረው እና ድርጅቱን በመልቀቅ እራሱን በመለየት ከፍርሀት ነጻ ሆኖ ለድርድር የማይቀርበውን ኢትዮጵያዊ እውነት ተናጋሪ ከሆነው ገብረመድህን አርዓያ አንደበት ግልጽ በሆነ እና በማያሻማ መልኩ ቁልጭ ብሎ ይገኛል፡፡ በጣም ልዩ በሆነ የቪዲዮ ቃለመጠይቅ ተደርጎ እና በዩቱቤ ድረ ገጽ በተለቀቀው (ከዚህ በታች የተዘረዘሩትን ከአማርኛው ትርጉማቸው ወደ እንግሊዝኛ ቋንቋ የመለስኳቸውን) ጽሁፍ ላይ ገብረመድህን ህወሀት ስልታዊ በሆነ መልኩ የኢትዮጵያን የብሄራዊ ማንነት፣ ታሪክ እና እምነት ለማጥፋት የሚከተሉትን አራት የፍልስፍና ምሰሶዎች እየተቀመ እንዳለ ግልጽ አድርጓል፡፡ እነርሱም፣

1ኛ) ኤርትራ የኢትዮጵያ ቅኝ ግዛት ናት፡፡ ኤርትራ የበለጸገች ሀገር ናት፡፡ ኤርትራ ከኢትዮጵያ በፊት ቀድማ የነበረች ሀገር ናት፡፡ ኢትዮጵያ በንጉስ ምኒልክ የተፈጠረች ሀገር ናት፡፡ ኢትዮጵያ የሚለው ስም አይታወቅም፡፡ ኢትዮጵያ ታሪክ የላትም፣ ምንም፤

2ኛ) ትግራይ በዓጼ ምኒሊክ ተወርራ እና የአማራ ቅኝ ግዛት የነበረች እራሷን የቻለች ነጻ ሉዓላዊ ሀገር ናት፡፡ ትግራይ የአማራ ቅኝ ግዛት ናት፡፡ ይኸ ነው እንግዲህ በህወሀት መመሪያ በሆነው ማኒፌስቶ (ማኒፌስቶው በቪዲዮው እንደተመለከተው) በግልጽ ተቀምጦ የሚገኘው፡፡ (ዋናውን እና በፒዲኤፍ ፎርማት በእጅ የተጻፈውን የህወሀትን ማኒፌስቶ ለማንበብ እዚህ ጋ ይጫኑ፣ በመስመር ላይ ለማግኘት ደግሞ እዚህ ጋ ይጫኑ)፡፡ ስለሆነም ትግራይን ከአማራ ቅኝ ተገዥነት ነጻ ማውጣት አለብን፡፡ እናም የትግራይን ሬፐብሊክ መመስረት አለብን፡፡

3ኛ) አማራ የትግራይ ህዝብ ጠላት ነው፡፡ አማራ አንድ ጠላት ብቻ አይደለም፣ ሆኖም ግን ድርብ ጠላት ነው፡፡ ስለዚህ አማራን መደምሰስ አለብን፡፡ አማሮችን ልናጠፋቸው ይገባል፡፡ አማራ እስካልጠፋ፣ እስካልተሸነፈ እና ከመሬት ላይ እንዲጸዳ (የዘር ማጥፋት እርምጃ እስካልተወሰደበት ድረስ ለማለት መሆኑን ልብ ይሏል) እስካልተወሰደበት ጊዜ ድረስ ትግራይ በነጻነት ልትኖር አትችልም፡፡ እኛ አሁን እንዲፈጠር ለምንፈልገው መንግስት አማራ ዋና መሰናክል ነው፡፡

4ኛ) ኢትዮጵያ በሚኒልክ የተፈጠረች ሀገር በመሆኗ እና የተፈጠረችውም በምኒልክ ወረራ በመሆኑ ከዚህም ጋር ተያይዞ በምኒልክ የተወረሩ ብዙ ብሄር ብሄረሰቦች እና ህዝቦች ስላሉ እነዚህ ህዝቦች አሁን ኢትዮጵያ እየተባለች ከምትጠራዋ ሀገር ነጻነታቸውን ማግኘት አለባቸው፣ እናም የእራሳቸውን ነጻ ሉዓላዊ ሀገር መመስረት አለባቸው፡፡ (ጎሳዎችን ሁሉ ገነጣጥለው እራሳቸውን የቻሉ ነጻ ሉዓላዊ ሀገር ለማድረግ የሚያደርጉትን ጥረት ልብ ይሏል!) ኢትዮጵያ በመባል የምትታወቀው ሀገር አዲስ ናት፡፡ እንዲያውም ከ100 ዓመት በላይ እድሜ የላትም፡፡ ይህች ሀገር መደምሰስ አለባት፡፡ መጥፋት አለባት፡፡ ብሄሮች እና ብሄረሰቦች የእራሳችንን መንግስት ማቋቋም አለብን፡፡ ኤርትራ ነጻነቷን ማግኘት አለባት፡፡ የትግላችን ዋናው መሰረቱም ይኸው ነው ነው እያሉ ያሉት እነዚህ የዕኩይ ምግባር እና የሰይጣናዊ መንፈስ አራማጆች፡፡   

ህወሀት እንደ ድርጅት ወይም ደግሞ በስልጣን ላይ ያሉት አመራሮቹ፣ ወይም ከስልጣናቸው ገለል የተደረጉት፣ ወይም ደግሞ ከስልጣናቸው በጡረታ ተገለሉት እስከ አሁን ድረስ ይህንን የህወሀት ማኒፌስቶ በመባል የሚታወቀውን ሰነድ በጋራ ወይም ደግሞ በተናጠል እየቀረቡ ስለሰነዱ ህጋዊነት ማስተባበያ ሳይሰጥ ወይም ደግሞ በይዘቱ ላይ ማሻሻያ ሳይደረግ ዝም ብሎ ተቀምጦ እንደሚገኝ ማስታወስ ተገቢ ነው፡፡ ማኒፌስቶው በአሁኑ ወቅትም የህወሀት መመሪያ እና የፍልስፍናው መሰረት ሆኖ በማገልገል ላይ ይገኛል፡፡

ኢትዮጵያን የማጥፋት ተልዕኮው እንዴት እንደሚሰራ፣

ለአስርት እና ከዚያ በላይ ዓመታት የዘለቀው የህወሀት ኢትዮጵያን የማጥፋት ተልዕኮ ዘርፈብዙ በሆኑ ስልታዊ ግንባሮች የተለያዩ አቀራረቦችን በመጠቀም በመተግበር ላይ ይገኛል፡፡ ኢትዮጵያን የማጥፋት ስልቱ በጣም ውስብስብ የሆነ እና የፖለቲካዊ ጦርነቱ ከባህል፣ ከማህበራዊ እና ከስነልቦናዊ ጦርነት ጋር ታዋህዶ በመተግበር ላይ ይገኛል፡፡ በዚህ በአሁኑ ትችቴ ላይ ሶስቱን ዋና ዋና የማስፈጸሚያ ስልቶች ብቻ (ሌሎች ተመሳሳይ ስልቶች በሚቀጥሉት ትችቶቼ የሚቀርቡ ይሆናል) የምንዳስስ ይሆናል፡፡ እነዚህም ስልቶች የሚከተሉት ናቸው፡፡ 1ኛ) የኢትዮጵያን ታሪክ እርባናየለሽ ማድረግ እና የኢትዮጵያን ባለታሪክ መሪዎች ስም ጥላሸት መቀባት፣ 2ኛ) “አማራን” እና “የአማራን” ህዝብ ስም ጥላሸት መቀባት፣ 3ኛ)  ኢትዮጵያን መከፋፈል፣ መገነጣጠል እና መሸጥ እንዲሁም የኢትዮጵያን የግዛት አንድነት እና ሉዓላዊነት መከፋፈል እና ማዳከም ዋና ዋናዎቹ ናቸው፡፡ እነዚህን የማስፈጸሚያ ስልቶች ከዚህ ቀጥሎ በዝርዝር እንመለክታለን፡፡

