4 ሚሊዮን ብር የተመደበለት የቦረና ዘመቻ በኪሣራ ተጠናቀቀ

በቦረና ዞን ውስጥ መጠነ ሰፊ እንቅስቃሴ ጀምሮ የነበረውን የኦሮሞ ነፃነት ግንባር አከርካሪ ለመስበር በሚል በኦሮሚያ ክልል ፕሬዝዳንት በኦቦ አባዱላ ገመዳና በቦረና ዞን አስተዳደር በኦቦ አደም ጅሎ መካከል በተደረገ የ4 ሚሊዮን ብር የባጀት ምደባ የተካሄደው ዘመቻ ሙሉ ለሙሉ መክሸፉን የውስጥ ምንጮች በተለይ ለዜና አገልግሎቱ ገለፁ፡፡

በተለይ በደቡቡ ቦረና ውስጥ ጠንካራ መሠረት ያለው የኦነግ ሰራዊትን ድል ያደርገዋል ተብሎ የታመነውና ከአካባቢው ሕዝብ የተውጣጣው በቂ ስልጠና የወሰደና በዘመናዊ መሳሪያዎች የተደራጀ የወያኔ/ኢህዴግ ሚሊሺያ ሰራዊት ከፍተኛ ኪሣራ ደርሶበታል፡፡

ከወራት በፊት አባ ዱላ ገመዳ አስተዳዳሪውንና ሌሎች የካቢኔ አባላትን በመሰብሰብ ሰፊ ውይይት ያደረጉ ሲሆን በወቅቱ በተያዘው ቃለ ጉባኤ ላይ እንደሚታየው “ኦነግ ካለው አፍራሽ እንቅስቃሴ የተነሳ የቀድሞውን ሥርዓት ለማምጣት ከተማማሉት ቅንጅቶች ጋር ሳይቀር ተባባሪ በመሆን ከ43 ሚሊዮን ብር በላይ ተቀብሏል” የሚል ይገኝበታል፡፡

በአስተዳደሩ አማካይነት 4 ሚሊዮን ብር በመመደቡ ቀደም ሲል ስልጠና ወስደው የነበሩ በርካታ የሚሊሺያ አባላትን በአዲስ መልክ በማሰልጠን የተደረገው ኦፕሬሽን የከሸፈ ሲሆን በአሁኑ ሰዓት ወያኔ/ኢህዴግ የደቡብ ቦረና ቤዙን አጥቷል፡፡

ቦረና ውስጥ ወያኔ/ኢህዴግ ሚሊሺያዎቹን ለውጊያ በሚያዘገጅበት ወቅት ባሌ ዞን ዶሎ መና ላይ የኦነግ ሰባተኛ ዙር ሰልጣኞች እየተመረቁ የነበረበት ወቅተ መሆኑ ብዙዎችን አስገርሟል፡፡