ድምፅ አልባው አብዮት በኢትዮጵያ
ላለፉት 20 አመታት በህዝቡ ጫንቃ ላይ ተጭኖ የኖረውና በብልጣብልጡ መሪ መለስ ዜናዊ በተቀየሰው መስመር መሰረት ለመጪው 40ና 50 ዓመታትም ይቀጥላል ተብሎ ሲፎክርበት የነበረው የትግሬ አፓርታይድ አገዛዝ ባልታሰበና ባልተጠበቀ መልኩ ፍሬን መያዙ ብቻም ሳይሆን ሿፈሪዎቹ ከመሪ ጨበጣው ገለል መደረጋቸው እውነትም ሀገሪቷ የድምፅ አልባ አብዮት እያስተናገደች መሆኗን የሚያሳይ ተጨባጭ ምልከታ ሳይሆን አልቀረም፡፡ ይህ አይታሰቤና ድንገቴ ክስተት ተጠራጣሪዎቹ እንደሚገምቱት አስቀድሞ በሚስጥር የተቀነባበረ (አንዳንዶች የጠቅላይ ሚኒስተሩ ምክንያተ- ቅስፈት የማይታዩ እጆች አሉበት ብለው እንደሚጠረጥሩት) አልያም እንደብዙዎቹ እምነት ‹‹የእግዚአብሔር ስራ›› ተብሎ ለጊዜው ሊታለፍ ቢቻልም ቅሉ ይህ አብዮት ተጀመረ እንጂ ተጠናቀቀ ብሎ የየዋህ ከበሮ ድለቃ ውስጥ እንደማያስገባ ማወቅ ከምንም በላይ አስፈላጊ ይመስላል፡፡ እስከ መጪው ሀገራዊ ምርጫ የሚያደርሱን ቀጣዮቹ ሶስት አመታት የድምፅ አልባው አብዮት ዘላቂነት አልያም አብዮቱ ድምፅ አውጥቶ የሚጮህበት ጊዜ መሆኑን መገመቱ አይከፈልም፡፡
የትግሬ አፓርታይድ አገዛዝን ሲዘውሩት የነበሩት ፅንፈኛ የህወሃት ሰዎች በትረ- ሙሴውን አምነውበት፣ አቅደውትና ፈቅደው አልያም ለዴሞክራሲ መርሆች ተገዢ ሆነው በህዝብ ሳይሆን በዛው በኢ.ህ.አ.ዴ.ግ የም/ቤት አባላት ድምፅ ለተሰጣቸው ሰዎች ያስተላለፉት መሆኑን ብናምን ኖሮ እውነትም ድቅድቅ ጨለማ የዋጠው የሀገራችን የዴሞክራሲ ጎዳና ጫፍ ላይ ብርሃን እየታየ ነውና በተደሰትን ነበር፡፡ ዳሩ ግን እውነታው ከዚህ ፍፁም የራቀ ይመስላል፡፡ ከህልፈተ-ህይወቱ በኋላ ‹‹ድንቅ ስትራቴጂስት›› እየተባለ የሚቆለጳጰሰው መለስ ዜናዊ ላለፉት ሀያ አመታት የተጓዘበት መንገድ እራሱ በቀየሰው ‹‹የትግሬ የበላይነትን ማስጠበቂያ›› መሆኑ ቀርቶ የስትራቴጂው ውጤት በተቃራኒው ለኢትዮጵያና ለህዝቧ ማድላቱ ታይቷል፡፡
