Skip to content

ጥቁሩ ሰው

“ጥቁሩ ሰው” ይናገራል!

የ አቶ ኦባንግ ሜቶ ቃለ ምልልስ ከ ጎልጉል ድረ ገጽ ጋር

November 16, 2012

Obang Metho

“ጥቁሩ ሰው” ይሉታል። ኢትዮጵያዊያን ለሚያሽከረከራት አስፈሪ ፈተና መፍትሄው ሰብአዊነትን ማስቀደም ብቻ ነው የሚል የጸና እምነት አለው። “ከጎሳ በፊት ሰብዓዊነት” በሚል መሪ ዓላማ ከሚመስሉት ጋር በመሆን ድርጅት አቋቁሞ መሥራት ከጀመረበት ጊዜ አንስቶ ባከናወናቸው ሥራዎች ከፍተኛ እርካታ እንደሚሰማው ያምናል። ኢትዮጵያዊያን ችግር ደርሶባቸዋል በሚባልበት ሁሉ ቀድሞ ደራሽ እንደሆነ ብዙዎች ይመሰክሩለታል። በዚህና በሰብዓዊ መብት ጉዳይ በሰራቸው ስራዎቹ ቁጥራቸው ቀላል የማይባሉ ደጋፊዎችና አድናቂዎች ለማፍራት ቢችልም “ከጀርባው ድብቅ ዓላማና አጀንዳ አለው፣ ብቻውን ይሮጣል” የሚሉትን ጨምሮ በግል አቋሞቹ ዙሪያ ነቀፌታ የሚሰነዝሩበትም አሉ።

የወደፊት ዕቅዱና የሚነቅፉት እንደሚሉት መቼ ፖለቲካ ፓርቲ መስርቶ ይፋ ያደርጋል? በሚሉትና በተመሳሳይ ጉዳዮች ዙሪያ ኦባንግ ሜቶ ከጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ ጋር ቃለ ምልልስ አድርጓል። ኦባንግ ሜቶ (ጥቁሩ ሰው) የአንደኛ ደረጃ ትምህርቱን ጋምቤላ ተማረ። ከዚያም ሁለተኛና የዩኒቨርሲቲ ትምህርቱን ካናዳ ተከታትሎዋል። በመጀመሪያ የጋምቤላ ልማት ኤጀንሲ (GDA) የሚባል ድርጅት አቋቁሞ በርካታ ተግባራትን እያከናወነ ነበር፡፡ በኋላም በጋምቤላ የዛሬ 9ዓመት አካባቢ ከ400 በላይ አኙዋኮች ሲጨፈጨፉ ህይወቱ ተቀየረ፡፡ ሁኔታው በአመለካከቱ ላይ ብቻ ሳይሆን በግል ህይወቱ ላይ ከፍተኛ ለውጥ አመጣ፡፡ ሁሉንም ትቶ ድምጽ አልባ ለሆኑት ድምጽ ለመሆን የአኙዋክ የፍትሕ ምክርቤትን በማቋቋምና በኃላፊነት በመሥራት የመለስ አገዛዝን እና የወንጀሉን ተዋናዮች በዓለምአቀፍ ፍርድርቤት ሊያስከስስ የሚችል ተግባር አከናወነ፡፡ ሆኖም ችግሩ የአኙዋክ ብቻ ሳይሆን የመላው ኢትዮጵያ መሆኑን በጥልቅ ከተረዳ በኋላ ኢትዮጵያ ነጻ ሳትወጣ አኙዋክ ብቻ ወይም ሌላው እንዲሁ በግሉ ነጻ ቢወጣ ችግሩ ፈጽሞ ሊቃለል እንደማይችል በተረዳበት ጊዜ ትግሉን ቀየረ፡፡ አዲሲቷ ኢትዮጵያ ብትመሠረት የሁላችንም ችግር መፍትሔ እንደሚያገኝ በማስተዋል ከበርካታ ኢትዮጵያውያን ጋር በመሆን ለአዲሲቷ ኢትዮጵያ የጋራ ንቅናቄን (አኢጋን) (http://www.solidaritymovement.org/) በማቋቋም የትግሉን መስመር አሰፋው፡፡ “ሁላችንም ነጻ ካልወጣን ማንም ብቻውን ነጻ መሆን አይችልም” የሚለውን መሪ መፈክር በማንገብ “ከጎሣ ይልቅ ለሰብዓዊነት ቅድሚያ” እንዲሰጥ በመታገል ዓመታትን አስቆጥሯል – ኦባንግ ሜቶ ለአዲሲቷ ኢትዮጵያ የጋራ ንቅናቄ ዋና ዳይሬክተር!

ጎልጉል፦ደስተኛ ነህ?

ኦባንግ፦ዘወትር የምመለከተው ወደፊት ነው። የማምንበትን አደርጋለሁ። የማደርገው ሁሉ ለኅሊናዬ ስል ነው። ኅሊናዬን እረፍት የሚነሳ ነገር አላደርግም። ግልጽ ነኝ።ዕቅዴ፣ ሃሳቤ፣ እምነቴ፣ ቀናነትና መደጋገፍ ላይ የተመሰረተ በመሆኑ ዘወትር ደስተኛ ነኝ። በየቀኑ በርካታ በረከቶች አሉኝ። ይህንን ስል ሃዘን አይሰማኝም ማለት ግን አይደለም። በርካታ ጉዳዮች እረፍት ይነሱኛል። ማንም ለራሱ ብቻ መኖር የለበትም …

ጎልጉል፦በተለይ የሚያስደስትህ ምንድር ነው?

ኦባንግ፦የወገኖቼን ችግር ለመቅረፍ የማደርገው ጥረት ልዩ እርካታ ይሰጠኛል። ሰዎችን ለመርዳት ተንቀሳቅሼ ምላሹ መልካም ዜና ሲሆን ደስታዬ ልዩ ነው። የልፋቴን ዋጋ ስመለከት ቀኑን ሙሉ በደስታ እንዳለቅስ ያደርገኛል። እንዲህ ያለውን እርካታ በሌላ በምንም መንገድ ላገኘው አልችልም። እንዲህ ያለው ደስታ ቀኑ ሁሉ የተባረከ እንዲሆን ያደርግልኛል። በሌላ በኩል ደግሞ …