1) የኢትዮጵያን ታሪክ እርባናየለሽ ማድረግ እና የኢትዮጵያን ባለታሪክ መሪዎች ስም ጥላሸት መቀባት፣

ከወያኔ ኢትዮጵያን የማጥፋት ተልዕኮ የመጀመሪያ መሳሪያ ማስፈጸሚያ ስልት ሆኖ የቀረበው ታሪካዊት ኢትዮጵያ የምትባል ሀገር እንደሌለች ሽምጥጥ አድርገው መካድ እና የቀድሞ የኢትዮጵያ መሪዎችን ስም ጥላሸት መቀባት እና የንቀት ትችትን ማቅረብ ነው፡፡ ለወያኔ ኢትዮጵያ ከመቶ ዓመታት የማይበልጥ ብቻ ታሪክ ያላት የፖለቲካ ህልው ናት፡፡ በወያኔ ተምኔታዊ ሀሳብ መሰረት ኢትዮጵያ በ19ኛው ክፍለ ዘመን መጨረሻ አካባቢ በዓጼ ሚኒልክ ተጠፍጥፋ የተፈጠረች የፖለቲካ መልካምድራዊ ህልው ናት፡፡ የወያኔ ትረካ ምኒልክ ጨካኝ ጦረኛ የነበሩ እና ጎረቤት የሆኑ ብሄሮችን እና ብሄረሰቦችን በጦር ኃይል ድል በማድረግ ለማስገበር እና የአማራን ግዛት ለመፍጠር በመንገዳቸው ላይ ያገኙትን ሁሉንም ነገር በመምታት እና በማቃጠል ላይ ትኩረት አድርገው የሰሩ እደነበሩ አድርገው ያስቀምጣሉ፡፡ ለወያኔ እና አሁን በህይወት የሌለው የወያኔ የክርስትና አባት የሆነው መለስ ዜናዊ “የሀበሻ ህዝቦች ሀገር” እየተባለች የምትጠራው ኢትዮጵያ (ወይም ደግሞ የአቢሲኒያ ህዝብ) የምትባለው ሀገር ወይም በግዛት ስፋቷ ኢትዮጵያ ተብላ የምትጠራው ሀገር አሁን ከሚኖረው ህዝብ ጋር ትንሽ ወይም ደግሞ ምንም ዓይነት ግንኙነት የሌላቸው ህዝቦች አድርጎ ያወራል፡፡

እንደዚህ ያለ የደናቁርት ታሪክን የመበረዝ እና የመከለስ እንዲሁም ታሪክን አዛብቶ የማቅረብ አባዜ የወያኔን ጭፍን አምባገነናዊነት ያመላክታል፡፡ እንደ ወያኔ ታሪክ ከሆነ በብሉይ ኪዳን በደርዘኖች የሚቆጠሩ እና በአዲስ ኪዳን ቢያንስ አንድ ዋቢ ማጣቀሻ ማስረጃዎች ኢትዮጵያ እና ኢትዮጵያውያን/ት መኖር አሁን በመኖር ላይ ላሉት ወይም ኢትዮጵያ ለምትባለው ምድር ምንም ነገር ማለት እንዳልሆነ ይገልጻል፡፡ በዘፍጥረት (2፡13) እንዲህ የሚል ቅዱስ ቃል ተጽፎ ይገኛል፣ “የሁለተኛውም ወንዝ ስም ጊዮን ነው፡ እርሱም የኢትዮጵያን ምድር ሁሉ ይከብባል፡፡“  በዘሁልቁ (12፡1) እንዲህ የሚል ቅዱስ ቃል ተካትቶ ይገኛል፣ “ሙሴም ኢትዮጵያይቱን  አግብቷልና፣ ባገባት በኢትዮጵያይቱ ምክንያት ማርያምና አሮን በእርሱ ላይ ተናገሩ፡፡”  እንደዚሁም በመዝሙረ ዳዊት (68፡31) እንዲህ የሚል ቅዱስ ቃል አለ፣ “ልዕልቶች ከግብጽ ይወጣሉ፣ ኢትዮጵያ እጆቿን ወደ እግዚአብሄር ትዘረጋለች፡፡“ እንደ ወያኔ ከሆነ ሁሉም የብሉይ ኪዳን ማስረጃዎች ሁሉ ተምኔታዊ (በእውን ተፈጥራ ላለች ሳይሆን በሀሳብ ተፈጥራ ላለች) ለሆነች ሌላ ኢትዮጵያ ነው፡፡ ሁሉም በመጽሐፍ ቅዱስ የተጠቀሱት ማስረጃዎች ሁሉ በወያኔ አመላካከት በአሁኑ ጊዜ ላለችው ኢትዮጵያ እየተባለች ለምትጠራ ሀገር ወይንም ደግሞ አሁን ኢትዮጵያ እየተባለች በምትጠራ ሀገር ለሚኖሩ ህዝቦች ቀደምት ትውልድ ምንም ዓይነት አስፈላጊነት የሌለው ነገር ነው፡፡      

በተመሳሳይ መልኩ ለወያኔ አሁን ያለችው ዘመናዊቷ ኢትዮጵያ ከጥንታዊ የአክሱም ግዛት (ከክርስቶስ ልደት በፊት ከ3ኛው-6ኛው ክፍለ ዘመን) ጋር ምንም ዓይነት ግንኙነት እና መስተጋብር የላትም፡፡ አክሱም ለኢትዮጵያ እና ለኢትዮጵያውያን/ት ሁሉ ልዩ የሆነ ጠቃሚነት ያለው የታሪክ አሻራ ቦታ ነው፡፡ አክሱም አሁን ላለችው ኢትዮጵያ የፖለቲካ መሰረት መሆኑ የሚያጠራጥር ጉዳይ አይደለም፡፡ አክሱም በብዙ ኢትዮያውያን/ት እና ኢትዮጵያዊ/ት ባልሆኑ ወገኖች በአፈታሪክ እንደሚነገረው ሁሉ የንግስተ ሳባ መናገሻ ከተማ ነበር ይባላል፡፡ የአክሱሙ ንጉስ ኢዛና ከክርስቶስ ልደት በኋላ በ4ኛው ክፍለ ዘመን የክርስትና ኃይማኖት የመንግስት ኃይማኖት እንዲሆን አድርገዋል፡፡ በአሁኑ ጊዜ በሀገሪቱ የሚገኙ በአስር ሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ኢትዮጵያውያን/ት የክርስትና ኃይማኖት እምነት ተከታዮች አክሱምን ሁለተኛው ቅዱስ እየሩሳሌም አድርገው ይቆጥራሉ ምክንያቱም አስርቱ ትዕዛዛት የተጻፉበት ጥርብ ድንጋይ ያለው በአክሱም ጽዮን ውስጥ ነው ተብሎ ስለሚታመን ነው፡፡ በወያኔ ታሪክ መሰረት ይኸ ሁሉ በሙሉ ልብወለድ ታሪክ ነው፡፡ ይህ ጉዳይ አሁን ካለችው ኢትዮጵያ እና ኢትዮጵያውያን/ ጋር ምንም ዓይነት ግንኙነት የለውም፡፡

ከክርስቶስ ልደት ከ615 በፊት በእስልምና እምነት ተከታዮች ላይ ይደርስ የነበረውን ማሰቃዬት ለመከላከል ሲባል በነብዩ መሀመድ ወደ አክሱም ጥገኝነትን እንዲያገኙ የተላኩትን የመጀመሪያውን የእስልምና ኃይማኖት እምነት ተከታይ ስደተኞች (የመጀመሪያ ስደት/First Hijira) ተቀብለው ያስተናገዱት እና ድጋፍም ያደረጉላቸው በወቅቱ የነበሩት የአክሱም ንጉስ ነበሩ፡፡ ነብዩ መሀመድ ያንን የጥሩ ተምሳሌት ጊዜ መዝግበው በመያዝ ለአክሱሙ ንጉስ እና ለሀበሻ ህዝቦች ከፍተኛ የሆነ ምስጋና አቅርበዋል፡፡ ይህንን በጎ ምግባር በአስተምህሮ ስብስባቸው ውስጥ በማስገባት ነብዩ መሀመድ እንዲህ ብለው ነበር፣ “እራሳቸው ጥቃት እስካልሰነዘሩ ድረስ ሀበሾችን ተዋቸው፣ እዳትነኳቸው!“ እንደወያኔ የወሮበላ ማፊያ ቡድን ከሆነ ይህ ሁሉ ተጨባጭ ታሪክ ልብወለድ ድርሰት ነው፡፡ ለወያኔ ነብዩ መሀመድ ስለሀበሻ ህዝቦች የተናገሩት ሁሉ አሁን ካለችው ኢትዮጵያ እና ኢትዮጵያውያን/ ጋር ምንም ዓይነት ግንኙነት የለውም፡፡ 

