በቅንጅት አስተባባሪዎች ላይ የተከፈተው ጥቃት ቀጥሏል

በመላው አገሪቱ በሚገኙ የቅንጅት አስተባባሪዎችና ለፓርቲው ከፍተኛ አስተዋጽኦ በሚያበረክቱ ግለሰቦች ላይ የተከፈተው ያለ ህግ ስርአት የማሰርና የማንገላታት ጥቃት መቀጠሉን አንድ የአመራር አባል ለዜና አገልግሎቱ ገለጹ፡፡

በደቡብ ኦሞ ዞን የጂንካ ወረዳ የቅንጅቱ አስተባባሪ የነበሩት አቶ ከተማ በላቸው በተመሳሳይ መንገድ የጥቃቱ ሰለባ በመሆን ላለፉት ሶስት ቀናት በእስር ላይ ከቆዩ በኋላ ዛሬ ከሰአት በኋላ በዋስ ተለቀዋል፡፡ በእስር የቆዩባቸውን ቀናት አስመልክቶ የነበራቸውን የፖሊስ ጣቢያ ምርመራ አስመልክቶ በስልክ በሰጡን አስተያየት ‹‹የፈጠራ ክስ መስርቶ የሃሰት ምስክሮችን ለማቅረብ ከፍተኛ ጥረት ሲካሄዱባቸው የቆዩባቸው አስነዋሪ ቀናት ነበሩ፡፡›› በማለት ገልጸዋል፡፡ አስተባባሪው የክልሉ ተወላጅ እንደሆኑ ቢታወቅም ብሄር ላይ ያተኮረ አሉታዊ ቅስቀሳ አድርገዋል የሚል ክስ እንደቀረበባቸውና ፍርድ ቤቱ የቀረበው ክስ ተጨባጭ መረጃ የሌለው ነው በማለት በዋስ እንዲሰናበቱ ማድረጉን አብራርተዋል፡፡

እንደ አቶ ከተማ አባባል በወረዳዋ ያሉት አብዛኞቹ አባላት በየጊዜው በሚደርሱባቸው እስር፤ ዛቻና ማስፈራርያዎች ራሳቸውን ከፓርቲ አባልነት በማግለል ላይ መሆናቸውን በሃዘን በማስታወስ በተለይ ሊቀመንበሩ ወስደዋቸው የነበሩት አስገራሚ የእግድ ውሳኔዎች ለበርካታ አባላት ፓርቲውን መልቀቅ መንስኤ እንደሆኑ ጠቁመዋል፡፡ በክልሉ ያሉት የፓርቲው አባላትና ደጋፊዎች በወ/ሪት ብርቱካን ሚደቅሳ ከሚመራው የስራ አስፈጻሚ ቡድን ጋር ቀጥተኛ ግንኙነት እንደሚያደርጉ በመግለጽ ፈታኙ ትግል ፍሬ እስከሚያፈራ በጽናት ለመቆም ቁርጠኝነታቸውን ጠብቀው እንደሚቆዩ ያላቸውን እምነት ጨምረው ገልጸዋል፡፡