የሩዋንዳ የዘር ማጥፋት ረዥም ጥቁር ጥላዉን በ(መካከለኛው) አፍሪካ ጥሎአል

ከፕሮፌሰር አለማየሁ ገብረማርያም

ትርጉም በነጻነት ለሀገሬ

 

1994 የሩዋንዳ የጭፍጨፋ እና የእልቂት ጸጸት 2014 የመካከለኛው አፍሪካ ሪፐብሊክ ሰማይ ላይ እያንዣበበ ነው!

ባለፈው ሳምንት የሩዋንዳ ህዝብ እርስ በእርስ የተራረደበትን 20ኛውን ዓመት የሩዋንዳ የዘር ፍጅት መጥፎ ገጽታ ለማስታወስ የሀዘን ሳምንት አውጆ ድርጊቱን በመራር ሀዘን ዘክሮታል፡፡ እ.ኤ.አ በኤፕሪል 6/1994 በመንግስት የስልጣን እርከን ላይ የነበሩ አክራሪ የሁቱ ጎሳ አመራሮች፣ የእነርሱ የፖለቲካ አመለካከት ደጋፊዎች እና የተደራጁ ታጣቂ ሚሊሻዎች  ስልታዊ የግድያ ወንጀሎችን በማቀናጀት እና በግንባር ቀደምትነት በመምራት 100 ተከታታይ ቀናት የወሰደ እልቂትን በማደራጀት ከ800 ሺ በላይ ሰላማዊ ህዝቦች በተለይም የቱትሲ እና አክራሪ ያልሆኑ የሁቱ ጎሳ አባላትን ፈጅተዋል፡፡ እ.ኤ.አ በ1994 ሩዋንዳ 5.5 ሚሊዮን ህዝብ የነበራት ሲሆን ከዚህ ውስጥ 14 በመቶ የሚሆኑት የቱትሲ ጎሳ አባላት ነበሩ፡፡ በአሁኑ ጊዜ ሩዋንዳ 11.5 ሚሊዮን ህዝብ ያላት ሲሆን ከዚህ ውስጥ የቱትሲ ጎሳ አባላት ህዝብ ብዛት ከ10 በመቶ ያነሰ ነው፡፡

ባለፈው ሳምንት የመካከለኛው አፍሪካ ሬፐብሊክ (መአሬ) “የሩዋንዳ አምሳያ” የሆነ ለመናገር የሚዘገንን አስፈሪ ቅዠታቸውን መጋፈጥ ቀጥለዋል፡፡ የተባበሩት መንግስታት ዋና ጸሀፊ ባንኪሙን በመአሬ እየተካሄደ ባለው “የዘር-ኃይማኖታዊ የማጽዳት” ዕኩይ ድርጊት ላይ ልባቸው በሀዘን የተሰበረ መሆኑን በመግለጽ ለዓለም አቀፉ ማህበረሰብ የሚከተለውን መልዕክት አስተላልፈዋል፣ “የዓለም አቀፉ ማህበረሰብ ከ20 ዓመታት በፊት በሩዋንዳ ህዝብ ላይ የደረሰውን ዕልቂት በግዴለሽነት ከዳር ቆሞ ሲመለከት ነበር… እናም አሁን ደግሞ ለመካከለኛው አፍሪካ ሬፐብሊክ ህዝቦች ህይወት ደህንነት በቂ የሆነ ምንም ነገር ባለማድረግ በከፍተኛ አደጋ ውስጥ ወድቀን እንገኛለን… ለአንዳንድ ሰዎች ይህ ጉዳይ የተረሳ ታላቅ አደጋ ነው፡፡ እኔ እዚህ ያለሁት የዓለም ህዝብ ጉዳዩን እንዳይረሳው ለማሳሰብ እና ለማገዝ ነው… እናም በአሁኑ ጊዜ ለመካከለኛው አፍሪካ ሬፐብሊክ ደህንነት በቂ የሆኑ ተግባራትን ባለማከናወን በትልቅ አደጋ ውስጥ ወድቀን እንገኛለን…በዚህች አገር የዘፈቀደ የጅምላ ግድያ ወንጀሎች በመፈጸም ላይ ይገኛሉ፡፡ የዘር-ኃይማኖት የማጽዳት ዘመቻ እውን በመሆን ላይ ይገኛል፡፡ አናሳዎቹ የሙስሊም ማህበረሰብ አባላት አገራቸውን ጥለው በመሰደድ ላይ ናቸው፡፡ እንዲህ ያለ ድርጊት ‘በፍጹም እንደገና አይደረግም’ እያልን እራሳችንን እያታለልን መቀጠል የለብንም፡፡ ይህንን አዘናጊ አባባል ብዙ ጊዜ ደግመን ደጋግመን ብለነዋል፡፡ ኃላፊነት በተሞላበት መልኩ ተገቢውን እርምጃ መውሰድ እና በአሁኑ ጊዜ በከፍተኛ ደረጃ እየተፈጸመ ያለውን የጅምላ ፍጅት በአስቸኳይ ማስቆም ይኖርብናል…“ በማለት ሀሳባቸውን አጠቃለዋል፡፡

ከ20 ዓመታት በፊት የሁቱ የዘር ግንድ የሆኑት የሩዋንዳው ፕሬዚዳንት ጁቬናል ሀብያሪማና ተሳፍረውበት የነበረው አውሮፕላን በተተኮሰ መሳሪያ ከተመታ በኋላ ህይወታቸው ማለፉ ይታወሳል፡፡ እ.ኤ.አ በ1993 የሁቱ እና የቱትሲ ጎሳ አባላት በጋራ የጥምር መንግስት ለማቋቋም የተጀመረውን ጥረት ወደ ጎን በማለት እና አክራሪ የሁቱ ጎሳ አባላት ቀደም ሲል በሁለቱ የጎሳ አባላት መካከል ተደርጎ የነበረውን የተኩስ አቁም ስምምነት በመጣስ የቱትሲ ጎሳ አባላትን እነርሱ በረሮዎች እያሉ በሚጠሯቸው የቱትሲ የጎሳ አባላት ላይ እልቂት በመፈጸም “የመጨረሻውን ጦርነት” ወደ ተግባር አሸጋገሩት፡፡ አካዙ (የሁቱ ጎሳ አባላት የፖለቲካ አመራሮች እና ልሂቃን) እየተባሉ የሚጠሩት የጅምላ ዘር ፍጅቱ ከመጀመሩ ቢያንስ ከአንድ ዓመት በፊት የቱትሲ ጎሳ አባላት የሆኑትን ሩዋንዳውያን/ት ዜጎችን ለመፍጀት የታሰበበት ዕቅድ ነደፉ፡፡ የእራሳቸውን ሬዲዮ ጣቢያ (ኮሊንስ) አቋቋሙ፡፡ እ.ኤ.አ በኤፕሪል 1994 የዘር ማጥፋት ፍጅቱ በተጀመረበት ወቅት እነዚህ የሁቱ የፖለቲካ አመራሮች ሬዲዮ ጣቢያቸውን ነፍሰ ገዳዮችን ለማደፋፈር እና ለማበረታታት ይጠቀሙበት ነበር፡፡ ግድያ እንዲፈጸምባቸው ያዘጋጇቸውን የቱትሲ ጎሳ አባላት ስም ዝርዝር የሚያነቡበት እና እነዚያን ዘግናኝ የዘር ፍጅት ወንጀሎች እንዲፈጽሙ ለሚታዘዙ ገዳይ ሚሊሻዎች (ኢንተርሀሞይ እና ኢምፑዛሙጋምቢ) የትዕዛዝ መልዕክቶች የሚተላለፉበት ነበር፡፡ ሁቱዎቹ በተደጋጋሚ በሬዲዮ ጣቢያው እንዲህ የሚል መልዕክት ያስተላልፉበት ነበር፣ “በእውነት ሁሉም የቱትሲ ጎሳ አባላት ከምድረ ገጽ መጥፋት አለባቸው፣ ቱትሲዎች ከዚህች አገር መጥፋት አለባቸው… ቱትሲዎችን እያነጣጠረ ለሚመታው መሳሪያ ምስጋና ይግባውና ቱትሲዎች ቀስ በቀስ በመጥፋት ላይ መገኘታቸው ብቻ አይደለም ዋናው ጉዳይ ሆኖም ግን እንደ አይጥ እየታደኑ መገደላቸው ጭምር እንጅ፡፡” እ.ኤ.አ በ1994 ከሩዋንዳ ከተማ ኪጋሊ በ30 ማይል ርቀት ላይ ከምትገኘው እና በሩዋንዳ ታላቅ ከተማ ከሆነችው ኒያማታ በምትባለው ከተማ የሚኖሩ 120 ሺ የሩዋንዳ ዜጎቸ ነበሩ፡፡ በአንድ ወር እና በአንድ ወር ከግማሽ ጊዜ ውስጥ በዚህች ከተማ ውስጥ 50 ሺ ብቻ ሰዎች ቀሩ፡፡ ከስድስት ቱትሲዎች መካከል አምስቱ ይገደሉ ነበር፡፡”