የ18ኛው ክፍለ ዘመን የእንግሊዝ የታሪክ ምሁር የነበሩት ኤድዋርድ ጊቦን “የሮማውያን የግዛት ድክመት እና አወዳደቅ“ በሚል ርዕስ በጻፉት ታዋቂ የታሪክ ስራቸው እንዲህ ብለው ነበር፣ “በኃይማኖታቸው ምክንያት ኢትዮጵያውያን/ት በሁሉም አቅጣጫ በጠላት በመከበባቸው ለአንድ ሺህ ዓመታት ገደማ ያህል የረሳቸውን የዓለም ህዝብ እነርሱም እረስተውት ተኝተው ቆይተዋል፡፡“ እንደ ወያኔ ከሆነ ጊቦን ተራ አፈታሪክ ነው የጻፈው እና የተረከው፡፡ አሁን በህይወት የሌለው መለስ ዜናዊ እ.ኤ.አ በ1993 ኢትዮጵያ የ100 ዓመት እድሜ ነው ያላት ብሎ ተናግሮ ነበር ፡፡ ያለዚያ ከምንም ተነስተው ምንም ነገር ሳያገናዝቡ እራሳቸውን አዋቂ አድርገው የሚቆጥሩ ደናቁርት እብሪተኞች አፈታሪክ የሚያወሩ እንጅ የታሪክ ሰዎች አይደሉም፡፡

እ.ኤ.አ በ1896 ኢትዮጵያ በአድዋ ጦርነት ላይ በኢጣሊያን ወራሪ ኃይል ላይ የተቀዳጀችው አንጸባራቂ ድል በአፍሪካ ታሪክ ውስጥ እጅግ በጣም ጠቃሚ ወቅት ሆኖ ተመዝግቧል፡፡ የአድዋ ድል በአፍሪካ ታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ የአፍሪካ ጥቁር ወታደር ኃያል የሆነውን የአውሮፓን ነጭ ኃይል አንጸባራቂ በሆነ መልኩ ድል አድርጎ ከግዛቱ ያስወጣበት ድል ነው፡፡ ከሁሉም በላይ በጣም የሚያስደንቀው ነገር ደግሞ የአውሮፓ ኃያላን አገሮች አፍሪካን እንደ ቅርጫ ስጋ ለመቀራመት እና በ10 ዓመታት ጊዜ ውስጥ ሁሉንም የአፍሪካ አገሮች ሙሉ በሙሉ ለመቆጣጠር ደባ ለመሸረብ የበርሊን ጉባኤን ባከሄዱ ሁለት ዓመታት ጊዜ ውስጥ ኢትዮጵያ ኃያሉን የኢጣሊያ ወራሪ ኃይል አሳፋሪ የሆነ ሽንፈት በማከናነብ ከግዛቷ ጠራርጋ ማስወጣት መቻሏ ነው፡፡ ኢትዮጵያ ለበርካታ ዓመታት የግዛት ሉዓላዊነቷን እና አንድነቷን አስከብራ የቆየች እና ማንኛውንም ሀገር ቅኝ ግዛት ለማድረግ ሙከራ ሲያደርግ የነበረውን ኃያል ሀገር ሁሉ በተሳካ ሁኔታ ስትከላከል የቆየች የጀግኖች ሀገር ናት፡፡ እንደ ወያኔ ታሪክ ከሆነ ይህ ሁሉ አንጸባራቂ ኢትዮጵያን ብቻ ሳይሆን አፍሪካውያንን/ትን ሁሉ ያኮራ አንጸባራቂ ታሪክ ዝም ብሎ የተጻፈ ልብወለድ ድርሰት ነው፡፡ እንደ ወያኔ አስተሳሰብ እና እምነት በአውሮፓ ኃያላን ቅኝ ገዥዎች ላይ የተቀዳጀነው አንጸባራቂ ድል እና ታሪክ ሁሉ በአሁኑ ጊዜ ካለችው ኢትዮጵያ እና ኢትዮጵያውያን/ት ጋር ምንም ዓይነት ግንኙነት የለውም፡፡ እንደ ጎጠኛው የወያኔ ወሮበላ የማፊያ ቡድን እምነት ከሆነ የአድዋ አንጻባራቂ ድል የትግራውያን/ት ብቻ ነው፡፡ ወትሮስ “የአክሱም ሐውልት ለወላይታው ምኑ ነው “ከሚል ጎጠኛ የወሮበላ ስብስብ ምን ሊጠበቅ!?

ሁለተኛው የወያኔ የእርባና የለሽነት እና ጠላሸት የመቀባት ዘመቻ ሌላኛው ጫፍ ያነጣጠረው ለዘመናት እንደ ባህሉ እና ወጉ ሲያስተዳድሩ የኖሩትን የአትዮጵያን ነገስታት ስም እና ስብዕና ጥላሸት መቀባት ነው፡፡ ከዚህ አንጻር በ19ኛው ክፍለ ዘመን በአድዋ ጦርነት ኃያሉን እና ወራሪውን የኢጣሊያ ኃይል ድባቅ በመምታት ድል የተቀዳጁትን እና እ.ኢ.አ አቆጣጠር በዚህ በያዝነው ዓመት 100ኛ ዓመት ክብረ በዓል የሚከበርለትን ድል በተቀዳጁት ዓጼ ምኒልክ ላይ የወያኔ ስም የማጥፋት እና የማጠልሸት ተግባር የበረታ ሆኗል፡፡ የወያኔው ቡድን ዓጼ ምኒልክን የዘር ማጥፋት የጅምላ ገዳይ እንደነበሩ አድርገው ይስሏቸዋል፡፡ እ.ኤ.አ ጃንዋሪ 2014 “የኢትዮጵያን ታሪክ የማጠልሸት አባዜ“ በሚል ርዕስ ባወጣሁት ትችቴ ላይ ባቀረብኩት የመሞገቻ ጭብጥ መሰረት የወያኔው የወሮበላ ቡድን በዓጼ ሚኒልክ ላይ ከመጠን ያለፈ ግነትን በማራገብ፣ ክብርን በማሳነስ እና ስም የማጠልሸት ተግባራትን እንደ ዋና ስራው አድርጎ በመውሰድ ዕኩይ ምግባሩን ሲፈጽም ቆይቷል፡፡ ዓጼ መኒሊክ ካረፉ ከ100 ዓመታት በኋላ የወያኔው የወሮበላ ቡድን ከመቃብር በመቀስቀስ ሰይጣናዊ ሰው ለማድረግ ሙከራ አድርጓል፡፡  መለስ ዜናዊ ካረፈ ከሁለት ዓመታት ገደማ በኋላ መለስን ከመቃብር በማስነሳት እና ከፍተኛ ዘመቻ በማድረግ የኢትዮጵያ ብቸኛው አዳኝ መሲህ አድርገው ለማቅረብ ሞክረዋል፡፡ የወያኔ የወሮበላ ቡድን ምኒልክ የኦሮሞ ህዝብ ጠላት እንደሆኑ አድርጎ ታሪክ እንደገና ለመጻፍ ይፈልጋል፡፡ እውነተኛው ነገር ግን መለስ በህይወት ቢቆይ ኖሮ እርሱ እና ግብረ አበሮቹ እብሪተኞቹ የወያኔ ባለስልጣናት እና አባላት ያልተነገሩ እና ለመግለጽ እጅግ የሚዘገንኑ ወንጀሎችን በኦሮሞ ህዝብ ላይ የፈጸሙ ስለመሆናቸው ለህግ ለማቅረብ ከበቂ በላይ መስረጃዎች አሉ፡፡

