በእነ አንዱዓለም አራጌ ላይ ውሳኔ ሳይሰጥ ቀረ


መረጃ ቲቪ አባል በመሆን የሳተላይት ቲቪውን ቀጥታ ስርጭት፣ ወቅታዊ ዜናዎችን እና ትንተናዎችን፣ የመዝናኛ ፕሮግራሞችን፣ ስፖርት እና ሌሎችንም ዝግጅቶቻችንን በፍጥነት እና ጥራት ስልክዎ፣ ኮምፒዩተርዎ ወይም ቲቪዎ ላይ ማየት ይችላሉ። እዚህ ሊንክ ላይ በመጫን አባል ይሁኑ


በሽብርተኝነት ተጠርጥረው በፌዴራል ዓቃቤ ሕግ ክስ የተመሠረተባቸው አቶ አንዱዓለም አራጌን ጨምሮ በስምንት ተጠርጣሪዎች ላይ ውሳኔ ለመስጠት ለግንቦት 3 ቀን 2004 ዓ.ም. ተሰጥቶ የነበረው ቀጠሮ ለሰኔ 14 ቀን 2004 ዓ.ም. ተቀጠረ፡፡ ክሱን እየመረመረው የሚገኘው የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ሦስተኛ ወንጀል ችሎት፣ መጋቢት 18 እና 19 ቀን 2004 ዓ.ም. የተሰሙ የተጠርጣሪዎቹ የመከላከያ ምስክሮች ቃል ከመቅረጸ ድምፅ ተገልብጦ ከመዝገቡ ጋር አለመያያዙንና ቀደም ብሎ የተሰማውም የመከላከያ ምስክሮች ቃል ከመዝገቡ ጋር የተያያዘው በቅርቡ በመሆኑ ሊደርስ እንዳልቻለ ለተጠርጣሪዎቹ አስረድቷል፡፡

አቶ አንዱዓለም አራጌ ችሎቱ እንደተሰየመ ባቀረቡት አቤቱታ፣ ‹‹ቤተሰቦቻችን፣ ጋዜጠኞችና የውጭ አገር ዜጐች ገብተው የመጨረሻውን ውሳኔያችንን እንዲሰሙ እንፈልጋለን፤ በመሆኑም ፍርድ ቤቱ ሰፋ ያለ አዳራሽ ይፍቀድልን፤›› በማለት ቢያመለክቱም፣ ለማመልከቻቸው ብይን ሳይሰጥ ውሳኔው አለመድረሱ ተነግሮ ጥያቄው ታልፏል፡፡

አቶ አንዱዓለም አያሌው የተባሉ ሌላ ተጠርጣሪ፣ ‹‹በማረያ ቤት ውስጥ እየረደሰብኝ ያለ በደል አለ፤ ፍርድ ቤቱ ሰምቶኝ ብይኑን በችሎት ይስጥልኝ፤›› በማለት ቢያመለክቱም፣ አቤቱታቸውን በጽሑፍ አድርገው በጽሕፈት ቤት በኩል እንዲያመለክቱ ፍርድ ቤቱ በመግለጽ፣ ችሎቱ አብቅቷል፡፡ ውሳኔውን ለመከታተል በኢትዮጵያ የአሜሪካ አምባሳደር፣ የእንግሊዝና የጀርመንን ዲፕሎማቶች፣ የተጠርጣሪዎቹ ቤተሰቦች፣ የአገር ውስጥና የውጭ አገር ጋዜጠኞች ተገኝተዋል፡፡

በሽብርተኝነት ተጠርጥረው ክስ ከተመሠረተባቸው ተጠርጣሪዎች መካከል አንዱዓለም አራጌ፣ ናትናኤል መኮንን፣ ዮሐንስ ተረፈ፣ የሸዋስ ይሁንዓለም፣ ክንፈሚካኤል ደበበ፣ ምትኩ ዳምጤ፣ እስክንድር ነጋና አንዱዓለም አያሌው በማረሚያ ቤት ሆነው ውሳኔያቸውን እየተጠባበቁ ይገኛሉ፡፡