በቤንች ማጂ ዞን የሚኖሩ የአማራ ተወላጆች አካባቢውን ልቀቁ መባላቸውን ገለጹ


መረጃ ቲቪ አባል በመሆን የሳተላይት ቲቪውን ቀጥታ ስርጭት፣ ወቅታዊ ዜናዎችን እና ትንተናዎችን፣ የመዝናኛ ፕሮግራሞችን፣ ስፖርት እና ሌሎችንም ዝግጅቶቻችንን በፍጥነት እና ጥራት ስልክዎ፣ ኮምፒዩተርዎ ወይም ቲቪዎ ላይ ማየት ይችላሉ። እዚህ ሊንክ ላይ በመጫን አባል ይሁኑ


በደቡብ ክልል ቤንች ማጂ ዞን ጉራፋርዳ ወረዳ የሚኖሩ በርካታ የአማራ ክልል ተወላጆች ሕገወጥ ሰፋሪዎች ናችሁ በሚል እስከ የካቲት 30 ቀን 2004 ዓ.ም. ድረስ አካባቢውን ለቀው እንዲወጡ ትዕዛዝ የተላለፈላቸው መሆኑን ለሪፖርተር ገለጹ፡፡ የጉራፋርዳ ወረዳ አመራሮችና የቀበሌ ኃላፊዎች በሰጧቸው ፈቃድ መሠረት በሕጋዊ መንገድ መሬት ተረክበው በአካባቢው መኖር መጀመራቸውን የገለጹት የአማራ ክልል ተወላጆች፣ ባልጠበቁትና ባላሰቡት ሁኔታ ሀብትና ንብረታቸውን ጥለው አካባቢውን እንዲለቁ ትዕዛዝ መተላለፉ አስደንጋጭ መርዶ እንደሆነባቸው ተናግረዋል፡፡

ቅሬታ አቅራቢዎቹ እንደሚሉት፣ በጉራፋርዳ ወረዳ በሚገኙ ቀበሌዎች የሚኖሩ በርካታ የአማራ ክልል ተወላጆች በሕጋዊ መንገድ ለተረከቡት መሬት ግብር ሲከፍሉ መቆየታቸውን የሚያረጋግጥ የግብር ካርድ እንዲሁም የወረዳና የቀበሌ አመራሮች ‹‹መሬት ይሰጣቸው›› ብለው ትዕዛዝ ያስተላለፉበት ደብዳቤ በማስረጃነት ቢኖራቸውም፣ ‹‹ሕገወጥ ናችሁ›› በሚል አካባቢውን በአስቸኳይ ለቅቀው እንዲወጡ ተወስኖባቸዋል፡፡
በክልሉ ከሰፈሩበት ጊዜ ጀምሮ ቡና፣ ፓፓያና የመሳሰሉ ተክሎችን በማምረት ሕይወታቸውን መቀየር ችለው እንደነበር የሚናገሩት እነኝሁ ሰፋሪዎች፣ ለሠሩት ቤትና ለተከሉት ተክል ግምት እንዲሰጣቸው ሲጠይቁ የወረዳው ኃላፊዎች ‹‹ቆርቆሮውን ነቅላችሁ መሄድ ትችላላችሁ›› የሚል ምላሽ እንደሰጧቸው ገልጸዋል፡፡

አንድ ስማቸው እንዳይጠቀስ የጠየቁ የጉራፋርዳ ነዋሪ፣ ‹‹ጉዳያችን እስከ እንባ ጠባቂ ተቋም ድረስ ብንወስድም ምንም በጐ ምላሽ ልናገኝ አልቻልንም፡፡ በሕጋዊ መንገድ ያፈራነውን ሀብትና ንብረት ጥላችሁ ሂዱ ማለት ትልቅ የሰብዓዊ መብት ረገጣ ነው፤›› በማለት በሰፋሪዎች ላይ እየደረሰ ያለውን በደል ተናግረዋል፡፡