የአፄ ዮሐንስን ‹‹ስህተት›› ላለመድገም ‹‹ስጋ ብፅዓት›› እያለ ይምልና ይገዘት የነበረው ሰው የህወሃትን የበላይነት ማስቀጠያ አማራጮችን ሁሉ ደምስሶ በብቸኝነት በራሱ ተክለ-ሰውነት ልክ በዙሪያው እንዲጠመጠሙ የፈቀደላቸው ሰዎች በስተቀር ጎምቱ፣ ጎምቱ የህወሃት አመራሮች አልፎ ተርፎም ግልገል የብአዴን፣ የኦሆዴድና የደኢህዴን ተከታዮችን ብቻ ከጎኑ በማሰለፍ ቀና ብለው ሊያዩት የማይደፍሩትን ኃይለማርያም ደሳለኝን ምክትል ጠቅላይ ሚኒስተር በማድረግ፣ የመከላለያና የደህንነት ተዋረዶችን በመንደር ልጆች ጠርንፎ በመያዝ በዴሞክራሲ አቀንቃኞች ዘንድ በማያሰማ መልኩ ከመጋረጃው በስተጀርባ ሊተገብረው አቅዶ የነበረውን የስትራቴጂ ንድፍ ተግባራዊ ሳያደርግ በሜዳ ተበትኖ ቀረ፡፡ ለዚህም ይመስላል አንጋፋው የህወሃት ሰው ስብሀት ነጋ ‹‹መለስ እራሱን ብቻ ሳይሆን ህወሃትንም ጭምር ገድሎ ነው የሞተው›› ማለታቸው፡፡
በመሆኑም አክራሪ ብሔርተኛ የህወሃት ሰዎች በአንድ ሰው ትከሻ ላይ ተማምነው የጫኑት ጭነት በድንገትና ሳያስቡት መራገፉ አይቀሬ ሆነ፡፡ በነሱ አባባል የአፄ ዮሐንስ ‹‹ስህተት››ን ያለመድገም ፉከራ ፎረሸ ማለት ነው፡፡ ምናልባትም የኃያላኖቹ በተለይም የአሜሪካ ተፅዕኖ ይህንን መራራ ፍሬ ለጊዜውም ቢሆን ለመዋጥ ሳያስገድዳቸው የቀረ አይመስልም፡፡ ይህ ማለት ግን አሁንም ያንን እኩያ አላማ ለመተግበር የሚያስችላቸውን አቅም አሟጠዋል ማለት እንዳልሆነ እሙን ነው፡፡
ፅንፈኛ የህወሃት ሰዎች በትረ-ሙሴውን ዳግም ለማስመለስ የማይፈነቅሉት ድንጋይና የማይምሱት ጉድጓድ እንደማይኖር ማመኑ ከወዲሁ ለሁሉም የሚበጅ ይመስላል፡፡ የም/ጠቅላይ ሚኒስትሩን የተተኪነት ስልጣን በፓርላማ የማፅደቅ ስነ ስርዓትን ማስተላለፍ፣ በህወሃትና በኢ.ህ.አ.ዴ.ግ ዝግ ስብሰባዎች የነበሩትን የተካረሩ እሰጣ- ገባዎች እንዲሁም በቅርቡ በእሽቅድምድም የተከናወኑ የጄነራሎች ሹመት (ከሰላሳ ሰባቱ ሀያ ስድስቱ የትግራይ ተወላጆች መሆናቸውን ያጤኗል) ለታዘበ ህወሃቶች እስከ መጨረሻው ሰዓት መፍጨርጨራቸውን ያመለክታል፡፡ ይህንንም ሙከራ በተጠናከረና በተደራጀ መልኩ ለመተግበር እንደሚሞክሩ መገመቱ ብልህነት ይሆናል፡፡ ድምፅ አልባውን አብዮት የማስቀልበስና በትረ-ስልጣኑን ደግሞ የመጨበጥ አልያም አብዮቱ ልጆቿን እየበላች እሪ ብላ የምትጮህበት ደማቅ ቀያይ መስመሮች ከወዲሁ ሊፈተሹና ግንዛቤ ሊወሰድባቸው ይገባል፡፡
