“ኢህአዴግ 800 ሚሊዮን አመታትን አባክኛለሁ” አለ! (አቤ ቶኪቻው)


መረጃ ቲቪ አባል በመሆን የሳተላይት ቲቪውን ቀጥታ ስርጭት፣ ወቅታዊ ዜናዎችን እና ትንተናዎችን፣ የመዝናኛ ፕሮግራሞችን፣ ስፖርት እና ሌሎችንም ዝግጅቶቻችንን በፍጥነት እና ጥራት ስልክዎ፣ ኮምፒዩተርዎ ወይም ቲቪዎ ላይ ማየት ይችላሉ። እዚህ ሊንክ ላይ በመጫን አባል ይሁኑ


ሰንደቅ ጋዜጣ በዛሬ እትሟ “አዲስ ራዕይ” የተሰኘውን የኢህአዴግ “ቅዱስ” መፅሀፍ ጠቅሳ እንደዘገበችው ከሆነ፤ ገዢው ፓርቲ ምንም እንኳ ላለፉት ሃያ አመታት ሲገዛ እና ሲሸጠን የቆየ ቢሆንም የተሳካለት ግን ግማሹን ያኸል ብቻ መሆኑን እንዳመነ አውስታለች።

ይህንን የሰሙ ሽሙጠኞችም ኢህአዴግ አስሩን አመቱ በኪሳራ ሲገዛን፤ እንዲሁም ሌላውን አስር አመት በትርፍ ሲሸጠን ከርሟል ማለት ነው ሲሉ በሪፖርቱ ተሳልቀዋል።

የምር ግን ኢህአዴግ እኮ ደስ የሚለኝ ለዚህ ነው። በኢቲቪ ቢዋሽ በአዲስ ራዕይ አይፎግርነም። ኢቲቪ ሃያውንም አመት እድገት በእድገት እንደነበርን፣ ሃያውንም አመት ከኢህአዴግ ጋር ያለፈው ግዜ ብሩህ እንደነበር፤ ግንቦት ሃያ እና የካቲት አስራ አንድ በመጡ ቁጥር ሲነግረን ከርሟል። አዲስ ራዕይ ደግሞ እንዲህ እውነቱን ታፍረጠርጠዋለች። ይሄ ጥሩ ነው። ምናልባትም እንደ ንስሀም ይቆጠር ይሆናል። (ሲሉ አስተያየት ሰጪዎች እየተናገሩ ነው። የሚለውን ጨምሩልኝማ…!)

አንድ ወዳጃችን “አስር አመት ሙሉ በብላሽ ነበር የመራናችሁ” የሚለውን ባነበበ ግዜ ወድያውኑ ያደረገው ነገር ምን እንደሆነ ያውቃሉ? የሂሳብ ማሽን ከኪሱ አወጣ ቀጠለናም፤ አስር የኪሳራ አመታትን ከእያንዳንዳችን መወሰዱን አሰመረበት ከዛስ…? ከዛማ የሰማንያ ሚሊዮኖች አስር አመት ስንት እንደሚመጣ መታው… 80ሚሊዮን ሲባዛ በ10 እኩል ይሆናል… 800 ሚሊዮን አመታት መጣ። “ስለዚህ መንገስታችን ይህንን ደሁሉ ጊዜ ስቀልድባችሁ ነበር እያለን ነው ማለት ነው።” ሲል ብስጭቱን ገልፆልናል።

የምር ግን ወዳጄ ሃያ አመት ሙሉ በስልጣን ላይ የነበረ ገዢ አፉን ሞልቶ “ግማሹን ብቻ ነው የተሳካልኝ!” ማለቱ ምን ማለት ነው? አልሆን ሲለው በቃኝ ብሎ አለመልቀቁ አያስጠይቅም ትላላችሁ? ቢያንስ ቢያንስ በእግዜሩ ዘንድ ማስጠየቁ አይቀርም ካላችሁ እናንተ የተባረካችሁ ናችሁ!

ቀጥሎ የሚገኘው የመካሪዎች ድምፅ ነው…

ኢህአዴጎች ሆይ ግማሽ ቀልድ ግማሽ ስራ ከኮሜዲያን እንጂ ከመንግስት የሚጠበቅ አይደለም እና የባከኑትን አስር አመታት ኪሳራ ከእግዜር እናገኘዋለን እናንተ ግን ሌላ አስር አመታት ደግሞ ሳታባክኑ ቢያንስ ቢያንስ አረፍ በሉ! … አይዟችሁ ቀጥሎ ደግሞ ተመልሳችሁ ወይ ታባክናላችሁ ወይ ትሰራላችሁ! ጎሽ እሺ በሉና ዛሬውኑ እረፍት አድረጉ ጎሽ…

መስታወሻ

የዝች አጭር ጨዋታ ሀሳብ ባለቤት የፌስቡክ ወዳጄ  “ጆሞ” መሆኑን ለመጥቀስ እወዳለሁ።

Filed under: Uncategorized