ይድረስ ለአቶ መለስ፤ አንድ ቀልድ ልንገርዎ…! (አቤ ቶኪቻው)


መረጃ ቲቪ አባል በመሆን የሳተላይት ቲቪውን ቀጥታ ስርጭት፣ ወቅታዊ ዜናዎችን እና ትንተናዎችን፣ የመዝናኛ ፕሮግራሞችን፣ ስፖርት እና ሌሎችንም ዝግጅቶቻችንን በፍጥነት እና ጥራት ስልክዎ፣ ኮምፒዩተርዎ ወይም ቲቪዎ ላይ ማየት ይችላሉ። እዚህ ሊንክ ላይ በመጫን አባል ይሁኑ


በአንድ ቤተሰብ ውጥ የሚኖሩ ሰዎች ነበሩ። የቤተሰቡ ሃላፊ የሆኑት አባወራ ሲያገኙ በድፍረት ሲያጡም በሌላ ድፍረት ጠጥተው ሞቅ ብሏቸው ነው የሚገቡት። ስጠረጥር የዘንድሮ ኑሮ እንደምንም ብለው ሞቅታ ውስጥ ካልተደበቁ በስተቀር እንደማይቻል ገብቷቸዋል።

አሁንም ስጠረጥር አባወራው በዱቤም ይሁን፣ በብድርም ይሁን፣ በቅልውጥ መጠጥ ቤት ካላመሹ በቀር በጊዜ ቤታቸው ቢገቡ የቤተሰቡ አባላት የሚጠይቋቸውን ጥያቄ መመለስ እንደማይችሉ  ስለሚረዱትም ይመስለኛል።

ታድያልዎ ከእለተታ አንድ ቀን አንዱ ልጃቸው “ዛሬስ አባዬ ሲመጣ ጠብቄ የማናግረው አለኝ” ብሎ ሲጠብቅ፣ ሲጠብቅ፣ ሲጠብቅ ተስፋ ሊቆርጥ ትንሽ ሲቀረው መጡ…ማ…? አባወራው! ልጅም ገና እንደመጡ የተበጫጨቀ የትምህርት ቤት ዩኒፎርሙን እያሳያቸው “አባዬ… ይኸውልህ ትምህርት ቤት የምለብሰው ዩኒፎርም ይሄ ነው… ጓደኞቼ እብዱ እብዱ… እያሉ ያበሽቁኛል። ደሞ ደብተሬም አልቋል። ሌላ ደግሞ …” እያለ ጥያቄ ቢያከታትልባቸው ግዜ በሞቅታ እና በመልስ እጦት ውስጥ ያሉት አባት ምን አሉት መሰልዎ… “አንተ ልጅ ዘወር በል ፖለቲካ አታውራብኝ!”

ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር ቀልዱ አላስቆትም!? እንግዲያስ ከቀልብዎ አይደሉም ማለት ነውና ደግመው ያንብቡት። ዘንድሮ እንደሁ ባለስልጣኑ ቀልብ ነዋሪው ደግሞ ቀለብ በፅኑ የተቸገረበት ሁኔታ ነው ያለው (አሁን እኔው ሳቄ መጣ!)

ይህንን ቀልድ ለምን አወራሁልዎ እንደው እስቲ ዘና ላድርጋቸው ብዬ ነውን? በፍፁም አይደለም አንበሳዬ… እህስ ይበሉና ይከተሉኝ ይምጡ አዲስ መስመር ላይ፤

አቶ መለስ የምሬን ነው የምልዎ ግራ መጋባት ይታይብዎታል። ትንሽ ይረጋጉ እንጂ… (አክብሬዎት እንጂ ሞቅታ ውስጥ ነው ያሉት!) ብዬ ልናገር ነበር። ነገር ግን ጠቅላይ ሚንስትሬ ነዎትና እንዲህ እንደዞህ አልልዎትም። ነገረ ስራዎ ግን ከላይ ካነሳውልዎ ሞቅ ያለው አባት ጋር ይመሳሰላል።

