ፕሬዜዳንት ኦባማ በሁለተኛው ዙር ምርጫ ምን ይጠበቅባቸዋል

ከፕሮፌሰር  ዓለማየሁ  ገብረማርያም

ትርጉም  ከነጻነት ለሃገሬ

ፕሬዜዳንት ኦባማ ሁለተኛውን ዙር የፕሬዜዳንትነት ምርጫ በማሸነፋቸው እንኳን ደስ ያለዎት ማለቱ አግባብ ነው፡፡ የአሜሪካንን መራጮች አብላጫ ድምጽ አግኝቶ ለማሸነፍ ብቃት ባለው አካሄድ ለድል በቅተዋል፡፡ ሚት ሮምኒም ለማይናቀው የምርጫ ግብግባቸው ሊመሰገኑ ተገቢ ነው፡፡ በማጠቃለያው የመለያያ ንግግራቸው ላይ ሚት ሩምኒ ግሩም የሆነ መልእክት አስተላልፈዋል፡፡ ‹‹በእንደዚህ አይነቱ ወቅት የደጋፊዎቻችንን ስሜታዊ ጫጫታ ማዳመጥ፤የፖለቲካ አካኪ ዘራፍ ባይነትን ለማስተናገድ ጊዜው አይደለም፡፡ መሪዎቻችን የሕዝቡን ፍላጎትና ምኞት ለማሳካት መንቀሳቀስ ሲኖርባቸው እኛ ሕዝቦች ደግሞ ለዚህ ሂደት አስፈላጊውን ድጋፍና ትብብር ለማድረግ በቀናነት መነሳሳት ይገባናል” ብለዋል::

ባለፈው ሳምንት በተከናወነው የምርጫ ሂደት ወቅት አንዳንድ ኢትዮጵያዊያን አሜሪካውያን በቁጭትና በምሬት ጣቶቻቸው እየጠቆሙ ሮሮ ምሬታቸውን አሰምተዋል:: ጥርሳቸውን በማቀጫቀጭ ንዴታቸውን አሳይተዋል:: ፤አይናቸው በቁጭት ቀልቷል፡፡ከፊሎቹ በፕሬዜዳንት ኦባማ ተግባር አዝነው ለተቃዋሚዋው አቻቸው ቅስቀሳ ሲያደርጉ ነበር፡፡ በአፍሪካና በኢትዮጵያ ስለሰብአዊ መብት ቀደም ሲሉ የተናገሩትን አጓጊና ተስፋ ያዘለ ዲስኩራቸውን ወደ ተግባር ለውጥው አንዳች ለውጥ ባለማምጣታቸው በኢትዮ አሜሪካውያን ዘንድ ክህደት አለያም ድክመት ሆኖ ታይቶባቸዋል፡፡ ከፊሎች ደግሞ ፕሬዜዳንቱ በአፍሪካ ላሉ ፈላጭ ቆራጭ ገዢዎች ደጋፊና ረዳት በመሆናቸው ተቀይመዋል፡፡ ሌሎች ደግሞ ፕሬዜዳንቱ ስላጋጠማቸው ሃገራዊ ችግርና ስለነበረባቸው ውጥረት አዝነውላቸዋል፡፡ የአሜሪካንን ዓለም አቀፋዊ ጥቅም ለማስጠበቅ የሚያስችለውን የአሜሪካንን የውጭ ፖሊሲ ማስተካከልና መቅረጽ ነበረባቸው፡፡ ለአሜሪካ በአፍሪካ ቀንድ አካባቢ የተከሰተው ሽብርተኛነት አሳሳቢ ነበርና ኦባማ ደግሞ ሽብርተኝነትን ለማክሰም ሰብአዊ መብትን ከጸረ ሽብርተኝነት ዓለም አቀፍ እንቅስቃሴ ጋር ማቀናጀት ነበረባቸው፡፡

