ጌታቸው ኃይሌ
ስለ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ጤንነት የተምታቱና እርስ በርሳቸው የሚጋጩ ዜናዎች የውይይት መድረኮችን
አልብሰውት በነበረበት ጊዜ፥ "እግዚአብሔር ይማራቸው። በዚህ በልጅነት እድሜያቸው ካልማራቸው
ግን፥ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ይመሩት የነበረው ወታደራዊ ድርጅት (ሕወሓት) ስለኢትዮጵያ የወደፊት ዕድል
አዲስ ፈር ለመትለም አርቆ ለማሰብ ሙሉ ነፃነትና ዕድል ሊሰጠው አስቦ ይሆናል" ብየ ከዚህ በታች
የምደግመውን ሐሳብ የያዘ ግልጽ ደብዳቤ በኅትመት ለሕወሓት ኀይሎች እንዲያደርስልኝ፥ ለፍትሕ
ጋዜጣ ልኬ ነበር። አምላክ ሞትን የአሸናፊነት ኀይል ስላቀዳጀው፥ በሹክሹክታ የተወራው እውነት ሆነ።
ሕወሓትም የአሸናፊነት ኀይል ስለተቀዳጀ፥ በፈለገው ሰዓት ጋዜጣውን ዘጋው፤ አሳታሚውንም እስር
ቤት ዘጋበት።
ባለፉት ሃያ አንድ ዓመታት ድርጅቱና በውድም በግድም የሚደግፋቸው ሕዝብ በአንድ ወገን፥ የቀረው
የኢትዮጵያ ሕዝብ በሌላ ወገን፥ ሆነን በቃላት አሎሎ ተደባድበናል። የድርጅቱ ሠራዊት በመሪው ትእዛዝ
የሌላውን ወገን መሪዎች አስሯል፤ የረታ ፍትሕ ነፍጓቸዋል፤ ብዙዎችን ለሞት አብቅቷል። በሁለቱ ወገን
ያለው ፍጥጫ እስካሁን አንዲት ምናን ያህል አልረገበም። ጋዜጣ ባነበብኩ ቊጥር የማየው እነዚያው
የቃላት አሎሎ ሲወናጨፉ አገኛቸዋለሁ። ሕዝቡ ሃያ አንድ ዓመት ሙሉ ውስጣዊ ሰላም ተነፍጎ ነበር
ማለት ነው። ከሓዲ ካልሆነ፥ ለዚህ ማስረጃ የሚፈልግ ሰው አይኖርም። ይህን አላስፈላጊ ፍጥጫና ጥላቻ
እስከመቸ አንከባክቦ ማኖር ይቻላል? ለምንስ ይጠቅማል? ያለነውኮ በመላ ዓለም ላይ የዲሞክራሲ ጮራ
በፈነጠቀበት በሃያ አንደኛው ምእት ዓመት ነው። ጭቆና የሰብአ ትካት እንጂ የሥልጣኔ መሪዋ የሆነችው
የኢትዮጵያ ልጆች ጠባይ ሊሆን አይገባም። የዲሞክራሲና የጭቆና ትግል የገብርኤልና የሳጥናኤል ትግል
ነው።
ጭቆና ወንጀል ነው። ወንድምን እኅትን እንደከብት መንዳት ነው። የኢኮኖሚ እድገት ብታመጡም
እንኳን፥ ሕዝቡን ነፃነቱን ከገፈፋችሁት፥ ሰውን እንደከብት ማድለብ ይሆናል። ትግራዊ ያልሆነ
ወንድማችሁ አለመሆኑን ያስተማራችሁ ርኩስ መንፈስ ነው። በተለየ ክርስቲያኑ ሕዝብ አክሱም ጽዮንን
"እናቴ" እያለ፥ "ትግራይ ካልሆንክ የናቴ ልጅ አይደለህም" አላችሁት። የታገላችሁት ኢትዮጵያውያን
ጀግኖች መሆናቸውን ለማሳየት፥ በክብራቸው እንዲኖሩ ለመታደግ መሆኑ ቀርቶ፥ ሥርወ መንግሥት
(dynasty) ለመለወጥ አደረጋችሁት።
ጠቅላይ ሚኒስትሩ የወረደባቸው የቃላት አሎሎ ስላቈሰላቸው፥ ቂም ይዘው፥ እልህ ገብተው ስለነበረ፥
ዕርቅ ለማውረድ ባያስቡበት ሊገርመን አይገባም። ያ የዕርቅ ዕድል የዛሬ ሃያ አንድ ዓመት አዲስ አበባን