ከየትኛው ልጀምርልዎ…

የዋልድባ ገዳም መነኮሳት ገዳማችን አይታረስ የአባቶቻችን አፅም አይፈንቀል… ብለው አቤት ቢሉ “ድብቅ የፖለቲካ ፍላጎት ያላቸው መነኩሴዎች አሏቸው” ይቅር ይበልዎ…! (አንድ ይበሉልኝ)

መምህራን ኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ያቀረበብን ዘገባ ትክክል አይደለም “ህይወታቸውን የሚቀይር ገንዘብ ተጨመረላቸው ብሎ ዘግቦ ህይወታችንን አዘበራረቀው በይፋ የተናገረው ስህተት መሆኑን ይናገርልን” ብለው አቤት ቢሉ “ድብቅ የፖለቲካ አጀንዳ ያላቸው መምህራን!” አሉዋቸው። (ሁለት)

ከደቡብ ክልል አማራዎች መፈናቀላቸው አግባብ አይደለም በሚል እኔ ሳልቀር አቶ ሽፈራው ሽጉጤ ያደረጉት ነገር ለመንግስትዎም ጥሩ ስም አያሰጠውምና አንድ ይበሉዋቸው ብለን ብንጠይቅዎ፤ “በኢትዮጵያዊነት እንታወቅ የሚሉ ልዩ የፖለቲካ ጥቅም ፈላጊዎች…” ሲሉ ሃሳቡን አጣጣሉት (እየቆጠሩ ነው…? ሶስት ይበሉልኝ)

“እስልምና ሃይማኖታችን ላይ ጣልቃ አይግቡ አህባሽን ከወደዱት ራስዎ ሊያምኑ ይችላሉ እኛ ላይ ግን አይጫኑብን እኛ ሙስሊሞች አላህን እንዴት እንድምናምን መንግስት ሊያስተምረን አይገባም መንግስት ሌላ ሀይማኖት ሌላ!” የሚል ተቃውሞ ሲነሳብዎ “ይሄ አክራሪነት ነው የተለየ የፖለቲካ አጀንዳ ያነገቡ እንደ ቱኒዚያ፣ እንደ ግብፅ፣ እንደ ሊቢያ፣ እንደ የመን እና እንደ ሴሪያ መሆን የፈለጉ ሰዎች የሚያነሱት አጀንዳ ነው…!” ብለው በራሰዎ ላይ አሟርተው  እርፍ አሉ።

እንደው የቅርብ የቅርቡን ልንገርዎት ብዬ እንጂ ሌላም ብጨምር ማለቂያ የለውም… የተጠየቁት ጥያቄ በሙሉ ፖለቲካ እየመሰልዎ ግራ ገብትዎ ግራ አጋብተውናል።

ነገረ ስራዎን እስቲ ልብ ብለው ይመልከቱት ሁኔታዎ “አባዬ ዳቦ ራበኝ” ለሚል ልጅ “ዘወር በል ድብቅ ፖለቲካ አታራምድብኝ” ብሎ የሚመልስ ሞቅታ ከተጠናወተው አባት ጋር ይመሳሰላል።

ክቡርነትዎ ሞቅ ካልዎ ቀዝቀዝ ያለ ሽሮ ፍትፍት ይውሰዱበት እና ጥያቄዎቹን በሙሉ ድጋሚ ይስሟቸው። እውነት እውነት እልዎታለሁ እስከ አሁን የሰማናቸው ጥያቄዎች በሙሉ አንድም ፖለቲካ የላቸውም።  ይልቅስ እንዲህ ሲያደፋፍኑ የፖለቲካ ጥያቄው እንዳይመጣብዎ ይፍሩ! “ለምን እፈራለሁ ሙሉ ትጥቅ እያለኝ!” ካሉ አሁንም ሞቅታ ውስጥ ነዎት ማለት ነውና ሲነጋ እንነጋገራለን!