መስጂድ የተገኙት እስከ አሁን ካልወጡ ለዋልድባው ገዳም ደግሞ ይቀመጡ


መረጃ ቲቪ አባል በመሆን የሳተላይት ቲቪውን ቀጥታ ስርጭት፣ ወቅታዊ ዜናዎችን እና ትንተናዎችን፣ የመዝናኛ ፕሮግራሞችን፣ ስፖርት እና ሌሎችንም ዝግጅቶቻችንን በፍጥነት እና ጥራት ስልክዎ፣ ኮምፒዩተርዎ ወይም ቲቪዎ ላይ ማየት ይችላሉ። እዚህ ሊንክ ላይ በመጫን አባል ይሁኑ


እኔ ዘወትር ስለመንግስቴ የምጨነቀው፤ እኔ ሁሌም የፀሐዩ መንግስቴ ነገር የሚያቃጥለኝ፣ እኔ ከታማሚ ካድሬዎች ይልቅ ለድርጅታችን ታማኝ የሆንኩት… ሰሞኑን ስለመንግስቴ አብዝቼ ስጨነቅ እና ስጠበብ ቆይቻለሁ።

ባለፈው ግዜ በመርካቶው አንዋር መስጂድ ውስጥ ሁለት የመካከለኛው ምስራቅ ወጣቶች “በቁጥጥር ስር” ውለው በኢቲቪ ዜና አይተናቸዋል። ወጣቶቹ “ከኤርፖርት በቀጥታ መርካቶ ሄደው ወረቀት ሲበትኑ እንደነበር” ተነግሮናል። እዚች ላይ አንዳንድ አስተያየቶችን ሰጥቼ ዘወር ልበል። እኔ የምለው ምናባታቸው ቆርጧቸው ነው ወረቀት የሚበትኑት? የሚለው ብስጭት ውስጤ እንዳለ ሆኖ ሲበትኑ የነበረውን ወረቀት ግን ብናየው  እንዴት ደስ ይለኝ ነበር።  አዎና ለብዙዎች ትምህርት ይሆን ነበር። በርግጥ እኔ እንደምጠረጥረው ከሆነ ዘንድሮ ሁሉ ሰው የተነሳው በርሳቸው ላይ ነውና ፈረንጆቹ ሲበትኑ የነበረው ወረቀት “መለስ በቃ” የሚል እንደነበር እጠረጥራለሁ። ይቅርታ እዝች ጋ ትዝ ያለኝን በአዲስ መስመር ላይ እናውጋት፤

በነ ኤልያስ ክፍሌ መዝገብ ተብሎ እነ ውብሸት ታዬ ፍርድ ቤት ሲመላለሱ በነበረበት ወቅት ያጋጠመኝን ነው የማወጋዎ… (ክቡር ፍርድ ቤት ይሄ ጉዳይ እልባት ስላገኘ እንዳሻን መቧለት እንችላለን አይደል…?) ‘ቴንኪው’ ክቡር ፍርድ ቤት እቀጥላለሁ፤ እናልዎ ያስታውሱ እንደሆነ ውብሸት ታዬ መታሰሩን ስንሰማ “የኤሌክትሪክ እና መብራት ሃይሎችን ለማውደም ሲሉ በህብረተሰቡ ጥቆማ በቁጥጥር ስር ዋሉ!” ተብሎ ነበር የተዘገበልን።

እኛም ታድያ አምርረን “እነዚህ እርኩሶች…” ብለን ጥርሳችንን ነክሰንባቸው ስናበቃ እንዴት እንዴት ብለው የስልክ እና የኤሌክትሪክ ተቋምን ሊያፈርሱ እንደነበር መስማት አለብን በማለት በየቀጠሮው ሁሉ ከፍርድ ቤት አንቀርም ነበር። ላካስ አቃቤ ህጉ ዋናውን ክስ ረስቶት ኖሮ፤  ክሱ “በቃ” የሚል ፅሁፍ አደባባይ ላይ አስፅፋችኋል ፎቶግራፍ አንስታችኋል በኢሜልና ፌስ ቡክ መልዕክት ተለዋውጣችኋል” በሚል ተለውጦ ተገኘ።

በዚሁ የተበሳጩ አንዳንድ ተቆርቋሪዎች “በቃ” የሚለውን የለጠፋችሁት ቴሌ ዋናው መስሪያ ቤት በር ላይ እና ግልገል ግቤ ሃይል ማመንጫ ላይ ነው! ቢባል እንኳ መጀመሪያ የሰማነውን ክስ ይመስል ነበር። ሲሉ አጉረምርመው እንደነበር ይታወሳል። የሆኖ ሆኖ ፍርድ ቤቱ ምን ሲደረግ “በቃ” ትላላችሁ ብሎ በርካታ አመታት ሲደመር ደጎስ ያለ ብር ፈርዶባቸዋል። ይኸው ከዛ በኋላ እንኳንስ ሌላ ቀርቶ ማህበረሰቡ የሚበላውን ምግብ ሆነ የሚጠጣውን ውሃ ሲበቃው፤ “በቃኝ” ማለት ፈርቶ እጅ በማውለብለብ ወይም አንገት በመነቅነቅ ብቻ ሆኗል ሀሳቡን የሚገልፀው። አስተማሪ የሆነ ርምጃ ማለት ይሄ ነው። ይሄማ ርምጃ አይደለም ሩጫ ነው… ካሉኝም ይሆናል።

