Skip to content

የኢትዮጵያ ትንሣኤ!

ፕሮፌሰር ዓለማየሁ ገብረማርያም

ትርጉም ከነጻነት ለሃገሬ

Ethiopia rise 1

የአፍሪካ አንድነት ድርጅት (ኦ ኤ ዩ) የአፍሪካ ሕብረት (ኤ ዩ በየአፍሪካ አንድነትን የተካው) ባለፈው ሳምንት በአዲስ አበባ ከተማ  የወርቅ ኢዩቤልዩውን በማክበር ላይ ነው፡፡ በሜይ 1963 አፍሪካ አንድነት ሲመሰረት፤የጋናው ፕሬዜዳንት ክዋሚ ንኩርማ የመዝጊያ ንግግሩን የደመደመበት በተለይ በእድገት ላይ ያለችውንና ተቀኚ የነበሩትን የአፍሪካ ሃገራት ወደ ነጻነት ለመራችው ኢትዮጵያ ለክብሯ በመረጠውና ባዘጋጀው ግጥሙ ነበር፡፡ ግርማዊ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴን አስመልክቶ ንኩሩማ  ሲናገር: ‹‹ግርማዊ ሆይ! በጓደኞቼና በራሴ ስም የሚቀረኝ ለኢትዮጵያና ለሕዝቦቿ በተለይም ለግረማዊነትዎ ያለኝን አክብሮት በመግለጽ በዚህች ታሪካዊ ሃገር ባደረግነው ቆይታ የተቸረንን አቀባበልና መስተንግዶ ሳላመሰግን ማለፍ አይቻለኝም፡፡ ንኩሩማህ ዘወትር ባነበብኩት ጊዜ ትውስታ የሚያጭርብኝን ይህን የግጥሙን ስንኝ አሰማ፡፡  የራሱ የንኩሩማህ ቃላት እነዚህ ናቸው፡፡

ኢትዮጵያ ትነሳለች!

ኢትዮጵያ የአፍሪካ ብሩህ አንቁ

ከለምለሞቹ ተራሮች መሃል

የጨለመባቸውን በነጻነት ጎዳና ስታጓጉዝ

የአባይ ወንዝ አናት

ኢትዮጵያ ትነሳለች!

ኢትዮጵያ የብልሆች ምድር

ኢትዮጵያ፤ የቀደምት አፍሪካ ሕግጋት ማሕደር

ለምለም የእውቀት ገበታ

የእኛ አፍሪካ የባህሏችን  አለኝታ

ብልኋ ኢትዮጵያ ትነሳለች፤ ገና

ደምቃ በሙሉ ክብር

አቤት የአፍሪካ ተስፋ

መዳረሻዋ  እድል

በ2011 በአፍሪካ ሕብረት ግቢውስጥ የግ ቀ.ኃ.ሥ. ሃውልት እንዲቆም ሃሳቡ ሲቀርብ፤የኢትዮጵያ ‹‹ታላቁና ባለራዕዩ መሪ›› በመቃወምና ኢትዮጵያዊነቱን በመርሳትና በመካድ  ሲናገር ምንጊዜም ስለ ፓን አፍሪካኒዝም ስናነሳ የሚታወሰን ክዋሚ ንኩሩማ ነው፡፡ ይህን ለመቀበል መቸገር አሳፋሪ ነው የሚሆነው›› በማለት የራሱን አሳፋሪ ክህደት ፈጸመ፡፡የከሰለ ልብ ባለቤት መሆን እንዴት ያሳፍራል! ሃፍረተ ቢስነት እንዴት ያሳፍራል! ቀደምት የአፍሪካ እንድነትን ምስረታና ተግባራዊነት ያረጋገጠን መሃንዲስ እውነታ መካድስ እንዴት ያለ አሳፋሪ ተግባር ነው፡፡የማይቻለውንና የማይሞከረውን የሁለት ጎራ ፍጥጫ፤ የ “ሞኖሮቪያ”ንና የ “ካዛ ብላንካን” ቡድናዊ መራራቅን አቀራርቦና አስማምቶ፤ አስታርቆና አዋህዶ የአፍሪካ አንድነትን ምስረታ እውን ስለመደረጉ ታሪክ የግርማዊ ቀ ኃ ሥን ውታ ጨርሶ የማይዘነጋው ነው፡፡ የአፍሪካ እንድነትን እውን ለማድረግ ያለመሰልቸት በትጋት ጥረዋል፡፡የአፍሪካ አንድነትን ለመመስረትም ስለ ፓን አፍሪካኖዝምም ለአፍሪካ ምሉእ ነጻነትም ታላቅ አስተዋጽኦ ያደረጉና አሁን ለደረሰበትም ደረጃ ተጠቃሽና ባለውለታነታቸው የማይዘነጋ ነው፡፡