የቤንች ማጂ ዞን አስተዳዳሪ አቶ ዓለማየሁ አይበራ በበኩላቸው፣ በሕጋዊ መንገድ የሰፈሩ የአማራ ክልል ተወላጆች አካባቢውን ለቅቀው እንዲወጡ ስለመደረጉ የሚያውቁት ነገር አለመኖሩን ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡

ሕገወጥ ሰፋሪዎች መውጣት ካለባቸው የደቡብና የአማራ ክልል እንዲሁም የፌዴራል መንግሥታት አውቀውት በታቀደ መልኩ መከናወን እንዳለበት የገለጹት አቶ ዓለማየሁ፣ አሁን ባለው ተጨባጭ ሁኔታ ከአማራ ክልል የመጡ ሰፋሪዎች በአጭር ጊዜ ውስጥ ክልሉን ለቅቀው እንዲወጡ የተደረገበት አሠራር ይኖራል የሚል እምነት እንደሌላቸው ተናግረዋል፡፡

‹‹የክልሉ መንግሥት ሰብዓዊነት የጐደለው ሥራ የሚሠራ አይደለም፡፡ ማንም ኢትዮጵያዊ ዜጋ በሕገወጥ መንገድ ስለመጣ በሕገወጥ መንገድ ውጣ ብለን እናባርረውም፤›› ያሉት አቶ ዓለማየሁ፣ ከአንድ ዓመት በፊት በደቡብ ክልል የሚኖሩ ሕገወጥ ሰፋሪዎችን በሚመለከት የአማራ ክልልና የደቡብ ክልል ኃላፊዎች ያደረጉትን ውይይት ተከትሎ የአማራ ክልል የራሱን ዝግጅት በማድረግ ከ800 በላይ የሚሆኑ በደቡብ ክልል ይኖሩ የነበሩ ሰፋሪዎች ወደ ባህር ዳር እንዲመለሱ መደረጉን አስታውሰዋል፡፡ አያይዘውም፣ ‹‹ከአማራ ክልል ወደ ደቡብ ክልል የሚደረግ ሰፈራ የለም፤ ወረዳዎች ላይ የምትፈርደው ነገር ይኖራል ብዬ አላስብም፣ መመለስ ያለበት ሰው ካለ መመለስ አለበት፡፡ ይሄ የእኛም የክልሉም አቋም ነው፡፡ ነዋሪ ያልሆነን ሰው ሥርዓት በሌለው ሁኔታ ተቀብለን ልናሰፍር አንችልም፤›› ብለዋል፡፡

ከክልሉ ያገኘነው መረጃ እንደሚያመለክተው፣ በደቡብ ክልል ጉራፋርዳ ወረዳ በሚገኙ 22 ቀበሌዎች ውስጥ በተለያየ ጊዜ ከሰሜኑ የአማራ ክልል መጥተው ለረጅም ዓመታት ኑሮአቸውን በዚያው የመሠረቱ ከ78 ሺሕ በላይ ዜጐች የሚገኙ ሲሆን፣ ከክልሉ ርዕሰ መስተዳደር በተላለፈ ቀጥተኛ መመርያ ከ1999 ዓ.ም. በኋላ ከሰሜን አካባቢ የመጡ ሰፋሪዎች ወደመጡበት እንዲመለሱ ታዟል፡፡ ይህን ውሳኔ ተከትሎም በአለንጋ ቀበሌ ማርያም ሰፈር በሚኖሩ ሰዎች ላይ በአስቸኳይ ተግባራዊ እንዲሆን የወረዳው የገጠር ልማት ምክትል ኃላፊ አዘዋል፡፡

