ቤተክርስቲያናችን እንደ ሕዝበ ክርስቲያኑ ከተሰደደች ጀምሮ ሃይማኖቷን ጠብቃና ባህሏን አጥብቃ ዜጎቿ ተበታትነው እንዳይቀሩ በማሰባሰብ ስታስተምርና ስትሰብክ እነሆ ዓመታትን አስቆጥራለች። በምዕራቡ ዓለም በዚህ በአትላንታ አሜሪካ በሕዝበ ክርስቲያኑ ትጋትና ጥረት አምላካችንን የምናመልክበት፣ ትምሕርት የምናስተምርበት፣ ክርስትና የምናጠምቅበት፣ ሙታንን ፍትሃት የምንሰጥበት፣ ቋንቋችንን የምናስተምርበት ቤተ እግዚአብሔርን አንፀን ይኸው ሃያ አምስት ዓመትን አስቆጠርን። ለኀያሉ እግዚአብሔር ምሥጋና ይድረሰውና ይኽንን በስደት ላይ እያለን አምላካችን ያደለንን የኢዩቤልዩ ፀጋ በታላቅ ድምቀት በጌታችን በመድኃኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ እናት በሰዓሊተ ምህረት ቅድስት ማርያም ካቴድራል በነሐሴ 19-20 , 2004 ዓ.ም.(August 25-26,2012) እናከብራለን።
የእግዚአብሔር ፀጋ ከእናንተ ጋር እንዲሆን እንጸልያለን።
መጋቢ ብሉይ አባ ኃይለሚካኤል
የካቴድራሉ አሰተዳዳሪ