….የወደፊቷን የአፍሪካን ራዕይ ከነጻነት አኳያ ብቻ ሳይሆን በአንድነታችንም አኳያ ነው የምናየው፡፡ይህን አዲስ ትግል በማወቅ ካለፈው ባገኘነው ውጤት መበረታታትና ጥንካሬ ተስፋ እናደርጋለን፡፡በመሃላችን ልዩነት እንዳለ እንገነዘባለን፡፡ አፍሪካውያን የተለያየ ባህል ባለሃብቶች ነን፤ልዩ ተሰጥኦና ልምዶች ያሉን ነን፡፡ ያም ሆኖ ሰዎች በበርካታ የሚያለያያቸው ሁኔታ ቢኖረንም በመግባባትና በመተሳሰብ አንድነት ማምጣትም እንደምንችል እንገነዘባለን፡፡… ታሪክ እንደሚያስተምረንና እንደሚያስታውሰን አንድነት ሃይል መሆኑን፤በመገንዘብ ግባችንን በማስቀደም፤ለጣምራ ግባችን የተባበረ ሃይላችንን ለዚሁ በማዋል ለዕውነተኛው የአፍሪካ ወንድማማችነት አንድነት ልንቆም ግድ ነው፡፡ …እንደ ነጻ ሰብአዊ ፍጡራን ጥረታችን አዲስ ግንኙነት ለመፍጠር መቆም ይገባናል፡፡በራሳችን መተማመንን፤ግባችን በማድረግ እኩልነትን ከሌሎች በእኩልነት ላይ መሰረት ካደረጉ ጋር ሁሉ አንድ ልንሆን ተገቢ ነው………

በግንባር ቀደም የአፍሪካ አንድነት አመሰራረት ላይ የምስረታውን አባቶች በምቃኝበት ወቅት፤ ለግላቸው የመዳብ ሃውልት ይቁምላቸው በሚል ሙግት ለመግጠም አይደለም፡፡እኔን አጅግ ያሳዘነኝ፤እራሳቸውን በከለላ ውስጥ እሰገብተው፤ እራሳቸውን መሆን ስለሚቸግራቸው፤ አጋጣሚውን በመጠቀም፤ታሪክን በማወላገድና መሰረቱን በማሳት፤ጭፍን ‹‹ራዕይ›› አለን የሚሉት በአፍሪካ መስራች አባቶች ስምና ተግባር ተከልለው፤(ይልቁንስ በራሳቸው ስምና ማንነት መቆም ባለመቻላቸው) የኢትዮጵያን የኖረና የዘመናት መታወቂያ ለማፈራረስ የቆመውንና የቆሙለትን ትልማቸውን ለማሳካት መጣራቸው ነው፡፡ ታሪክ ስለሥልጣንና ማንነት ቢሆን ኖሮ ቀ ኃ ሥን ማንም ቀድሞ አይገኝም፡፡ ቀ ኃ ሥ ከማንም የአፍሪካ መሪ የላቀ አስተዋጽኦ አላቸው፡፡ በዘመኑ የአፍሪካ አንድነትን ከመሰረቱት አቻ መሪዎች ‹‹የአፍሪካ አንድነት አባት›› ተብለው በ1972 ዓም በተካሄደው 9ኛው የአፍሪካ መሪዎች ስብሰባ ላይ በይፋ ተመርጠዋል፡፡ ቀደም ሲል በምስረታው ወቅት በ1963 ዓም የመጀመርያው የአፍሪካ አንድነት ሊቀመንበር ሆነው ተመርጠዋል፡፡ ዳግመኛም በ1966 ድጋሚ ሊቀመንበር ሆነው እንዲመሩ ዳግም ተመርጠው በሁለት ዘመናት በሊቀመንበርነት ተመርጠዋል ፡፡ የአፍሪካን ኮሎኒያሊዝም ቅስም ለመስበርና ከአፍሪካ ምድር ጨርሶ እንዲጠፋ ለማድረግ ግንባር ቀደሙ ናቸው፡፡ከኋላ የመጣ አይን አወጣ እንዲሉ የማንም ጭራ ነስናሽ ጥብቅና የሚሹ አይደሉም ይሄው ጭራ ነስናሽ የራሱን ሃውልት ለማቆም የነግ ድጋፍ ለማግኘት የተደረገችው ይቺ በንኩሩማህ ስም የተቸረች ሙስናዊ አካሄድ የትም አታደርስም፡፡

ታሪክ በርካታ እንቆቅልሾች አሉት፡፡ምናልባት በሃውልቱ መቆም ወቅት ንከሩማህ ወይ ሞት በማለት አጥበቀው ሲሞግቱ የነበሩ ስለፓን አፍሪካኒዝም በተነሳ ቁጥር መታወሱን ብቻ ያቀነቀኑት ንክሩማህ ስለ ኢትዮጵያ ያለውን ስር የሰደደ ፍቅርና አክብሮት ቢያውቁ ኖሮ በመቃብራቸው ውስጥ መንደፋደፋቸው አይቀርም፡፡ንክሩማህ በልቡ ውስጥ ለኢትዮጵያ የተለያ ጓዳ ነበረው፡፡ምንም እንኳን ስለ ፓን አፍሪካኒዝም ቀደምት ቢሆንም ኢትዮጵያን ደግሞ እንደ አፍሪካ አንጸባራቂ የጸረ ኮሎኒያሊዝም ብርሃን በመመሰል ከቅኝ ገዢዎች ጋር ሲያደርጉ በነበረው ትግል ወቅት የዚህች የነጻ ኢትዮጵያ ኮከብነት መሪያቸው እንደነበረ ያስታውሳሉ፡፡ከዚሁ አኳያ የኢትዮጵያን የጸረ ኮሎኒያሊዝምን ጥቃት በመታገል ነጻነቷን ጠብቃ መቆየቷ የሚያኮራ መሆኑን በማስገንዘብ፤የአፍሪካ አንድነት አሽከርካሪ መሆኗንም አረጋግጠዋል፡፡