በአሁኑ ጊዜ የመካከለኛው አፍሪካ ሬፐብሊክ (መአሬ) በኃማኖት ጽንፈኝነት፣ በጅምላ ጥላቻ እና በእርስ በእርስ ጦርነት ማጥ ውስጥ ተዘፍቃ ተበታትና ትገኛለች፡፡ እ.ኤ.አ በ2013 ሰለቃ ሚሊሻ (እ.ኤ.አ በማርች 2013 የመአሬን መንግስት በኃይል ያስወገዱት የአማጽያን ህብረት ቡድኖች) “በአገሪቱ ሰሜናዊ ምስራቅ እና በመላ አገሪቷ የጭካኔ ግድያዎችን ማድረግ ጀመሩ፣ እናም የአገሪቱን ዋና ከተማ ባንጉይን በመቆጣጠር የአገሪቱን ፕሬዚዳንት ፍራንኮይስ ቦዚዝን ከስልጣን አባረሩ፡፡ በቀጣዮቹ አስር ወራት የሰለቃ ኃይሎች ለቁጥር የሚያታክቱ ሰላማዊ ህዝቦችን ፈጁ፣ ብዙ መንደሮችን በእሳት አጋዩ እንዲሁም በሺዎች የሚቆጠሩ ቤቶችን ዘረፉ፡፡ “ከስልጣን የተወገዱትን ፕሬዚዳንት ቦዚዝን ጨምሮ 90 በመቶ የሚሆነው የመካከለኛው አፍሪካ ሬፐብሊክ ህዝብ የክርስትና እምነት ተከታይ ቢሆንም ቅሉ አብዛኞቹ የሰለቃ ኃይሎች እና መሪያቸው ሚሸል ጆቶዲያ የእስልምና ኃይማኖት እምነት ተከታዮች ናቸው፡፡ እንደ አምነስቲ ኢንተርናሽናል ዘገባ ከሆነ የሰለቃ አማጽያን የበቀል ጥላቻ ባላቸው የክርስትና እምነት ተከታይ በሆኑት እና ምንም ዓይነት የጦር መሳሪያ ለምሳሌም ያህል ጎራዴ ባልታጠቁት እንዲሁም ባልተጠናከረ መልክ በተደራጁት በሳንጎ በሚኖሩት ጸረ ባልካ ተዋጊዎች ላይ ተኩስ በመክፈት ፈጣን የሆነ የማጥቃት እርምጃ ወሰዱባቸው፡፡ እ.ኡ.አ በ2013 የመጀመሪያዎቹ አራት ወራት ውስጥ የጸረ ባልካ ተዋጊ ኃይሎች በሙስሊሙ ማህበረሰብ አባላት ላይ በተለይም በመካከለኛው አፍሪካ ሬፐብሊክ ሰሜናዊ ምስራቅ በሚኖሩት ዜጎች ላይ ዘግናኝ የሆነ የጥቃት እርምጃ ወስደውባቸዋል፡፡ ጥቃቱ በተጠናከረ መልኩ የቀጠለ ሲሆን በአሁኑ ጊዜ የዓለም አቀፉ ማህበረሰብ የሰላም አስከባሪ ኃይል በምዕራብ የመካከለኛው አፍሪካ ሬፐብሊክ የሚኖሩ የሲቪል የሙስሊም ማህበረሰብ አባላት ላይ እየተካሄደ ያለውን የዘር ማጽዳት ዘመቻ ማስቆም አልቻለም፡፡ ከሩዋንዳ ዋና ከተማ ከባንጉይ በ150 ማይል ርቀት ላይ በምትገኘው ያሎኬ በምትባል ከተማ ከአንድ ዓመት በፊት ወደ 30 ሺ የሚገመቱ የሙስሊም ማህበረሰብ አባላት በስምንት መስጊዶች አማካይነት እምነታቸውን እያራመዱ በሰላም እና በፍቅር ይኖሩ ነበር፡፡ ሆኖም ግን እንደ ሂዩማን ራይትስ ዎች እማኝነት ከሆነ በአሁኑ ጊዜ ከ500 ያነሱ የሙስሊም ማህበረሰብ አባላት እና አንድ መስጊድ ብቻ ቀርተዋል፡፡

ባለፈው ዓመት የዓለም አቀፍ የሰብአዊ መብት ተሟጋች ድርጅቶች በመካከለኛው አፍሪካ ሬፑብሊክ እየተካሄደ ያለውን የዘር-ኃይማኖት የማጽዳት አደገኛ ዘመቻ በማስመልከት የመጀመሪያ የማስጠንቀቂያ ደዎል አሰምተው ነበር፡፡ እ.ኤ.አ በ2013 አምነስቲ ኢንተርናሽናል በመካከለኛው አፍሪካ ሬፐብሊክ በመካሄድ ላይ ያለው “የሰብአዊ መብት ቀውስ ከቁጥጥር ውጭ መሆኑን የሚገልጽ ሪፖርት በማውጣት ማስጠንቀቂያ ሰጥቶ” ነበር፡፡ የኃይል እርምጃው እና እልቂቱ እየጨመረ በመጣ ጊዜ ብዙ ሺ የዓለም አቀፉ ማህበረሰብ የሰላም አስከባሪ ኃይሎች (2 ሺ የፈረንሳይ ወታደሮች እና ወደ 6 ሺ የሚጠጉ የአፍሪካ ህብረት ወታደሮች) ወደ መካከለኛው አፍሪካ ሬፐብሊክ ተልከዋል፡፡ ባለፈው ሳምንት የተባበሩት መንግስታት 12 ሺ የሰላም አስከባሪ ኃይል እንዲሰማራ ትዕዛዝ አስተላልፎ ነበር፡፡ ሆኖም ግን ተመደበ የተባለው የሰላም አስከባሪ ኃይል እ.ኤ.አ እስከ ሴፕቴምበር 2014 ድረስ ባለው ጊዜ ውስጥ በቦታው አልደረሰም፡፡ ሂዩማን ራይትስ ዎች የተባለው ዓለም አቀፍ የሰብአዊ መብት ተሟጋች ድርጅት “በመካከለኛው አፍሪካ ሬፐብሊክ ላይ ገደቡን ባለፈ መልኩ እየተካሄደ ያለው የኃይል እርምጃ ሁነኛ ገደብ ካልተበጀለት በስተቀር በጠቅላላው በአገሪቱ ውስጥ የሚኖሩት ማህበረሰቦች በሙሉ አገሪቱን ጥለው ለመሰደድ ይገደዳሉ” የሚል ጠንካራ ማስጠንቀቂያ በመስጠት የጉዳዩን አሳሳቢነት በውል አመላክቷል፡፡ በዚህ የሰው ልጅ እልቂት የአካሄድ ፍጥነት መጠን ከተሰላ እና የዘር ማጽዳት የኃይል እርምጃ ዘመቻው ዒላማ በዚሁ ፍጥነት የሚቀጥል ከሆነ በአብዛኛው የመካከለኛው አፍሪካ ሬፐብሊክ ምንም ዓይነት የሙስሊም ማህበረሰብ አባላት የሚባል ነገር ሊገኝ አይችልም፡፡” በማለት ስጋታቸውን ለዓለም አቀፉ ማህበረሰብ አሳውቀዋል፡፡

የሩዋንዳን የ1994 እና የመካከለኛው አፍሪካ ሬፐብሊክ የ2014 ሁኔታ በጎንዮሽ በንጽጽር ሲታይ አስደንጋጭ ሁኔታ ነው፡፡ እ.ኤ.አ የ1994 ሩዋንዳን ሁኔታ ስንመለከት የአፍሪካ ህብረት እና የዓለም አቀፉ ማህበረሰብ ዩናይትድ ስቴትስን እና የተባበሩት መንግስታትን ጨምሮ ከቁጥጥር ውጭ ወጥቶ ለነበረው የዘር ማጽዳት እልቂት እና ፍጅት ጆሮ ዳባ ልበስ የሚል ምላሽ ነበር የሰጡት፡፡ እ.ኤ.አ የ2014 የመካከለኛው አፍሪካ ሬፐብሊክ ሁኔታ ሲገመገም ደግሞ “በዘር-ኃይማኖት ማጽዳት” ዕኩይ ምግባር ምክንያት በ10 ሺዎች የሚቆጠሩ ሰላማዊ ዜጎች ሲጨፈጨፉ እና በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩት ደግሞ ከቀያቸው ሲፈናቀሉ ዓለም አቀፉ ማህበረሰብ የይስሙላ የሰላም አስከባሪ ኃይል በመመደብ የታዕይታ ስራ ለማሳየት ከመሞከር ባለፈ የንጹኃን ዘጎችን ህይወት ለመታደግ የሚያስችል ተጨባጭነት ያለው ስራ ሲሰራ አልታየም፡፡ ለድፍን ሙሉ ዓመት በመካለኛው አፍሪካ ሬፐብሊክ በግልጽ ሊታይ የሚችል ጥላቻ እና አደጋውንም መከላከል የሚያስችል ዕድል የነበረ ቢሆንም የአፍሪካ ህብረት እና የዓለም አቀፉ ማህበረሰብ አጋጣሚውን በበጎ መልኩ ሳይጠቀምበት ባክኖ ቀርቷል፡፡ አምነስቲ ኢንተርናሽናል እንዲህ የሚል ማሳሰቢያ ሰጥቷል፣ “ለ10 ወራት በስልጣን መንበር ላይ በመቆየት  ለደረሰው ዕልቂት፣ ከህግ አግባብ ውጭ ለተፈጸሙ ግድያዎች፣ ለአስገድዶ መድፈር፣ ማሰቃየት እና ዝርፊያ እንዲሁም በገፍ ለክርስቲያን መንደሮች በእሳት መጋየት እና መውደም ሰለቃዎች ተጠያቂዎች ናቸው፡፡ ሰለቃዎች ጥቃታቸውን ከሰነዘሩ በኋላ ወደ ኋላ ሲያፈገፍጉ ዓለም አቀፉ ኃይል ለጸረ ባልካ ታጣቂዎች ድጋፉን በመስጠት ከተማ በከተማ ላይ እየተቆጣጠሩ ኃይላቸውን እንዲያጠናክሩ አጋጣሚውን ፈጥሮላቸዋል፡፡ የተከሰተው የኃይል እርምጃ እና የሙስሊም ማህበረሰብ አባላትን የማፈናቀሉ ሁኔታ የሚጠበቅ ክስተት ነበር፡፡“