ጎልጉል፦በተለይ የምትጠላው ምንድነው? ይህንን ጥያቄ የማነሳው …

ኦባንግ፦(…አቋርጦ በመግባት) ተንኮል። ጥላቻ። ድንቁርና፡፡ ውሸት …

ጎልጉል፦የፖለቲካ ፓርቲ የማቋቋም ድብቅ አጀንዳ አለው የሚል አስተያየት ይደመጣል፤

ኦባንግ፦ለጊዜው አላሰብኩም። ባቋቁምስ? ምንድነው ችግሩ? ማንስ ያገባዋል? ምንም ነገር የማድረግ መብቱ እኮ የኔ የግሌ ነው፤

ጎልጉል፦በየጊዜው የሚነሳ ጉዳይ ስለሆነ ግልጽ እንዲሆን ነው የጠየኩህ፤

ኦባንግ፦ከዚህ በፊት ያስታወቅኩኝ ይመስለኛል። የፖለቲካ ፓርቲ የማቋቋም ወይም በተቋቋሙት የፖለቲካ ድርጅቶች ውስጥ የመሳተፍ ባለመብቱ እኔ ብቻ ነኝ። ማንም አያገባውም። እንዲህ ዓይነት ሌሎችን የመቆጣጠር አዝማሚያ ሊገባኝ አይችልም።በተወለድኩበት ጋምቤላ በመቶሺህ የሚቆጠሩ ሰዎች በአንድ ሃኪም ብቻ ሲመረመሩ ሳይ አመመኝ። ይህ ሳይበቃቸው ጭፍጨፋ ተከተለ። ይህኔ ማንም ሳይቀሰቅሰኝ የተገፉና የሚረገጡ ወገኖችን ለመታደግ ማንም ሳይቀሰቅሰኝ ወሰንኩ። ችግራቸውን ይፋ ለማድረግ አደባባይ ወጣሁ። ድርጅት አቋቋምኩ። በህይወት እያሉ የሚያጣጥሩ ሰዎችን መንገድ ላይ እያዩ ጥሎ መሔድ ይቻላል? ሰብዓዊነት ነው? እየሞቱ ያሉ ዜጎችን ለመርዳት፣ የነሱ ስቃይ ይመለከተኛል ብሎ መነሳት ምን ድብቅ አጀንዳ ይኖረዋል? እንዲህ አይነቱን ኋላ ቀርና የቀረ አስተሳሰብ አልወደውም። አጠላዋለሁ። ከየት እንደመጣሁ የኢትዮጵያ ህዝብ ያውቃል። እኔ የመጣሁት ፍትህ ለተጠሙ ድምጽ ለመሆን እንጂ ለተንኮል አይደለም። ተንኮል ምን እንደሆነም አላውቅም። ድብቅ ነገርም የለኝም። ከማንስ ነው የሚደበቀው?

ጎልጉል፦ስለዚህ የፖለቲካ ፓርቲ የማቋቋም ሃሳብ የለህም ማለት ነው?

ኦባንግ፦በራሴ ጊዜ ሁሉንም አደርገዋለሁ። ማንም ለኔ ሃሳብና እቅድ ጊዜ አያወጣልኝም። ማድረግ በምፈልግበት ጊዜ ባደባባይ ልክ አሁን እንደምሰራው አደርገዋለሁ። ለሁሉም ነገር የራሴ የጊዜ ምርጫ አለኝ። እኔ በራሴ ሳንባ የምተነፍስ ሰው ነኝ። እኔን በተመለከተ ምን እያደረኩ እንደሆነ በማሰብ የሚጨነቁ የራሳቸውን ስራ እንዲሰሩ እመክራቸዋለሁ። እኔ የራሴን እቅድ ይዤ እየሰራሁ ነው። ሌሎችም የራሳቸውን፣ ያዋጣናል ያሉትን ይስሩ። በቃ!! ተመለሰልህ?

ጎልጉል፦”ለሁሉም ጊዜ አለው” ብለኸኛል፤

ኦባንግ፦አዎ! ለሁሉም ጊዜ አለው። ፍትህ ለጠማቸው ወገኖች በሚቻለው ሁሉ መድረስ ግድ ነው። የሌሎችን ኑሮና ስቃይ መካፈል ሰው የመሆናችን አንዱ መግለጫ ነው።በእውነት፣ በቀጥተኛው መንገድ፣ የተከታዮችን ልብ ሳንሰብር ማገልገል ለማንም የሚተው ሥራ አይደለም፡፡ ሁላችንም ያገባናል። ባገራቸው ጉዳይ ከሚያገባቸው ዜጎች መካከል አንዱ ነኝ።

ጎልጉል፦ብቻህን ትሮጣለህ ይሉሃል?

ኦባንግ፦እንዲህ ያለው ኢትዮጵያን አሁን ካለችበትም ደረጃ እንደገና ወደ ባሰ ኋላ ቀርነት ለሚመልሳት አመለካከትና አስተሳሰብ እንግዳ ነኝ። በነጻነት የማምን ነጻ ሰው ነኝ። ወዳጆቼን ቅር ያሰኛል እንጂ በርካታ ጉዳዮችን ማንሳትና መናገር የምችልበት አጋጣሚዎች ነበሩ። ራሳችንን ችለን ከመስራት ይልቅ ሌላው ላይ መንጠልጠል ምን ጥቅም እንዳለ ሊገባኝ አይችልም። እኔ የምመራው ድርጅት የራሱ መዋቅር ያለው፣የሚሰራውን የሚያውቅ፣ በሙያቸውና በዜግነታቸው ዓላማውን ተቀብለው ያለ አንዳች ጥቅም የሚያገለግሉት ቦርድና ስራ አመራር ያለው ነው። አባላቶቹም በፍቅር ድርጅታቸውን አምነው የሚሰሩ ናቸው። እኔን ብቻውን ይሮጣል የሚሉ ወገኖች የሚያስቀይሙት እንግዲህ እንዲህ ያሉትን፣ የማያውቋቸውን ሰዎች ነው። እኔ እስከማውቀው ድረስ ብቻዬን አይደለሁም። አብረውኝ የሚሮጡና በነጻ ከፍቅር ብዛት ከጎኔ ያሉት ወገኖች እጅግ ብዙ ናቸው። ችግሩ እነዚህ አብረውኝ ያሉ ሰዎች በየቦታው መታየት የሚፈልጉ ስላልሆኑ ለአንዳንድ ሰዎች ብቻዬን ያለሁ ይመስላቸዋል፡፡ እና ብቻውን ይሮጣል ይሉኛል፡፡

ጎልጉል፦ድርጅትህ የተለየ መስፈርት አለው?

ኦባንግ፦ በመጀመሪያ “ድርጅትህ” ያልከውን አልቀበልም፡፡ እኔ መሪ ብሆንም ለአዲሲቷ ኢትዮጵያ የጋራ ንቅናቄ “የኦባንግ ድርጅት አይደለም”፡፡ የጋራ ንቅናቄያችን ምንም መስፈርት የለውም፤ በፍጹም። እንደሚታወቀው ሥራችን ሁሉ ህጋዊ ነው፡፡ የጥንካሬያችን መሠረትም ይኸው ነው፡፡ ድርጅታችን በአሜሪካ አገር በሕግ የተመዘገበና የመክሰስም ሆነ የመከሰስ መብት ያለው ነው፡፡ ገቢና ወጪያችንንም በየጊዜው በህጋዊ መልኩ ለመንግሥት መ/ቤቶች ሪፖርት እናደርጋለን፡፡ የወያኔን ሕገወጥነት የምንቃወመው ራሳችን ሕገወጥ በመሆን አይደለም፡፡ እናም ስለዚህ በሕጋዊነት ላይ የጸና አቋም አለን፡፡ ከዚህ ሌላ ግን የጋራ ንቅናቄያችን አገራቸውን የሚወዱ፣ ሰብዓዊነትን የሚያከብሩ፣ የወደፊት ልጅ ልጆቻቸው ህይወት የሚያሳዝኗቸው፣ እነሱ ያለፉበት መንገድ ስህተትና ኋላ ቀር እንደሆነ የተረዱ በነጻነት የሚምኑ፣ በበጎ ፈቃድ፣ በቀናነት፣ በፍቅርና በርህራሄ የሚያምኑ ነጻ ሰዎች የሚቀላቀሉት ድርጅት ነው። (http://www.solidaritymovement.org/)

