“ጉልቻ ቢለውጥ ወጥ አያጣፍጥም” (የኢትዮጵያን ሪቪው ወቅታዊ ርዕሰ አንቀጽ)


መረጃ ቲቪ አባል በመሆን የሳተላይት ቲቪውን ቀጥታ ስርጭት፣ ወቅታዊ ዜናዎችን እና ትንተናዎችን፣ የመዝናኛ ፕሮግራሞችን፣ ስፖርት እና ሌሎችንም ዝግጅቶቻችንን በፍጥነት እና ጥራት ስልክዎ፣ ኮምፒዩተርዎ ወይም ቲቪዎ ላይ ማየት ይችላሉ። እዚህ ሊንክ ላይ በመጫን አባል ይሁኑ


 “ጉልቻ ቢለውጥ ወጥ አያጣፍጥም” የኢትዮጵያን ሪቪው ወቅታዊ ርዕሰ አንቀጽ

  በፒ.ዲ.ኤፍ. ለማንበብ እዚህ ላይ ይጫኑ

በኢትዮጵያ ላይ እንደ አልቅት ተጣብቆ የህዝቡን ደም እየመጠጠ፣ እየገደለ፣ እያሰቃየና የፈለገውን እያደረገ ለሃያ አንድ ዓመታት በሥልጣን ላይ የቆየው ቅጥረኛው፣ ጎሰኛው፣ አምባገነኑና ዘራፊው የህወሃት አገዘዝ ቁንጮ መለስ ዜናዊ በስልጣን ላይ ቢቆይም ወይም በትረ ስልጣኑን ለሌላ ወያኔ ቢያስተላልፈው፣ አጠቃላዩ የአፈናውና የግፈኛው ሥርዓት ተገርስሶ እስካልወደቀ ደረስ ለኢትዮጵያ ሕዝብ የሚያመጣው አንዳችም ለውጥ አይኖርም።  ሕወሃቶች ከደደቢት በረሃ ተማምለው የመጡበትን ታላቁንና ለብዙ ዘመናት የኖረውን የኢትዮጵያን ሉዓላዊነቷንና አገራዊ አንድነቷን የማፈራረስና የማዳከም የጥፋት ዓላማቸውን ከሥልጣን እስካልተነቀሉ ድረስ እንደሚቀጥሉበት በሥልጣን ኮርቻ ላይ ከተፈናጠጡበት ጊዜ አንስቶ እየታየ ነው። “ከዝንጅሮ ቆንጆ ምን ይመራርጡ” እንደሚባለው መለስ ዜናዊ በሌላ ወያኔ ቢተካ ለኢትዮጵያ ሕዝብ የሚያመጣው ምንም ዓይነት ለውጥ አይኖርም።

የህወሃት ቡድን ከመነሻው አንስቶ እስከአሁን ድረስ ከአርባ ዓመታት በላይ የሰራበትን ወደፊትም ለመቀጠል በዕቅድ ይዞ የሚንቀሳቀስበትን መሠረታዊ የኢትዮጵያን ብሔራዊና አገራዊ አንድነት የማፈራረስና የማላላት እኩይ ዓላማ ኢትዮጵያዊያን እስካላስቆሙት ድረስ እንደሚቀጥልበት ምንም ዓይነት ብዥታ ሊኖር አይገባም።  አንዳንድ የዋሆች  የእባቡን የወያኔን ባሕርይ ካለመረዳት እንደሚሉት “መለስ በሌላ ወያኔ ቢተካ የተሻለ ጊዜ ሊመጣ ይችላል” ብለው ሲናገሩ ይደመጣሉ። የወያኔ ድርጅት እንደ ድርጅት አምባገነን፣ ጸረ-ዲምክራሲ፣ አፋኝ፣ ጎሰኛ፣የንጹሃን ደም አፍሳሽና ከሁሉም በላይ ጸረ ኢትዮጵያዊ ነው። ስለሆነም የወያኔን ድርጅት እንደ ድርጅትና ሥርዓት ከኢትዮጵያ ህዝብ ጭንቃ ላይ አወርዶ በማፈራረስ በምትኩ ኢትዮጵያዊ የሆነ ዲሞክራሲያዊ ድርጅት መተካት እንጅ ወያኔዎችን  አንዱን ወያኔ ከሌላው ወያኔ ጋር በማነጻጸር “እከሌ ከእከሌ” ይሻላል እያሉ ከእውነታው የተለየ ጉንጭ አልፋ ወሬ ማናፈስ፣ ወያኔዎችን መጥቀም እንጅ ለኢትዮጵያ ሕዝብ ምንም ማለት አይደለም።