አሁን በህይወት የሌለው መለስ ዜናዊ ግርማዊ ቀዳማዊ አጼ ኃይለ ስላሴ አሁን ምንም ዓይነት የአስተሳሰብ እና የድርጊት ለውጥ ሳይኖር ወደ የአፍሪካ ህብረትነት (ከአውሮፓ ህብረት ምግባር እና የአመራር ፍልስፍና ሳይሆን ስም ብቻ ተኮርጆ) የተለወጠውን እና ከዚያ በፊት ግን የአፍሪካ አንድነት ድርጅት ምስረታ ስላበረከቷቸው ጠቃሚ ነገሮች ሁሉ ሙልጭ አድርጎ በመካድ ጥላሸት በመቀባት ያለ የሌለ ጥረት ሲያደርግ ቆይቶ ነበር፡፡ በዚያን ወቅት በጥላቻ የተሞላው መለስ ዜናዊ ግርማዊ ቀዳሚ ዓጼ ኃይለ ስላሴ እንደ ጋናው የመጀመሪያ ፕሬዚዳንት እንደ ክዋሜ ንክሩማህ የፓን አፍሪካ አራማጅ አልነበሩም በማለት ተራ ቅጥፈትን በመከናነብ የድሁርነት አስተሳሰቡን ያለምንም ሀፍረት በማራመድ ለእነዚህ ባለውለታ ንጉሰ ነገስት በአፍሪካ ህብረት ቀጥር ግቢ ውስጥ ሀውልታቸው እንዳይቆም የሞት ሽረት ትገል አድርጎ ነበር፡፡ ታሪካዊ ማስረጃዎች ግን የተለዬ ታሪክ ይነግሩናል፡፡ የጋናው ፕሬዚዳንት ክዋሜ ንክሩማህ ግን ያለ ግርማዊ ቀዳማዊ ዓጼ ኃይለስላሴ ጥረት እና ትግል የአፍሪካ አንድነት ድርጅት እውን አይሆንም ነበር በማለት በተደጋጋሚ ይናገሩ ነበር፡፡ እ.ኤ.አ በ1972 በተካሄደው 9ኛው የአፍሪካ ርዕሰ ብሄሮች እና የአፍሪካ አንድነት ድርጅት መንግስታት እንዲሁም የመሪዎች ጉባኤ ላይ ግርማዊ ቀዳማዊ ዓጼ ኃይለ ስላሴ በአቻዎቻቸው የአፍሪካ አንድነት ድርጅት የአፍሪካ አባት ተብለው ተመርጠው ነበር፡፡ እ.ኤ.አ በ1963 ግርማዊ ቀዳማዊ ዓጼ ኃይለ ስላሴ የመጀመሪያው የአፍሪካ አንድነት ድርጅት ሊቀመንበር ሆነው ተመርጠዋል፣ እንዲሁም እ.ኤ.አ በ1966 እንደገና ለሁለተኛ ዙር ያንኑ ተመሳሳይ የስልጣን ቦታ ማንም ሌላ የአፍሪካ መሪ ተመርጦ የማያውቀውን ድጋሜ ለሁለተኛ ጊዜ ተመርጠው አገልግለዋል፡፡

መለስ በህይወት ከተለዬ በኋላ አንድ የዜና ምንጭ ከድሮው “ፕሬዚዳንት” ግርማ ወልደጊዮርጊስ ጋር ባደረገው ቃለ መጠይቅ “ፕሬዚዳንት” ግርማ ወልደጊዮርጊስ ለ”ጠቅላይ ሚኒስትር” ኃይለማርያም ደሳለኝ እንዲህ የሚል ደብዳቤ ጽፈው እንደነበር ጠቁሟል፣ “ንጉሱን ለማስታወስ ሀውልት መገንባት አለበት… የአፍሪካ የመጀመሪያው መሪ ነበሩ፣ እናም ይህ ሀውልት የማቆም ሁኔታ ካበረከቱት አስተዋጽኦ አንጻር ይገባቸዋል ብዬ አስባለሁ፡፡“ ከመለስ አስመሳዮች እና አሽከሮች ግን በዚህ ጉዳይ ላይ ጥቂት ነገሮች ብቻ ሊከናወኑ ይችላሉ ተብሎ ይጠበቃል!

በግልጽ ለመናገር የኢትዮጵያን ታሪክ እርባናየለሽ የማድረግ እና በየዘመኑ የተነሱ ታሪካዊ መሪዎችን ስም ጥላሸት የመቀባት ሁኔታ አንድ ነገርን ለማሳካት የሚደረግ ግብ ነበር፡፡ ይኸውም የታሪክን ሰዓት ወደ መጀመሪያ ዓመት በመመለስ የሀገሪቱ አባት እና የወያኔ የሀገሪቱ የልምድ አዋላጅ በማድረግ የመለስ ዜናዊን ታሪክ አንድ ብሎ ለማስጀመር ነበር፡፡ ወያኔ እና የወያኔ አመራሮች ታሪካዊ መዛግብትን በማዛባት እና እውነተኛውን ታሪክ በመካድ ታሪክን እንደገና ለመጻፍ፣ አዛብቶ ለመጻፍ፣ አጋንኖ ለመጻፍ እና እውነተኛውን ታሪክ ያለመጻፍ እና በሌላ መልኩ በቅዱሱ የመለስ ዜናዊ ታሪክ ለመተካት የሚደረግ ከንቱ ሙከራ ነው፡፡ የዓጼ ምኒሊክ ታሪክ እንዲጻፍ አይፈልጉም፣ ይልቁንም የዘመናዊት አፍሪካ ታላቁ መሪ መለስ ዜናዊ እንደሆነ ተደርጎ እንዲጻፍ ይፈልጋሉ፡፡ የዓጼ ምኒልክን ስም እና ክብር በማጠልሸት መለስን አዲሱ የአፍሪካ ዝርያ መሪ፣ የልማታዊ መንግስት ፈጣሪ እና አምጭ፣ የዴሞክራሲ አራማጅ፣ የዓለም አቀፍ አየር ሙቀት የአፍሪካ መሪ፣ የአየር ለውጥ ባለሙያ እና ጅሀዲስቶችን እና አሸባሪዎችን ደምሳሽ እና ወዘተ ተብሎ እንዲመለክበት ይፈልጋሉ፡፡

2) አማራን እና የአማራን ህዝብ ጥለሸት መቀባት፣

የወያኔ ጸረ አማራ ፍልስፍና እና በአማራ ላይ የሚደረግ ጥላሸት የመቀባት ዘመቻ መሰረተ ቢስ እና ምክንያታዊነት የሌለው ኢሞራላዊ ድርጊት ነው፡፡ የወያኔው ማኒፌስቶ እንዲህ በማለት ያውጃል፣ “አማራዎች የትግሬዎች ጠላቶች ናቸው፡፡ የወያኔ የገንዘብ ኃላፊ የነበሩት ገብረመድህን ዓርዓያ እንደገለጹት የወያኔ ፍልስፍና የመሰረት ድንጋይ አማራ የትግራይ ህዝቦች ጠላት ነው የሚል ነው፡፡ አማራዎች አንድ ጠላት ብቻ አይደሉም ሆኖም ግን ድርብ ጠላቶች ናቸው፡፡ ስለሆነም አማራን መደምሰስ አለብን፡፡ አማራዎችን ልናጠፋቸው ይገባል፡፡ አማራዎች እስካልጠፉ እና እስካልተሸነፉ ድረስ፣ እንዲሁም የዘር ማጥፋት እርምጃ እስካልተወሰደባቸው ድረስ ትግራይ በነጻነት ልትኖር አትችልም፡፡ የምናስበውን መንግስት ለመፍጠር እንዳንችል አማራ ዋና መሰናክል ይሆናል፡፡” አሁን በህይወት የሌለው መለስ እና ህወሀት አንዴ ስልጣን ከያዙ በኋላ የጥላቻ ፍልስፍናቸውን በአማራ እና በአማራ ህዝብ ላይ ሙሉ በሙሉ መተግበር ነበር፡፡ እናም አማራን ለመደምሰስ ሁሉንም ነገር አደረጉ፣ ሆኖም ግን…

ወያኔ በእብሪተኝነት የዘር ማጥፋት ወንጀል እየፈጸመበት ያለው አማራ እና የአማራ ህዝብ ለመሆኑ ማን ነው?