እርግጥ ንክሩማህ ስለ ፓን አፍሪካኒዝም ንቁ ተሟጋች መሆናቸው ባይካድም፤ ለፓን አፍሪካኒዝም ግን አንድም ግጥም አላበረከተም፡፡ አፍሪካ ስለአፍሪካ ብሩህ እሳቤ ያለው ቢሆንም ለአፍሪካ ግጥም አላሰፈረም፡፡ ንክሩማህ ፓን አፍሪካኒዝምንና አፍሪካ ይወድ ነበር፤ለኢትዮጵያ ግን የበረታ ፍቅር ነበረው፡፡ለዚህም ነው በምስረታው ወቅት በመዝጊያው ላይ ባደረገው ንግግሩ ላይ ስለኢትዮጵያ ግጥም ጀባ አለ፡፡ ከዓለም መሪዎች መሃል ለኢትዮጵያ ታሪካዊነትና ግንባር ቀደምትነት፤ ስለ ሕዝቦቿ መስተንግዶ የጻፈ ብቸኛ መሪ ንክሩማ ነው፡፡

ቀ ኃ ሥ ወቅቱ ሲመጣ ሃውልታቸው እንደሚገነባ አያጠራርም ምክንያቱም ‹‹እውነት በርብራብ ስር ወድቃ አትቀርም፤ ቅጥፈትም በዙፋን ላይ ተኮፍሶ አይኖርምና››::

ወደኋላ መለስ ብለን ስናስታውስ፤ ንክሩማህ የበረታ ፓን አፍሪካኒስት ብቻ ሳይሆን የአፍሪካ ‹‹ትንቢተኛም›› ነበር፡፡ ንክሩማህ ማየት የተሳናቸው ባለራዕዮች ኢትዮጵያን ወደ ዘር ፖለቲካ አረንቋ ውስጥ ከመድፈቃቸው አስቀድሞ ኢትዮጵያ ገና እንደምትልቅ ያወቀ ነበር፡፡ንክሩማሕ የኢትዮጵያን ገኖ መዝለቅ ሃፍረት ለባሾች ‹‹የአፍሪካ ትንሳኤ …. ከማለታቸው በፊትና ከመቀላመዳቸው አስቀድሞ ያውቅ ነበር፡፡ንክሩማህ ባለጊዜ አስመሳዮች ለራሳቸው ስም ለመገንባት ጉብ ቂጥ ከማለታቸውና ‹‹ኒዮሊቤራሊዝም›› ከመዝፈናቸውና ደሟን ጨርሰው እንባዋን ከመምጠታቸው አስቀድሞ ስለማንኛውም በዝባዢና አስመሳይ ለቀስተኛ ጠንቅቆ ያውቅ ነበር፡፡

በእርግጥም የንክሩማህ ግጥም ‹‹ትንቢት›› ነበር፡፡ ‹‹ኢትዮጵያ ትነሳለች እንደ ንጋት ጸሃይ በርታ እንደ ውድቅት ጨረቃ ደምቃ ኢትዮጵያ ትነሳለች! ከምር ገና በላይዋ ላይ ያጠላውን ጥቀርሻ ዲክታተርሺፕ አስወግዳ ት ትነሳለች፡፡ኢዮጵያ ካጠመዳት ክፉ ደዌ ተላቃ እንደገና እንደ ብርቅዬ አልማዝ ታበራለች! ከዘረኝነትና ሃይማኖት ክፍያ ትላቀቃለች፡፡ ኢትዮጵያ ከወረራት የመከራ ከበባ ተላቃ፤ ልጆችዋን ካስመረራቸው ክፉ አሳቢና እኩይ ምርጊት አላቃ እጆችዋን ከተበተባት የዘርና የጎሳ ፖለቲካ፤ ከችግርና ከመከራ፤ ከእልቂትና ከደዌ ነጻ አድርጋ ልጆችዋን በአንድነት ታቅፋለች፡፡  ኣምላክም መልሶ ያቅፋታል::

