Message from Tesfaye GebreAb

ይድረስ ካንባቢዎቼ [pdf]
እኔ ደህና ነኝ!
እናንተስ እንዴት ሰነበታችሁ?

“የጋዜጠኛው ማስታወሻ” የመጀመሪያው እትም ተሸጦ አልቆአል። መፅሃፉን ለገዛችሁ ሁሉ ምስጋናዬ ይድረሳችሁ። ሁለተኛው እትምም ታትሞ ለስርጭት ዝግጁ ሆኖአል። ከመጪው ህዳር ወር ማብቂያ ጀምሮም በሁሉም ክፍለአለማትና ከተሞች ይሰራጫል። “የጋዜጠኛው ማስታወሻ” ሁለተኛ እትም የጀርባ ሽፋን ላይ የፕሮፌሰር ጌታቸው ሃይሌ፤ የተክለሚካኤል አበበ እና የነአምን ዘለቀ ቅንጫቢ አስተያየቶች ታትመውበታል። መፅሃፉን ለማከፋፈል የምትሹ ወደ [email protected] ደብዳቤ በመፃፍ ፍላጎታችሁን መግለፅ ትችላላችሁ።

“የደራሲው ማስታወሻ”ን ቃል በገባሁት መሰረት ፅፌ ጨርሻለሁ። 21 ምእራፋትና 406 ገፆች ላይ ተጠናቆአል። ይህ አዲሱ መፅሃፍ፤ “ቀዳሚው ውሃ ነበር!” የሚለውን ብሂል ያስታውሳል። ጥቂት የማረም ስራ እና ቀሪ ቴክኒካዊ ተግባራት ብቻ ነው የቀሩኝ። በመጪው የፈረንጆች አዲስ አመት ማግስት ለስርጭት ይበቃል ብዬ ተስፋ አድርጌያለሁ።

በመጨረሻ፤ ኢሜይል ለላካችሁልኝ ሁሉ ከልብ አመሰግናለሁ። ምላሽ ላልላኩላችሁ በጊዜ እጥረት ነውና ከይቅርታ ጋር የክብር ምስጋና ተቀበሉኝ። አብዛኞቻችሁ እንደተመኛችሁልኝ እንደ ከዋክብት ባልራቀ ጊዜ ውስጥ ተያይዘን ወደ ቢሾፍቱ እንገማሸራለን። የወንዛችንን ዘፈን እየዘፈንን ወደ ጣና፤ ወደ አባይ፤ ወደ አዳባይ፤ ወደ ጨንቻ፤ ወደ አኝዋክ፤ ወደ ሌቃ ዱለቻ፤ ወደ አይሳኢታ፤ ባገራችን ዋሽንት ታጅበን እንዋባለን። ይህ ህልምም ቅዠትም አይደለም። የአገዛዝ ስርአቱ የቆመበት መሰረት ውስጡ የተበላ ነው። ምሰሶው ቀፎውን ቀርቶአል። ጠጋ ብለው የልብ ትርታውን ሲያዳምጡት የጭንቀት ኡኡታው ጆሮ ይበጠርቃል። ዝርዝሩን “የደራሲው ማስታወሻ” ያወጋችሁዋል። በሰላም ያገናኘን።

ተስፋዬ ገብረአብ
[email protected]