የመጀመሪያው መንገድ ላለፉት 21 አመታት በመላ ሀገሪቷ በሚገኙ ተቋማት ውስጥ በተዘረጋው የህ.ው.ሃ.ት መረብ በመታገዝ በአዲሱ አመራር ላይ ከፍተኛ ተፅዕኖ ማሳደር ይሆናል፡፡ ከጦሩና ደህንነቱ ማዋቅሮች በተጨማሪ እስከ ወረዳ/ ቀበሌ በሚገኙት መንግስት ተቋማትና የግሉ ዘርፎች ተሰግስገውና ቁልፍ የአመራር ቦታዎችን ተቆናጠው የሚገኙ የህወሃት አባላትን በተደራጀ መልኩ ማንቀሳቀስ ከተቻለ የነኃይለማርያም ካቢኔ በርቀት መቆጣጠሪያ መሳሪያ የማሽከርከሩ አቅም ብቻም ሳይሆን በቀጣዩ ጥቂት አመታት ውስጥ በድምፅ አልባው አብዮት በድንገቴ የተነጠቁት የፖለቲካ አመራር መዘውር መልሰው ሊጨብጡ አለመቻላቸውን በድፍረት መናገር ሊያዳግት ይችላል፡፡ እርግጥ ነው ይህ መስመር ‹‹ምጡቅ ስትራቴጂስቱ›› በህይወት ኖሮ ቢሆን ምነኛ በቀለላቸው ነበር፡፡ አሁን ያለው ሁኔታ ግን በተለያዩ ‹‹የባለስልጣን›› በሽታዎች ተደሽቀው የምናያቸው የትጥቅ ትግሉ አንጋፋ የህወሃት ሰዎችም ሆኑ በትግል ውስጥ እምብዛም ያልተሳተፉት ‹‹ወጣት ተተኪ ትውልዶች›› በረከት ስምኦን የሚመራውን የብ.አ.ዴ.ን፣ የኦ.ህ.ዴ.ድ፣ የደ.ኢ.ህ.ዴ.ንና አፍቃሪ ኤርትራ የሆኑ የህወሃት አባላት ጥምረት በቀላሉ ሊያስገብሩት እንደማይችሉ ባያጠራጥርም ቅሉ ይህ መስመር አይሞከሬ እንዳልሆነ መገመቱ አይከፋም፡፡
ሁለተኛው ቀይ መስመር ደግሞ ምናልባት የመጀመሪያው ሙከራ ካልተሳካ አልያም ከመጀመሪያው አካሄድ ጋር በማጣመር ህወሃቶች ሊያስኬዱት እንደሚችሉ ይገመታል፡፡ ይህም መንገድ አሁንም ላለፉት 21 አመታት የተሰራውን ሰራ መሰረት በማድረግ እንደ
ወገብ ቅማል በሀገሪቷ ወሳኝ ተቋማቶች ውስጥ ተለጥፈው የሚገኙት የህወሃት አገልጋዮች ትላልቅ የልማት ፕሮጀክቶችን የማጓተት አካሄድ ጀምሮ ህዝቡን በአገልግሎት አሰጣጥ፣ በኢኮኖሚ እንቅስቃሴዎች ብሎም በፀጥታ ጉዳዮች እንዲያማርርና ለዚህ ሁሉ ውድቀት የፈረደበት የሀይለማርያምና ካቢኔው ‹‹የአቅም ማነስ›› ፕሮፖጋንዳ በማስጮህ ህዝቡን ‹‹መለስ ማረን›› እስከማሰኘት ሊያስኬዱ ይችሉ ይሆናል፡፡
ሌላው ቀርቶ አቶ መለስ የአረብ አብዮትን መዛመት ማስቀየሻ የተጠቀሙበት የአባይ ግድብን ጨምሮ ለፖለቲካ ፍጆታነት ያልዘለሉትን ትላልቅ የባቡር መስመር ዝርጋታዎች፣ ራላቸው ለአቶ መለስ ዳገት የሆኑባቸውን የሱኳር ፋብሪካዎችን ጨምሮ የተለያዪ ኢንዱስትሪዎች ግንባታ ‹‹አለማሳካት›› የአዲሱ አመራር ‹‹የአቅም እጦት›› ማመላከቻ አድርገው እንደሚጠቀሙባቸው አያጠራጥርም፡፡
