የወያኔ እጩዎች ህገ-መንግስታዊ መብታችን ተጥሷል እያሉ ነው

በቀጣዩ ሚያዝያ ለሚካሄደው የአከባቢና የማሟያ ምርጫ ያለፈቃዳቸው በወያኔ መልማዮች ለምርጫው የታጩ ዜጎች ህገ መንግስታዊ መብትን በመጠቀም ሽፋን ያለፍላጎታቸው በመመዝገብ መብታቸው እየተጣሰ መሆኑን በመግለጽ ላይ ይገኛሉ፡፡

በሰሜን ሸዋ ዞን ኦሮሚያ ክልል አሌልቱ ወረዳ ኦህዴድን በመወከል ከቀረቡት 300 የቀበሌ ም/ቤት እጩዎች ሁለት ሶስተኛ ያህሉ ኮታ እንዲሞላ ብቻ ያለፈቃዳቸው የተመዘገቡ መሆናቸውን ለዜና አገልግሎቱ ቀረቤታ ያላቸው ምንጮች ገልጸዋል፡፡ ቁጥራቸው 80 የሚሆን የግዳጅ እቹዎች በትናንትናው እለት የሚቀዋ ከተማ የምርጫ ጽ/ቤት ጉዳዩን እንዲመረምረው በሚል ፊርማ አሰባስበው በወኪሎቻቸው በኩል አቤቱታ ለማቅረብ ቢሞክሩም ወኪሎቹ ማስፈራርያ የደረሰባቸው ሲሆን ‹‹የቅንጅት አሽከሮች›› የሚል ዘለፋ እንደደረሰባቸው ምንጮቻችን ገልጸዋል፡፡

ምርጫው ከመካሄዱ አስቀድሞ ወያኔ በአዲስ አበባ የመከላከያ ሚኒስትሩን አቶ ኩማ ደመቅሳን ለከንቲባነት እንዲሁም ሌሎች ሹማምንቱን በተመሳሳይ ሃላፊነት ላይ ለማስቀመጥ ዝግጅቱን ማጠናቀቁ የአደባባ ምስጢር መሆኑ ይታወቃል፡፡