የጋራ ንቅናቄያችን የያዘው ራዕይ ብቻውን ታላቁ ሃብቱ ነው። ግን ከግብ የሚያደርሱት ሰዎች ይፈልጋል። እነዚህ ሰዎች ጎሳና የደም ግንኙነት የማያግዳቸው የአዲሲቷ ኢትዮጵያ መስራቾች ናቸው። እኔን ውሰደኝ። ከጋምቤላ ነው የተገኘሁት። ይህ ታላቅ ሃብት ነው ያልኩት ታላቅ ዓላማ ስለገዛኝ እንጂ ከጋምቤላ ጉዳይ ጋር መሮጥ እችል ነበር። የጋምቤላን ጉዳይ ብቻ አንጠልጥዬ ብሮጥ መስበክ የምጀምረው የቀድሞውን ስህተት ይሆናል። ስህተት መድገም ታጋይ ወይም የሰብአዊ መብት ተሟጋች አያሰኝም።

ጎልጉል፦ላቋርጥህና “የቀድሞውን ስህተት መስበክ” ስትል ምን ማለት ነው?

ኦባንግ፦ነብሱን ይማረውና አቶ መለስ ይሰብከው የነበረው ሁሉ ጥላቻ ነበር። ኢትዮጵያ ውስጥ ባለው እውነት መሠረት ሁሉም የተረገጠ ህዝብ ነው። ሁሉም የተገፋ ህዝብ ነው። የቱን ጠልተህ፣ የቱን ትወዳለህ? መለስ አማራውን ነፍጠኛና የሌላው ህዝብ ሁሉ ጠላት አድርጎ ሰበከ። ኦሮሞውን ጠባብ እያለ ከሌላው ጋር አጣላው። የተጨቆኑ በሚል ብሄር ብሄረሰቦችን ጥላቻ አስታጠቃቸው። በጥላቻ ላይ መሰረት ያደረገው ስብከት ህይወት ቀጠፈ፡፡ አሁንም ሰው እየሞተ ነው። መፈናቀል አስከተለ። አሁንም አልቆመም። ከሰውነት ባህርይ የወጣና ዘግናኝ ጭፍጨፋ ተካሄደ … ብዙ ማለት ይቻላል። ከጥላቻ የሚገኘው ትርፍ እንግዲህ ይህ ነው። ቀደም ባሉት ስርዓቶችም ቢሆን ከዘመን ጋር አብሮ ባለመሄድ ምክንያት በርካታ ችግሮችን ለማሳለፍ ተገደናል። እናም ይህ አስነዋሪና ኋላ ቀር ፖለቲካ አንድ ቦታ ላይ መቆም ይገባዋል። የምናስቀረው ደግሞ እኛ የዚህ ዘመን ሰዎች ነን። ጥላቻን መስበክ መቆም አለበት። ይህንን ለመረዳት የሚያስፈልገው ቀና መሆን ብቻ ነው። በቀናነት ብቻ ብዙ መራመድ ይቻላል። ቀና ስንሆን ብዙ ነገር ይገለጥልናል። በሁሉም መንገድ ተሞክሮ አልሆነም። ቀና በመሆን ግን ይቻላል።

ጎልጉል፦አቶ መለስ በህይወት እያሉ ስለተጨቆኑና ስለተረገጡ ህዝቦች ሲሉ መታገላቸውን በተደጋጋሚ ይናገሩ ነበር። ባንተ አመለካከት ዋናው ስህተታቸው ምኑ ላይ ነው?

ኦባንግ፦አቶ መለስ ህወሓትን ከፊት አድርገው አዲስ አበባ ሲገቡ እውነተኛ ብሔራዊ እርቅ አድርገው ቢሆን ኖሮ ዛሬ ተገፍተን በስደት ያለን ሁላችን በየሙያችን አገራችንና ወገኖቻችንን እናግዝ ነበር። የሆነው ግን የተለየ ነው። መለስ “እነሱ” ብሎ ሌሎችን በመወንጀል ጥላቻን ማወጅ ጀመረ። ትውልድን የሚያንጽ ብሄራዊ ሚዲያ ሳይቀር የጥላቻና የቂም ስብከት እንዲያስተጋባ ተደረገ። የዚህ መዘዝ ዛሬ ላይ ጣለን። የጋራ ንቅናቄያችን “እነሱ” የሚል ቋንቋ የለውም። ስንጀምር “እኛ” ብለን ነው። ይህ ልዩ ያደርገናል። የሰው ልጆች ጥላቻን ለመሸከም አይመጥኑም። ጥላቻ የሚዘራብን እንደሰው ስለማንታይ ነው። እንደ ሰው ስላልተከበርን ነው። ሰው መልካም ነገር እንዲያደርግ ከፈጣሪ የተሰጠው ልዩ ስጦታ አለው፡፡ መለስ ግን ይህንን ረስቷል። በብሄር ብሄረሰብ ስም ሲምል ሁላችንንም ሳያሳፍር ነው። ብቻውን ወይም ጥቂት ሰዎች ይዞ ወደ ጥፋት ሄደ፤

ጎልጉል፦ “መሳፈር” ብታብራራልኝ?

ኦባንግ፦በምሳሌ ልግለጸው። ምሳሌው ለመለስ ብቻ አይደለም። ለሁላችንም የሚሆን ነው። አውሮፓና አሜሪካ ወይም ባደጉት አገሮች ተማሪዎች የጉብኝት ጉዞ አላቸው። ለጉብኝት ሲነሱ አውቶቡስ ይቀርባል። አወቶቡሱ እንደቀረበ ቀድመው የሚገቡት ተማሪዎች ናቸው። ተማሪዎች ገብተው ሲያልቁ አስተማሪዎቹ ይቆጥሯቸዋል። ሁሉም መግባታቸውን ካረጋገጡ በኋላ አስተማሪዎቹ ተሳፍረው ሾፌሩን አውቶቡሱን እንዲያንቀሳቀስ ይነግሩታል። አስተማሪዎቹ ተማሪዎቹን ቅድሚያ ሰጥተው ማስገባትና የተባለው ቦታ ድረስ የማድረስ ሃላፊነት አለባቸው። ጉብኝቱም ካለቀ በኋላ ሁሉም  ተማሪዎች አውቶቡስ ውስጥ ተመልሰው ሳይገቡ አውቶቡሱ ዝም ብሎ አይነሳም። ሁሉም ተማሪዎች መኖራቸውና ማንም እንዳልቀረ ደግመው ደጋግመው ያረጋግጣሉ። እንደመጀመሪያው ሁሉም ተማሪዎች መሳፈራቸው ሲረጋገጥ አውቶቡሱ እንዲንቀሳቀስ ለሾፌሩ ያስታውቃሉ።

ጎለጉል፡- ታዲያ ከዚህ ምሳሌ የምንማረው ምንድነው?