ንክሩማህ እውነተኛው የኢትዮጵያ ልጅ ነው፡፡መጤዎቹ ኢትዮጵያ የ100 ዓመት ታሪክ ነው ያላት ቢሉም ንክሩማ ግና አስቀድሞ ሃሰት በማለት ኢትዮጵያማ የሰው ዘር መገኛ ማዕከል ነች ብሏቸዋል፡፡ ኢትዮጵያን በፈላጭ ቆራጭነት ሊገዙና ሕዝቦቿንም ለመራና ሰቆቃ ሲዳርጉ ንክሩማ ግን አስቀድሞ ‹‹እምቢኝ! ኢትዮጵያማ የአፍሪካ አንጸባራቂ ሉል ናት፡፡ ማንጸባረቅ ማብራት አለባት! ልቀቋት ትግነንና ታብራ ብሏል፡ ንክሩማ ‹‹ ኢተዮጵያ የብልሆች ሃገር ናት፤አባይን የጦር መንስኤ ሊያደርጉ ሲዶልቱ ንክሩማ እምቢኝ! ‹‹ኢትዮጵያ የአባይ መመንጫ ናት›› አባይ ደሞ የህይወትን ስጦታ ለአፍሪካ ያድላል ብሏቸዋል፡፡ መንፈሳችንን ለማጉደፍና ለማጣጣል ሲሸርቡና ለመከራና ለስቃይ ሲያዘጋጁን፤ ንክሩማ እምቢኝ!‹‹ኢትዮጵያማ የአፍሪካ ራዕይ ተስፋ ነች›› አላቸው፡፡ ንክሩማ የጋና ብቻ ሳይሆን የኢትዮጵያም ልጅ ነው፡፡ አንዳንድ ጊዜ በተስፋ አስቆራጭ ትቢያዎች ልንቆሽሽ መስሎ ሲሰማን በንክሩማ ትንቢታዊ አባባል ብርታት እናግኝ፡፡ ‹‹ኢትዮጵያ ገና ትትነሳለች›› ስለዚህም በግርማዊ ቀ ኃ ሥላሴና በንክሩማ  መሃል ውድድር የለም፡፡ ሁለቱም የኢትዮጵያ የተከበሩ ልጆች ናቸውና:: ንክሩማን ማክበር ማለት ቀ ኃ ሥላሴን ማክበር ነው፡፡ የሜይ 1963ቱን የንክሩማን ግጥም ሳነብ፤ ቀ ኃ ሥላሴ በኦክቶበር 1963 በተባበሩት መንግሥታት ስብሰባ ላይ ያደረጉት ንግግር ትዝ ይለኛል፡፡ በዚያ ንግግራቸው ቀ ኃ ሥላሴ ለአፍሪካን ፓን አፍሪካኒዝም ጥብቅና ከመቆማቸውም ባሻገር የአፍሪካን  ነጻነት ጠብቆና አክብሮ ለማቆየት የሚያስፈልገውን አይዲዮሎጂ በሚገባ አስገንዝበው ነበር፡፡

…አንዱን ዘር ከፍተኛ ሌላውን ዝቅተኛ አድርጎ የሚያሳየው ፍልስፍና ጨርሶ እስካልተወገደ ድረስ፤ አንደኛ ዜጋና ሁለተኛ ዜጋ የሚለው ደረጃ እስካልፈረሰ ድረስ፤ የአንድ ፍጡር ቀለም ከዓይኖቻችን ቀለም የተለየ ትርጉም እንደሌለው እስካልተረጋገጠ ድረስ፤ሁሉም ሰብአዊ መብቶች ከዘርና ከጎሳ ከቀለም ልዩነት ባሻገር ለሁሉም እኩል እስካልሆኑ ድረስ፤ በተስፋነት ብቻ የሚታሰቡ እንጂ አንዳችም እርባና አይኖራቸውም… እኛ አፍሪካዊያን አህጉራችን ከዳር እስከዳር ሰላም እስክትሆን ድረስ አስፈላጊ ከሆነ ትግላችንን አናቆምም፡፡ ደግሞም ድልን በእጃችን እንደምናደርግ ጥርጥር የለንም፡፡ መልካምነት እኩይነትን እንደሚረታው ስለምንገነዘብ ድል እንደማይርቀን እርግጠኞች ነን፡፡

ቦብ ማረሊም እነዚህን ቃላቶች ለዜማው ‹‹ዋር›› (ጦርነት) ለሚለው የአፍሪካ የትግል ዜማ የሆነውን  ሙዚቃውን አጅቦበታል፡፡(ምናለ አንድ ባለሙያስ የንክሩማን ግጥም ወደ ዜማ ቢለውጠው… ኢትዮጵያ ትትነሳለች፤ ትገናለች…  ታበራለች…. ወደ ላይ ትወጣለች::)

በምትገነዋ ኢትዮጵያ አንድን ጎሳ፤ ሃይማኖት፤ቋንቋ፤ጾታ ከሌላው አብልጦ የሚያጎላ፤ ፍልስፍና አይኖርም፡፡ በኢትዮጵያ አንደኛ ደረጃ ዜጋና ሁለ፤ተኛ ደረጃ ዜጋ አይኖርም፡፡በነገዋ ገናና ኢትዮጵያ ዘር ጎሳ፤ ሃይሞኖት፤ወረዳ፤ጾታ፤ሁሉ ከዐይኖቻችን ቀለሞች መለያየት ያለፈ ትረጉም አይኖራቸውም፡፡ በምትገነዋ ኢትዮጵያ ሁሉም እኩል የሰብአዊ መበት ባለቤት ይሆናል፡፡

ወይ ጉድየአፍሪካ አንድነት ድርጅትየአፍሪካ ሕብረት

ወይ ጉድ! የአፍሪካ አንድነት ድርጅት/ የአፍሪካ ሕብረት ስለ አፍሪካ አንድነት/አፍሪካ ሕብረት አስተያየት ማስፈር ልብ ሰባሪ ጉዳይ ነው፡፡ በ2013 በዓለም ካሉት 47ሃገራት እድገት ከማያሳዩት ሃገራት መሃል 36ቱ በአፍሪካ ይገኛሉ፡፡ በአንድ ወቅት የታንዛኒያ መሪ የነበሩት ጁሊየስ ኔሬሬ የአፍሪካ አንድነት ድርጅትን ‹‹የመሪዎች የወሬ ማሕበር›› በማለት ጠቅሰውት ነበር፡፡ ሌሎች ደግሞ‹‹የፈላጭ ቆራጭ ጋጠወጥ ራስ ወዳድ መሪዎች ክበብ›› ይሉታል፡፡ጋናዊው ታዋቂ ኢኮኖሚስት ጆርጅ አይቴ ‹‹እባካችሁ ስለ አፍሪካ አንድነት ድርጅት ማውራት ይብቃን፡፡ በአህጉራችን ካሉት ድርጅቶች ሁሉ አዘቅዝቆ የሚሄድና እርባና ቢስ የሆነ ድርጅት ነው፡፡‹‹ዴሞክራሲን›› እንኳን በሚገባ ሊተረጉም ያልቻለ ድርጅት ነው፡፡ የራሱ የሆነ ወጥነት ያለው ተግባር ጨርሶ የሌለው ነው›› ይለዋል፡፡