የያዙ ዕለት አምልጧል። በዚያ ጊዜ ያልፈራቸውን ሕዝብ እሳቸው ስለፈሩት ብቻ፥ ፍጥጫ
የሚፈጠርበትን ሁኔታ ማዘጋጀታቸው አይረሳም። የሽግግር መንግሥት ቻርተር እንጻፍ ብለው ስብሰባ
ከጠሩ በኋላ፥ ዲሞክራሲያዊ ሐሳብ በሚያቀርበው ላይ የስድብ ውርጂብኝ የሚያዥጎደጉዱ ቂመኞች
ለቀውበት እንደነበረ ታስታውሳላችሁ። የሚያኮራ ታሪካችን ይከበር በሚለው ላይ የተናካሽ ውሻ ጥርሱን
የሚያወጣውን እየፈለጉ ለቀውበት እንደነበረ ታስታውሳላችሁ።
"አገዛዜን ሕዝብ ይደግፈዋል፤ ሕዝቡ እኔንም ይደግፈኛል" ይሉት የነበረው ከእውነት የራቀ መሆኑን
እሳቸውም፥ እናንተም፥ እኛም፥ እንዲያውም በቀብራቸው ሥነ ሥርዓት ላይ ያደነቋቸው ሳይቀሩ፥
መላው ዓለም ያውቀዋል። አቶ መለስ እንደ ሙሶሊኒ፥ እንደ ሂትለር፥ እንደ መንግሥቱ ኃይለ ማርያም
የተወደዱም የተጠሉም መሪ ነበሩ። ይሄ የማይካድ ሐቅ ነው። ታሪክም የሚያስታውሳቸው እንደዚሁ
ከነዚህ ከመሰሎቻቸው ጋር ነው። ታሪካቸውን በዚህ መልክ ያስመዘገቡት ተገድደው ሳይሆን ወደውና
ሌሎችን አስገድደው ነው። የሚያነቧቸው መጻሕፍት ሕዝብ እንዴት አፍኖ መግዛት እንደሚቻል
የሚያስተምሩ እኩያን የሰፊ ሕዝብ ጠሮዎች የጻፏቸው መጻሕፍት ናቸው። ታዲያ ሕዝብ ምን
አይቶባቸው ይደግፋቸዋል? ኢትዮጵያን ሕዝቧንም ምድሯንም እየበደሉ እንዴት ይደግፋቸዋል? አፉን
የዘጉት፥ ነፃ ምርጫ የነፈጉት፥ በሕዝብ ማህል የማይገኙት፥ ሕዝብ እንደማይፈልጋቸው ስላወቁት ነው።
ሲያልፉ ማንም ቀና ብሎ እንዳያያቸው ሕዝቡን መሬት ያስደፉ እንደነበሩት እንደ አፄ ዮሐንስ፥ ጠቅላይ
ሚኒስቴሩም ወደ አይሮፕላን ጣቢያ ሲሄዱና ሲመጡ ሕዝቡን ፊቱን አዙሮ እንዲቆም ያደርጉት የነበረው
ሕዝብ እንደማይፈልጋቸው ስላወቁት ነው።
አሁን ግን አቶ መለስ በሕይወት ከሌሉ፥ የሌሉት ለዕርቅ ደንቃራ የሆኑትን ቂማቸውንና እልሃቸውን ይዘው
ነው። እሳቸው የያዙትን ይዘው ገለል ስላሉ፥ ብሔራዊ ዕርቅ ለማውረድ ድርጅታችሁ ሊታለፍ
የማይገባው ዕድል ተሰጥቶታል። የዕርቅ በር ከፍቶ ወደፊት በመገሥገሥ ፈንታ፥ ባለበት ረግቶ፥ ሌላ
መለስ ዜናዊ እንዳይሰጠን ድርጅቱን አሳስባለሁ። ይህን ሐሳብ ያቀረበውን ሰው ማንነት ትታችሁ ሐሳቡን
አስቡበት።
አንድ ጨቋኝ ሲያልፍ ግብር አበሮቹ የተሻለ ዘመን እንደሚያመጡ የብዙ አገሮች ታሪክ አሳይቶናል።
በሀገራችንም ዕርቅ በፈቃድ የማምጫው ጊዜ አሁን ነው። እምቢ ለማለት አቅም እያለው ማንም
ሳያስገድደው በፈቃዱ ሰላም የሚያመጣ ወገን ገናና ነው። በኀይል የተገለበጠና በፈቃዱ ዕርቅ ያመጣ
ባለሥልጣን ዕድላቸው የተለያየ እንደሆነ ግልጽ ነው። "ስሕተትን በጊዜዋ ማን ልብ ይላታል" እያሉ
የተቆጩ፥ ኀይል እያላቸው አርቆ ማየት አቅቷቸው የወደቁ ባለሥልጣኖች ናቸው። ይኸንን ለማየት
የሕወሓት ሰዎች ሊያቅታችሁ አይገባም። ዕርቅ፥ ዲሞክራሲ፥ ነፃነት ጥቅማቸው ለሕዝብ ብቻ ሳይሆን