ኦባንግ፡- የምንማረውማ አውቶቡሱ አገር ነው። ተማሪዎቹ ህዝብ ናቸው። እንግዲህ መለስ አገር ሲመራ ሁላችንንም ቆጥሮና መሳፈራችንን አረጋግጦ መሆን ሲጋባው ብቻውን ተሳፍሮ ሌሎች የሚፈልጋቸውን ጨምሮ ቆለፈብንና ብቻውን ነጎደ። አንዳንድ የሚጠቅሙትን ከጎኑ አደረገ። በመሪያችን ያልተቆጠርን በዛን። አታስፈልጉም የተባልነው በለጥን። የተቆለፈብንና የጉዞው ተመልካች የሆን ከልክ በላይ ሆንን። መለስ ካለፉት ስርዓቶች ትምህርት ተምሮ ጉዞውን አንድ ላይ በእርቅና በፍቅር ሊያደርገው ይችል ነበር። መለስ ተገፍቻለሁ ብሎ በረሃ ገባ። ከበረሃ ሲመለስና መሪ ሲሆን እኔንና እኔን መሰል ወገኖችን ገፋንና ከአውቶቡሱ ውጪ አደረገን። ሳንቆጠር የቀረን በሙሉ ሌላ አውቶቡስ ፍለጋ ተሰደድን፤ አሁንም እየተሰደድን እንገኛለን፡፡ በመለስ አውቶቡስ የሚቆጥረን ስላልነበረ ሌላ የሚቆጥረን እንፈልጋለን፡፡ ዛሬም ተመልሰን ይህንን ለመድገም መስራት ያለብን አይመስለኝም። አንዱ ሌላውን እየገፋ በበቀል ታሪክ መሄድ መቆም አለበት። ይህ የእኛ ትውልድ ቢያንስ ቢያንስ ይህንን ማድረግ አለበት። መለስ አልቆጠረንም ብለን የራሳችንን አውቶቡስ ይዘን ከመሄድ ይልቅ መጀመሪያ ወገናችንን እንሰብስብ፤ እንቁጠር፡፡ በተራ ብልጣብልጥነትና በተንኮል ሳይሆን በቀናነት!! ቀናነት!! ቀናነት!! …

ጎልጉል፦እዚህ ላይ አቶ መለስን ብቻ ተጠያቂ እያደረክ ነው?

ኦባንግ፦እሳቸው ይህንን የጥላቻ ታሪክ መቀየር ይችሉ ነበር። መገፋትና መጨቆን አግባብ አይደለም ብለው የታገሉትን ወንድሞችና እህቶች ሞት ሊያከብሩት ይገባ ነበር። “በጠላቶቻችን መቃብር ላይ” ብለው ባይነሱ ኖሮ የኢትዮጵያ መከራ ያቆም ነበር። በየመን፣ በመካከለኛው ምስራቅ፣ በአውሮፓ፣ በአሜሪካ፣ በኬኒያ፣ በደቡብ አፍሪካና በተለያዩ አገራት በስደት የሚማቅቁ ወገኖች የመለስ ስርዓት ውጤቶች ናቸው። ድህነት ከፍቶ ቆሻሻ መብላት የጀመሩ ትውልዶች የታዩት፣ በባህር ላይ ሲሰደዱ የሚያልቁ ወገኖች፣ በሲና በረሃ የሰውነት ክፍላቸው እየተወሰደ የውሻ ሞት የሚሞቱት ወገኖች፣ የድርጅት አባል ካልሆናችሁ ስራ አታገኙም ተብለው በረሃብ የሚጠበሱ አካሎቻችን የመለስ ስርዓት ውጤቶች ናቸው። መለስ መነጋገሪያ ይዞ የተናገራቸው የጥላቻና እርስ በርስ የሚያባላ ቅስቀሳ እኔ መድገም አልፈልግም።ማናችንም ልንደግመው አይገባም። በነገራችን ላይ ኢህአዴግ ራሱ የሁሉም ነገር መሃንዲስ መለስ እንደሆነ አሁን እያረጋገጠ ነው። እኔ የምለው ግን በቀል የሌለባትን አገር ለመመስረት እናተኩር ነው እንጂ መለስን በመውቀስና በመደብደብ ለውጥ አይመጣም። ጥላቻውን ማስተጋባት ከቀጠልን የቀድሞው ስህተት ምሩቃን እንሆንና ምንም በማያውቀው በመጪው ትውልድ፣ በልጅ ልጆቻችን ላይ የምንፈርድ እንሆናለን።ይህንን ካደረግን ከነመለስና ከሌሎች በምን እንሻላለን ለሚለው ጥያቄ መልስ የለም። አርቆ መመልከት አግባብ የሚሆነው እዚህ ላይ ነው።

ጎልጉል፦ስጋት አለህ ማለት ነው?

ኦባንግ፦እኔ ብቻ ሳልሆን አብዛኛው ህዝብ፣ በተለይም ወደ የትኛው አቅጣጫ እንደሚሄድ መወሰን ያልቻለው ህዝብ ጭንቀት ውስጥ ስለመሆኑ ጥርጥር የለኝም። ጎጆ ቤት ስትገባ ጎንበስ ማለት አለብህ። ኢትዮጵያችን ዙሪያውን ምስጥ በበላው እንጨት የቆመ ጎጆ ተደርጋለች። የከፋቸው ብዙ ናቸው። ተገደው ሳይወዱ በሃይል የሚመሩ የጥላቻ ፖለቲካ ውጤት የሆኑ ጥቂት አይደሉም። በእንዲህ አይነት ጎጆ ውስጥ ለመግባት በጣም ጎንበስ ማለት ግድ ነው። አለበለዚያ አንዱ እንጨት ከተነካ ጎጆዋ ጎጆ መሆኗ ይቀራል። ይህ አርቀህ ስታይ የምትመለከተው ገጽታ ነው። ይህቺ ጎጆ ጎጆ መሆኗ ከቀረ ቢሮጥም መድረሻ የለም። ጎጆዋን የበላት ምስጥ ጥላቻ ነው። ይህንን ጥላቻ ስናስወግድና በሰብዓዊነት መሰረት ላይ ተተክለን መንቀሳቀስ ስንችል ጎንበስ ሳንል ደረታችንን ገልብጠን ብንገባም የማይነቃነቅ ቤት ይኖረናል። ያቺኑ በቋፍ ላይ ያለች ጎጆ በመጠጋገን ለመኖር ማሰብ በኔ እምነት ኋላ ቀርነት ነው። ራዕይ አልባ መሆን ነው። የአውሬ አስተሳሰብ ነው። ተራ የእሳት አደጋ ወይም የአምቡላንስ አገልግሎት አይነት ነው። እና …