ይህ አካሄድ የድምፅ አልባውን አብዮት ከመቀልበሱም በላይ ላለፉት ሀያ አንድ አመታት ፊታቸው የተለመዱ የህወሃት ሰዎችን ‹‹መተካካቱን›› ወደጎን ትቶ ወደ በትረ-ሹመቱ ሊመልሳቸው ያስችል ያሆናል፡፡ ጉዳዩ ሀገርንና ህዝብን የማዳን ነውና ልምድ ያላቸው ይመለሱ ይሆናል አካሄዱ፡፡ አልፎ ተርፎም የበረከት ሚዲያን በቀላሉ መቆጣጠር ቢያዳግታቸውም በተገኘው አጋጣሚ ሰርስረው በመግባት በህዝቡ መካከል መጠራጠርንና መከፋፈልን በመጫር አዲሱ አመራር በድንገቴ ያገኙትን የህዝብ ይሁንታ የመከፋፈልና የማቀጨጭ ሙከራ ከማድረግ እንደማይቆጠቡ መገመቱ አይከፋም፡፡
ህወሃቶች በርቀት መቆጣጠሪያ መሳሪያው የኃይለማሪያምን አመራር ሊሾፍሩት ካልቻሉ ወይም ህዝቡ በአዲሱ አመራር እንዲማረር፣ እንዲጠራጠርና አመኔታ እንዲነፍገው አልያም አሁን በጀመሩት ‹‹የብሔር ተዋፅኦን ያማከለ የመተካከት ሂደት›› ክርክር ገፍተው ለውጤት ካልደረሱ ሶስተኛውን አማራጭ መስመር ሊይዙ ይችላሉ ተብሎ ይገመታል፡፡ ይህም መስመር መለስ ዜናዊ ብቻም ሳይሆን ትግል ጓዶቻቸው የነበሩት የሻዕቢያና የወያኔ ሰዎች እየተጠቀሙበት እዚህ ደረጃ ያደረሳቸው በቂ ተሞክሮና ልምድ ያካበቱበት የመጠፋፋት መስመር ነው፡፡
ከየትኛውም ተቋማት በበለጠ ትኩረት የተሰጠው ደህንነት መ/ቤትን በመጠቀም እምቢኝ አሻፈረኝ ብለው የትግሬ አፓርታይድ አገዛዝን ለማደናቀፍና ህወሃቶች የፖለቲካ መዘውሩን ዳግም ለመጨበጥ የሚያደርጉትን መፍጨርጨር ሊገታ ወይም ሊያሰናክል የሚሞክርን ግለሰብም ሆነ ቡድን በተለመዱት የሀገር ክህደት፣ ሙስናና በተለያዩ ክሶች በማዋከብ እንዲሁም ቀድሞ ደህንነቱ ለክፉ ቀን በሰበሰባቸው የባለስልጣናት የግልም ሆነ የቤተሰብ ሚስጥሮች በማሸማቀቅና በማስበርገግ ከአመራር አስፈንጥረው የማስወጣ አካሄድ ሊጠቀሙ ይችሉ ይሆናል፡፡ ከስልጣ ግፍተራውና ከቃሊቲው ሽኝት በዘለለ መልኩም ቁንጮ በረከትን ጨምሮ የሃይለማርያን ስብስቦች በአደጋም ሆነ የመለስን ሞት ባፋጠነው ‹‹ኢንፌክሽን›› ተጣድፈው አለመሞታቸው አልያም እንደ ኦ.ህ.ዴ.ዱ አለማየሁ አቶምሳ ከአልጋ አለመቆራኘታቸው ማን ያውቃል፡፡ ይህ ሁሉ ቀያይ መሰመሮች ወደታሰበው መንገድ ካላደረሱ ጦሩ ሌላ ደርግ የወታደራዊ መንግስት ግልበጣ ሙከራ አለማድረጋቸው ምን ዋስትና ይኖረናል፡፡
ይህንንስ የጨለማ ዘመን አታምጣው ብሎ መለመኑ ሳያስፈልግ አይቀርም፡፡ ወትሮስ ቢሆን ኢትዮጵያ እጆቿን ወደ እግዚአብሄር አይደል የምትዘረጋው?
