የአዲስ አበባ እጩዎች ዝርዝር ይፋ ሆነ

በአዲስ አበባ ከተማ ለቀጣዩ የሚያዝያ የህዝብ ተወካዮች ም/ቤት የማሟያና የክፍለ ከተማ/የቀበሌ/ ም/ቤትየሚወዳደሩ እጩዎች ዝርዝር በዛሬው እለት ይፋ ሆነ፡፡ ዝርዝሩን የሚያሰራጩ ከ300 በላይ አባላት ተመድበዋል፡፡

በምርጫ ውድድሩ የኢትዮጵያውያን ዴሞክራሲያዊ ሃይሎች ህብረት፤ የኦሮሞ ፌዴራላዊ ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ፤ የመላው ኢትዮጵያውያን ብሄራዊ ንቅናቄ፤ የኢትጵያውያን ዴሞክራሲያዊ ህብረት፤ ኢህአዴግ፤ የግል ተወዳዳሪዎችና የአየለ ጫሚሶ ቅንጅት ይገኙበታል፡፡

አብዛኞቹ ተቃዋሚ ፓርቲዎች እጩዎቻቸውን ያቀረቡት ለተወካዮች ም/ቤት የማሟያ ምርጫ ሲሆን በአብዛኞቹ ክፍለ ከተሞች ከፍተኛ ፖለቲካዊ አንድምታ ያለውን የክፍለ ከተሞች ም/ቤት በተለያዩ ምክንያቶች ሳይሳተፉባቸው ቀርተዋል፡፡ የወያኔ ዋንኛ ትኩረት ደግሞ እነዚህ የምርጫ እድሎች በመሆናቸው ሙሉ ሃይሉን በክፍለ ከተማ ም/ቤቶች ላይ በማድረግ ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው እጩዎችን አቅርቧል፡፡ የእጩዎቹን መስፈርትም ከዚህ በፊት ያደርግ እንደነበረው ‹‹በታማኝነት›› ከማድረግ ይልቅ በምርጫ 97 ቅንጅት የተማረውን ሃይል በማሰባሰቡ ያገኘውን ህዝባዊ ድጋፍ ግንዛቤ ውስጥ በመክተት ዝቅተኛው የትምህርት ደረጃ 12ኛን ያጠናቀቀ እንዲሆን በማድረግ የሃይል ሚዛኑን ለመቀየር ሲንቀሳቀስ ቆይቷል፡፡ በዚህ መሰረትም ለምርጫው ከሚቀርቡት ከ60 በመቶ በላይ ያህሉ የመጀመርያ ድግሪ ያላቸው እንዲሆኑ አድርጓል፡፡ በዝርዝሩ ዙርያ ተቃዋሚዎች በዚህ ሳምንት መግለጫ ይሰጣሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡

በክልል ለምርጫው ከቀረቡ የተቃዋሚ ፓርቲ እጩዎች በደረሱባቸው የተለያዩ ተጽእኖዎች የተወሰኑት ራሳቸውን ማግለላቸውን ፓርቲዎቻቸው የገለጹ ሲሆን በአዲስ አበባ ወረዳ 18 ሪቼ አከባቢ መኢብንን በመወከል እጩ ሆነው የቀረቡትና ቀድሞ የፓርላማ ፕሮቶኮል ሹም እንደነበሩ የሚታወቁት ወ/ሮ ገነት አየለ ተመሳሳይ ማስፈራርያ ደረሰኝ በማለት ራሳቸውን ከምርጫው ማግለላቸውን ሊቀ መንበሩ አቶ መስፍን ሽፈራው ገልጸዋል፡፡

ይህ በእንዲህ እንዳለ በጋሞጎፋ ዞን የዛላ ወረዳ የቅንጅት አስተባባሪ የነበሩትና ባለፈው ሳምንት ከስራ ቦታቸው ታፍነው በመወሰድ ታስረው የነበሩት አቶ አየለ የመጨረሻ ማስጠንቀቂያ ተሰጥቷቸው ተፈተዋል፡፡ አስተባባሪው ከስራ አስፈጻሚው ቡድን ጋር አንዳችም አይነት ግንኙነት ሲያደርጉ ቢገኙ ሃላፊነቱን እንደሚወስዱ አስፈርመው እንደፈቷቸው ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