ጎልጉል፡- ምሳሌዎች ሁሉ ይገርማሉ፤ ቅድም ስለ አውቶቡስ ስትናገር ነበር አሁን ደግሞ ጎጆ …

ኦባንግ፡- (በማቋረጥ) ልክ ነህ ለኔ ትልቅ ትርጉም ስላላቸው ነው፡፡ … እና ወደ ጀመርኩት ሃሳቤ ስመለስ … ራሴን በርካታ ጥያቄዎች እጠይቃለሁ። የማገኘው መልስ ይገርመኛል። የኢትዮጵያ ልጆች ደንቆሮዎች ነን እንዳልል፣ በመላው ዓለም ታላላቅ ባለሙያዎች አሉ። ደሃ ነን እንዳልል፣ ሃብት አለን። ታሪክ አልባ ነን እንዳልል፣ የታላላቅ ታሪክ ባለቤት ነን። ባህል አልባ ነን እንዳልል፣ አስገራሚ ባህሎች ባለቤት እንደሆን እረዳለሁ። ታዲያ ችግራችን ምንድነው? እስራኤል ታናሽ ህዝብ ነው። ግን የት ደርሰዋል? እኛ ለምን? ምንድነው የጎደለን? መሪ የሚባሉት ሰዎች በልተው ሌላው ጦሙን ሲያድር ምን እርካታ ይሰማቸዋል? አገር እየሳሳች ስትሄድ በጋራ መፍትሄ እንፈልግ፣ በጋራ እንስራ፣ አንድነታችንን እናጠናክር፣ እጅ ለእጅ እንያያዝ፣ በግሌ የማገኘው ነገር ይቅርና ቅድሚያ አገሬን ለማለት ያልቻልነው ለምንድነው? ይህ ስጋት የኔ ብቻ አይሆንም። ሁሉም ራሱን መጠየቅና ለህሊናው ታምኖ አቅጣጫውን ማስተካከል አለበት። በግልጽ የአመለካከት ለውጥ ማካሄድ አስፈላጊ ነው። የጋራ ንቅናቄያችን ይህንን ጥሪ ማስታላለፍ ይፈልጋል። ማስተዋልና አመዛዝኖ መጓዝ፣ የራስን ስራና የራስን ድርሻ መስራት፣ ሌላውን አለመረበሽ፣ አለመተንኮስ፣ ተንኮል አለመስራት፣ ከሁሉም በላይ ራስን ማክበርና ለሌላው ስቃይ መታመም ያስፈልጋል።

ጎልጉል፦መሪ የመሆን እቅድ አለህ?

ኦባንግ፦ጥሩ መሪ ሊኖረን እንደሚገባ አምናለሁ። ጥሩ መሪ ያስፈልገናል። የራሱን ጎሣ ወይም ወገን ብቻ ሳይሆን ሁላችንም አውቶቡሱን መሳፈራችንን፣ ሁላችንም መቆጠራችንን ካረጋገጠ በኋላ አውቶቡሱ ውስጥ ገብቶ በሩን የሚዘጋ መሪ ያስፈልጋል። እንዲህ አይነት መሪ ሲኖረን (ስንመርጥ) ሲና በረሃ መታረድ ይቆማል። በባህር የሚጠፋው ነብስ ባገሩ አምራች ይሆናል። የተሻለች አገር ለመፍጠር ግን ዝምታ፣ አያገባኝም፣ የለሁበትም ማለት አይሰራም። ጥላቻን መስበክ ፈጽሞ ወደዛ አያደርስምና ሊታሰብበት ይገባል። አገራችን ከያቅጣጫው እስካሁን የተዘራባት ጥላቻ ይበቃል። አስተሳሰባችንን ቀይረን ከሰራን አገር ቤት ውስጥ ትክክለኛ መሪ እናገኛለን። ስለመቀመጫና ስለ መሪነት ያለን አስተሳሰብ ይህ ነው። የመሪ ችግር አለብን። ጦሟን አድራ ልጆቿን እንደምትመግብ እናት ለሚመራው ህዝብ የሚጨንቀው መሪ ለማየት ደግሞ ሳልሰለች የወደፊቱን እያየሁ እሰራለሁ። እንሰራለን።

ጎልጉል፦እናት ስትል ስለ አያትህ እያነሳህ የምትናገረውን አስታወሰኝ …

ኦባንግ፦(አሰበ፤ ከቆይታ በኋላ) አያቴ በህይወቴ ውስጥ ትልቅ ቦታ አላት። መቼም ቢሆን የማልረሳው ዘር ዘርታብኛለች። በሷ ዘመን ሳትማር ስለትምህርት አስፈላጊነት መክራኛለች። አሳስባኛለች። በቃል ብቻ አይደለም ቢጫ እርሳስና 32 ሉክ (ገጽ) ያለው ደብተር ገዝታ ወደ ትምህርት ቤት እንድሄድ አድርጋለች። ህጻን በነበርኩበት ወቅት ሌሎችን ስለማክበር፣ ስለመውደድ፣ ስለመንከባከብ፣ ከጨለማ ውስጥ በመውጣት ለራሳችን ብርሃን ማብራት እንዳለብን ደጋግማ ትነግረኝ ነበር። አሁን ሳስበው የአያቴ ምክርና ተግባራዊ ድጋፍ እዚህ እንዳደረሰኝ ይሰማኛል። ሳስባት በረከት ይሞላኛል።

ጎልጉል፦የምክራቸው መነሻ ምን ነበር? የትምህርትን አስፈላጊነት ለመረዳት የረዳቸው የተለየ አጋጣሚ ነበር?

ኦባንግ፦ቤተ ክርስቲያን ታዘወትር ነበር። በተፈጥሮ ብልህና አዋቂ ናት። ለማወቅ የግድ ዶክተርና ተመራማሪ ወይም መሃንዲስ መሆን አያስፈልግም። ደጋግሜ የምናገረው አንድ ነገር አለ። ሰው ቅን ሲሆን፣ ቅን ሆኖ ለመኖር ሲወስን ብዙ ነገሮች ይታዩታል። በቀናነት የሚገለጽና የሚገኝ ግንዛቤ የሚፈራርስ አይደለም። ቀና ስትሆን ማንንም ለማስደሰት አትኖርም፤ ምክንያቱም ትክክለኛ የሆነ ነገር ብቻ ነው የምታደርገው። ቀና ሰው ባመነበት ሳያስመስል አክብሮና ተከብሮ ይኖራል። ይህ የአያቴ ውርስ ረዳኝ። ከሺዎች ዓመታት በፊት የነበሩትን ኢትዮጵያዊያንና ታሪካቸውን ስንመለከት ከየትኛውም ኮሌጅ አልተመረቁም። ግን አዋቂነታቸው አሁን ድረስ እኛ ልንቀጥልበት ያልቻልነው ነው። የጸዳ ህሊናና ስብዕና ስላላቸው ወገኖች ሳስብ ደስ ይለኛል። አሁን እኔ የማደርገው አያቴ አድርግ ያለችኝን ነው። ነገሮች ተስተካክለው ቢሆኑ ኖሮ እኔ የጸረ ድንቁርናን ዘመቻ አርበኛና አዝማች እሆን ነበር። ድንቁርና ባህላችን እንዳልሆነ አስተምር ነበር። ካገራቸውና ከምድራቸው ሌላ መሄጃ የሌላቸውን ህዝቦችን እንዲገለሉ የሚያደርገውን ቅዠት የሆነና በጣም አስደንጋጭ የሆነ አመለካከት ለማስወገድ እደክም ነበር። ራቁታቸውን የሚሄዱ፣ ጎዳናና ዱር ውስጥ የሚተኙ፣ “ልዩነታችን ውበታችን ነው” እያሉ ለፍቅርና ለአክብሮት ሳይሆን ለቱሪዝም አግልግሎት ገንዘብ መሰብሰቢያ የሚውሉትን አካሎቻችንን የማዳን ስራ እሰራ ነበር። ያ በአገር መስዬ ባስቀመጥኩት አውቶቡስ ውስጥ ከሌሎች ወገኖቻቸው ጋር ባንድነት ተቆጥረው መሳፈራቸውን የሚያረጋግጥላቸው ስርዓት እንዲገነባ እታገል ነበር። አገር ማለት ህዝብ ነው። በእውነት መምራት ከመሪ ብቻ ሳይሆን አምኖ መመራትም ከተመሪው ህዝብ ይጠበቃል። ሁሉም ኢትዮጵያዊ አግባብነት ያለው ኑሮ ለመኖር ይመጥናል። ሁላችንም የዚህ አለም ስደተኞች ነን። ነጮቹም፣ ሃብታሞቹም፣ ድሃዎቹም፣ ጥቁሮቹም … ህይወታችን ዘላለማዊ አይደለንም። የኮንትራት ህይወት የምንመራ ነን። በዚህ ውስን የኮንትራት ህይወታችን ምንም በማያውቁና ለችግር መንስዔ ላልሆኑ ልጆቻችን የተስተካከለ ዘመን ማውረስ የኛ ግዴታ ነው። ጨለማና ከድንቁርና ውስጥ መውጣት አማራጭ የለውም። አያቴ በዛን ወቅት ይህንን ታስብ ነበር። ይህንን እንዳደርግም ዘርና ጎሳ ሳትለይ ታስጠነቅቀኝ ነበር። በቀናነት!!

