‘ታላቁ ሩጫ’ ተላለፈ

 የሚሌኒየሙን በዓል በማስመልከት በጳጉሜ ወር ይደረጋል ተብሎ ሲጠበቅ የነበረው ታላቁ ሩጫ ተሰርዞ ለሕዳር ወር ተላለፈ፡፡ 

ታላቁ ሩጫ ከተጀመረበት ጊዜ አንስቶ በርካታ የአዲስ አበባ ነዋሪዎች በሩጫው ላይ ሢሳተፉ ይስተዋሉ ነበር፡፡ በተለይ በ1999 ዓ.ም ሕዳር ወር ላይ በተደረገው ሩጫ ‹‹የታሰሩት ይፈቱ›› በሚል መሪ መፈክር ተሳታፊው ተቃውሞውን ያሰማበት ሆኖ ነበር ያለፈው፡፡ 

እንደ ዝግጅቱ አስተባባሪዎች ገለጻ  ታላቁ ሩጫ መደረግ የነበረበት ልክ በዓመቱ ቢሆንም የሚሌኒየሙን በዐል ድምቀት ይሰጠዋል በሚል በጳጉሜ 4  መዘጋጀቱን ከወራት በፊት አዘጋጆቹ አስታውቀው ነበር፡፡ በዚህም መሰረት ከ30 ሺህ በላይ ተሳታፊዎችን መዝግበው መሮጫ ቲሸርት አድለዋል፡፡  ለአንድ ተሳታፊም 40 የኢትዮጵያ ብር አስከፍለዋል፡፡ ለሚመለከተው የመንግስት አካል አስታውቀዋል፡፡ 

የታላቁ ሩጫ አዘጋጅ አትሌት ኀይሌ ገ/ስላሴ በዛሬው እለት ለጋዜጠኞች እንደገለጸው እስከትላንት ድረስ  የሚያውቀው ታላቁ ሩጫ አለመሰረዙን ነው፡፡  ነገር ግን በትናንትናው ለት በቃል እንደተነገረው ከጸጥታ ጋር በተያያዘ በመስቀል አደባባይ ይዘጋጅ የነበረው ታላቁ ሩጫ መጀመሪያ ይደረግበት ወደነበረው ሕዳር ወር ይተላለፍ መባሉን ነው፡፡ 

አያይዞ እንደገለጸው ለዚህ ዝግጅት ከኢትዮጵያ ውጭ ያሉ በርካታ አትሌቶች መጋበዛቸውንና በርካታ ኢትዮጵያውያን አትሌቶች ይሳተፉ እንደነበር ነው፡፡ 

መንግስት ጸጥታውን ለመጠበቅ በሚል ሚሌኒየሙን በማስመልከት የሚደረጉ ህዝብን ሊያሳትፉ ይችላሉ ተብለው የሚገመቱ ዝግጅቶችን (እነ አልሙዲ ከሚያዘጋጁት በስተቀር) በሙሉ እንዲሰረዝ አድርጉዋል፡፡  

አንዳንድ አስተያየት ሰጪዎች ስልጣን ላይ ያለ መንግስት የጸጥታ ችግር ካለበት ይቆጣጠራል እንጂ በፍርሃት አይሰርዝም ሲሉ ይናገራሉ፡፡  

ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ከተጀመረ አራት አመታት ያስቆጠረ ሲሆን መነሻውና መድረሻው መስቀል አደባባይ የሆነ 10 ኪ.ሜ ሩጫ ነው፡፡ በዚህ ሩጫ እስከ 30 ሺህ የሚገመት ሰው የሚሳተፍ ሲሆን ባለፈው በተደረገው ሩጫ ሕዝቡ የቅንጅት አመራሮች እንዲፈቱ የጠየቀበት፣ ለኢኃዲግ ያለውን ጥላቻ ያሳየበት ነበር፡፡