የነተመስገን ዘውዴ ያለመከሰስ መብት እንዲነሳ አየለ ጫሚሶ ጠየቁ

ቅንጅትን በመወከል ለሕዝብ ተወካዮች ም/ቤት የተወዳዳሩትና የፓርቲው የፓርላማ ተመራጮች
ጊዜያዊ አስተባባሪ ሆነው የቆዩት አቶ ተመስገን ዘውዴና አብረዋቸው በፓርላማ ያሉት 45 የቅንጅት ተመራጮች ያለመከሰስ መብት ሊነሳ መሆኑን የውስጥ ምንጮች ለዜና አገልግሎቱ ገለፁ፡፡

ከእስር ከተፈቱትና በተቀዳሚ ም/ሊቀመንበር ብርቱካን ሚደቅሳ ከሚመሩት የቅንጅቱ አመራር ጋር ፓርቲውን በማስረከብ ዙሪያ ሲነጋገሩ የሰነበቱት እነ አቶ ተመስገን ያለመከሰስ መብታቸው እንዲነሳ የወያኔ/ኢህአዴግና የመንግሥት ተወካይ ለሆኑት ለአቶ ሽፈራው ጃርሶ ጥያቄ ያቀረቡት ምርጫ ቦርድ የቅንጅትን ስያሜ የሰጣቸው አየለ ጫሚሶ ናቸው::

የአየለ ጫሚሶ አቤቱታ ጭብጥ “በአቶ ተመስገን ዘውዴ የሚመራው ቡድን በሕጋዊ ፓርቲያችን ላይ ሕዝቡን በማነሳሳት የተቃውሞ ሰልፍ ሊጠራብንና ሁከት ሊያስነሳብን ነው” የሚል ሲሆን በትናንትናው እለት አቶ አየለ ጫሚሶና ተባባሪዎቻችው በዮርዳኖስ ሆቴል ባደረጉት አስቸኳይ ስብሰባ ማመልከቻው አልቆ ለወያኔ/ኢህአዴግ ተወካይ አቶ ሽፈራው ቀርቧል፡፡

የወያኔ/ኢህአዴግ ተወካዩ ጭብጡን ከመረመሩ በኋላ መጀመሪያ ግለሰቦቹ የፓርቲ አባልነታቸው ይሰረዝ ባሉት መሠረት በዛሬው የእነ ተመስገን ዘውዴ የቅንጅት አባልነት ተሰርዟል ተብሏል፡፡

የአየለ ጫሚሶ ቡድን “የእሳት አደጋ ጥሪ” ያሉትን የነ አቶ ተመስገንን ያለመከሰስ መብት መነሳት የጠየቁበት ምክንያት ሰሞኑን ከህዝብ የሚሰነዘርባቸው ወቀሳና ቁጣ አስደንግጧቸው ነው ይላሉ ታዛቢዎች፡፡