በታሪክ የምጻት ቀን፣

አፍሪካ ከ1994ቱ የሩዋንዳ እልቂት እና ፍጅት ትምህርት ቀስማለችን? ዓለም አቀፉ ማህበረሰብ ለአፍሪካ ደህንነት በእርግጠኝነት በጽናት ቆሟልን? በሩዋንዳ ላይ አጥልቶ እንደነበረው የእርስ በእርስ እልቂት አፍሪካ ጆሮ ዳባ ልበስ ብላ ዝምታን በመምረጧ ምክንያት እንደተከሰተው ዘግናኝ ድርጊት ሁሉ አሁንም ልትወገዝ ትችላለችን? በዘር-ኃይማኖት ማጽዳት እና በዘር ማጥፋት ዘመቻ መካከል ያለው ልዩነት ምንድን ነው (በቀልቀሎ እና ስልቻ ያለ  ዓይነት ልዩነት)? በሩዋንዳ ላይ ተከስቶ የነበረው አስከፊ የዘር ማጽዳት ዘመቻ ተመልሶ በመካከለኛው አፍሪካ ሬፐብሊክ መምጣቱ ይሆን? ሩዋንዳ የወደፊቷ መካከለኛው አፍሪካ ሬፐብሊክ ነበረችን? እናም የመካከለኛው አፍሪካ ሬፐብሊክ የወደፊቷ የአፍሪካ ተምሳሌት ልትሆን ትችል ይሆን?

የዘር የዘር ማጥፋት ወጀልና የኃይማኖታዊ ወገንተኝነት ኢቦላ ከሚባለው አጥፊ  በሽታ (ቫይረስ) ተማሳሳይ ነው፡፡ እንደ ኢቦላ ቫይረስ የዘረኝነት እና የኃይማኖት ወገንተኝነት ሲጀምር አሳሳቢ አይደለም ፡፡ የኃይማኖት ጭቆናን እና ዘረኝነትን የሚዋጉ ህዝቦች እራሳቸውን እንደ ትክክለኛ ዜጋና ለፍትህ ታጋይ ሆነው ይቀርባሉ፡፡ በትግላቸው ጽናት መሰረት ድልን ሲቀዳጁ የተነሱለትን ዓላማ ወደ ጎን ገሸሽ በማድረግ ለሚሊዮኖች ስቃይ እና ሞት ምክንያት በመሆን ሌሎች በተቃራኒው ከቆሙት ጽንፈኞች እኩል የሆነ ወይም የበለጠ የህዝብ እልቂት ወንጀሎችን ይፈጽማሉ፡፡ እንደ ኢቦላ ቫይረስ ሁሉ ዘርኝነት እና የኃይማኖት ጽንፈኝነት የአፍሪካ የፖለቲካ ሰውነት ውህዶች ሆነዋል፡፡ አፍሪካ ከኃይማኖት ጽንፈኝነት እና ከዘረኝነት እንድትጸዳ ከተፈለገ በአስቸኳይ የክትባት መድኃኒት መገኘት አለበት፡፡

በወደፊቷ አፍሪካ የዘር ፍጅት እና በሰው ልጅ ላይ ሊፈጸም የሚችል አስፈሪ ሁኔታ

ካርል ማርክስ “የኮሙኒስት ማኒፌስቶ” በሚለው መጽሀፋቸው ላይ ለዓለም ህዝብ እንዲህ በማለት አሳውቀው ነበር፣ “በአውሮፓ ላይ አስፈሪ መዓት እያንዣበበ ነው- የኮሙኒዝም አስፈሪ ሁኔታ፡፡“ እንደዚሁም በተመሳሳይ መልኩ “በአፍሪካ ላይ አስፈሪ መዓት እያንዣበበ ነው- የዘር ፍጅት አስፈሪ ሁኔታ እና በሰው ልጆች ላይ ሊፈጸም የሚችል አስፈሪና አሰቃቂ ሁኔታ፡፡“ ማርክስ እንዲህ በማለት ተናግረው ነበር፣ ”እስከ አሁን ድረስ ያለው የህብረተሰብ ታሪክ የመደብ ትግል ታሪክ ነው፡፡“ ሁኔታው ከዚህ አንጻር ሲቃኝ የወደፊቷ አፍሪካ የዘር ፍጅት እና በሰው ልጆች ላይ የሚደረግ እልቂት የሚተወንባት መድረክ አህጉር ልትሆን ትችል ይሆን? በዓለም አቀፉ የወንጀለኞች ፍርድ ቤት የሮማ ስምምነት አንቀጽ 5 (a) ስር የተደነገገው በዘር ማጽዳት እና በሰው ልጆች ላይ የሚፈጸሙ ወንጀሎችን በሚመለከት የህግ ጥበቃ መብትን ያጎናጽፋል፡፡ አንቀጽ 6 “የዘር ማጽዳት” ውሱን የሆኑ ድርጊቶችን በማካተት ማለትም “የብሄራዊ፣ የጎሳ፣ የዘር ወይም ደግሞ የኃይማኖት ቡድንን በአጠቃላይ ወይም በከፊል ለማጥፋት ሆን ተብሎ ታቅዶ የሚፈጸም  ድርጊት“ ነው በማለት በግልጽ አስቀምጦታል፡፡ እነዚህ ድርጊቶች ከሌሎች በተጨማሪ “በአንድ ቡድን አባላት ላይ ሆን ተብሎ በተጠና ስልት ዕቅድ ተነድፎ ግድያ ለመፈጸም ወይም ደግሞ በአካል ወይም በአእምሮ ላይ ሙሉ ለሙሉ ወይም ደግሞ በከፊል ከፍተኛ የሆነ አካላዊ ጉዳት ለማድረስ“ የሚሉትን ያካተተ ነው፡፡

አንቀጽ 7 በሰው ልጆች ላይ የሚፈጸሙ ወንጀሎች በሚለው አንቀጽ ስር “ግድያ፣ ባርነት፣ ማጋዝ ወይም ደግሞ ህዝብን በኃይል ማፈናቀል፣ በእስር ቤት ማማቀቅ ወይም ደግሞ ዓለም አቀፍ መሰረታዊ የህግ ድንጋጌዎችን በመጣስ ማሰቃየት፣ አስገድዶ መድፈር እና በማንኛውም የታወቀ ቡድን ወይም በፖለቲካ፣ በዘር፣ በብሄር፣ በጎሳ፣ በባህል፣ በኃማኖት እና በጾታ በተዋቀረ ስብስብ ላይ ሌሎች የአካላዊ ነጻነቶችን መገደብ“ በሚል በማያሻማ መልኩ አስቀምጦታል፡፡

በሰው ልጆች ላይ የሚፈጸሙ ወንጀሎች እና መለስተኛ የዘር ማጥፋት ዕኩይ ምግባሮች በአሁኑ ጊዜ በአፍሪካ ተደጋግመው የሚከሰቱ ባህሪያት ሆነዋል፡፡ ከዓለም አቀፍ የሰብአዊ መብት ተሟጋች ድርጅቶች በስተቀር ጥቂት አፍሪካውያን/ት (መሪዎች እና የአፍሪካ ልሂቃን አባላትን ጭምሮ) እና ጥቂት የምዕራቡ ዓለም የመገናኛ ብዙሀን እና የዲፕሎማሲው ማህበረሰብ አባላት በአፍሪካ በመካሄድ ላይ በሚገኘው የዘር ማጥፋት እና በሰው ልጆች ላይ በሚፈጸሙ ወንጀሎች ላይ ግልጽ ውይይት ለማካሄድ ዝግጅት አድርገዋል፡፡ እ.ኤ.አ በ1994 የፕሬዚዳንት ክሊንተን አስተዳደር በሩዋንዳ ላይ በተፈጸመው ለመናገር በሚዘገንን የሰው ልጆች ዕልቂት ላይ ያልሰማ በመምሰል በአሁኑ ጊዜ የፕሬዚዳንት ኦባማ የደህንነት አማካሪ በሆኑት ሱሳን ራይስ ከእርሳቸው የስራ ባልደረቦች ጋር ድንገተኛ ስብሰባ በማድረግ “’የዘር ማጥፋት’ የምትለዋን ቃል የምንጠቀም ከሆነ እና ምንም ነገር ሳናደርግ እጃችንን አጣጥፈን በመቀመጥ ሁኔታውን የምንመለከት ከሆነ በኖቬምበር በሚካሄደው የኮንግረሱ ምርጫ ላይ የሚያስከትለው እንደምታ ምን ሊሆን ይችላል?“ የሚል የሸፍጥ ንግግር ማሰማታቸው የሚታወስ ነው፡፡