የሆነው ሆኖ ቀጣዮቹን አመታት ለሀገሪቷና ለህዝቧ በፖለቲካውም ሆነ በኢኮኖሚው መስክ ጫና የሚፈጥርባቸው ሊሆኑ እንደሚችሉ ገምቶ መንቀሳቀሱ ተገቢ ይሆናል፡፡ ድምፅ አልባው አብዮት ተጀመረ እንጂ አልተቋጨም የተባለውም ለዚሁ ነው፡፡ ምንም እንኳን የህዝቡ ተለዋዋጭ ባህሪ በፖለቲካና ማህበራዊ ጥናት አጥኚዎች ጥልቅ ሙሁራዊ ዳሰሳ ማካሄድ ማስፈለጉ የግድ እያለ መምጣቱ ባይካድም አሁን የተከሰተው አልታሰቤ ለውጥ በበጎ አጋጣሚነቱ ለመጠቀም ህዝቡ ቁርጠኝነት መላበስና አንዳንድ ጋሬጣዎች በቀላሉ ጠልፈው እንዳይጥሉት መጠንቀቁ አይከፋም፡፡
አዲሱ አመራርም ሳይፈራና ሳይርበተበት የጓዶቹን ምክርና እገዛ ከኋላው በማስተካከል እንደ ቀድሞ መሪ ከህዝብ ተራርቀው ሳይሆን በመቀራረብ መስራቱ በማይጨበጠው ‹‹አባይን የደፈረ›› ጀግንነት ሳይሆን በሀገር ማዳንና ታሪክን በመቀየር ጀግንነቱን አስመዝግቦ ማለፍ ይጠበቅበታል፡፡ ባልተቻኮለና ባልተጓተተ ውሳኔዎች የሀገሪቷን ወሳኝ ተቋማት ቅርፅና ይዘት መከለሱ ከምንም በላይ ግድ የሚል ቀዳሚ እርምጃ እንደሆነ መቼስ አቶ በረከት አያጡትምና አካሄዱን ለአቶ ኃይለማርያም ሹክ ማለታቸው እንደማይቀር እውን ነው፡፡
ከፊታችን ባሉት በጣም ጥቂት አመታት ውስጥ አዳዲሶቹ አመራሮች የራሳቸው አቅምና ድፍረት በማጎልበት፣ የውጭ ግንኙነታቸውን ማጠናከር ይጠበቅባቸዋል፡፡ አቶ ኃይለማርያም በአጋጣሚ ያገኙትን የህዝብ ይሁንታ ምክንያታዊና ዘላቂ ይሆን ዘንድ የማንም መሳሪያ ሳይሆኑ በቆራጥነት የተገኘውን እድል መጠቀም የሚችሉበት ወሳኝና ታሪካዊ ምዕራፍ ላይ መሆናቸውን በአፅንኦት ሊገነዘቡት ይገባል፡፡
አቶ ኃይለማርያም የፖለቲካ ምህዳሩን የማስፋት እቅድ ሊነድፉ እንደሚገባቸው ሁሉ የፖለቲካ ተቃዋሚዎችም በተለይም በውጭ አለም የሚገኙት ለአዲሱ አመራር እድል እንዲሰጡ የግድ የሚል ሁኔታ ውስጥ ያለን ይመስላል፡፡ አዲሱ አመራር ትላልቅ የፖሊሲ ጉዳዮች ላይ አሁኑኑ ይደራደር ብሎ ጠርዝ ላይ ቆሞ መገፋፋቱ ብልህነት እንዳልሆነ ሁሉ፥ ለወደፊቱ በአንኳር ሀገራዊ ጉዳዪች ላይ ለመነጋገር መስማማቱና በየማጎሪያው ተወርውረው የሚገኙ የህሊና እስረኞችን የመፍታት ጅማሮ ለነገ የማይባል የህዝብ ወገንተኝነትን አመላካች ነው፡፡
ላለፉት 20 አመታት ከመሬት ላይ ተፈጥፍጠው የነበሩትን ሀገራዊ እሴቶቻችንን ዳግም የማነሳሳት ታሪካዊ ሀላፊነትን በቁርጠኝነት መወጣትን አሁንም ህዝቡ ከአዲሱ አመራር የሚጠብቀው እርምጃ መሆኑን ተገንዝቦ መንቀሳቀስ ግድ ይላል፡፡
በተዛማጅ ህወሃቶችም ከኢትዮጵያ ውጭ ሌላ ሀገር እንደሌላቸው አስረግጠው አምነው፣ የፖለቲካ ቁማራቸውን አቁመው፣ የእስከዛሬውን ይባርክ ብለው ከእንግዲህ በፍትሃዊ መንገድ ከሌላው ወገናቸው ጋር በእኩልነት ለመኖር ይወስኑ ዘንድ እግዚአብሔር ልቦና ይሰጥልን፡፡