ውይ ወዳጄ እልም ብዬ ሌላ ወግ ውስጥ ገባሁ አይደል? አሁን ወደ ዋናው መስመር ተመልሻለሁ። ከወዳጆቼ ጋር ስናወጋ እነዚህ ከመካከለኛው ምስራቅ መጥተው መስጂድ ውስጥ የተገኙት ልባቸው የተደፈነ ጎረምረሶች ሲበትኑ የነበረው ወረቀት ምንነት ብናውቀው እና እነርሱም ላይ አስተማማኝ ርምጃ ቢወሰድ ለሁሉም ትምህርት ይሆን ነበር። የሚል አስተያየት ሰንዝሪያለሁ።

ይህንን አስተያየት ስሰጥ የሰማኝ አንድ ወዳጄ፤ “ርምጃው በአስተማሪነቱ እንኳ እንከን አይወጣለትም” አለኝ። ቀጠለናም፤ “አነዚህ ፈረንጆች ከሌላ ሀገር የመጡ ስለሆኑ በ24 ሰዓት ውስጥ ወደ ሀገራችሁ ተመለሱ ከተባሉ፤ እኛ ሀገራችን እዚሁ የሆነው፤ በተመሳሳይ መልኩ ወረቀት ስንበትን የተገኘን እንደሆነ መንግስታችን በ24 ሰዓት ውስጥ ወደ መጣንበት ሊመልሰን ነው ማለት ነው። ከዚህ የበለጠ አስተማሪ እርምጃ ከየት ይምጣልህ?” አለኝ። እኔም እኛ የመጣንበት የት ነው? ብለው  በጣቱ ወደ ሰማይ እየተኮሰ “ከአላህ ዘንድ ነዋ!” አይለኝ መሰልዎ…

እንደዚህ ወዳጄ ንግግር መንግስታችን ባለፈው ግዜ አርሲ አሳሳ ውስጥ ወደ ሰባት የሚጠጉ ወጣቶች ላይ የወሰደባቸው ርምጃ ለዚህ ማሳያ ነው።

የምር ግን መንግስት በሆነ ባልሆነው እግዜሩ የሰጠን ቪዛ ሳያልቅ “ወደመጣችሁበት ተመለሱ” እያለ የሚያሰናብተን ከሆነ ከእግዜሩ ጋር ያለው ዲፕሎማሲ አይሻክርበትም ትላላችሁ?  በዚህ ጉዳይ ላይ ማብራሪያ እንዲሰጡን በውጪ ጉዳይ ሚኒስቴር አፈ ቀላጤ አቶ ዲና ሙፍቲንን ብንጋብዝ “በአሁኑ ሰዓት ከተለያዩ ሀገሮች ጋር መልካም ግንኙነት አለን በተለይም ከቻይና… ስለዚህ ከእግዜሩ ጋር ያለን ግንኑነት አያሳስበንም!” ሊሉን እንደሚችሉ እንጠርጥር ወይስ አንጠርጥር…?

የኔ ነገር…  አረ ወደ ዋናው ርዕሰ ጉዳይ መልሱኝ ወዳጄ… እኔ የምለው እነዛ በመስጊድ የተገኙ የመካከለኛው ምስራቅ ጎረምሶች ግን ወደ ሃገራቸው መመለሳቸውን እንደ አንድ የመንግስት ታማኝ  አልደገፍኩትም ብዬ ጀምሪልዎ አይደል። ለምን በሉኝ…? ለምን ማለት ጥሩ ጥያቄ ነው…! ነገ ደግሞ “ዋልድባ ገዳም ወረቀት ሲበትኑ ተገኙ” ብለን ዜና ለመስራት ገና ሌላ ሰው ልናስመጣ ነው? እንደኔ አስተያየት ከሆነ በ ”ቢፒአር” ም እንተሰለጠንነው አንድን ስራ በጥቂት ሰዎች ማሰራት ውጤቱ አመርቂ ነው። በዛ ላይ ደግሞ ገና ሌላ ሰው ማሰልጠን እና መለማመጡም መካራ ነው። እናም እላለሁ መስጂድ የተገኙት እስካሁን ካልወጡ ለዋልድባ ገዳም ደግሞ ይቀመጡ!

ሰላም ነዎት ግን ወዳጄ ትላንት እኮ አልተገናኘንም… ሰላም ይግጠመን እስቲ!