ጎልጉል፦የአዲሲቷ ኢትዮጵያ የጋራ ንቅናቄም ሆነ አንተ ራስህ ባብዛኛው ስለ “ድርሻ” ትናገራላችሁ። ምን ለማለት ነው?

ኦባንግ፦አዎ! ድርሻ እንላለን። ድርሻ፣ ድርሻ፣ ድርሻ፣ ድርሻ፣ … ድርሻ በማለት ዛሬም ወደፊትም እንጮሃለን። እጅ፣ እግር፣ አፍንጫ፣ ዓይን፣ ምላስ፣ አፍ፣ … ሁሉም ባግባቡ ድርሻቸውን ሲወጡ ሁሉንም የተሸከመው አካል የተሳካ ስራ ይሰራል። ጤነኛም ይሆናል። እግር የዓይን ስራ ልስራ ካለ ችግር ነው። አፍንጫ ምላስ ልሁን ሲል አካል ሙሉ እንቅስቃሴው ይበላሻል። እኛም እንዲሁ ነን። ሁላችንም ድርሻ አለን፤ ድርሻ የሌለው የለም፤ ድርሻችንን ማወቅ አለብን። ድርሻችንን መወጣት አለብን ስንል የማንችለውን ከመስራት በመቆጠብ የምንችለውን ማድረግ ማለት ነው። ሁሉንም ባቅም በእውቀት ማድረግ ማለት ነው። መተማመንና መግባባትን ማስፈን። ለጥቅምና ለጊዜያዊ ደስታ በሚል ሌሎችን በመምሰል ከራስ እውነተኛ ማንነት ጋር አለመጣላት በራሱ የድርሻን መወጣት ነው።

ጎልጉል፦የድርሻን ከመወጣት ጋር በተያያዘ በድርጅትዎ ያስተዋሉት ወይም በሌሎች ድርጅቶች ውስጥ ሊቀየር ይገባዋል የሚሉት ደካማ ጎን አለ?

ኦባንግ፦ስለ ማንኛውም ድርጅት ለይቼ አስተያየት መስጠት አልፈልግም። የምናገረው በጥቅል ለሁላችንም ይሆናል ብዬ የማምንበትን ነው። ወደ ጋራ ንቅናቄያችን ስመለስ ግን ብዙ አስገራሚ ገጠመኞች አሉኝ። በሺህ የሚቆጠሩ ወገኖችን ከስደት ችግር እንዲወጡ አድርገናል። በያሉበት አገርም ህጋዊነት እንዲያገኙ ድርጅታችን ካለው ታዋቂነትና ሕጋዊነት አኳያ ያለአንዳች ክፍያ በነጻ የረዳናቸው እጅግ በርካታ ናቸው፡፡ በዚህ ስራችን ብዙ መናገር ባንፈልግም የሚያውቁ ያውቁናል። እንዳንዶች ርዳታ ካገኙና ከችግር ከተላቀቁ በኋላ ተመልሰው እኛው ላይ ዘመቻ የሚያካሂዱ አሉ። ጥላቻን ስለማወግዝና በክፋት አንድ ርምጃ መራመድ እንደማይቻል ስለማምን ወደኋላ ተመልሼ ማሰብና መናገር የማልፈልጋቸው ጉዳዮች አሉ። ዋናው መናገር የምፈልገው ከራስ ጋር የመታረቅና ቀና የመሆን አስፈላጊነት ላይ ነው። በተንኮል ደስተኛ ሆነን አንኖርም። በቀላሉ ተንኮል ባሰብን ቁጥር እያነስን፣ እየቀጨጭን፣ ጭንቀት እየጨመርን እንሄዳለን። ለፖለቲካ ብቻ ሳይሆን ይህ ለጤናም ጥሩ አይደለም። ጥሩ እንቅልፍ እንኳን መተኛት አንችልም፡፡ ከሁሉም በላይ ሌሎች ከኛ ብዙ የሚጠብቁ ወገኖችን እናሳዝናለን። ትውልድን እናከስራለን። መከራችንን ራሳችን እናረዝመዋለን።

ጎልጉል፦መናገር እየፈለክ የምትጠነቀቅ ይመስላል። ለምን ግልጽ አታደርገውም?

ኦባንግ፦እኔ ነጻ ሰው ነኝ። ማስመሰልና ማድበስበስ፣ ተንኮል፣ ከበስተጀርባ ምናምን የሚባል ነገር አላውቅበትም። እንዲህ ያለውን ባህልም አልደረስኩበትም። ስለማይጠቅም ሞክሬውም አላውቅም። የጋራ ንቅናቄያችን በጀርመን፣ በሜክሲኮ፣ ካናዳ፣ እስራኤል፣ ስፔን፣ ስዊድን፣ እንግሊዝ፣ ማልታ፣ ሊቢያ፣ ሳዑዲ አረቢያ፣ የመን፣ ዱባይ፣ ኬኒያ፣ ደቡብ አፍሪካ፣ ዩጋንዳ … አገርቤት በወያኔ ስርዓት ተገፍተው የተሰደዱ፤ ተቸገርን ብለው ሲጠሩን ካበት ቦታ ጎሳ፣ ብሄር፣ ዘር፣ ክልል፣ ጾታ፣ ማንነት፣ ቀለም ሳንጠይቅ ደርሰናል። የምንችለውን እጅግ ውስን በሆነ አቅም ያለ በቂ ርዳታ አድርገናል። ከሺህ በላይ ወገኖች ከስቃይ እንዲገላገሉ ጊዜያዊ መፍትሄ እንዲያገኙ አድርገናል። ምንም እንኳ ስደት የሚያስደስት ነገር ወይም ማዕረግ ባይሆንም ከችግር በመላቀቃቸው ደስተኞች ነን። በስደት ካምፕ ውስጥና እስር ቤት ከመማቀቅ መገላገለቸው የበረከት ያህል ያረካናል። የሚያሳዝነው ግን እነዚህ ወገኖች እነሱ ባለፉበት ችግር ውስጥ ሆነው ለዓመታት ለሚማቅቁ ሌሎች ወገኖቻቸው አለማሰባቸው ነው። ያለፉበትን መርሳታቸው ነው። መጀመሪያ እንድረዳቸው ሲጠይቁንና ስናገኛቸው “የጋራ ንቅናቄው የሚያደርገውን አንተም የምትሠራውን እናደንቃለን፤ አባል መሆን እንፈልጋለን፤ አብረን እንሰራለን” ይላሉ። ችግራቸው ሲቃለል ሁሉንም ይረሱታል። ለራሳቸው እንኳን መታመን አይችሉም። በችግራቸው ወቅትና ከችግራቸው በኋላ የማስተውለው ተለዋዋጭ ገጽታቸው ያሳዝነኛል። ቅድም ያልኩት የድርሻ ጉዳይ የሚነሳው እዚህ ላይ ነው። በመከራ ውስጥ ያሉትን ለመርዳት፣ ለስደት መሰረታዊ መፍትሄ ለማምጣት የድርሻን መወጣት አስፋላጊ የሚሆነው እዚህ ላይ ነው። እኛ ሳንረዳዳ ሌሎች አልረዱንም ብንል በጣም ትክክል አይሆንም፤ ከቀልድ አያልፍም።