የወያኔ ወሮበላ የማፊያ ቡድን የአማራን ህዝብ ጭራቅ ነው በማለት ተከታታይነት ያለው የፕሮፓጋንዳ ዘመቻ ቢከፍትበትም እውነታው ግን አማራ የሚባለው ህዝብ ከዓለም የመጨረሻ ደኃ እንደሆነ መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡ የአልጃዚራ ዘገባ በቅርቡ እንዲህ የሚል መደምደሚያ ላይ ደርሷል፣ “አማራ በኢትዮጵያ ብቻ አይደለም ደኃ ሆኖ የሚገኘው፣ ሆኖም ግን በአፍሪካም ጭምር እንጅ፡፡“

የአማራን ህዝብ ማሰቃዬት እና ማጥፋት የወያኔ ዋና ፍልስፍና እና ኃይል ሆኖ ቀጥሏል፡፡ አሁን በህይወት የሌለው መለስ በአማራ ህዝብ ላይ ጥልቅ የሆነ ጥላቻ የነበረው ሰው ነበር፡፡ ያለምንም ማጋነን የለየለት ጸረ አማራ ነበር ማለት ይቻላል፡፡ ለመለስ አማራን መጥላት አነደሚተነፍሰው አየር ለሂወቱ አስፈላጊው ነበር፡፡ መለስ በፖለቲካዊ ምክንያቱ አማራን አምርሮ ይጠላ ነበር! መለስም ሆነ ሌሎች የወያኔ መሪዎች አማራ የተባለውን ህዝብ ለምን እንደሚጠሉት ወይም ደግሞ ለምን የጥላቻ ስሜት እንደሚያንጸባርቁ በቂ የሆነ ምክንያት የላቸውም፡፡ የወያኔን እና አመራሮቹን በአማራ ህዝብ ላይ ያላቸውን ጥልቅ እና ስር የሰደደ ጥላቻ በማጥናት ምክንያቶቹን ለመገንዘብ የዓለም ታሪክን መመርመር የተሻለ ይሆናል፡፡

የመለስ እና የወያኔ በአማራ ላይ ያላቸው ፍጹም የሆነ ኢምክንያታዊ ጥላቻ እና የሂትለር እና የናዚ ሰው በላ ድርጅት በአይሁዶች ላይ የነበራቸው ጥላቻ ለንጽጽር በትይዩ የሚታይ ጉዳይ ነው፡፡ ሂትለር ለጀርመን ህዝብ ችግሮች እና ለሁሉም ሰይጣናዊ ድርጊቶች ተጠያቂዎቹ አይሁዶች ናቸው ብሎ ያምን ነበር፡፡ መለስም አሁን ላሉት እና ድሮ ለነበሩትም ለሁሉም የኢትዮጵያ ህዝብ ችግሮች እና ሰይጣናዊ ድርጊቶቸ ሁሉ ተጠያቂው የአማራ ህዝብ ነው ብሎ ያምን ነበር፡፡

ሂትለር እና ናዚዎች ህዝብን በጎሳ በመከፋፈል ያምኑ ነበር፡፡ በእነዚህ በተከፋፈሉ የተለያዩ ጎሳዎች መካከል ሁልጊዜ ቀጣይነት ያለው ትግል መኖር አለበት ብለው ያምኑ ነበር፡፡ እነዚህ ናዚዎች “አሪአን ሬስ” የተባለው ጎሳ ምርጥ እና ጠንካራ እንዲሁም ሌሎችን ጎሳዎች ለመግዛት የታደለ ነው ብለው ያምኑ ነበር፡፡ አይሁዶች እና ሌሎች የአሪአን ሬስ ጎሳ አባላት ያልሆኑ ህዝቦች እና ጎሳዎች የበታች ጎሳዎች (ከሰውነት የወረዱ ፍጡሮች) ናቸው ብለው ያምኑ ነበር፡፡

ለመለስ እና ለወያኔ ትግራውያን/ት ሌሎችን ጎሳዎች ለመግዛት ምርጦቹ እና ጠንካራዎቹ ናቸው ብለው ያምናሉ፣ ምክንያቱም ወያኔ በሽምቅ ውጊያ ታንክ፣ አውሮፕላን እና ሌሎች የተለያዩ የጦር መሳሪያዎችን ያከማቸውንጠንካራውን ወታደራዊ ኃይል ያሸነፈ ድርጅት ስለሆነ ነው ብለው ያምናሉ፡፡ በቀጣይነት የእድሜ ልክ ገዥዎች መሆን እንዳለባቸው እራሳቸውን አሳምነዋል፡፡ ወያኔ እና አመራሮቹ እራሳቸውን ከናዚዎች የአሪአን ሬስ አፋኝ ቡድን የዘር ጎሳ ጋር እኩል እድርገው ይቆጥራሉ፡፡ ሌሎቹ የኢትዮጵያ ብሄሮች እና ጎሳዎች አማራን ጨምሮ ትንሽ የጎሳ ፍጡሮች ናቸው ብለው ያምናሉ፡፡ ስለሆነም በኢትዮጵያ በአሁኑ ጊዜ የፖለቲካ አመራሩ፣ ቢሮክራሲው፣ የፖሊስ ኃይሉ፣ የደህንነት እና ወታደራዊ ተቋማት በሙሉ በወያኔ የበላይነት እና ቁጥጥር ስር ውለዋል፡፡ በአሁኑ ጊዜ የወያኔ አገዛዝ እና ሆድ አደር ደጋፊዎቹ በአጠቃላይ የኢኮኖሚ ዘርፎችን ባንኮችን፣ የግንባታ እና የስሚንቶ ምርቶችን፣ የማዕድን ዘርፉን፣ የትራንስፖርት፣ የኢንሹራንስ እና የአስመጭ እና ላኪ የስራ መስኮችን በሙሉ በእነርሱ ቁጥጥር ስር አውለዋል፡፡

አሁን በህይወት የሌለው መለስ ኢትዮጵያውያን/ት ፍጹም በሆነ መልኩ በጎሳ ማንነታቸው፣ በቋንቋ እና በባህል መሰተጋብራቸው መከፋፈል አለባቸው ብሎ የሚያምን ነበር፡፡ ይህም በጎሳ ቡድኖች መካከል ውድድር ይኖራል የሚል መሰሪ አስተሳሰብ ነበረው፡፡ መለስ የእራሱን የሸፍጥ “ፌዴራሊዝም” መሰረተ እና ክልል እያለ የሚጠራውን የአገዛዝ ስርዓት በመፍጠር የሸፍጥ ዕኩይ ተግባሩን ተግባራዊ ማድረግ ጀመረ፡፡ በኢትዮጵያ ህገመንግስት አንቀጽ 39 መለስ እንዲህ የሚል ነገር ጽፎ አስቀምጧል፣ “ብሄር፣ ዜግነት ወይም ደግሞ ህዝቦች ለዚህ ህገመንግስት የሰዎች ስብስቦች ወይም ደግሞ የጋራ ባህል ያላቸው ትልልቅ ጎሳዎች ወይም ደግሞ ተመሳሳይ ልማዶች፣ የጋራ ቋንቋዎች፣ እምነቶች ወይም ተመሳሳይ ማንነቶች እና የሚታወቁ የተፋፈጉ ግዛቶች ላይ የሚኖሩ ህዝቦችን ያካትታል፡፡”