እ.ኤ.አ ከ2003 መጀመሪያ አካባቢ ጀምሮ የሱዳን መንግስት በዳርፉር ግዛት ላይ የጎሳ/የዘር ልዩነቶችን በማጉላት የአረብ ዘላኖች ከአፍሪካ ዘላኖች ጋር የጥላቻ ስሜት እንዲያድርባቸው በመስበክ ጥላቻን ሲያራግብ ቆይቷል፡፡ የሱዳን መንግስት ጃንጃዊድ (እንደ ሩዋንዳ ኢንተርሀሞይ ተመሳሳይ የሆኑትን) እየተባሉ የሚጠሩትን የአረብ ሚሊሻ አባላትን የአፍሪካን የጎሳ ቡድኖች እንዲወጉ እስከ አፍንጫቸው ድረስ ያስታጥቃል፡፡ የሱዳን መንግስት ከሰማይ የቦንብ ናዳ ሲያዘንብ የጃንጃዊድ ታጣቂ ኃይሎች ደግሞ መንደሮችን በእሳት ያጋዩ ነበር፣ የውኃ ጉድጓዶችን በመርዝ ይበክሉ ነበር፣ ሴቶችን አስገድደው ይደፍሩ ነበር፣ እንዲሁም ግማሽ ሚሊዮን የሚሆኑ ህዝቦችን የገደሉ ሲሆን ከሚሊዮን በላይ የሚሆኑ ንጹሀን ዜጎች ደግሞ እንዲፈናቀሉ አድርገዋል፡፡ እ.ኤ.አ በ2009 ዓለም አቀፉ የወንጀለኞች ፍርድ ቤት ብዙ ህዝብ ያለቀበትን ዘመቻ በመሩት፣ አስገድደው በደፈሩት እንዲሁም በሰላማዊ የዳርፉር ዜጎች ላይ ዘረፋ በፈጸሙት በሱዳኑ መሪ በኦማር አልባሽር እና በሌሎች ባለስልጣኖች ላይ የመያዣ ደብዳቤ ትዕዛዝ ቆርጦባቸዋል፡፡ አልባሽር ይህንን ሁኔታ በማስመልከት በዓለም አቀፉ የጦር ወንጀለኞች ፍርድ ቤት ክስ ላይ እንዲህ በማለት አፊዘዋል፣ “ሁሉንም ነገር ልቅም አድርጋችሁ ንገሯቸው፣ ለICC ዋና አቃቤ ህግ፣ ለፍርድ ቤቱ አባላት ዳኞች እና ለማንም ይህንን ፍርድ ቤት ለሚረዳ ሁሉ ከእኔ ጫማ ስር መሆናቸውን ንገሯቸው“ ብለዋል ትዕቢት እና እብሪት በተቀላቀለበት አንደበት፡፡

እ.ኤ.አ በ2007 መጨረሻ አና በ2008 መጀመሪያ አካባቢ ተከስቶ በነበረው የኬንያ የድህረ ምርጫ ውዝግብ ምክንያት በተወሰደው የኃይል እርምጃ ድርጊቱን በበላይነት ያቀነባበሩት እና የመሩት ኡሁሩ ኬንያታ ከሌሎች ተከላካዮች ጋር የእርሳቸውን ምክትል ፕሬዚዳንት ዊሊያም ሩቶን ጨምሮ በአሁኑ ጊዜ በዓለም አቀፉ የወንጀለኞች ፍርድ ቤት ክስ ተመስርቶባቸው የፍርድ ሂደቱ በመታየት ላይ ይገኛል፡፡ በዚያ አጨቃጫቂ ውዝግብ በተነሳው ሁከት ምክንያት ከ1,100 በላይ የኬንያ ዜጎች እንደተገደሉ የሚታመን ሲሆን 600 መቶ ሺ የሚሆኑ ዜጎች ደግሞ ተፈናቅለዋል፡፡ ኬንያታ በሮማ ደንብ መሰረት በሰው ልጆች ላይ የተፈጸሙ ወንጀሎች ማለትም ግድያ፣ ማጋዝ ወይም ደግሞ በኃይል ማፈናቀል፣ በአስገድዶ መድፈር፣ በማሰቃየት እና በሌሎች ኢሰብአዊ በሆኑ የወንጀል ድርጊቶች በሚል ስድስት ዓይነት ክሶች ቀርበውባቸዋል፡፡ ሆኖም ግን ኡሁሩ ኬንታ በሄግ የICCን የፍርድ ቤት ክፍሎች በጭራሽ ሊያዩ አልቻሉም፡፡ እውነት ለመናገር በሰው ልጆች ላይ ወንጀል ፈጽመው ከፍትህ ያመለጡት ኬንያታ እና አጋሮቻቸው ብቻ አይደሉም፡፡ ሌሎች ብዙዎች የአፍሪካ “ዘር አጥፊዎች” እና በሰው ልጅ ላይ ወንጀልን የሚፈጽሙ አፍሪካውያን ወንጀለኞች በICC እና በሌሎች ችሎቶች ላይ አፍንጫቸውን  በትቢት ቀሰረው ይነፋሉ፡፡

በደቡብ ኢትዮጵያ በኦሞ ወንዝ ሸለቆ የሚኖሩት የአካባቢው ቀዳሚ ኗሪ ህዝቦች በጊቤ ሶስት ግድብ ግንባታ በመንደር ምስረታ ሰበብ በመፈናቀላቸው ምክንያት የመጥፋት ችግር እያንዣበበባቸው ይገኛሉ፡፡ እ.ኤ.አ በ2012 በዓለም ዕውቅናን ያተረፉት የተፈጥሮ ሀብት ክብካቤ እና ጥንታዊ የሰው ዘር ተመራማሪ የሆኑት ባለሙያ ዶ/ር ሪቻርድ ሊኬይ የጊቤ ሦስት ግድብ ግንባታ የግል ጥቅም ማሳደጃ “ሳይንሳዊ” ጥናት በስነምህዳሩ ላይ ሊከሰቱ የሚችሉትን ውጤቶች አሳንሶ የሚያይ መሆኑን የምር በመሞገት “ግድቡ በርካታ የሆኑ አሉታዊ ውጤቶችን እንደሚያስከትል እንዲያውም አንዳንዶቹ በሁለቱም በኩል ማለትም በአካባቢው ስነምህዳር እና ለዘመናት ህይወቱን በዚህ ወንዝ የታችኛው ክፍል ላይ መስርቶ ለሚኖረው ማህበረሰብ ህይወት ፍጅት እና ዕልቂት“ ሊሆን እንደሚችል አስረግጠው ተንብየዋል፡፡ በኢትዮጵያ ያለው ገዥ አካል በቀዳሚ የጊቤ ሸለቆ ኗሪ ህዝቦች ላይ የጊቤ ሶስትን ግድብ በመገንባት የዘር ማጥፋት እና በሰው ልጆች ላይ ወንጀል በመፈጸም ድርጊት ተጠያቂ ሊሆን ይችላልን? 

በምዕራብ ኢትዮጵያ የጋምቤላ ህዝቦች ለዘመናት ቅድመ አያቶቻቸው ሲጠቀሙበት የነበረውን የህዝቡ አንጡራ ሀብት የሆነውን ለም መሬታቸውን እና ቤቶቻቸውን በመንጠቅ ለህንድ ባለሀብቶች አስረክበዋል፡፡ አንድ የህንድ ኩባንያ “2,500 ካሬ ኪ/ሜ ስፋት ያለው ድንግል ለም መሬት – በእንግለዝ የዶርሴት ግዛትን የሚያህል” ከታክስ ነጻ በሚባል መልኩ በሳምንት 150 ፓውንድ (245 ዶላር) ሂሳብ “አከራይቷል፡፡” ለካራቱሪ ኩባንያ ጥቅም ሲባል በጋምቤላ የሚኖሩ በአስር ሺዎች የሚቆጠሩ ኢትዮጵያውያንን/ትን ከሚኖሩበት ቀዬ እንዲፈናቀሉ በማድረግ የገዥው አካል የመንደር ምስረታ ፕሮግራሙ አካል አድርጎታል፡፡ በተባበሩት መንግስታት የህጻናት መርጃ ድርጅት ጥናት መሰረት “ቀዳሚ ኗሪ ህዝቦችን ጥንት አያት ቅድመ አያቶቻቸው ይኖሩበት ከነበረው ቀያቸው መንቀል በአሁኑ ጊዜ በገጠሪቱ የጋምቤላ አካባቢ በጣም አሳሳቢ ደረጃ ላይ ደርሷል፡፡ በቅርብ ጊዜ ውስጥ የአኙዋክ (ምናልባትም የሌሎች አናሳ ብሄረሰቦች) ባህል ፍጹም በሆነ መልኩ ይጠፋል የሚል ግምት አለ፡፡“ በማለት ድርጅቱ ስጋቱን ገልጿል፡፡ በኢትዮጵያ ያለው ገዥ አካል በጋምቤላ በመንደር ምስረታ ፖሊሲው ጠቀሜታ ሰበብ በዘር ማጥፋት እና በሰው ልጆች ላይ እየፈጸመ ላለው ወንጀል ተጠያቂ ነውን? 