ጎልጉል፦በአብዛኛው ለአዲሲቷ ኢትዮጵያ የጋራ ንቅናቄ የሚያወጣቸው ጽሁፎች እና መግለጫዎች ወደ ሕዝቡ በተገቢው ሁኔታ እንደማይደርስ በአንድ ወቅት ተናግረህ ነበር፡፡ ምክንያቱ ምንድርነው? ችግሩ ያለው የት ላይ ነው?

ኦባንግ፦የጋራ ንቅናቄያችን ማንኛውንም ጽሁፍ ከማውጣቱ በፊት በቂ የሆነ ጥናት ያደርጋል፡፡ በተጠያቂነት የምናምን ስለሆነ ለምናወጣቸው ጽሁፎች ማስረጃ እንሰበስባለን፡፡ ከዚያም ጽሁፉ አስፈላጊ ከሆነ በእንግሊዝኛ ብቻ ወይም በአማርኛ ብቻ ወይም በሁለቱም ቋንቋዎች እናወጣለን፡፡ በዚህ አጋጣሚ በሌላ ቋንቋ ለመርዳት የሚፈልጉ ካሉ በራችን ክፍት ነው – ድርሻ የሚለው ነገር በዚህ መልኩ ሊወሰድም ይችላል፡፡ እናም ጽሁፎችን ካዘጋጀን በኋላ ባለን የኢሜይል ሊስት መሠረት በዓለም ዙሪያ እጅግ በርካታ ለሆኑ ግለሰቦች፣ በዳያስፖራም ሆነ አገርቤት ለሚገኙ ለሁሉም የኢትዮጵያ ድረገጾች፣ የሬዲዮ ጣቢያዎች፣ የሚዲያዎች (ዋና ዋና ለሚባሉት የምዕራብ ሚዲያዎችን ጨምሮ)፣ የፖለቲካ ድርጅቶች፣ የአርነት ንቅናቄዎች፣ የሲቪክ ማኅበራት፣ አገር ቤት ለሚገኙ የመንግሥት መ/ቤቶች፣ ባለሥልጣናት እና ቁጥራቸው እጅግ ብዙ  ለሆነ ግለሰቦች እንበትነዋለን፡፡ ድርጅቶችንና ሚዲያን በተመለከተ አይደርሰኝም የሚል ይኖራል ብዬ አልገምትም፡፡ ይህ ከሆነ በኋላ ጽሁፎቻችን በኢሜይል የማይደርሳቸውና ከሚዲያ መረጃ የሚያገኙ በሙሉ ድረገጾች ላይ ያነባሉ ብለን ስንጠብቅ በርካታዎቹ ጽሁፎቻችን አይለጥፉም፡፡ በፌስቡክ ወይም በኢሜይል ጽሁፋችንን አንብበው በኢትዮጵያውያን ድረገጽ ላይ ሳይለጠፍ በመቅረቱ ግራ ተጋብተው በየጊዜው የሚደውሉልን (ከኢትዮጵያ ድረስ)፣ የሚጽፉልን፣ ምክንያቱን የሚጠይቁ … እጅግ በርካታ ናቸው፡፡ የሚያሳዝነው በጣም እርግጠኛ የሆንባቸውና ወሳኝ የሆኑ ጽሁፎችም ሳይለጠፉ ቀርተዋል፡፡ ምክንያቱን በጭራሽ በማናውቀው ሁኔታ ለረጅም ጊዜ መለጠፍ ያቆሙ ድረገጾችም አሉ፡፡ እስካሁን የነገሩን ነገር የለም፡፡ እኛ ሥራችን ስለሆነ ለታሪክም ስለሚያስፈልግ የምንልከውን ጽሁፍ ማን እንደደረሰውና ማን በማሰራጨቱ እንደተባበረ መረጃ እናስቀምጣለን፡፡ ሳያቋርጡ የሚተባበሩንና ጊዜው ሲደርስ ስም ጠቅሰን የምናመሰግናቸው ድረገጾችና ሚዲያዎች አሉ፡፡ እና ለማለት የምፈልገው ከእኛ በኩል ምንም ችግር እንደሌለ ነው፡፡ ካለ ግን ለመስማትና ለማስተካከል ዝግጁ ነን፡፡

ጎልጉል፦በቅርቡ እስራኤል አገር በእስር ላሉ ወገኖች የጀመራችሁት እንቅስቃሴ በምን ተቋጨ?

ኦባንግ፦የሚቋጭ ነገር የለም። ከእስር የተፈቱ አሉ። ህጻናት ከተማ እንዲገቡ ተደርጓል። ወደፊት በተከታታይ ከሌሎች አካላት ጋር በመሆን እንሰራለን። በቅርቡ ዝርዝር ሪፖርት የሚኖረኝ ይመስለኛል። እዚህ ላይ ግን አንድ አስገራሚ ነገር መናገር እፈልጋለሁ። እስራኤል ወገኖቻችን መታሰራቸውን የሰማነው በሚያስደነግጥ ሁኔታ ነበር። በሲና በረሃ የደረሰባቸው ግፍ ማንም ኅሊና ያለውን ወገን ያስደነግጣል።እረፍትም ይነሳል። በማያውቁት የሲና በረሃ ውስጥ አካላቸው በገንዘብ እዳ ሲሰረቅና ሲወሰድ ከመስማት በላይ የወገንን ልብ የሚያደማ ምንም ጉዳይ የለም። ከዚህ መከራ የተረፉትንና በመከራ ላይ ያሉትን ለመታደግ ወስነን ርዳታ ያደርጉልን ዘንድ ሶስት ሺህ የኢሜል መልዕክት በአብዛኛው ለኢትዮጵያውያን አሰራጨን። ምላሽ ያገኘነው ከሰባት ሰው ብቻ ነው። ይህ ያስደነግጣል። ምን ሆነናል? ያሰኛል። በዚህ ላይ ብዙ መናገር አልፈልግም፤ ወደ ሌላ ጉዳይ እንሂድ፤ …