በቅርቡ ወያኔመውደቂያው እንደተቃረበ ስላወቀ እንዳበደ ውሻ በመልከፍከፍ  ከፍተኛ ትኩረቱን ያደረገው የሃይማኖት ተቋማትን ማጋየትና ማፈራረስ እንዲሁም ምዕመናንን ማበጣበጥ ላይ ነው። ታሪካዊዎቹን የአሰቦትና የዝቋላ ገዳማት ላይ እሳት በመለኮስ እንዲሁም ጥንታዊውንና ተደፍሮ የማያውቀውን የዋልድባ ገዳምን በመድፈር የመንኮሳትን መካነመቃብር በትራክተር በማረስና ቤተመቅደሶችን በማፈራረስ እኩይ ተገባር ላይ ተሰማርቶ ይገኛል። ሙስሊም ኢትዮጵያዊያንን ሙሉ በሙሉ በቁጥጥሩ ስር ለማስገባት ወያኔ እንደ ሸቀጥ ከውጭ ባስመጣው “አህባሽ”  በሚባለው የተጭበረበር አስትምህሮት ሐይማታቸውን ለመበረዝና ለመከለስ እንዲሁም የሀገር ፍቅራቸውንና አንድነታቸውን ለማናጋት የሚያደርግባቸውን   ደባ ለማክሸፍ ሙስሊም ኢትዮጵያዊያን የሕይወት መስዋዕትነት ጭምር እየከፈሉ ይገኛል። ወያኔ ይህ ብቻ ሳይበቃው ሙስሊም ኢትዮጵያዊያን የሃይማኖታቸውን አስተዳዳሪዎችን እራሳቸው በመስጊዶቻቸው መምረጥ ሲገባቸው ሰርጎ ገብ ካድሬዎችን በማሰማራት ሐይማኖታቸውን በሰላም እንዳያካሂዱ እንቅፋት በመፍጠር ላይ ይገኛል። ሆኖም ሙስሊም ኢትዮጵያዊያን በአንድ ቃልና ድምጽ በሙስሊምነታቸውና በኢትዮጵያዊነታቸው ወያኔ የሚያደርስባቸውን ግፍና በደል ተጋፍጠው በመመከት ላይ ይገኛሉ። ይህ ሙስሊሞች መብታቸውን ለማስከበር በሰላማዊና ህጋዊ ሁኔታ በማድረግ ላይ ያሉት እንቅስቃሴ ወያኔን  በከፍተኛ ሁኔታ ፍርሃትና መርበትበት ውስጥ ጥሎታል። የሙስሊሞች ጥያቄ ወያኔን እንዲህ ሊያንዘፈዝፈውና ሊያወራጨው  የቻለው ሙስሊሞች እንደ ሙስሊምነታቸውንና እንደ ኢትዮጵያዊነታቸው አንድ  ሆነው በመነሳታቸውና የወያኔን የጎሳ አጥር ሰበረው በመውጣታቸው ነው። ሙስሊሞች እንደ ኢትዮጵያዊ ሆነው ጥያቄያቸውን በአንድነት ባያቅርቡና በተበታተነ ሁኔታ ቆመው ቢሆን ኖሮ ወያኔ “የኦሮሞ ሙሲሞች እንዲህ አሉ” ወይም “የአፋር ሙስሊሞች እንዲያ አሉ” ወይም የጉራጌ ሙስሊሞች ይህንን ጠየቁ ወዘተ” እያለ  እንደለመደው ከፋፍሎ ለመግዛት በሚችልበት ህኔታ ሊያላግጥበትና ለራሱ መጠቀሚያ ሊያደርገው በቻለ ነበር። ሙስሊም ኢትዮጵያዊያን በዚህ ተጋድሏቸው የኢትዮጵያን ሕዝብ አንድነትና በጎሳ አለመለያየት ለወያኔ ብቻ ላይሆን ለመላው ዓለምም አረጋገጠዋል።ይህም የትግል ሥልት ለወደፊቱ በተጠናከረና በተቀላጠፈ ሁኔታ ሊቀጠልበት የሚገባ በፍጥነት ውጤት የሚያመጣ የትግል ዘዴ ነው።

ኢትዮጵያውያኖች በሙሉ በአሁኑ ሰዓት ጎሳና ሃይማኖት ሳይለዩ ከወያኔ ጋር ከፍተኛ ትንንቅና ፍልሚያ የገቡበትና የሚደርሳባቸውን ጭቆናና የግፍ አገዛዝ ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ለማስወገድ የህይወት መሰዋዕትነትን ጭምር እየከፈሉ የሚገኙበት ወሳኝ ወቅት ነው። ስለሆነም ኢትዮጵያዊያን ይህንን በኢትዮጵያዊነት የጀመሩትን አንድነት አጠናክረው በመቀጠል ይህንን የበሰበሰ አምባገነንና ፈላጭ ቆራጭ፤ ከላይ እስከ ታች ድረስ ድረስ በምዝበራ፣ በጉቦና በዝርፊያ የተጨማለቀ የባዕዳን ተላላኪ የወያኔን አገዛዝ አሽቀጥረው የሚጥሉበት ጊዜ ቅርብ እንጅ እሩቅ እንደማይሆን ሳይታለም የተፈታ ነው።