የክልሉ ፕሬዚዳንት አቶ ሽፈራው ሸጉጤ ከሦስት ዓመት በፊት ለቤንቺ ማጂ ዞን አስተዳደር ጽሕፈት ቤት በጻፉት ደብዳቤ እስከ 1999 ዓ.ም. ነሐሴ 30 ድረስ የመጡ በወረዳ፣ በቀበሌ አመራርም ይሁን በራሳቸው መንገድ መሬት የያዙ ዜጐች እስከ 2 ሔክታር የእርሻ መሬትና 1000 ካሬ ሜትር የቤት መሥሪያ እንዲሰጣቸውና ባሉባቸው ቀበሌያት እንደሕጋዊ ሰፋሪ ተመዝግበው የክልሉ ነዋሪ መሆናቸውን አውቀው በክልሉ ሕጐች መሠረት እንዲተዳደሩ እንዲደረግ፣ ከ1999 ዓ.ም. ነሐሴ 30 ቀን 2003 ዓ.ም. በኋላ የመጡ ማናቸውም ዜጐች ወደመጡባቸው አካባቢዎች በሰላማዊ መንገድ እንዲሸኙ እንዲደረግና ይህም ከቀሪዎቹና ከሚሄዱት ዜጐች ጋር በሚደረግ ውይይት መደበኛ የሕግ አፈጻጸም ተከትሎ ተግባራዊ እንዲደረግ ትዕዛዝ አስተላልፈው ነበር፡፡

ፕሬዚዳንቱ በዚሁ ደብዳቤያቸው እንደገለጹት፣ በአሁኑ ወቅት በአገሪቱ ሰፋሪን በሚመለከት ያለው አሠራር ከክልል ክልል የሚፈጸም ሳይሆን በክልሎች በውስጣቸው ብቻ እንዲፈጽም የጋራ አገራዊ ስምምነት ላይ የተደረሰ ከመሆኑ በተጨማሪ፣ በርካታ ሕገወጥ ሰፋሪዎች የያዙት መሬት በክልሉም ሆነ በአገሪቱ በሰፈራ ለሚደራጁ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ በመንግሥት ዕውቅናና ባለቤትነት ከሚሰፍሩ ሰፋሪዎች በእጅጉ የተለየና የሰፋ በመሆኑ፣ የሕገወጥ የመሬት ይዞታ መጠንን ማስተካከል እንደሚገባ ስምምነት ላይ መደረሱን አስታውቀው ነበር፡፡

የክልል መስተዳደሩን ትዕዛዝ ተከትሎም የጉራፈርዳ ወረዳ የተ/ሀ/አ/ጥበቃ ኃላፊና የግብርና ጽሕፈት ቤት ምክትል ኃላፊ ለአለንጋ ቀበሌ አስተዳደር ጥቅምት 29 ቀን 2004 ዓ.ም. በጻፉት ደብዳቤ፣ የቀበሌው አመራሮችና ባለሙያዎች በሕገወጥ መንገድ መሬት የያዙ አርሶ አደሮችን ተከታትለው እንዲያስረክቡ፣ ይህንን የማያደርጉ የቀበሌ አመራሮችና ባለሙያዎች ካሉ ግን በሕግ ተጠያቂ እንደሚሆኑ አስጠንቅቀዋል፡፡

‹‹በ2003 ዓ.ም. መጨረሻ በወረዳችን በተደረገው የመሬት ልክዮሽ ሕጋዊና ሕገወጥ አርሶ አደሮች በልኬቱ ጊዜ ተለይቶ በሕገወጥ መንገድ /በሕገወጥ ምርትና በግዥ/ መሬት የያዙ አርሶ አደሮች መሬቱ ለመንግሥት ሙሉ በሙሉ ገቢ መደረጉ ይታወቃል፡፡ ምክንያቱም በመሬት አስተዳደር አጠቃቀም አዋጅ ቁጥር 110/99/ በደንብ ቁጥር 66/2000 አንድ አርሶ አደር መሬት ተለክቶ የይዞታ ማረጋገጫ ደብተር የሚሰጠው መሬቱን በሕጋዊ መንገድ ሲያገኝ ብቻ መሆኑ ተቀምጧል፡፡ ስለሆነም እስካሁን ያመረቱትን አንስተው ለቀበሌ አስተዳደር መሬቱን እንዲያስረክቡና መሬቱ የሕዝብና የመንግሥት መሆኑን አውቆ፣ ቀበሌው በደረሰው ስም ዝርዝር መሠረት ተከታትሎ መሬቱን እንዲረከብና ያልተለዩትን አሁንም በየጐጡ በመለየት ሪፖርት እንዲያደርጉ እያሳሰብን ክትትል በማያደርጉ የቀበሌ አመራርና ባለሙያ በሕግ ተጠያቂ እንደሚሆኑ ጭምር በጥብቅ እናሳስባለን፤›› ይላል የወረዳው የግብርና ጽሕፈት ቤት ምክትል ኃላፊው ደብዳቤ፡፡