በኢትዮጵያ ያለው ገዥ አካል ወደ ሩብ ምዕተ ዓመት ያህል በዘር ላይ የተመሰረተ ያልሰለጠነ የጎሳ ፖለቲካ ፓኬጆችን እየነደፈ በእውቀት ላይ የተመሰረተ ሳይሆን “የጎሳ ፌዴራሊዝም” እያለ በሚጠራው የእውር ድንብርብር ዘረኛ ስርዓት በጭፍን ፍላጎት ግላዊ እና ቡድናዊ ጥቅመኝነትን በማራመድ ላይ ይገኛል፡፡ ገዥው አካል የኢትዮጵያን ህዝብ በዘር እና በጎሳ በመከፋፈል በአስፈሪ የአከላለል ስልት ሰውን ያህል ክቡር ፍጡር እንደ ከብት በቦታ በመከለል “ክልል” (በተለምዶ የተቀነበበ የሚል ትርጉም ሲኖረው በተመሳሳይ ትርጉም ቃሉ የተከለከለ ወይም የተቀነበበ ዞን የሚል ትርጉም ይዞ ይገኛል) በሚል የዜጎችን የመዘዋወር እና በመረጡት ቦታ ሰርቶ ለመኖር ያለውን መብት የሚደፈጥጥ የፖለቲካ ፍልስፍና ላይ የተመሰረተ ነው፡፡ “የክልልነት” ፍልስፍና የአፓርታይድን “ባንቱስታኒስም” (“ጥቁር ደቡብ  አፍሪካውያን/ት የጎሳ ቤቶች”) ብዙዎችን ባህሪያቶች ይጋራል፡፡ ሁለቱም የፖለቲካ ፍልስፍናዎች በዘር እና በቋንቋ በመለያየት በአንድ መንደር ላይ እንዲሆኑ የፈረጇቸውን የጎሳ ቡድኖች በመጨረሻ ወደ አንድ ወጥ “እራሱን የቻለ” ብሄር በመመስረት ላይ ዓላማ ያደረገ ስልት ነው፡፡ “ክልላዊነት” “የመንደራዊነት“ መገለጫ አንዱ አካል ሲሆን ኢትዮጵያን ወደ ተበጣጠሱ የተለያዩ መንደሮች፣ ሰፈሮች እና ጎጦች ያሳንሳል፡፡ “ክልሎች” በመሰረቱ የዳበሩ እና የተጠናከሩ የአፓርታይድ ቅጅ ባንቱስታንስ ናቸው፡፡ “ክልላዊነት” የዘር ማጥፋት እና በሰው ልጆች ላይ ወንጀል የመፈጸም መፈልፈያ ቦታዎች ናቸውን? በኢትዮጵያ ያለው ገዥ አካል ከህዝቦች ፍላጎት ውጭ በኃይል እየተገበረ ባለው “ክልላዊ” ፖሊሲው ሰበብ ለሚፈጸመው የዘር ማጥፋት እና በሰው ልጆች ላይ ለሚፈጸም ወንጀል ሙሉ ኃላፊነቱን ሊወስድ ይችላልን?

ከአስርት ዓመታት በላይ በኢትዮጵያ ያለው ገዥ አካል “የዘር ፌዴሪያሊዝምን” በመተግበር ላይ የሚገኝ ቢሆንም እንኳ የኦጋዴን አካባቢ ህዝቦችን የነጻ ብሄርነት ጥያቄን በኃይል በማፈን በኢትዮጵያ የኦጋዴን ህዝቦች ላይ በማያቋርጥ መልኩ የጥቃት ዘመቻዎችን በማድረግ ህዝብን ለእልቂት እና ፍጅት ዳርጎ በማሰቃየት ላይ ይገኛል፡፡ አገዛዙ የኦጋዴን ህዝብን በማስራብ እና የኦጋዴንን ከተሞች እና መንደሮች በኢኮኖሚ እንቅስቃሲያቸው ዝግ እንዲሆኑ የማድረግ ፖሊሲን የመተግበር ዓላማን በመፈጸም ላይ ይገኛል፡፡ ገዥው አካል በቅርብ ርቀት በሚተኮሱ የአውሮፕላን ላይ ጥቃቶች የኦጋዴንን ሰላማዊ ህዝብ በጅምላ ይደበድባል፣ እንዲሁም በድርቅ ለተጎዳው የአካባቢው ህዝብ ከእርዳታ ሰጭ ድርጅቶች የሚመጣውን እርዳታ እንዲቋረጥ በማድረግ ሰብአዊ መብትን ይደፈጥጣል፡፡ ግድያዎችን፣ ማሰቃየትን፣ አስገድዶ መድፈርን እና አፍኖ የደረሱበትን የማሳጣትን ዕኩይ ተግባራት የኦጋዴንን ህዝብ ለማጥቃት ገዥው አካል የሚጠቀምባቸው ስልቶች ናቸው፡፡ ሂዩማን ራይትስ ዎች “የጅምላ ቅጣቶች፡ በኢትዮጵያ በኦጋዴን አካባቢ በሶማሊ ክልል የጦር ወንጀሎች እና በሰው ልጆች ላይ የሚፈጸሙ ወንጀሎች“ በሚል ርዕስ የገዥውን አካል ጽልመታዊ የዕልቂት ወንጀሎች የሚያትት ባለ130 ገጽ ዘገባ አውጥቶ ነበር፡፡ በኢትዮጵያ ያለው ገዥ አካል በኦጋዴን ህዝብ ላይ እየተፈጸመ ላለው የዘር ማጥፋት፣ በሰው ልጆች ላይ ለሚፈጸሙ ወንጀሎች እና የጦር ወንጀለኝነት ኃላፊነቱን ይወስዳልን? 

እ.ኤ.አ በ2005 በኢትዮጵያ ያለው ገዥ አካል በግንቦት ወር የተደረገውን አገር አቀፍ ምርጫ ተከትሎ በተቀሰቀሰው ሁከት በመቶዎች የሚቆጠሩ ያልታጠቁ ንጹሀን ዜጎችን የመግደል ትወናውን ፈጽሟል፡፡ ፖሊስ እና የደህንነት ኃላፊዎች በቅርቡ በህይወት በተለዩት በአቶ መለስ ዜናዊ ቀጥተኛ ትዕዛዝ እና ቁጥጥር ስር በመሆን እንዲሁም በእርሳቸው ቁልፍ አዛዦች አስተባባሪነት የንጹሀን ዜጎች እልቂት እንዲፈጸም ተደርጓል፡፡ በአቶ መለስ የተቋቋመው የአጣሪ ኮሚሽን ቢያንስ 193 ንጹሀን ሰላማዊ አማጺዎች ከህግ አግባብ ውጭ በዘፈቀደ በመንግስት ታጣቂ ኃይሎች መገደላቸውን፣ ሌሎች 763 ዜጎች ደግሞ መቁሰላቸውን እና 30 ሺ ዜጎች ደግሞ የዘፈቀደ እስራት የተፈጸመባቸው መሆኑን በዘገባው አካትቶ ለመንግስት አቅርቧል፡፡ የኮሚሽኑ ማስረጃ በመቀጠልም እ.ኤ.አ ኖቬምበር 3/2005 በአዲስ አበባ ከተማ በሚገኘው ታዋቂው ቃሊቲ እየተባለ በሚጠራው የማጎሪያ እስር ቤት ተፈጠረ በተባለ ሁከት ሰበብ የግቢው ጥበቃዎች በ15 ደቂቃ የጊዜ ርዝመት ውስጥ ከ1,500 በላይ ጥይቶችን በመተኮስ በእስር ቤቶች ላይ ያርከፈከፉ ሲሆን በዚሁ የተቀነባበረ ዕኩይ ተግባር 17 ንጹሀን የህግ ታራሚ ዜጎች ሲገደሉ 53 ዜጎች ደግሞ ከባድ ቁስለኛ ሆነዋል፡፡ አቶ መለስ በግላቸው በሰው ልጆች ላይ ለተፈጸሙ ወንጀሎች ኃላፊነትን መውሰድ ይኖርባቸው ነበርን? በአሁኑ ጊዜ በአገዛዙ የስልጣን ወንበር ላይ ያሉት ባለስልጣኖች ወይም ደግሞ ሌሎች በህገወጥ ድርጊቱ ላይ ተሳትፎ የነበራቸው ሆኖም ግን በአሁኑ ጊዜ በአገዛዙ የስልጣን ወንበር ላይ የሌሉ የወንጀሉ ተጠርጣሪዎች .. 2005 የኢትዮጵያ አገር አቀፍ ምርጫ በሰው ልጆች ላይ ለተፈጸመው ወንጀል እና ዕልቂት ኃላፊነት መውሰድ አለባቸውን?   

እ.ኤ.አ በሜይ 2012 የአማራ ተወላጆችን ከደቡብ ኢትዮጵያ “በዘር ማጽዳት” የዘመቻ ስልት ሀብት እና ንብረት አፍርተው ከኖሩበት ቦታቸው በመባረራቸው በይስሙላው ፓርላማ ተገኝተው ይህንን ዘገባ ያቀረቡት እና ለህዝብ ይፋ ያደረጉት ሰዎች ኃላፊነት የማይሰማቸው ዜጎች ናቸው በማለት የይስሙላ ጩኸታቸውን በማሰማት የእርሳቸውን የግዳጅ ማፈናቀል (አንዳንዶች “የዘር ማጽዳት” እያሉ የሚጠሩትን) ለማስተባበል ሞክረዋል፡፡ አቶ መለስ እንዲህ ብለዋል፣ “አማራዎች ወይም ከምስራቅ ጎጃም መጥተው የሰፈሩት “ሰፋሪዎች” (ሰውን በእራሱ ሀገር ላይ “ሰፋሪ” ወይም “በህገወጥ መልክ የሰፈሩ“ እያሉ መጥራት ምን ያህል አዋራጅ ነው ንቀት ነው!) በአካባቢው ስነምህዳር ጥበቃ አንጻር ታሳቢ ሆኖ በደቡብ መጥተው ከሰፈሩበት ቀያቸው መነሳት አለባቸው” ሲሉ አስረግጠው ተናግረው ነበር፡፡ አቶ መለስ በግል በእራሳቸው በሺዎች የሚቆጠሩየአማራዜጎችን ከደቡብ ኢትዮጵያ ከሚኖሩበት ቀያቸው ከፍላጎታቸው ውጭ በግዳጅ በማባረራቸው በሰው ልጆች ላይ በተፈጸመ ወንጀል ኃላፊነት መውሰድ ይኖራባቸው ነበርን? 

