የዛላ ወረዳ የቅንጅት አስተባባሪ ታሰሩ

በጋሞጎፋ ዞን ዛላ ወረዳ የቅንጅት አስተባባሪ የሆኑት አቶ አየለ አርብ እለት ከሰአት በኋላ በወያኔ ካድሬዎች ከስራ ቦታቸው ታፍነው ከተወሰዱ በኋላ እስካሁን በእስር ላይ እንደሚገኙ ምንጮቻችን ገለጹ፡፡

የቅንጅት የስራ አስፈጻሚ ቡድን በደቡብ ክልል ደጋፊዎቹንና አባላቱን አነጋግሮ ከተመለሰ በኋላ በደጋፊዎቹና በአስተባባሪዎቹ ላይ ከፍተኛ የማንገላታትና ተደጋጋሚ እስሮች ያጋጠሙ ሲሆን የዛላ ወረዳ አስተባባሪ የሆኑት አቶ አየለ ያለምንም ጥፋት ከስራ ቦታቸው በፖሊች አባላት ታፍነው መወሰዳቸው የወረዳዋን ነዋሪ ቁጣ ቀስቅሷል፡፡የዛላ ወረዳ ነዋሪ ሆኑ አንድ ግለሰብ በስልክ በሰጡን አስተያየት የወረዳዋ ህዝብ ለዘመናት የተፈራረቁ ገዢዎች የግፍ በትራቸውን ሲያሳርፉባት ኖረዋል በማለት በአስተባባሪው ላይ የተፈጸመው እስር ሆን ተብሎ ህዝቡን ለማሳቀቅ የተወሰደ እርምጃ ነው ብለዋል፡፡

በአባሉ ላይ የተወሰደውን እርምጃ አስመልክቶ ምን የህግ እንቅስቃሴ ጀምራችኋል በማለት ለቅንጅቱ አመራሮች ጥያቄ ያቀረብንላቸው ሲሆን ጉዳዩን በቅርብ እየተካታተሉት መሆኑን ገልጸው እንዲህ አይነት ግብታዊ እርምጃዎች የስርአቱን አምባገነናዊነት ከማረጋገጥ የዘለለ ትግሉን ወደኋላ የሚስብበት ምንም እድል አይኖርም በማለት ገልጸዋል፡፡