ናዚዎች ሀዝቦችን በገፍ የማባረር እርምጃዎችን ወስደዋል፣ እናም አይሁዶችን ናዚዎች ከያዟቸው ግዛቶች ሁሉ በግዳጅ እንዲባረሩ አድርገዋል፡፡ እ.ኤ.አ በኤፕሪል 2012 “አረንጓዴ ፍትህ ወይም ደግሞ  የጎሳ ኢፍትሀዊነት “ በሚል ርዕስ ባወጣሁት ትችት አሁን በህይወት የሌለው መለስ ዜናዊ  በአስር ሺዎች የሚቆጠሩ አማራዎችን ከደቡብ ኢትዮጵያ እንዲባረሩ ትዕዛዝ ሰጠ፡፡ ያደረገውን ዕኩይ ምግባር ለማስተባበል በማሰብ የምስራቅ ጎጃም ሰፋሪዎች እና ደኖችን እየመነጠሩ ያሉ መሬትን የወረሩ እና የተቀራመቱ ወንጀለኞች ናቸው በማለት የሚከተለውን አንጃ ግራንጃ ንግግር አሰምቶ ነበር፡፡

“…በታሪክ አጋጣሚ ባለፉት አስር ዓመታት ብዙ ሰዎች –30 ሺህ የሚሆኑ ሰፋሪዎች ከምስራቅ ጎጃም ፈልሰው በመምጣት በህገወጥ መልክ በደቡብ ኢትዮጵያ በቤንች ማጅ ዞን ሰፍረው ነበር፡፡ በጉራ ፈርዳ ወደ 24 ሺ የሚሆኑ ሰፋሪዎች ሰፍረው ይገኛሉ፡፡ አካባቢው ደን ያለበት በመሆኑ ምክንያት በርካታ ህዝብ አይኖርበትም፡፡ በሁሉም ዓይነት መለኪያ ቢታይ ጉራ ፈርዳ ትንሿ ምስራቅ ጎጃም በመሆን ህገወጥ በሆነ አሰፋፈር እና አመራር ላይ ትገኛለች…ሰፋሪዎች ወደ ጫካው አካባቢ በመሄድ ጫካውን ለመኖሪያነት በሚል ሰበብ መመንጠር እና ማውደም የለባቸውም፡፡ ይህ ህገወጥ ድርጊት ነው፡፡ ስለሆነም መቆም አለበት…በአማሮች ላይ ማሰቃየት እና ከሰፈሩበት ቦታ ማፈናቀል እየተባለ የሚደረገው ውንጀላ እና የአመጽ ቅስቀሳ ኃላፊነት የጎደለው እና ለማንም የማይጠቅም ጉዳይ ነው…”

እ.ኤ.አ በ1991 የመንግስት ስልጣንን ከወታደራዊው መንግስት ለወያኔ የወሮበላ ቡድን በዕርቅ ሰበብ ያስረከቡት የቀድሞው የዩናይትድ ስቴትስ የአፍሪካ ጉዳዮች ረዳት ጸሀፊ የነበሩት ኸርማን ኮኸን እ.ኤ.አ ጃኗሪ 2012 በሰጡት ቃለ መጠይቅ እንዲህ ብለው ነበር፣ “እናም እርሱን (መለስን መሆኑ ነው) ስለመሬት ይዞታ ጠይቄው ነበር፣ ገበሬዎች የመሬት ባለቤት እንዲሆኑ እንዲፈቀድላቸው የማግባባት ስራ ቅስቀሳ ሳደርግ ነበር፡፡ እርሱም ይህ ጥሩ አይደለም ምክንያቱም አማሮች መጥተው ይወስዱባቸዋል፣ እናም ገበሬዎቹ በንጉሱ ዘመን እንደነበሩት ሁሉ ተመልሰው ወደ ጭሰኝነት ይገባሉ፡፡“

ናዚዎች አይሁዶችን በጥላቻ የተሞሉ የሚል ስም በመስጠት እና የወረደ አስተሳሰብ ያላቸው እያሉ በመሳደብ ስማቸውን ጥላሸት ይቀቡ ነበር፡፡ የወያኔ የወሮበላ የማፊያ ቡድንም በተመሳሳይ መልኩ በአማራ ህዝብ ላይ የጥላቻ ሰይጣናዊ መንፈስን በማንገስ እና በጎሳዎች መካከል ጥላቻን እና ውጥረትን በመፍጠር ብሄርን ከብሄር በማጋጨት የአማራን ስም ጥላሸት በመቀባት ላይ ይገኛል፡፡ አማሮች ለወያኔ የወሮበላ የማፊያ ቡድን አባላት አንድ ጠላት ብቻ አይደሉም ሆኖም ግን ድርብ ጠላት ናቸው፡፡ ለወያኔ የወሮበላ እና የማፊያ ቡድን አባላት አማሮች ቅኝ ገዥዎች፣ እብሪተኞች፣ ትምክህተኞች፣ ጨቋኞች፣ በህገወጥ መልክ የሚሰፍሩ ወንጀለኞች፣ ጦረኞች፣ ነፍጠኞች (ጠብመንጃ ያዥዎች፣ መሬት ነጣቂ ሰፋሪዎች)፣ የባርነት ጌቶች፣ ወዘተ ናቸው፡፡ ማቋረጫ በሌለው መልኩ አማራን ጥላሸት የመቀባት የፕሮፓጋንዳ ስራ የተፈጠረው አማራን ጥላሸት ለመቀባት ብቻ አይደለም ሆኖም ግን አማራን የስቃይ ሰለባ፣ ከህግ አግባብ ውጭ የመያዝ፣ ስልጣንን ከህግ አግባብ ውጭ መጠቀሚያ፣ የማታለል ስራ የመስራት፣ ይፋ የመተው እና ደንታቢስ የሆነ ዓላማን በአማሮች ላይ ለመተግበር ታስቦ ጭምር  እንጅ፡፡

ቬይና ላይ አድጎ በህይወት ዘመኑ በአይሁዶች ላይ የተፈጠረውን የሂትለር ጭፍን ጥላቻ ለማወቅ እጅግ ከባድ እንደመሆኑ ሁሉ በተመሳሳይ መልኩ መለስ ይባል የነበረ ቀንዳም ሰይጣን፣ ስም እንኳ ሳይቀር የሰዎችን ስም ቀምቶ የእራሱ ያደረገ ቀማኛ በመናገሻ ከተማዋ በአዲስ አበባ አድጎ በህይወት ዘመኑ በአማሮች ላያ ሲያራምድ የነበረውን ጭፍን ጥላቻ መንስኤ ለማወቅ እጅግ በጣም አስቸጋሪ ነገር ነው፡፡ መለስ የሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱን የተከታተለው እዚሁ አዲስ አበባ ነው፣ እናም የዩኒቨርስቲ ትምህርት የመጀመር ዕድሉንም አግኝቶ የነበረው በዚህቸው ታሪካዊ ከተማ ነበር ማጠናቀቅ ባይችልም፡፡

3ኢትዮጵያን መከፋፈል፣ መገነጣጠል እና መሸጥ እንዲሁም የኢትዮጵያን የግዛት አንድነት እና ሉዓላዊነት መከፋፈል እና ማዳከም

በአሁኑ ጊዜ መለስ እና የወያኔ የወሮበላ የማፊያ ቡድን ኢትዮጵያን በመከፋፈል፣ በመገነጣጠል እና በመሸጥ እንዲሁም ከዕውቀት እጦት የተነሳ የሀገሪቱን ጥቅም እና ሉዓላዊነት አሳልፎ በመስጠት እጅግ በጣም ረዥም ርቀት ተጉዘዋል፡፡ እ.ኤ.አ ፌብሯሪ 2014 “ኢትዮጵያን ከቅርጫ ማዳን” በሚል ርዕስ የኃይለማርይም ደሳለኝ (በእራሱ ነጻነት ምንም ሀሳብ የሌለው እና ምንም ማድረግ የማይችል በወያኔ የሚጦዝ አሻንጉሊት) የኢትዮጵያን ሉዓላዊ ግዛት ቆርሶ ለሱዳን ለመስጠት ያደረገውን እኩይ ምግባር ህጋዊ መሰረት እንደሌለው እና የኢትዮጵያን አንጡራ ሉዓላዊ ግዛት በማንአለብኝነት መስጠት እንደማይችሉ እና ህገመንግስት እየተባለ ከሚጮሁለት ሰነድም በላይ እንደሆነ ሞግቼ ነበር፡፡ ይህ ትችት እ.ኤ.አ በ2008 “በምዕራቡ ግንባር ሁሉም ነገር ጸጥታ የሰፈነበት አይደለም” በሚል ርዕስ መለስ በሚስጥር የኢትዮጵያን የግዛት መሬት ቆርሶ ለሱዳን ለመስጠት እያደረገ የነበረውን ሰይጣናዊ ተግባር በመሞገት አቅርቤው ለነበረው ትችቴ ተቀጥላ ነው፡፡