በዚሁ ዓመት ባለፈው ኤፕሪል በኢትዮጵያ ያለው ገዥው አካል የአማራ ተወላጆችን ከቤንሻንጉል ጉሙዝ (በኢትዮጵያ ካሉት ዘጠኝ ክልሎች አንዱ የሆነ “ክልል”) በግብሩ “የዘር ማጽዳት” ተብሎ በሚገለጸው መሰረት በግዳጅ እንዲባረሩ ትዕዛዝ ተሰጥቷል፡፡ ታዋቂው የተቃዋሚ ድርጅቶች አመራር እና በዓለም አቀፉ የወንጀለኞች ፍርድ ቤት የሩዋንዳ ዋና አቃቤ ህግ የነበሩት ዶ/ር ያዕቆብ ኃይለማርያም የአማራ ተወላጅ የሆኑ ዜጎችን ከቤንሻንጉል ጉሙዝ በግዳጅ እንዲባረሩ መደረጉ በውስጠ ተዋቂነት “የዘር ማጽዳት” መሆኑን ከሙያ አንጻር ያላቸውን አስተያየት በማከል ሀሳባቸውን አካፍለዋል፡፡ አንድ ዓይነት ውሱን ቋንቋ በመናገራቸው ምክንያት ብቻ በግዳጅ ኃይልን በመጠቀም እንዲባረሩ መደረጉ በክልሉ ውስጥ አለመረጋጋትን ሊፈጥር ይችላል፣ እንዲሁም ደግሞ ይህ ዓይነቱ ስልታዊ የዘር ማጽዳት በአግባቡ ተጠናቅሮ ለተባበሩት መንግስታት የጸጥታው ምክር ቤት ቢቀርብ ድርጅቱ የዓለም አቀፉን የወንጀለኞች ፍርድ ቤት በማዘዝ ወንጀሎችን እንዲመረምር ማስጀመር ይቻላል፡፡

በአሁኑ ጊዜ  በአገዛዙ የስልጣን ወንበር ላይ ያሉት ባለስልጣኖች  ሚስጥር አድርጎ የያዙት ቢሆንም ብዙ የኢትዮጵያ አካባቢዎች  በድርቅ እና በረሀብ እየተጠቁ ነው፡፡ በዚህ ዓመት በፌብሯሪ ከ91 ሚሊዮን የኢትዮጵያ ህዝብ ውስጥ 2.7 ሚሊዮን የሚሆኑ ዜጎች በረሀብ የተጠቁ መሆናቸውን ቢሮክራሲያዊ በሆነ መልኩ የአገዛዙ ባለስልጣኖች  ይፋ በማድረግ ሰብአዊ እርዳታ እንደሚፈልግ  አስታውቀዋል ፡፡ አጠቃላይ የምግብ ፍላጎት (ቀደም ሲል ገዥው አካል ዝቅ አድርጎ የገመተው ቢሆንም) 388,635 ሜትሪክ ቶን እንደሚያስፈልግ ተገምቷል፡፡ በረሀቡ በይበልጥ የተጠቁት ክልሎች ጋምቤላ (16.7%)፣ ሶማሊ (13.8%)፣ ትግራይ (11.3%) እና አፋርን (10%) ያጠቃለለ ነው፡፡ ገዥው አካል ለዚህ ችግር 51.6 ሚሊዮን የአሜሪካ ዶላር ብቻ ማለትም በጠቅላላው ከሚያስፈልገው ውስጥ 12.8 በመቶ ብቻ የሚሸፍን በጀት መድቧል፡፡ እየመጣ ላለው ረሀብ የማስጠንቀቂያ ደወሉ እየተደወለ ቢሆንም የይስሙላው ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ መንግስት ባለ “ሁለት አሀዝ የኢኮኖሚ እድገት” ያስመዘገበ መሆኑን በታላቅ ኩራት ተናግረዋል፡፡ በድርቅ ከተመቱ አካባቢዎች የሚገኙ መረጃዎች በገዥው አካል ተጽዕኖ ምክንያት ሙሉ በሙሉ ይፋ የማይደረጉ ሲሆን መረጃዎች ስለማይታዩ እና ስለማይዘገቡ በሺዎች የሚቆጠሩ ኢትዮጵያውያን/ት በረሀብ በየወሩ ይሞቱ ነበር፡፡ በኢትዮጵያ ያለው ገዥ አካል በሚያሳየው ቸልተኝነት እና ለረሀቡ በቂ በጀት ባለመመደብ ምክንያት የተሟላ መረጃ እያለው የረሀብ እልቂቱ እንዲከሰት በማድረጉ ሰበብ በረሀብ ለሞቱ የዘር ማጥፋት ኃላፊነት ይወስዳልን?

በኢትዮጵያ ያለው ገዥ አካል እ.ኤ.አ በሜይ 1991 ስልጣን ከያዘበት ጊዜ ጀምሮ “በአማራ” እና በሌሎች ዜጎች ላይ ሰንፋጭ በሆነ የጎሳ ተኮር የማጠልሸት ንግግር ላይ ተጠምዶ ቆይቷል፡፡ አሁን በቅርቡ ከሶስት ወራት በፊት ገዥው አካል በ19ኛው ክፍለ ዘመን የኢትዮጵያ መሪ የነበሩትን እና በኢትዮጵያ አቆጣጠር የመቶኛ ሙት ዓመት በዚህ ዓመታ ተከብሮላቸው የዋሉትን የዳግማዊ ዓጼ ምኒልክን ስም የማጠልሸት እና የማዋረድ ዕኩይ ምግባር ላይ በመተወን እና በማስተባበር ዘመቻ ላይ ተሰማርቶ ነበር፡፡ ገዥው አካል በጎሳ ቡድኖች መካከል ጥላቻን በመዝራት እና መሰሪ ተግባራትን በመስራት አጼ ምኒልክን እንደ መሳሪያ በመጠቀም የጥላቻ ዘመቻውን ቀጥሎበት ነበር፡፡ የጥላቻ ዘመቻው በይበልጥ ይካሄድ የነበረው በገዥው አካል የቅርብ ታማኝ ሎሌዎች፣ መሰሪ ተዋንያኖች እና አሻንጉሊቶች አማካይነት ነበር፡፡ በሎሌዎቹ አማካይነት ገዥው አካል ጥላቻን የሚቀሰቅሱ ቃላትን፣ ሰንፋጭ ንግግሮችን እና የአጼ ሚኒልክን ጨካኝነት የሚል ውንጀላን በማራገብ በዘለፋ ላይ በመሰማራት ተልዕኮውን ለማሳካት ጥረት ሲያደርግ ቆይቷል፡፡ አጼ ሚኒልክ ከሞቱ ከ100 ዓመታት በኋላ ገዥው አካል ምኒልክ ሰይጣኑ ገዳይ እንደነበሩ አድርጎ ለመሳል ጥረት አድርጓል፡፡ የዚህ ዓይነቱ መሰረተቢስ ፕሮፓጋንዳ ዓላማው ምንድን ነው? በአሁኑ ጊዜ እየተደረገ ያለው ሰንፋጭ ንግግር በጎሳ ጥላቻው ላይ ነዳጅ ለመጨመር የተሰላ በሰው ልጆች ላይ የሚፈጸም ወንጀል ነውን?

በቅርቡ በህይወት የተለዩት አቶ መለስ ዜናዊ የብሩህ አእምሮ ባለቤት ናቸው (የውጭ አድናቂዎቻቸው ማዳም ሱሳን ራይስ እና ክላሬ ሾርት እንደሚያምኑት) ትንሽ ጥበብ እና በዘልማድ የሚመሩ ቢሆኑም እንኳ፡፡ ህጻናት እርስ በእርሳቸው እንዲፈራሩ ምዕናባዊ ጭራቅን እንደሚጠቀሙ ሁሉ አቶ መለስም የዘር ማጥፋትን በህዝቡ ላይ በማስፈራሪያነት ይጠቀሙበት ነበር፡፡ እ.ኤ.አ በ2010 አቶ መለስ የሩዋንዳን የዘር ማጥፋት ሰለባዎች ትዝታ ክብር የማዋረድ እና ዘለፋ ማካሄድ ብቻ አይደለም ያደረጉት፣ ሆኖም ግን ሰንፋጭ የሆነ ንግግሮችን በማሰማት የአሜሪካ ደምጽ የአማርኛው አገልግሎትን ከሩዋንዳው ሚሌ ኮሊን የሬዲዮ ጣቢያ ጋር በማነጻጸር የፖለቲካ ጠቀሜታ ትርፍን ለማግኘት የዳከሩበት ዕኩይ ምግባር እንጅ፡፡ አቶ መለስ እንዲህ ብለው ነበር፣ “የአሜሪካ ድምጽ የአማርኛው አገልግሎት የሩዋንዳን ሬዲዮ መጥፎ ባህሪያት በመቅዳት ዝቅተኛውን የጋዜጠኝነት የሙያ ስነ ምግባር በማያሟላ መልኩ እና በጎጅ የፕሮፓጋንዳ ስራ ላይ ተጠምዶ በብዙ መልኩ ለበርካታ ዓመታት እያስተላለፈ ያለው ፕሮፓጋንዳ እንደሆነ እናምናለን፡፡“ አቶ መለስ የአሜሪካ ድምጽ የአማርኛው አገልግሎት ለኢትዮጵያ የሚያስተላልፈውን ፕሮግራም ለማፈን በሚል ህገወጥ ተግባር ለረሀብ ሰለባዎች ረሀብ ማስታገሻ እና ለጤና ክብካቤ እንዲሁም ለትምህርት አገልግሎት ሊውል ቢችል ኖሮ ብዙ ጠቀሜታ ሊኖረው የሚያስችል በርካታ ሚሊዮን የአሜሪካ ዶላር ለዘር ማጽጃ ህገወጥ ተግባር አውለዋል፡፡

