የምርጫ 97 ጥቃት ሰለባዎች ሊረዱ ነው

ምርጫ 97ትን ተከትሎ በተፈጠረው ቀውስ የቤተሰብ አባላቸውን ላጡ ዜጎች ማቋቋሚያ የሚሆን ገንዘብ በማሰባሰብ የጥቃቱ ሰለባ የነበሩት ዜጎች ተጠቃሚ የሚሆኑበትን መንገድ በማመቻቸት ላይ መሆናቸውን አንድ የቅንጅት ለአንድነትና ለዴሞክራሲ ፓርቲ የአመራር አባል ለዜና አገልግሎቱ ገለጹ፡፡

አንዳንድ ቤተሰቦች የግፉ ሰለባ በመሆን የበለጠ ተጎጂዎች ነበሩ ያሉት እኒሁ የአመራር አባል ህዝቡ በዴሞክራሲያዊ መንገድ አመራሩን በመምረጥ ለነጻነት ላሳየው ቁርጠኝነት ምላሹ ኢ-ሰብአዊ ጭፍጨፋ ቢሆንም የሰማእቱን ዉለታ ለመዘከር ፓርቲያቸው ሰፊ እቅድ ማዘጋጀቱን ገልጸዋል፡፡ የቅንጅት ይህን እቅዱን ተግባራዊ ለማድረግ ትግሉን በተለያዩ መንገዶች ሲያግዙ ከነበሩ በውጭ የሚገኙ ኢትዮጵያውያን ጋር እንደሚሰራ ጠቁመዋል፡፡

የቅንጅት ለአንድነትና ለዴሞክራሲ ፓርቲን ህልውና ለማጥፋት ከፍተኛ ርብርብ እየተደረገ ያለበት ፈታኝ ወቅት ቢሆንም ትግሉን የሚያጎለብቱ በርካታ ድርጅታዊ ስራዎች እየተሰሩ መሆኑን የገለጹት እኒህ አመራር እስረኞችን ከማስፈታቱ ስራ ጎን ለጎን የግፍ ጥቃቱ ሰለባ የሆኑ ቤተሰቦችን የማደራጀቱ ተግባር ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ቃል ገብተዋል፡፡