ኢትዮጵያን ማዳን በሚለው የክርክር ጭብጤ መለስ ወይም ማንም ቢሆን የኢትዮጵያን የግዛት መሬት ለሱዳን አሳልፎ ለመስጠት ምንም ዓይነት ህጋዊ ስልጣን የለውም የሚል ነበር፡፡ በአሁኑ ጊዜም ኃይለማርያም የኢትዮጵያን ሉዓላዊ ግዛት በማንአለብኝነት በመድፈር አንጡራ መሬቷን ለሱዳንም ሆነ ለሌላ የመስጠት መብትም ሆነ ስልጣን የለውም፡፡ ያንን የክርክር ጭብጥ ባቅርብም ቅሉ መለስ በንቀት እና በእብሪት ልቡ ተደፍኖ ጉዳዩን ከምንም ሳይቆጥር ከአማራ ክልል ብዛት ያለውን መሬት ቆርሶ ለሱዳን ለመስጠት ስምምነት ተፈራረመ፡፡ ኃይለማርያም እና አሻንጉሊት አለቆቹ በአሁኑ ጊዜ ይህንን ህገወጥ የመሬት ዝውውር “ስልታዊ የስምምነት ማዕቀፍ” በሚል ሌላ ማደናገሪያ በመሸንቀር እና በማታለል ነገሩን ውጠን ዝም እንድንል ለማድረግ ጥረት እያደረጉ ነው፡፡ እውነታው ግን በአሁኑ ጊዜ በስልጣን ላያ ያለው ገዥው አካል በኢትዮጵያ ህገመንግስት ወይም በዓለም አቀፍ ህግ ምንም ዓይነት ህጋዊ መሰረት ሳይኖረው ማንኛውንም የኢትዮጵያ የሆነውን የግዛት መሬት ለሱዳን ወይም ለሌላ ለማንኛውም ሀገር አሳልፎ መስጠት አይችልም፡፡

እ.ኤ.አ ማርች 2011 “ኢትዮጵያ፡ ለሽያጭ የቀረበች ሀገር” በሚል ርዕስ ሀገሪቱ ቀስ በቀስ በመዋለ ንዋይ አፍሳሽነት ስም ምንም ዓይነት የሞራል ስብዕና ለሌላቸው እምነተቢሶች በሚስጥር እየተሸጠች መሆኗን በመጥቀስ የተሰማኝን ቁጭት በመግለጽ ይህ እኩይ ድርጊት በአስቸኳይ እንዲቆም የሚያሳስብ ትችት አቅርቤ ነበር፡፡ ኢትዮጵያ ለሽያጭ ቀርባለች፡፡ እያንዳንዱ ሰው የእርሷን ቁርጥራጭ መሬት በእርካሽ ዋጋ እያገኘ ነው፡፡ የመሬት ተቀራማች ጆቢራዎች ከሁሉም የዓለም ክፍሎች በመምጣት ጋምቤላ ላይ እየወረዱ ነው፡፡ መለስ ዜናዊ ኩራት በተቀላቀለበት መልኩ ህንድን፣ ቻይናን፣ ፓኪስታንን እና ሳውዲ አረቢያን ጭምሮ 36 ሀገሮች የእርሻ መሬት በሊዝ እየወሰዱ መሆናቸውን ተናግሮ ነበር፡፡ በዚያው ወር (ማርች 2011) ስምምነቶች አደገኛ በሆነ ፍጥነት እየተደረጉ ትላልቅ ትራክተሮች እና ከባድ የዛፍ ማስወገጃ ማሽነሪዎችን በማሰማራት እረግረጋማ ቦታዎችን ማንጠፋጠፍ እና መሬቶችን ማረስ ተጀመረ…በዓለም ከሚገኙ 25 የእርሻ ስራን ከሚሰሩ ድርጅቶች መካከል አንዱ የሆነው ካሩቱሪ የተባለው ድርጅት ፓልም ዘይት፣ ስኳር፣ ሩዝ እና ሌሎች ምግብ ነክ ነገሮችን በማምረት ከጋምቤላ ክልል ወደ ዓለም አቀፍ ገበያዎች በማቅረብ መስራት እንደሚችል ዕቅድ አወጣ፡፡

እ.ኤ.አ ማርች 2013 “መሬት እና የኢትዮጵያ የሙስና ዘረፋ” በሚል ርዕስ የዓለም ባንክ “ሙስናን በኢትዮጵያ መመርመር“ በሚል ርዕስ አጥንቶ ያቀረበውን ባለ550 ገጽ በዋቢነት በመጥቀስ በኢትዮጵያ የመሬት ዘርፉ ላይ ሙስና በብዙ መልኮች እየተገለጸ እና እየተፈጸመ እንደሆነ ለማሳየት ሞክሪያለሁ፡፡ በመጀመሪያ ደረጃ “የተማሩ እና ነባር ባለስልጣኖች” በሀገሪቱ ውስጥ በጣም ተፈላጊ ናቸው የተባሉትን መሬቶች በመንጠቅ ለእራሳቸው አድርገዋል፡፡ እነዚህ ወፍራም ድመቶች ደካማ ፖሊሲዎችን እና የህግ ማዕቀፎችን እንዲሁም ያለውን ደካማ ስርዓት እና ያሉትን ፖሊሲዎች እና ህጎች ለእራሳቸው ጥቅም እያወሉ ለእራሳቸው ጥቅም ከፍተኛ የሆነ ሙስና እየሰሩ እንደሆኑ ገልጨ ነበር፡፡ መሬትን ከተማም ሆነ በገጠር፣ እንደዚሁም ከቤት ስራ ማህበራት እና ከከተማ አልሚዎች ጋር በሚኖራቸው የስራ ግንኙት እራሳቸውን ከሙስና እና ከማታለል ስራዎች ጋር በማዛመድ ሙስናን ይሰራሉ፡፡ እነዚህ ተጽዕኖ ፈጣሪዎች እና በጥሩ ሁኔታ ትስስር ያላቸው ግለሰቦች መሬት በሀገሪቱ ካለው ህግ እና ደንብ ውጭ ለእራሳቸው እንዲመደብላቸው ያደርጋሉ፡፡

ለሩብ ክፍለ ዘመን ያህል አሁን በህይወት የሌለው መለስ ዜናዊ እና ህወሀት የጎሳ ፌዴራሊዝም በሚል የጎሳ ፖሊተካ ዕቅድን ይዞ በማራመድ ላይ ይገኛል፡፡ የወያኔው ወሮበላ የማፊያ ቡድን የኢትዮጵያን ህዝብ በጎሳ ሸንሽኖ ክልል (በጥሬ ትርጉሙ የተገደበ፣ የጎሳ ቤቶች እንደዚሁም የእራስ የግል የሆነ ዞን ወይም አንድ የተወሰነ ቦታ የሚል ትርጉምን ይይዛል)    እየተባሉ በሚጠሩ ትላልቅ የአካባቢ የፖለቲካ ተቋማት በማዋቀር ዜጎችን እንደ ከብት በአንድ አካባቢ ብቻ በማጎር ተግባራዊ በማድረግ ጥረት ላይ ይገኛል፡፡

