የተቃዋሚ ፓርቲ እጩዎች ራሳቸውን እያገለሉ ነው

በሰሜን ሸዋ ዞን ግራር ጃርሶ ወረዳ የጉለሌ ንኡስ ወረዳ የኦፌዴንና የኦህኮ እጩዎች ያለ ህግ ስርአት በእስር ላይ ከቆዩ በኋላ ራሳቸውን ከምርጫው ማግለላቸውን ለወረዳው ምርጫ ጽ/ቤት አስታወቁ፡፡

ፍጹም ሰላማዊ በሆነ መንገድ ለፓርቲዎቻቸው በእጩነት ቀርበው የነበሩት ወጣቶች በምርጫ ቅስቀሳ ወቅት ታፍሰው ወደ ድሬ ዳለቲ ማረሚያ ቤት ከተወሰዱ በኋላ በደረሰባቸው ማስፈራርያና ዛቻ ከእስር እንደወጡ ራሳቸውን ለማግለል እንደተገደዱ አንደኛው እጩ ለዜና አገልግሎቱ ገልጸዋል፡፡ እርምጃው የወያኔን ካድሬዎች ሳይቀር ውዝግብ ውስጥ የከተተ ሲሆን በደሉ የተፈጸመው በእጩዎቹ ሳይሆን በመራጩ ህዝብ ላይ እንደሆነ እንቆጥረዋለን በማለት በዋና ከተማዋ የካምቦ ነዋሪ የሆኑትና የምርጫ አስፈጻሚ ተብለው ቢመረጡም ፈቃደኛ ሳይሆኑ የቀሩት አቶ ወርዶፋ ተሹ በተለይ ለዜና አገልግሎቱ ገልጸዋል፡፡ አቶ ቡልቻ ደመቅሳ በበኩላቸው ፍርዱን የኢትዮጵያ ህዝብ ይሰጣል ብለዋል፡፡

በሌላ በኩል የኦህኮ እጩ የነበሩ አንድ ግለሰብ በዚሁ ዞን ገብረ ጉራቻ ከተማ ላይ ወደ ምርጫ ጽ/ቤት ቦንብ ይዘው ሲገቡ ይዘናቸዋል በሚል ወደ እስር ቤት የተወሰዱ ሲሆን የከተማዋ የኦህኮ ምርጫ ሃላፊ አሳፋሪ የሃሰት ውንጀላ በማለት ድርጊቱን ኮንነውታል፡፡