ለገዢውም አካል ነው። እስቲ ሞክሯቸውና የሚሆነውን እንይ።
የሚሆነውን እስክናይ ለመገመት ግን አያስቸግርም፤ ሰብአዊ መብት ከተከበረ፥ ላምና አንበሳ፥ አህያና
ጅብ፥ ምጥማጥና ዶሮ፥ አብረው ይውላሉ፤ አብረው ያድራሉ። የጨቆኑና የተጨቆኑ ያለፈውን
ረስተው ሳይፈራሩ በሀገር ልጅነት፥ በወንድማማችነት፥ በእትማማችነት አብረው ያመሻሉ። ባላንጣዎች
አብረው ይዘምታሉ። ሊቃውንቱ፥ ምሁራኑ፥ መምህራኑ ችሎታቸውን ለነፃነት ከመታገል ላይ ቀንሰው
ድኽነትና ድንቁርና ከሚጠፉበት ላይ ያውላሉ፤ ልዩነቶች ከጉዳት ወደ ጥቅም የሚለወጡበትን ዘዴ
ለመፈለግ የተረጋጋ መንፈስ ያገኛሉ። ኢትዮጵያ የሚቀርቧት እንጂ የሚርቋት ሀገር መሆኗ ይቀራል።
ሀገሪቱ ያስተማረቻቸው ልጆቿ በስደት ሌላ ሀገር ከማገልገልና ሀገራቸውን ከመናፈቅ ይድናሉ።
በትምርት አንጻ ያሳደገቻቸው ልጆቿ ሌላ ሀገር እንዴት እንደሚያገለግሉና እንደሚያዳብሩ በሰፊው
ተነግሯል። ብዙዎች በምርምር ያገኙት ለእድገት የሚጠቅም ግኝት በስማቸው ተመዝግቦላቸዋል። አሁን
በቅርብ እንኳን የአሜሪካ ላዕላይ ፍርድ ቤት የፕሬዚዴንት ኦባማን የሕዝብ ጤና ጥበቃ አቅድ ደግፎ
ሲፈርድ የኢኮኖሚ ጥቅሙን ያሳየው የዶክተር ብርሃኑ ዓለማየሁን ምርምር ጠቅሶ መሆኑ በፍርድቤቱ አፍ
ተነግሯል።
በጎሳ፥ በቤት የከፋፈላችሁን የነገዶችን መብት ለማስከበር እንደሆነ ታምናላችሁ። ከፋፍሎ ለመግዛት
መሆኑን ዓይናችሁ እያየ ትክዳላችሁ። ነገዶቹ እንዳላመኑበት ምርጫ 97 መስክሯል። ነገዶቹ ካላመኑበት
የናንተ እምነት አዲስ ሃይማኖት እንደማስተማር ይቈጠራል። ጥቂት ጥቅመኞች ለይምሰል ያህል የተቀበሉ
ቢመስሉ አትታለሉ። ሕዝቡ ለመቀበሉ ማስረጃ አይሆኑም። እንዲያውም፥ ልብ አላላችሁትም እንጂ፥
ልብ ብትሉት፥ በጎሳ በዘር መከለል ከመጣ፥ ሀገሪቷ ብቻ ሳትሆን፥ እያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ ብዙ ክልሎች
(የአማራ፥ የሲዳማ፥ የኦሮሞ . . . ክልሎች) ይወጣዋል።
ሕወሓቶች አስቡበት፤ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ሲሄዱ፥ "ቂሜን፥ እልሄን አደራ" ብለዋችሁም እንደሆነ፥
እሳቸውን በሌሉበት ከመታዝዝ ከአገር ልጆች ጋር በሰላምና በጤና አብሮ መኖር ይብስብናል ብትሉ፥
ዓለም በጀግንነትና በአርቆ አስተዋይነት ይመዘግባችኋል እንጂ፥ ማንም በአደራ በላነት አያማችሁም።
ለዘለቄታው የሚያዋጣው፥ ብሔራዊ የአንድነት መንግሥት ሲሆን አሁኑኑማቋቋም፥ ካልሆነም፥ ቀስ
በቀስ ከዚያ የሚያደርሰውን መንገድ ተልሞ መጓዝ ነው። ዕድል አምልጧችሁ የሚተገትገን፥
የምንተገትገው ሌላ ተጠልቶ የሚያስጠላችህ መሪ አታምጡብን። የብዙዎችን ጎባጣ መንገድ ያቀና
የወንድሞቻችሁና የእኅቶቻችሁ የሰላም አምላክ ቀናውን መንገድ እንድትይዙ፤ አርቆ አስተዋይነትን
ይስጣችሁ። ወደከፋ ከመሸጋገር ያድነን።