በወያኔ እየተራመደ ያለው የክልልነት ፍልስፍና የአፓርታይድን የባንቱስታን (የጥቁር አፍሪካውያን/ት ክልል) ብዙ መገለጫዎች ይጋራል፡፡ አፓርታይድ በደቡብ አፍሪካ የባንቱስታንስ (የጥቁር ክልሎች) እንደፈጠረ ሁሉ በኢትዮጵያ ህገመንግስት አንቀጽ 39ን በማስገባት መለስም የጎሳ ክልሎችን ፈጥሯል፡፡ የአፓርታይድ አንቀጽ 51 ባንቱስታንስን ፈጥሯል፡፡ የመለስ አንቀጽ 39 ደግሞ ለብሄር ብሄረሰቦች ወይም ደግሞ ተመሳሳይ ልማድ፣ የመግባቢያ ቋንቋ፣ እምነት ወይም ተመሳሳይ ማንነት እና በከፍተኛ ብዛት በአካባቢው የሚኖሩትን ህዝቦች፣ እንዲሁም ጎረቤት የሆኑ ተዛማጅ ህዝቦችን በአንድ ላይ በማጀል ሰውን እንደ ከብት በመገደብ ክልል የሚል የመጠርነፊያ አካባቢዎችን አዋቅሯል፡፡ የአፓርታይድ እና የወያኔ ሁለቱም ፍልስፍናዎች ዓላማዎች ያነጣጠሩት የተወሰኑትን የጎሳ ቡድኖች በመንደር በማሰባሰብ እና ቋንቋን መሰረት ያደረጉ ግዛቶችን በመፍጠር በመጨረሻም ራስ ገዝ የሆኑ ሀገሮችን እንፈጥራለን በማለት የበሽታ ፈውስ መድሀኒት በማለት ለህዝቡ ለመስጠት የሚል ሲሆን በሌላ በኩል ግን ህዝብ ገዳይ የሆነ መድሀኒት ያዝዛሉ፡፡

ፕሮፌሰር ቴድ ቬስታል “የሰብአዊ መብት ድፍጠጣ በዴሞክራሲያዊት ኢትዮጵያ፡ የመንግስት እገዛ የሚደረግለት የጎሳ ጥላቻ“ በሚል ርዕስ ባቀረቡት ጽሁፍ የህወሀትን የክልላዊ የጎሳ ምደባ ስልት ግልጽ ያደርጋል ብለው ነበር፡፡ እንደዚሁም ህወሀት የኢትዮጵያ ህዝቦች አብዮታዊ ዴሞክራሲያዊ ግንባር (ኢህአዴግ) በሚል ሸፍጥ በሀገሪቱ ውስጥ የብዙሀን ፓርቲ ስርዓት ያለ ለማስመሰል እና በጎሳ ላይ የተመሰረተ እና በብሄር ብሄረሰቦች ላይ ትኩረት ያደረገ የጎሳ ፌዴራል መንግስት መመስረት እንደሆነ ግልጽ አድርገዋል፡፡ ይኸ በጉልህነት የሚታይ ከሌኒን የተኮረጀ የአገዛዝ መርህ ከዊልሶኒያን የበለጠ ከማቼቬሌን የሸፍጥ አካሄድ መሳ ለመሳ ነው፡፡ ኢህአዴግን/ኢፌዴሪን የሚያጦዙት እና የሚፐውዙት ብዛት ያላቸው ትግራውያን ስለሆኑ ሌሎች የጎሳ ቡድኖች እንዲለያዩ እና የእየራሳቸውን ጎሳ ብቻ እንዲይዙ በማድረግ አንዱ ጎሳ የሌላኛውን ባህል እና ቋንቋ አንዲሁም ልማድ እየፈራ በፍርሀት ቆፈን በእራሱ አካባቢ ብቻ ተሸብቦ ሲኖር ትላልቅ ጉዳዮች ግን በአንድ ፓርቲ ገዥው የወያኔ ወሮበላ ማፊያ ቡድን የሚፈጸሙ ይሆናል፡፡ ስለሆነም አህአዴግ በውሸት እና በሸፍጥ ፍልስፍና ብሄር ብሄረሰቦች ለአንዲት ታላቅ ሀገር ኢትዮጵያ የሚለው በእርሱ ቁጥጥር ስር እየዋለች ሌሎች እርሱን የሚቃወሙት የበለጠ እየተከፋፈሉ እና እየተሸነፉ ይሄዳሉ፡፡

አሁን በህይወት የሌለው መለስ ዜናዊ ኢትዮጵያን የባህር መዉጫ በማሳጣት እና ሀገሪቱን ወደብ አልባ በማድረግ የሀገሪቱን ጥቅም በእጅጉ የጎዳ ዕኩይ ድርጊት ፈጽሟል፡፡ የቀድሞው የዩኤስ አሜሪካ ፕሬዚዳንት የነበሩት ጂሚ ካርተር እና የቀድሞው የዩኤስ አሜሪካ የአፍሪካ ጉዳዮች ረዳት ጸሐፊ ኸርማን ኮኾን መለስን በማስጠንቀቅ እና በመለመን ዓይነት አቀራረብ የአሰብን ወደብ ወደ ኢትዮጵያ በመመለስ የባህር በር እንዲኖራት የጠየቁት እና ያሳሰቡት ተመዝግቦ ተቀምጧል፡፡ ሆኖም ግን የእነዚህ አንጋፋ የዲፕሎማት ሰዎች ልመና እና ጥያቄ መለስ ጆሮ ዳባ ልበስ ብሎት ቀርቷል፡፡

እ..ኤ.አ በ2000 ከኤርትራ የሁለት ዓመታት ጦርነት እና ወደ 80 ሺ የኢትዮጵያ ወታደሮች ካለቁ በኋላ አሁን በህይወት የሌለው መለስ የኢትዮጵያ እና የኤርትራን ጦርነት ለማቆም የሚያስችለውን የአልጀርሱን ስምምነት ፈረመ፡፡ ያ ስምምነት በሁለቱ ሀገሮች መካከል የድንበር መስመሮችን የሚያካልል እና ሌሎች ጉዳዮችን የሚፈታ የድንበር ኮሚሽን እንዲቋቋም አደረገ፡፡ ስለስምምነቱ ሊታመን የማይችለው የሚያስገርመው ነገር እና ይቅርታ ሊደረግለት የማያገባው አሳዛኙ ነገር እ.ኤ.አ በ1998 ኤርትርራውያን/ት በሰሜን ኢትዮጵያ የምትገኘውን ባድሜን ከወረሩ በኋላ እና ኤርትራውያን/ትም በዚያ ጦርነት በተሸነፉ ጊዜ መለስ ከመቅጽበት እንደ ባህር ዓሳ በመገለባበጥ የባድሜን አንጸባራቂ የኢትዮጵያውያንን/ትን ድል በመቀልበስ ባድሜን በእርቅ ሰበብ ለወራሪዎቹ የሚሰጥ ስምምነትን በመፈረም አጠቃላይ የዲፕሎማሲ ሽንፈትን የመከናነቡ ጉዳይ ነው፡፡ ይህ ሁኔታ በዘመናዊው የዓለም ታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ አንድ ሀገር እጅግ ግዙፍ የሆነ የሰው ህይወት ገብሮ እና ለቁጥር የሚያታክት ንብረት እንዲወድም አድርጎ በኃይል አሸንፎ ከግዛቱ ወራሪውን ኃይል ካባረረ በኋላ እንደገና እንደ መዳብ ብረት ተለምጦ ያንኑ በአሸናፊነት የተቆጣጠረውን የእራሱን ግዛት ለዓለም አቀፍ ዕርቅ ተገዥነት በሚል የደካሞች አስተሳሰብ ወይም ደግሞ ለዕኩይ ዓላማው ሽፋን በመስጠት አሳልፎ ለጠላት የሚሰጥ በዓለም ላይ የመጀመሪያው ሳይሆን አይቀርም፡፡

(ይቀጥላል)

ኢትዮጵያ በክብር ለዘላለም ትኑር!

 ህዳር 16 ቀን 2007 .