ይፋ የሆነው የወያኔ እጩዎች ዝርዝር ውዝግብ አስነሳ

በቀጣዩ ሚያዝያ ለአከባቢና ማሟያ ምርጫ በወያኔ ካድሬዎች በሚመለመሉበት ወቅት ፈቃደኛ ያለመሆናቸውን ገልጸው የነበሩ አንዳንድ የአዲስ አበባ ነዋሪዎች ይፋ በተደረገው የእጩዎች ዝርዝር ውስጥ ስማቸው በመገኘቱ በምርጫ ጣቢያዎች ውዝግብ በመነሳት ላይ ነው፡፡

ለቀጣዩ ምርጫ አራት ሚሊዮን እጩዎችን ያቀረበው ወያኔ ባልታሰበ መንገድ የተቀሰቀሰውን የቅሬታ ውዝግብ ለማብረድ በምርጫ አስፈጻሚዎች አማካይነት የማረጋጋት ስራ እየሰራ ይገኛል፡፡ እጩዎች በሚመለመሉበት ወቅት ምንም አይነት የፖለቲካ ተሳትፎ የሌላቸውን ግለሰቦች ሳይቀር በወያኔ እጩነት ለማጋበስ አሳፋሪ እንቅስቃሴ ሲካሄድ የነበረ ሲሆን በወቅቱ ‹‹ተቃዋሚዎች አይደለንም፤ ሆኖም በፖለቲካዊ ጉዳዮች በተለይም ፓርቲ ወክሎ እጩ ሆኖ ለመቅረብ ልምዱም ዝግጅቱም የለንም፡፡›› ያሉ ግለሰቦችን በዝምታ ካለፉ በኋላ የትም አይደርሱም በሚል እሳቤ ዝርዝራቸው ይፋ በመደረጉ ከምርጫ ጣቢያዎቹ ማስታወቂያ ሰሌዳዎች ላይ በአስቸኳይ ስማቸው እንዲሰረዝ ሲሟገቱ የተመለከቱት ዘጋቢዎቻችን ሪፖርት ያመለክታል፡፡

የምርጫ ጣቢያ ሃላፊዎቹ ውዝግቡ እንዳይባባስ በሚል የተፈጠረ ችግር ካለ በአስቸኳይ ይስተካከላል ከማለት አልፈው ስማችን ያላግባብ ይፋ ሆኗል የሚሉትን ቅሬታ አቅራቢዎች ስም ከሰሌዳው ላይ የመሰረዝ አስገራሚ ድራማ ሲሰሩ ተስተውሏል፡፡ ተመሳሳይ በደል የደረሰባቸው አንድ በጡረታ ላይ የሚገኙ ግለሰብ እንደገለጹልን በግድ እጩ የተደረጉት ሁሉ ይውጡ ቢባል ጉዱ ይታይ ነበር፤ ይሁንና በካድሬዎች ማስፈራርያ እየተሰጣቸው በዝምታ ሁኔታውን እየተከታተሉ ነው በማለት የሁኔታውን አስከፊነት አስቀምጠውታል፡፡