የአፍሪካ ሕበረት ዋና መስሪያ ቤት በቻይና መንግሥት ምጽዋት በ200 ሚሊዮን ዶላር ተሰራ በተባለና የቻይና ስጦታ “ለታዳጊዋ” አፍሪካ በተበረከተ ጊዜ ቅሬታዬን አስቀምጬ ነበር፡፡ የቻይና የግንባታ ኩባንያ ስራውን በአጠቃላይ ከቻይና በተገኘ ቁሳቁስና ቻይናዊያን ዜጎች ሰራተኞች ገነባው ሲባልና አስፈላጊውን ቁሳቁስ ሁሉ ያሟላውም ያው ቻይና ኩባንያ ነው ሲባልና ወንበርና ጠረጴዛም ሳይቀር ከቻይና ተጓጓዘ መባሉም ክፉኛ አሳዝኖኝእንደነበር ገልጫለሁ፡፡ በስጦታው ርክክብ ወቅትም የአፍሪካ ‹‹ሃፍረተ ቢስ መሪዎች›› ተርታ ገብተው እንደ ውሃ ወረፍተኛ ለቻይና የምስጋና ውርጅብኝ ሲያጎርፉ  ‹‹የአፍሪካ ትንሳኤ… የአፍሪካ ሬኔሳንስ ተጀመረ ለማስቀጠልም መንገዱን አግኝተናል በማለት አሸሸ ገዳሜ ሲሉ ነበር፡፡››

አፍሪካ አልተነሳችም አልኩ፡፡ አፍሪካ ለልመና ተዳርጋለች፡፡‹‹የቻይና ትንሳኤ በአፍሪካ ተጀምሯል›› በአዲስ አበባ የተገተረው አዲሱ የአፍሪካ ሕብረት ግንብ የአፍሪካ የሃፈረት ግንብ  እንጂ የአፍሪካ ኩራት ግንብ አይደለም፡፡ የአፍሪካ መሪዎች በአንድነት ለአፍሪካ ሚሆን ቋሚ ቢሮ ለመገንባት አቅሙን ካጡ፤ ለአፍሪካ ትንሳኤ የሚሆነውን መስራት ከተሳናቸው ያሁኑን ግንብ ‹‹የአፍሪካ ምጽዋተኞች አንድነት አዳራሽ›› ከማለት አላልፍም:: የአፍሪካ አንድነት ድርጅት/ የአፍሪካ ሕብረት እና ሰብአዊ መብት የአፍሪካ አንድነት ድርጅት/የአፍሪካ ሕብረት በአፍሪካ የፖለቲካ፤ የኤኮኖሚ እና የሶሻል ግንኚነቶችንና ነጻነትን ከማጠናከርና ተግባራዊ በማድረግ ወደ ልማት አቅጣጫውን ከማራመዱ አስቀድሞ ማከናወን ያለበት ሰብአዊ መብትን ነው፡፡ የአፍሪካን  ልማት  ለማከናወንም ሆነ አቅዶ ወደ ግብ ለማድረስ የሰብአዊ መብት መከበር ቅድሚያ ሊሰጠው የሚገባ ተግባር ነው፡፡ ሕዝቦች በነጋ በጠባ ለመከራና ስቃይ እየተዳረጉና የግፍ ኑሮ፤ የባርነት ቀንበር ተሸክመውጀርባቸው በተደራራቢ ችግር ጎብጦ ልማትን አመጣለሁ ብሎ ሩጫ ለመውደቅና ለከፋ መከራ ለመዳረግ መጣር ብቻ ነው፡፡

የአፍሪካ አንድነት ጸረ ኮሎኒያሊዝም፤ኒዮ ኮሎኒያሊዝም ጸረ ጸረ ጸረ ብሎ የሚደረድራቸው ማለቂያ የሌላቸው ጸረዎች በችግርና በመከራ ላሉ ሕዝቦች አንዳችም ጠቀሜታ የሌላቸው ልፈፋዎች ብቻ ናቸው፡፡ የአፍሪካ አንድነት ድርጅት/ የአፍሪካ ሕብረት ጤት አልባ ከዚያም አልፎ ዋጋ ቢስ መሆኑን ለሰብአዊ መብት ካለው አመለካከትና ከከወነው ተግባር ነው፡፡ በበርካታ የአፍሪካ ሃገራት ክፍሎች ጦርነት የየቀናት ክስተት ነው፡፡ሰዎች በየቦታው ሲተላለቁ የአፍሪካ አንድነት እጁን አጣጥፎ ከመመልከት ውጪ አንዳችም እርምጃ አልወሰደም፡፡ የአፍሪካ ጉልበተኛና ፈላጭ ቆራጭ ገዢዎች ከውጪ ወራሪ በከፋ መልኩ ሕዝቦችን ሲጨፈጭፉ ለስደት ሲዳርጉ በግፍ ከመኖሪያቸው ሲያፈናቅሉ የአፍሪካ አንድነት ድርጅት አይኑን ጨፍኖ፤ ጆሮውን ደፍኖ፤አፉን ለጉሞ የድርጊቱ ተባባሪ መሆንን የመረጠ ነው፡፡ ለሕዝቦች እልቂት ደንታ የሌ፤ልው ድርጅት/ ሕብረት፡፡ የሩዋንዳ እልቂት በሚሊን የሚቆጠሩትን ንጹሃን ዜጎች በሞት ሲቀጥፍ የአፍሪካ አንድነት ቢሮውን ዘግቶ አርቲ ቡርቲ ከማራገብ ውጪ ምንም ያደረገው አልነበረም፡፡ ሌላው ቀርቶ የአፍሪካ አንድነት ግድያውን ‹‹ጄኖሳይድ›› ለማለት እንኳን ድፍረቱና ወኔው አልነበረውም፡፡!