እንደዚህ ያሉ አስደንጋጭ ቃላት ናቸው ከአቶ መለስ አፍ ግልጽነት በጎደለው መልኩ የሚወረወሩት፡፡ አቶ መለስ “የአሜሪካ ድምጽ የአማርኛው አገልግሎት እንደ ሬዲዮ ሚሌ ኮሊንስ የመሳሰሉ መጥፎ ልምዶችን በመኮረጅ“ ሲሉ ለማስተላላፍ የፈለጉት መልዕክት ምንድን ነበር? በመስመሮች መካከል ያሉ መልዕክቶች ነበሩን? የአሜሪካ ድምጽ የአማርኛው አገልግሎት የመጨረሻውን ጦርነት ለማድረግ ጥሪ በማቅረብ ጥቂት ኢትዮጵያውያንን/ትን እንደ “በረሮ”፣ “ ጎጅ ነብሳት“ እና “አይጦች“ ለመጨፍጨፍ መደምደማቸው ነበርን? በአሜሪካ ድምጽ የአማርኛው አገልግሎት ስርጭት ምክንያት በአገሪቱ ውስጥ ሊንቀሳቀሱ የሚችሉት ዘር “አጽጅዎች” እነማን ናቸው? አቶ መለስ  ለዘር ማጥፋት ተግባራት ጥቂት ኢትዮጵያውያንን/ትን “ከአገሪቱ ለማስወገድ እና ለማጥፋት” ገዳይ ሚሊሻዎችን እና አፋኝ ቡድኖችን የሚመራው እና የሚያስተባብረው የአሜሪካ ድምጽ የአማርኛው አግልግሎት ነው ማለታቸው ነበርን? አቶ መለስ ሆን ብለው የሩዋንዳን የዘር ማጥፋት ዘመቻ ለፖለቲካ ዓላማ ይጠቀሙበት ነበር፡፡ እርሳቸው እንደሚሉት እና ለኢትዮጵያውያን/ት እንዲሁም በገንዘብ ለሚረዷቸው የውጭ ለጋሽ ድርጅቶች ከእርሳቸው እና ከአገዛዛቸው ውጭ ኢትዮጵያ ሌላዋ ሩዋንዳ እንደምትሆን በተጨባጭ ለማሳመን ጥረት ያደርጉ ነበር፡፡ ማንም ገዥ አካል ቢሆን የዘር ማጽዳት ስልትን በመጠቀም በስልጣን ላይ ተጣብቀው ለመቆየት ለሚፈልጉ አምባ ገነኖች ለዘላለም ተቃውሞ ሊደረግባቸው ይገባል!

ማንኛውም አፍሪካዊ ወንድ እና ሴት አንድ አንድ ምክንያቶችን በመፍጠር ለተስፋ መታገል አለባቸው፣

በማንኛውም የአፍሪካ አገር ላይ የዘር ማጥፋት እና በሰው ልጆች ላይ ወንጀል መፈጸም በእያንዳንዱ የአፍሪካ አገር ላይ የዘር ማጥፋት እና በሰው ልጆች ላይ ወንጀል እንደመፈጸም መቆጠር አለበት፡፡ በሩዋንዳ ላይ የተፈጸመው የዘር ማጥፋት ዘመቻ የአፍሪካ የዘር ማጥፋት ዘመቻ ነው፡፡ የቱትሲ እና ጽንፈኛ ያልሆኑ የሁቱ የጎሳ አባላትን ለመፍጀት የተቀነባበረ ወንጀል ብቻ አይደለም፡፡ ይህ ድርጊት በሁሉም አፍሪካውያን/ት እና በሰው ልጆች ላይ የተፈጸመ የፈሪዎች ወንጀል ነው፡፡ ይህ ዕኩይ ምግባር በማንኛውም ህያው በሆነ/ች አፍሪካዊ/ት ላይ ሊረሳ የማይችል ጥልቅ ትውስታን እና ጠባሳ ጥሎ የሄደ ወንጀል ነው፡፡ አፍሪካውያን/ት ተስፋ መቁረጥ ሳይሆን ይህንን አስቀያሚ ክስተት ማስታወስ አለባቸው፡፡ ከዕልቂት የተረፉት እና የኖቤል ሽልማት አሸናፊ የሆኑትን የኤሊ ዋሲልን አባባል በመዋስ “ሁሉም አፍሪካዊ/ት ገዳዮችን ማስታወስ አለበት፡፡ እያንዳንዱ/ዷ አፍሪካዊ/ት የወንጀሉን ሰለባዎች ማስታወስ አለበት/ባት እያንዳንዳቸው ለተስፋ ሲሉ አንድ ሺ አንድ ምክንያቶችን ለመፍጠር ቢችሉም አንኳ፡፡ ምክንያቱም ስናስታውስ ተስፋ እንቆርጣለን፡፡ ምክንያቱም ስናስታውስ ተስፋን ለማስወገድ ኃላፊነት ይኖረናል፡፡ ተስፋ ከተስፋ ማጣት የበለጠ ተፈጻሚነት አለው፡፡“

ለዘር ማጥፋት እና በሰው ልጅ ላይ ለሚፈጸም ወንጀል የሰው ልጅ ልብ ዋና ማስቀመጫ ሳንዱቅ ነው፣

በሩዋንዳ የተፈጸመው የዘር ማጥፋት ወንጀል እ.ኤ.አ ኤፕሪል 6/1994 ጎራዴዎችን የታጠቁ ወሮበሎች መንገዶችን በወረሩበት ጊዜ አልተጀመረም፡፡ የዚያ የዘር ማጥፋት ዘር የተዘራው ከጎሳዊነት አስተሳሰብ ውጭ ቀደም ሲል ከአስርት ዓመታት በፊት በመጥፎ አካሄድ በሚመሩ እና በተወገዙ ሩዋንዳውያን/ት ልብ ውስጥ የተጸነሰ ነበር፡፡ ጥላቻ እና ታጋሽየለሽነት ዘር ወይም ኃይማኖት የላቸውም፡፡ የዘር ማጥፋት ቀስ በቀስ ጥላቻን በሚንከባከቡ እና ቀስ በቀስ ወደ ታላቅ ብስጭት ውስጥ በመግባት በወንዶች እና በሴቶች አእምሮ ውስጥ የሚበቅል እርኩስ መንፈስ ነው፡፡ በዋሻ ጨለማ ውስጥ እንደሚበቅል እንጉዳይ የዘር ማጥፋት እንጉዳይም በጨለማ ልብ ውስጥ የሚበቅል አረም ነው፡ አፍሪካውያን/ት ተስፋ መቁረጥ የለባቸውም፡፡ የዶ/ር ማርቲን ሉተርኪንግን እንዲህ የሚል መልዕክት ማስታወስ አለባቸው፣ “ጨለማን ጨለማ አያስወግደውም፣ ብርሀን ብቻ ነው ያንን ማድረግ የሚችለው፡፡ በተመሳሳይ መልኩ ጥላቻን ጥላቻ አያስወግደውም፣ ፍቅር ብቻ ነው ያንን ለማድረግ የሚችለው፡፡“ የእውነት ብርሀን ብቻ ነው የጨለመውን ልብ ሊያበራ የሚችለው፡፡

ዝምታ እና ግዴለሽነት ለዘር ማጥፋት እና በሰው ልጅ ላይ ለሚፈጸም ወንጀል ኦክስጅን ናቸው፣

የዘር ማጥፋት እና በሰው ልጅ ላይ የሚፈጸም ወንጀል የዝምታ እና የምንቸገረኝነት ወንጀሎች አስፈላጊ ወንጀሎች ናቸው፡፡ ታላላቆቹ ኃያላን አገራት በሩዋንዳ የዘር ፍጅት ጊዜ ዝምተኛ ምስክሮች ነበሩ፡፡ እ.ኤ.አ ከኤፕሪል 6/1994 ጀምሮ ምን እንደሚካሄድ በእርግጠኝነት ያውቁ ነበር፡፡ ሆንም ግን ዝም ማለትን መረጡ፡፡ የአፍሪካ ህብረት፣ የተባበሩት መንግስታት እና የአውሮፓ ህብረት ዝምታን መረጡ፣ ሆኖም ግን ሁኔታውን በሚገባ ያውቁ ነበር፡፡ የእርስ በእርስ መተራረዱ ከ100 ቀናት በላይ ወሰደ፣ እናም የ800 ሺ ሰዎችን ህይወት ቀጠፈ ምክንያቱም ይህንን ሰይጣናዊ ድርጊት ሊያስቆሙ ይችሉ የነበሩት ኃይሎች ለጉዳዩ ደንታ አልነበራቸውም፡፡ አፍሪካውያን/ት እራሳቸውን ለማዳን ሌሎችን የውጭ ኃይሎች መጠበቅ የለባቸውም፡፡ እራሳቸውን ከእራሳቸው መጠበቅ አለባቸው፡፡ ለዚህም ነው ሁሉም አፍሪካውያን/ት የጎሳ ጥላቻን እና የኃይማኖት አለመቻቻልን የሚያራግቡትን የሰይጣን ፈረሰኞች በአንድ አእምሮ እና ቃል ማውገዝ ያለባቸው፡፡ አፍሪካውያን/ት በዘር፣ በጎሳ፣ በኃይማኖት፣ በቋንቋ፣ በጾታ ወይም በማንኛውም ሌላ ጉዳት ሊያስከትል በሚችል መልክ ክፍፍል እየፈጠሩ ጥላሸት በመቀባት የሚለያዩትን መሰሪ ግለሰቦች እና ቡድኖች በንቃት መቋቋም አለበት፡፡