የመኢአድ ምክትል የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ጌታቸው አበበ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ የመንግሥት ኃላፊዎች ነዋሪውን ሕዝብ ‹‹የያዝኩትን መሬት በፍቃዴ መልቀቄን በፊርማዬ አረጋግጣለሁ›› የሚል ወረቀት ላይ እንዲፈርሙ እያስገደዱ ነው፡፡ የሚሰፍሩበት ተለዋጭ ቦታ ሳይሰጣቸው በመሬት ላይ የተከሉት ተክል፣ ያፈሩት ሀብትና ንብረት ግምት ሳያገኝና ካሳ ሳይከፈላቸው ከክልሉ እንዲወጡ እየተደረጉ ነው፡፡

መንግሥት ለሕዝብ ከማሰብና ከመቆርቆር ይልቅ፣ ሕዝብን በማማረርና በመበደል ሥራ ላይ መጠመዱን የገለጸው መኢአድ፣ ይህ የመንግሥት ድርጊት ኃላፊነት ከጐደለው መንግሥት የሚጠበቅ እንጂ ለሕዝብ ቆሜያለሁ ከሚል መንግሥት የማይጠበቅ ተግባር በመሆኑ፣ መንግሥት እያካሄደ ካለው ዜጐችን በማፈናቀል እንቅስቃሴ በአስቸኳይ እንዲያቆም ጥሪ አቅርቧል፡፡

ከክልሉ ያገኘነው መረጃ እንደሚያመለክተው፣ የጉራፋርዳ ወረዳ ያዘጋጀው የመሬት ማስመለሻ ቅጽ እንዲህ ይላል፡፡

‹‹እኔ አቶ/ወ/ሮ ______ የመጣሁበት አገር ______ ዞን ______ ወረዳ ______ ቀበሌ ______ ጎጥ ሲሆን፣ በ______ ዓ.ም. ከነበርኩበት አገር መጥቼ ከነ______ ቤተሰቦቼ ጋር በተለያየ መንገድ መሬት ይዤ ሳርስ የነበርኩ ሲሆን፣ አሁን የክልሉ መንግሥት ባወጣው ደንብና መመርያ እንዲሁም የደቡብ ብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ክልል የተሻሻለው ሕገ መንግሥት አንቀጽ 40 ንዑስ አንቀጽ 3 በሚደነግገው መሠረት፣ መሬት የማይሸጥ የማይለወጥ የክልሉ ሕዝቦች የጋራ ንብረት በመሆኑ በሕገወጥ መንገድ በያዝኩት መሬት ላይ ያለኝ ______ እንደደረሰ በማንሳት ለቀበሌው መሬት አስተዳደር በቀን ______ ለማስረከብ ይህንን መተማመኛ ሰጥቼ የፈረምኩ ሲሆን፣ በተባለው ቀንና ሰዓት ባልለቅ /ባላስረክብ/ እንዲሁም ሌላ ተጨማሪ አዝዕርት ብዘራ በሕግ እንድጠየቅ ተስማምቻለሁ፡፡››