የአፍሪካ አንድነት ድርጅት/ የአፍሪካ ሕብረት ሶማልያ ለሁለት አሰርት ዓመታት በመበታተን ላይ ሳለች፤ የጎሳ መሪዎች ተቀራምተዋት ለጥፋት ሲዳርጓት እንኳን መድረስ ቀርቶ ከሩቅ ሆኖም ማስጠንቀቂያም ሆነ ማስፈራሪያ አልሰነዘረም፡፡ ለተፈጠረው ችግር ሌሎች ሃገራት ጥቅማቸውን ለማስጠበቅ በሚያመቻቸው መንገድ ጣልቃ ገብተው ሲያማትሩ የአፍሪካ አንድነት በቂ ጦር እንኳን ለመላክና ሕዝቡን ከመከራ ለመታደግ አልሞከረም፡፡ በኮት ዲቭዋር የተፈጠረውን ችግር የፈረንሳይ ወታደሮች ገብተው ሲፈነጩበት የአፍሪካ እንደነት በስፋራው ቀርቶ በአካባቢውም አልደረሰም፡፡ በማሊም የተፈጠረውን ሽብር ለማስታገስና ስርአት ላመስያዝ የፈረንሳይ 5000 ወታደሮች ሲዘልቁ የአፍሪካ አንድነት ከጠቅላይ ቢሮው ንቅንቅም አላለም፡፡ በኢትዮጵያም የምርጫ  በጠራራ ጸሃይ ሲሰረቅና ተሸናፊው አሸናፊ ሆኖ ሲወጣ በዝምባብዌ፤በኬንያ፤ በዩጋንዳ ተመሳሳይ የምርጫ ውጤት ዘረፋ ሲካሄድ የአፍሪካ አንድነት በገለልተኛነት ከዳር ቆሞ ከተመልካችነት አላለፈም፡፡

የአፍሪካ ሕብረት የሰብአዊ መብትን ጥሰት በተመለከተ፤ ወንጀለኞችን መደገፍን  ሙያ ብሎ ይዞታል፡፡ የሱዳኑ ኦማር አል በሺር በሰብአዊ መብት ጥሰትና በጦር ወንጀለኛነት በግፍ ጭፍጨፋ በዓለም አቀፍ ወንጀለኞች ፍርድ ቤት ተከሰው መያዣ ሰነድ ሲተላለፍባቸው ‹‹የአፍሪካ ሕብረት አባል ሃገራት በሮም የተፈረመውን የፍርድ ቤቱን ስምምነት አናከብርም በማለት የሱዳኑን አልበሺርን አሳልፈን አንሰጥም አቋም ያዙ›› ይህ ደግሞ ነግ በኔ በሚል ስጋትና አስቀድሞ መንገድ ለመዝጋት ሲሉ ተመሳሳይ ወንጀለኛ መሪዎች የወሰዱት አቋም ነበር፡፡ በዚህም የአፍሪካ ሕብረት ተግባሩን መወጣት ባለመቻሉና ፍላጎትም በማጣቱ አይ ሲ ሲ ዓለም አቀፍ የወንጀል ፍርድ ቤት ጣልቃ መግባቱ አስፈላጊ ሆነ፡፡ ከ2011 አንስቶ በሰባት የአፍሪካ ሃገራት ውስጥ ይሄው ፍርድ ቤት የማጣርያ ምርመራውን በማካሄድ ላይ ነው፡፡