ከእርቅ በፊት እውነት እና ፍትህ፤

የዓለም አቀፋዊ ወንጀሎች ቡድን ተጠሪ የሩዋንዳ አቃቤ ህግ የሆኑት በቅርቡ እንዲህ ብለው ነበር፣ “በህይወታችን ሙሉ እነርሱን እንከታተላቸዋለን፣ እናም ከእኛ በኋላ የሚመጡትም እንደዚሁ ይከታተሏቸዋል፡፡ ያለእውነት እና ትክክለኛው ፍትህ ሳይሰጥ ምንም ዓይነት ዕርቅ ሊኖር አይችልም፡፡“ ይኸ ለሁሉም አፍሪካውያን/ት ትልቁ መልዕክት ነው፡፡ ፍትህ እና እውነት/ዕርቅ የአንድ ሳንቲም ሁለት ገጽታዎች ናቸው፡፡ በየትኛውም ጎን ሳንቲም ወደ ላይ ቢጓን አንድ ጎኑን የሰብአዊ መብት ፊት ያሳያል፡፡ ኔልሰን ማንዴላ እንዲህ ብለው ነበር፣ “ዕርቅ ማለት ያለፈውን ኢፍትሀዊ ውርስ ለማስተካከል በጋራ መስራት ማለት ነው፡፡“ ያለፉት ኢፍትሀዊነቶች ለወደፊት በአፍሪካ ዕድል ላይ የሚያጠሉ ረዥም የጨለማ ጥላሸቶች ናቸው፡፡

የማስተማር ኃላፊነት፣

በሩዋንዳ እና በዳርፉር የተፈጸሙ የዘር ማጽዳት ዘመቻ ሰለባዎችን ማስታወስ እና በመካከለኛው አፍሪካ ሬፐብሊክ በመካሄድ ላያ ያለውን “የጎሳ-ኃይማኖት ማጽዳት” ዘመቻ ማውገዝ ብቻውን በቂ አይደለም፡፡ የአፍሪካ ወጣቶች ስለዘር ማጽዳት እና በሰው ልጆች ላይ ስለሚፈጸሙ ወንጀሎች መማር አለባቸው፡፡ የዚህ ዓይነቱ መረጃ የአፍሪካ ትምህርት ቤቶች፣ ኮሌጆች እና ዩኒቨርስቲዎች የትምህርት ስርዓት አካል መሆን አለባቸው፡፡ ድንቁርና የዘር ማጥፋት እና በሰው ልጆች ላይ የሚፈጸሙ ወንጀሎች ማዳበሪያ ነው፡፡ ባንኪሙን ለሩዋንዳ ህዝቦች እንዲህ በማለት ተናግረዋል፣ “’ድጋሜ በፍጹም’ እንደገና እና እንደገና የሚሉትን ቃላት በማለት ብቻ ተወስነን መቅረት የለብንም፡፡“ እነዚህ ህይወታቸውን ያጡትን እና በተስፋ መቁረጥ ህይወታቸውን ለማትረፍ የሚሰደዱትን የመካከለኛው አፍሪካ ሬፐብሊክ ነጻ ወንዶችን፣ ሴቶችን እና ልጆችን ለማገዝ በጣም ዘግይተው የመጡ ባዶ ቃላት ናቸው፡፡

የአፍሪካ መሪዎች ዓለም አቀፋዊ የሰብአዊ መብት ተሟጋች ድርጅቶችን ከመተቸት እና በጥላቻ መልክ ከማየት ይልቅ ድርጅቶቹ የአፍሪካ ወጣቶችን ስለሰብአዊ መብት ትምህርት እንዲሰጡላቸው  መጋበዝ እና እነርሱም በተራቸው ያገኙትን ስልጠና እና እውቀት በመጠቀም ሌሎች አቻ ጓደኞቻቸውን እና ማህበረሰቡን በእውቀት፣ በክህሎት እና በአመለካከት አቅማቸውን በማሳደግ በዓለም አቀፍ ደረጃ ተቀባይነት ያላቸውን የሰብአዊ መብት መርሆዎች ማስፋፋት ይችላሉ፡፡ በአፍሪካ የሰብአዊ መብት ትምህርት መስጠት በጣም አስፈላጊ እና በአፍሪካ ግጭቶችን ለማስወገድ ቅድመ የክንውን ተግባር ነው፡፡ ከቀደሙት የዘር ማጥፋት እና በሰው ልጆች ላይ ከተፈጸሙት ወንጀሎች የማይማሩ እራሳቸውን ይደግሟቸዋል፡፡

የአፍሪካ አጭር ወንዶች እና ረዥሙ ጥላቸው፣

የአፍሪካ ምሁራን በአፍሪካ ያለ የአስተዳደር ችግር የታላቅ ሰው አገዛዝ ህግ የሚለው መሪዎች መንግስትን የእራሳቸው መጠቀሚያ መሳሪያ በማድረግ የመንግስት ሀብትን ለእራሳቸው እና ለደጋፊዎቻቸው በማከፋፈል በተራቸው እነዚህ ደንበኞች ደግሞ መንግስት በስልጣን ላይ እንደ መዥገር ተጣብቆ በማገዝ የእራሳቸውን ግላዊ ጥቅም ለማስጠበቅ ጥረት ያደርጋሉ በማለት ትንታኒያቸውን ያቀርባሉ፡፡ የአፍሪካ አስተዳደር ትልቁ ችግር ግን በተቃራኒው እንደሆነ አምናለሁ፡፡ የቆየ አባባል እንዲህ በማለት ያስተምረናል፣ “አጭር ወንዶች  (ያፍሪካ መሪዎች ) ጥላቸው በረዥም ሲዘረጋ ለጸሐይ  መጥለቂያዋ ጊዜ መሆኑን ይነግራል ፡፡“ በአፍሪካ በትልልቅ የስልጣን ደረጃ ላይ ያሉ ታላላቅ ሰዎች እና ታላላቅ መሪዎች ለመምሰል የሚያስመስሉ እጅግ በጣም ብዙ አጫጭር ወንዶች አሉ፡፡ የአፍሪካ አጫጭር መሪዎች በእርግጠኝነት ህዝብን እያሳደዱ የሚያድኑ የተኩላ ጅብ መንጋዎች ናቸው፡፡ በጣም አናሳ የሆነ እውቀት ያላቸው እና ገደብ የሌለው ጉዳት ለማድረስ ሌት ከቀን የሚታትሩ ጭራቆች ናቸው፡፡ የአፍሪካ አጫጭር መሪዎች ትንሽ ራዕይ ያላቸው እና ያልተገደበ ስልጣን ያላቸው ናቸው፡፡ አናሳ ፍቅር ያላቸው ትንሽ ወንዶች ናቸው፡፡ በጥላቻ እና ነገሮችን ሁሉ በኃይል ለመጨፍለቅ የሚተጉ ናቸው፡፡ እነዚህ በአፍሪካ ያሉ አጫጭር መሪዎች መጥፎ መሪዎች ብቻ አይደሉም፣ ሆኖም ግን መጥፎ ወንዶች መጥፎ የሰው ዘሮች ጭምር እንጅ፡፡ ረዥሙን ጥላቸውን ይዘረጋሉ፣ እናም አፍሪካን “ጨለማው አህጉር” እንድትሆን አድርገዋል፡፡ “ያለፉ (አሮጌ) ኃጢያቶች ረዥም ጥላዎችን ይዘረጋሉ፡፡”ይባላል ::  የትንንሽ ሰዎች (ያፍሪካ መሪዎች ) ኃጢያቶች በአፍሪካ ረዥም የጨለማ ጥላ ጦርነት፣ የዘር ማጥፋት እና በሰው ልጆች ላይ የሚፈጸሙ ወንጀሎችን ይዘረጋሉ፡፡

ከአጭር አፍሪካ  መሪዎች  በላይ ከፍ ብለው በመቆም ረዥሙን የጨለማ ጥላቸውን በማስወገድ በብርሃናማው የፍቅር ጸሀይ፣ እውነት፣ መቻቻል ስምምነት፣ ፍትህ እና ዕርቅ መለወጥ የእያንዳንዱ/ዷ አፍሪካዊ/ት ኃላፊነት ነው፡፡

የ1994ን ሩዋንዳ አስታውሳለሁ፡፡ የ2014 የመካከለኛው አፍሪካ ሬፐብሊክን አስታውሳለሁ፡፡ ተስፋ ከተስፋ ማጣት የበለጠ መሆን የሚችል ክስተት ነው፡፡

ኢትዮጵያ በክብር ለዘላለም ትኑር!

ሚያዝያ 7 ቀን 2006 .