አማራንና አማርኛን ማጥፋት የህወሃት ፕሮግራም ነው

By Goolgule.com

April 15, 20013amhara

 

 

አማርኛ ተናጋሪዎችን የማመናመን፣ የማደህየት፣ የማራቆትና ክልላቸውን እያሳነሱ የማጥፋት እቅድ በህወሃት መርሃግብር ውስጥ የተካተተ ዋና ተግባር እንደሆነ ተገለጸ። አማርኛ ቋንቋንም ማሽመድመድ የዚሁ እቅድ አካል መሆኑ ተዘግቧል።

አቶ ገ/መድህን አርአያ ከኢሳት ሬዲዮ ጋር ባካሄዱት ቃለ ምልልስ በህወሃት ፕሮግራም ገጽ 18 አካባቢ “አማራ የትግራይና የኤርትራ ህዝብ ጠላት እንደሆነ ተመልክቷል” ብለዋል፡፡ አያይዘውም አማራ ማጥፋት የቅስቀሳው ዋና መሳሪያ ቢሆንም የትግራይ ህዝብ አልተቀበለም ብለዋል። ቅስቀሳውን አንቀበልም ያሉ “የትግራይ ሸዋ” ተብለው መገደላቸውን ይፋ አድርገዋል።

በተለይ የድርጊቱ ዋና አስተባባሪ በማለት የጠቀሷቸው አቶ መለስ ዜናዊ፣ አቶ ስብሃት፣ አቶ ስዩም መስፍን፣ አቶ አባይ ጸሐዬን የጠቀሱት አቶ ገ/መድህን፣ በ1972 በሰሜን ጎንደር የዘር ማጥፋት ወንጀል መፈጸሙን አጋልጠዋል። በወቅቱ የተካሄደው ጭፍጨፋ ከፍተኛ የዘር ማጥፋት ወንጀል እንደሆነም አመልክተዋል። “በሰላም እጃቸውን የሚሰጡ ወታደሮች እንኳ አማርኛ የሚናገሩ ከሆነ ይረሸኑ ነበር” ሲሉ እነ መለስ ያለቸውን በዘር ላይ የተመሰረተ ቆሻሻ አመለካከት አጋልጠዋል።

“ኢትዮጵያ የምትበተነው አማራ ሲጠፋ ነው” በሚለው የነመለስ ሃሳብ መተግበር የጀመረው ህወሃት አዲስ አበባ ከገባበት ጊዜ ጀምሮ መሆኑንን ያወሱት አቶ ገ/መድህን፣ ህወሃት ያሰማራቸው ከ350ሺህ በላይ ካድሬዎች ቁጥራቸው በውል የማይታወቅ አማራዎች በተለያዩ ምክንያቶች እንዲጨፈጨፉ ማድረጋቸውን አመልክተዋል።

ብአዴንን “አማራን ለማጥፋት የተፈጠረ፣ ጸረ አማራ ድርጀት” ሲሉ የሰየሙት አቶ ገ/መድህን፣ አመራሮቹ የኤርትራና የትግራይ ተወላጆች መሆናቸውን በርግጠኛነት ተናግረዋል። የትግራይ ህዝብ የተወከለው “በባንዳ ልጆችና የኤርትራ ተወላጆች ነው” ሲሉም ህዝቡ አደጋ ላይ እንደሚገኝ ጠቁመዋል። የክልሉ ፕሬዚዳንት አቶ አባይ ወልዱን “የባሻ ወልዱ ልጅ ነው” በማለት የትግራይ ህዝብ በባንዳ ኤርትራዊ ልጅ እንደሚመራ ያመለከቱት አቶ ገ/መድህን፤ ብርሀነ ገብረክርስቶስ፣ ቴድሮስ ሃጎስ፣ ቴድሮስ አድሃኖም፣ በማለት በመዘርዘር የባንዳ ልጆች መሆናቸውን ይፋ አድርገዋል።

“አማራው የሚኖርበትን መሬት በመውሰድ መሬቱን ያጠቡበታል፣ ከሌላው ክልል በማባረር የሚኖርበትን ክልል ያጠቡታል” ያሉት አቶ ገ/መድህን፣ ይህ የሚደረገው ከመጀመሪያው እንዲጠፋ የተወሰነበትን ህዝብ አጥብቦ በማፈን በችግር ለመግረፍና ለመቆጣጠር ተብሎ እንደሆነ ገልጸዋል።

ዘር የማጥራት የህወሃት የቀደመ ድርጅታዊ መዋቅር እንደሆነ በማመልከት መለስን የጠቀሱት አቶ ገ/መድህን፣ “አማራውን ዝም ካልነው አያስቀምጠንም” የሚለው የመለስ መፈክር አካል የሆነው የቤኒሻንጉል ክልል ርምጃ የህወሃት ቤት ስራ እንደሆነ አረጋግጠዋል። አማራውን ፋታ ማሳጣት፣ ማንገላታት፣ ስነልቦናውን መግፈፍ ህወሃት በፕሮግራም ደረጃ የያዘው እቅድ ስለሆነ ወደፊትም እንደሚቀጥል አቶ ገ/መድህን ተናግረዋል።

“ሞት መፍራት አያስፈልግም። የተቀደሰ ሞት መሞት ክብር ነው” ሲሉ በቃለ ምልልሳቸው መጨረሻ የተናገሩት የቀድሞው የህወሃት የፋይናንስ ሃላፊ ህዝቡ ተባብሮ ህወሃትን ማስወገድ ካልቻለ ማፈናቀሉና መሰደዱ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አስጠንቅቀዋል።