የአፍሪካ ሕብረት የሌለው ቢሮ ያላቋቋመው የመብት ማስከበርያ ጽ/ቤት የለም ግን አንዳቸውም ለተግባር አልበቁም፡፡ የአፍረካ ሕብረት የሰብአዊ መብት ቢሮ፤ የአፍሪካ ሕብረት የልጆች መብት፤ የሴቶች መብት፤ በማለት በርካታ ኣዋጅ አውጥቷል ቢሮም አቋቁሟል፡፡ የአፍሪካ ሕብረት የፖለቲካ ቢሮም አለው፡፡ የዚህም ቢሮ ተግባሩ ሰብአዊ መብትን ማስከበር፤ የዴሞክራሲ ስርአትን ትግበራ ማረጋገጥ፤ምርጫዎችን በአግባቡ ተካሂደው የህዝብ ፍላጎት ማሟላት ቢሆኑም አንዱንም አላከናወነም፡፡ በአባል ሃገራት ምርጫ ወቅት ዳጎስ ያለ ወጪ በመመደብ ታዛቢዎች ቢሊክም ታዛቢዎቹ ሆቴላቸውን ሳይለቁና ምርጫ ጣቢያዎችም ቢሆን እንደነገሩ ደረስ መለስ ከማለት አልፎ አንዳችም ውጤት ያለው ትዝብት አላከናወኑም፡፡ በየሄዱበት ሃገር ያለው ገዢ ፓርቲ የሚሰጠውን መግለጫ ደግፈው ተጋብዘውና ተሸልመው ከመመለስ ውጪ ምንም አላደረጉም:: በ2010 ነፍሳቸውን በተገቢው ቦታ ያኑረውና መለስ ዜናዊ 99.6 በመቶ ምርጫ አሸነፍኩ ሲል፤በቀድሞው የቦትስዋና ፐሬዜዳንት ማሲሬ ለታዛቢነት የተሰማራው ቡድን ምርጫው ፍትሃዊና ሰላማዊ ነበር፤ የምንግስት መዋቅርን መጠቀምና ሕገ ወጥ የሆነ ሂደትም መራጩንም ማስፈራራትና መስገደድም ያልነበረበት ምርጫ ነበር በማለት ማሲሬ ቀልማዳ ትዝብቱን ተፈራረመ፡፡ ሲደመድምም ምርጫው የአፍሪካን አንድነት የምርጫ ደንብና ስርአት ያሟላ፤ የመራጩን ሕዝብ ፍላጎት ያካተተ፤… የአፍሪካ ሕብረት ተቃዋሚዎች ከምርጫው አስቀድሞ ያሰሙትን ቅሬታ የሚያረጋገጥ አንዳችም ሁኔታ አልታየም፡፡ ክሱን ወይም ውንጀላውን የሚረጋግጥ አንዳችም ሁኔታ አላየንም በማለት ነበር፡፡

አፍሪካ ከመቼውም በከፋ መልኩ አሁን ተበታትናለች፡፡ፓን አፍሪካኒዝም አፈር ዲቤ በልቷል፤ እድሜ ለአፍሪካሕብረት፡፡አሁን በአፍሪካ ላይ በማንዣበብ ላይ ያለው አዲስ አየዲዮሎጂ ነው፡፡ የአፍሪካ ጨቋኝ ገዢዎች በድፍረትናበማን አለብኝነት የዘር ብሔርተኝነትን በስልጣን ለመቆየት አመቺ ስለሆናቸው በመንዛት ላይ ናቸው፡፡ የዘርማንነት፤ የዘር ጥራት፤የዘር መኖርያ፤ በሚል ሰበብ ሕዝብን መጨፍጨፍና ከራሳቸው ከገዢዎች ውጪ ያለውን ዘር በሚልያስቀመጡትን ሁሉ ለማጥፋትና ብቸኛ ዘር ሆነው ለመኖር እየገሰገሱ ነው፡፡

በኢትዮጵያም ‹‹የብሔር ፌዴራሊዝም›› በሚል ቆንጆ መጠቅለያ የተጀቦነ ፖለቲካዊ ሂደት እየተንደረደረነው፡፡ኢትዮጵያዊያን በማንነታቸው በትውልዳቸው በቀያቸው መገለልና መገፋት መፈናቀል እየደረሰባቸው ነው፡፡በክልልተደልድለው ያለፍላጎታቸው ስም ወጥቶላቸው ለጥቃት ተዘጋጅተዋል፡፡ ጥቂት የገዢው መደብ አባላት በድሎት እንዲኖሩናያለሃሳብ እንዲንደላቀቁ 80 ሚሊዮን ሕዝብ ለግፍ ተዳርጓል፡፡እንዳይናገር በሆዳም ካድሬዎችና ለጊዜው ገዢዎችእራሳቸውን በሸጡ አጎብዳጆች ተወጥሮ መከራ እየወረደበት ነው፡፡ ሆዳሙ ያዜማል ሆዳሙ ይገጥማል፤ ሆዳሙ ይጨፍራል፤ሆዳሙ ቅኔ ያፈሳል ሆዳሙ ያጨበጭባል ሆዳሙ ይደሰኩራል፤ ሆዳሙ ሆዱን ይሞላል ሕዝቡ ግን ለመከራና ስቃይተዳርጓል፡፡