ጎልጉል፦በቅርቡ በኖርዌይ ከኢትዮጵያ ጥገኝነት ጠያቂዎች ማህበር አመራሮች ጋር እንዲሁም ከተለያዩ አካላት ጋር ተወያይተህ ነበር፤

ኦባንግ፦የስደት ማመልከቻ ተቀብሎ ከሚወስነው፣ የመጀመሪያ ማመልከቻ ውድቅ ሲደረግ ይግባኝ ሰሚ ሆኖ ብይን ከሚሰጠው፣ ለስደት ማመልከቻ ግብአት ይሆን ዘንድ ውሳኔ መረጃ ከሚያዘጋጀው ላንድ ኢንፎ (Land Info) ከሚባለው ወሳኝ መ/ቤትና በጣም በዝቅተኛ ዋጋ እየሰሩ ጉልበታቸውን ለሚበዘበዙ ተከራካሪ ለመሆን ከሚሰራ ተቋም ጋር ተነጋግረን ነበር። ከሁሉም ጋር ጥሩ የተባለ መግባባት የሰፈነበት ውይይት አድርገን ስለነበር አንድ ለውጥ እጠብቅ ነበር። በግልም መረጃ ልኬላቸዋለሁ። ከውይይታችን አንድ ሳምንት በኋላ ላንድ ኢንፎ ያወጣው አዲስ ሪፖርት የዚሁ ከማህበሩ ጋር በመሆን ያደረግነው ውይይት ውጤት ይመስለኛል። ስራው ተጀመረ እንጂ አላለቀም። ላንድ ኢንፎ በራሱ ድረገጽ፣ በኖርዌጂያን ቋንቋ ይፋ ያደረገው መረጃ በግልጽ እንደሚያሳየው፣ እኛም በተደጋጋሚ ስንናገረው እንደነበርነው የኖርዌይ መንግስት ዲፖርት ለማድረግ የተስማማው ወገኖቻችን የት እንደሚያርፉ ሪፖርቱ ቁልጭ አድርጎ ያሳያል። በራሳቸው ባለሙያና በራሳቸው ቋንቋ የተሰራ በመሆኑ መቀበል የግዳቸው ነው የሚሆነው። በዚህ አጋጣሚ በውይይታችን ወቅት በገቡት ቃል መሰረት ላደረጉት ምስጋና ይገባቸዋል።

ጎልጉል፦በቀጣይ ምን ታስቧል? ምንስ መደረግ አለበት ትላለህ?

ኦባንግ፦በየካምፑ ያሉትን ወገኖቻችንን ሙሉ በሙሉም ባይሆን ከኖርዌይ ጠንካራ አጋሮቻችን፣ ከማህበሩና ከድርጅታችን አባላት ጋር በመሆን ለመጎብኘት ዝግጅት አለን። ሌሎችም ጠንከር ያሉ ስራዎች ይሰራሉ። ቅድም ለማለት እንደፈለኩት ሁላችንም ድርሻ አለን። ማንም አያገባኝም ማለት አይችልም። በኖርዌይ ያሉ ወገኖች አሁን በጀመሩት መንገድ ቢደራጁ ከኖርዌይ አልፈው ሌሎች አገራት ያሉ ወገኖቻቸውን የመጎብኘትና የመርዳት አቅም መፍጠር ይችላሉ። ማህበራቸውን አጠናክረው ቢሰሩ በኖርዌይ እንደማንኛውም ማህበራት የገንዘብ ድጋፍ ማግኘትና ከተረጂነት መላቀቅ ይቻላቸዋል። መደራጀት ወሳኝ ነው። ይህንን ስል አልሞከሩም ለማለት አይደለም። አባላቶች ሙሉ ድጋፍ እንዲያደርጉላቸው ለማሳሰብ ስለፈለኩ ነው። እያንዳንዱ አባል ህግና ደንብ በሚፈቅደው መስራት መብቱን ለማስከበር መስራት ይገባዋል። እጁና እግሩን አጣጥፎ አስቀምጦ ሌሎችን መውቀስ አግባብ አይደለም። የመኖሪያ ፈቃድ ያገኙ ወገኖችም ወንድምና እህቶቻቸውን ለመርዳት፣ ለማገዝ፣ ለመተባበር፣ ለመጎብኘት፣ ችግራቸውን ለመካፈል መነሳሳት አለባቸው። ወረቀት ማግኘት ብቻውን የመኖር ምስጢር አይደለም። የሰው ልጅ ከወረቀት በላይ ነው፡፡ በመረዳዳትና የተቸገሩ ወገኖችን በማገዝ ውስጥ የሚገኘው የህይወት ትርጉምና ምስጢር ይበልጣልና!!

ጎልጉል፡- የዕለት ቀንህ ምን ይመስላል?

ኦባንግ፡- በጋራ ንቅናቄያችን የምንሠራው ሥራ ሁሉ ምንም ድብቅ ነገር ስለሌለ ስልኬም ሆነ የኢሜይል አድራሻዬ የስካይፕና የፌስቡክ አካውንቴ ክፍት ነው፡፡ ማንም ሰው በፈለገው ጊዜ ማግኘት ይችላል፡፡ ከዓለም ዙሪያ አለ በሚባለው መገናኛ ሁሉ መልዕክት ይመጣልኛል፡፡ ምስጋና፣ ድጋፍ፣ ዕርዳታ፣ ነቀፋ፣ ስድብ (ወያኔ ከሆኑም ካልሆኑ)፣ የስብሰባ ጥሪ፣ ለምን ይህንን አትሠራም የሚል ትዕዛዝ፣ አስተያየት፣ የፍቅር መልዕክት፣ … ሁሉም ዓይነት ይደርሰኛል፡፡ አብረውኝ ከሚሠሩት ጋር እየተጋራን እናነበዋለን፣ እንሰማዋለን፣ … ይህንን ብቻ መከታተል በራሱ የአንድ ቀን ጊዜ ይፈልጋል፡፡ ከበርካታ ሰዎች ጋር እገናኛለሁ፤ በየቀኑ የጋራ ንቅናቄያችንን የቤተሰብ መጠን ይሰፋል፤ “ከጎሣ ይልቅ ሰብዓዊነት ይቅደም” የሚለውን በተግባር አይበታለሁ፡፡ በጣም ያስደስተኛል፡፡ ስለዚህ ሁሉንም ነገር ፕላን እያወጣሁ አከናውነዋሁ፡፡ በየቀኑ የማደርገውን በዕቅድ አደርጋለሁ፡፡ ነገር ግን በጣም ጊዜ የሚያስፈልገው ነገር መሥራት ካለብኝ ስልኬንም ሁሉንም ነገር ዘግቼ ጊዜዬን ለብቻዬ አሳልፋለሁ፡፡ ያኔ ደውለው ያጡኝንም ሆነ ፈልገውኝ ያላገኙን በሙሉ ይቅርታ እላለሁ፡፡

ጎልጉል፦“ጥቁሩ ሰው” የሚሉህ ለምንድነው? ስሙ ተስማምቶሃል? ወይስ ……

ኦባንግ፦(ሳቀ!!) ቀለሜ ጥቁር ነው። ጥቁር ሰው ነኝ። በትክክለኛው ቀለሜ ተጠራሁ። ቀናህ እንዴ … !? (በፈገግታ ድምጽ)

ማሳሰቢያ፡ – አቶ ኦባንግ ሜቶ ቃለመጠይቁ ያደረገው በአማርኛ ሲሆን አንዳንድ ጊዜ ሃሳቡን ለመግለጽ እንግሊዝኛ የተጠቀመበትን ቦታ የቃለምልልሱ ፍሰት ለመጠበቅ ስንል በአማርኛ መልሰን አቅርበነዋል፡፡

Leave a Reply