ታላቁ የአፍሪካ ደራሲ ቺኒዋ አቼቤ  (Things Fall Apart) ለምንድን ነው በአፍሪካ ሁሉም ነገርየሚፈራርሰው በሚል መነሾ ጻፈ፡፡የኔ መለስ አጭር ነው፡፡ባለፈው የግናሽ ምእተ አመት ነጻነት የአፍሪካን ግፈኛገዢዎች ተጠያቂ የሚያደርግ ድርጅት ለመፍጠር ባለመቻሉ ነው እላለሁ፡፡ላለፉት 50 ዓመታት የአፍሪካ መሪዎችተጠያቂነትን አሻፈረን ብለዋል፡፡ የዚህ ተጠያቂ ሕዘቡ እንደሆነ ለማሳመን ጠረታቸው መጠን የለውም፡፡አፍሪካ ከቅኝገዢዎች በተተወለት ሁኔታ ውስጥ ነው ያለው፡፡ሰበብ እየተደረገ ዘወትር በማያልቅ ጥሪ የሚጠቆመው፤ ነጮች፤ የቅኝገዢዎች ቅሪት፤ ካፒታሊዝም፤ ኢምፕሪያሊዝም፤ ኒዮ ሊቤራሊዝም፤ ግሎባላይዜሽን ነው መሸሻው፡፡ ….. የዓለምየገንዘብ ተቋም ነው፤የዓለም ባንክ ነው፤……የአህጉሩ ያለማደግና ያለመልማት ሰበቡ  የመኑስናው፤ የመልካምአስተዳደር እጦት ሁሉም በመጥፎና እርኩስ መንፈስ የመጡ እንጂ የአህጉሩ አይደሉም ማለት ይዳዳቸዋል፡፡ነገሮች ሁሉ በአፍሪካ ፍርስርሳቸው የሚወጣበት ሰበብ የአፍሪካ ‹‹መሪዎች›› የሕዝቦቻቸውን ሰብአዊ መብትባለማክበራቸው ነው፡፡የአቼቤን አባባል ለማጠናከር፤ አፍሪካ አሁን ያለችበት ሁኔታ ውስጥ ያለችበት መንስኤየአፍሪካ መሪዎች እንደመሪ ሊሆኑና ሊያደርጉ የሚገባቸውን የመሪነት ሚና መጫወት ባለመቻላቸው ነው፡፡ ‹‹ጥቂትየአፍሪካ መሪዎች የሕዝቦቻቸውን ክብርና ሰብአዊ መብት በአግባቡ ያከብራሉ፡፡ አፍሪካ መሪዎች ናቸው በሚባሉትገዢዎቿ እያደናቀፉ እየጣሏት እንዴትስ መነሳትና መግነን ትችላለች? ለመነሳት በሞከረች ቁጥር ያንን የመርገምትቦት ጫማቸውን ማጅራቷ ላይ አሳርፈው እንዳትነሳ፤ እንዳታድግ፤ እንዳትለማ ረግጠው ይዘዋት እንዴት ብላ ነውየምታድጋው? ያም ሆኖ ጊዜው ሲደርስ አፍሪካ ፍርስርሳቸው የወጡባት አፍሪካ ተሰባስበው አንድ የገነነች አፍሪካሆና ትነሳለች!ስለዚህም ለአፍሪካ አንድነት/ አፍሪካ ሕብረት 50ኛው ዓመት የወርቅ ኢዩቤልዩ ለግ ቀ ኃ ሥላሴና ለክዋሚህንክሩማህ የማበረክተው ስንኝ

ኢትዮጵያ ከፍ በይ! የኢትዮጵያ ትንሳኤ! የአፍሪካ ትንሳኤ

 

ኢትዮጵያ የአፍሪካ አንጸባራቂ ማዕድ ትነሳለች ትገናለች

ከፈላጭ ቆራጭ ስርአት ተላቃ

የግድበ አፍሪካ ምድር እንደሚበራው የበጋ የንጋት ፍንጣቂ

በአፍሪካ ምሽት ሰማይ እንደምትበራው የጨረቃ

ብርሃን አንቂ ኢትዮጵያ ትንሳኤዋ ያበራል ትገናለች::
ኢትዮጵያ ከራስ ደጀን ጉብታ ጫፍ ትንሳኤዋ ይታያል

እስከ ኪሊማንጃሮ ዘልቆ ይጠራል

ከፖለቲካው አረንቋ መታወቂያነት

እስከ ሀገራዊ ኩራት በልዩነት

ኢትዮጵያ አስከብራ የሁሉንም ማንነት ትነሳለች::
በአፍሪካ ምድር የነጻነት ብርሃኗን ትረጫለች

የሊቃውንት ሃገር ኢትዮጵያ ከመንደርተኛ አዋቂዎች በላይ ተንብያ

ህዝቦቿ ተሰባስበው ተዋህደው ተፋቅረውና ተግባብተው

ሰብአዊነትን ወግነው አንድነትን መቻቻልን አንግበው

ኢትዮጵያ ትነሳለች ትገናለች::
ኢትዮጵያ የነግህ የአፍሪካ ተስፋ

በትንሳኤዋ የረገጧትን የጨፈለቋትን  አልፋ

ቅጥፈታቸውን ጭካኔያቸውን ሙስናቸውን

ያን ያለፈ ዘመናቸውን ከነምኞታቸው ገንዛ በብረት ሳጥን

የሕግ የበላይነትን አስከብራ፤ኢትዮጵያ እንደ ጸሃይ ታበራለች::
በምድሯም ሰላም እስከ ዘልዓለሙ እንዲሰፍን ታደርጋለች

የኢትዮጵያ ትንሳኤ በማይደፈሩት ሃቀኛ ወጣቶቿ

ከፍ ትላለች ተደግፋና ተሞሽራ በልጆቿ

ኢትዮጵያ እስከማዕዜኑ ትገናለች

ለወጣቱ ትውልድም  የዘልአለም ቤቱ ትሆናለች::

*የተቶረገመው ጽሁፍ (translated from):

http://open.salon.com/blog/almariam/2013/05/26/ethiopia_shall_rise

(ይህን ጦማር ለሌሎችም ያካፍሉ::) ካሁን በፊት የቀረቡ የጸሃፊው ጦማሮችን  ለማግኘት እዚህ ይጫኑ::

http://www.ecadforum.com/Amharic/archives/category/al-mariam-amharic

http://ethioforum.org/?cat=24

Leave a Reply