እኔም ፕሬዜዳንቱ በመጠኑም ቢሆን ሰብአዊ መብትን በተመለከተ አጀንዳ ለመቅረጽ ባለመቻላቸው በምር ቅር ተሰኝቼባቸዋለሁ፡፡ ከዚሁ ጋር ደግሞ በአሜሪካ ውስጥ ስለአለው የኤኮኖሚ ችግር፤አንዳንድ አጣዳፊ የሆኑ ሶሻል ፖሊሲዎችን መንደፍ፤ስለነበረባቸው ሁለት ጦርነቶችን በማካሄድና በዓለም ዙርያ የተነሱና የተካረሩ ግጭቶችን ጦዘው ችግር ከማባባሳቸው አስቀድሞ ማስታገስ ስለነበረባቸው ነው በሚል አልፋቸዋለሁ፡፡ በደቡብ ሱዳን ሬፈረንደም ላይ ስለወሰዱት አቋምና ስለተገኘውም ድል አንድ ሌላ አፍሪካዊ ሃገር እንዲፈጠር በመቻላቸው አደንቃቸዋለሁ፡፡

ፕሬዜዳንት ኦባማ ጥቂት የአሜሪካ ወታደሮች ሃይል እንዲዘምትና ያን የደም ጥማት አራራው አናቱ ላይ የወጣበትን ጆሴፍ ኮኒንና የደም ጥማት ጓደኞቹን እንዲይዟቸው ካልተቻለም እንዲገሏቸው ማዘዛቸው ታላቅ ድርጊት ነው፡፡ እንደኔ እምንት በጣም ትልቅ የሚባል ክሌፕቶክራሲ ፕሮጄክት ፕሮጄክት (ወሮበላአገር በዝባዞች) ተግባራዊ ማድረጋቸውም ታላቅ ተግባር ነው፡፡ ‹‹አፍሪካ ሙሳዊነት ብክነት›› (Africorruption, Inc.”,) በሚለው መጣጥፌ ላይ እንዳቀረብኩት፤ዋነኛው የአፍሪካ መሪዎች ተግባራቸው ሙስና ነው ብዬ ነበር፡፡ አብላጫዎቹ የአፍሪካ ገዢዎች ዋነኛ መመርያቸውና ተግባራቸው የራሳቸውን ሃገር ብሔራዊ የገንዘብ ተቋማትና ሪሶረሱን በመበዝበዝና በመስረቅ፤እጅጉን የተወሳሰበ የግድያና የወንጀል ኢንተርፕራይዝ መፍጠር ነው፡፡ እንደ ግሎባል ፋይናንሻል ኢንተግሪቲ ዘገባ በስውርና በሰበብ አስባቡ ከኢትዮጵያ ወደ አሜሪካ የፈረጠጠው የሃገሪቱ ሃብት ከ2000-2009 ባለው ጊዜ  $11.7 ቢሊዮን ዶላር ነው፡፡ በሊቢያ ሕዝብ ላይ ላለፉት 41 ዓመታት ተንሰራፍቶ ፍዳቸውን ሲያበላቸው የነበረውን የሊቢያውን ጋዳፊን ከስር መሰረቱ ነቅሎ ለመጣልና ለሊቢያውያን የእፎይታ ዘመን ለማምጣት በተባበሩት መንግስታት መመርያ ላይ በመንተራስ የተባበሩት መንግስታት የ1973ን ውሳኔ  ሬዞሉውሽን እንዲያልፍ በማድረጋቸውና አብላጫውን የጦሩን ሂደት የኔቶ አባል ሃገራት ሃላፊነት እንዲሆን በማድረጋቸው እጅጉን አደንቃቸዋለሁ፡፡ ከዚህም ባለፈ በጠነከረ አመራር የሚስጥር የነበሩትን የሲ አይ ኤ ወህኒ ቤቶች እንዲዘጉና የነበረውም ስቃይና የመከራ አመራመር እንዲያበቃ አድርገው የጓንታኔሞ ቤዝም ተዘግቶ የፍርድ ሂደቶች ሁሉ አግባብነት ወዳለው የሲቪል ፍርድ ቤቶች እንዲዛወር በማድረጋቸው የዓለም አቀፍ ሰብአዊ መብት ድንጋጌዎች እንዲከበሩ በወሰዱት እርምጃ አከብራቸዋለሁ፡፡ በኢትዮጵያ ብሎም በጠቅላላው አፍሪካ አህጉር ስለ ሰብአዊ መብት ብዙ ሊያደርጉ ሲችሉ አላደረጉትም፡፡ ባለፉት ሁለ፤ት ዓመታት ስለአሜሪካ ፖሊሲ ድክመት በርካታ ጦማሮችን ጽፌያለሁ፡፡ በአፍሪካ የአሜሪካ ፖሊሲ ድክመት አሜሪካም ሆነ ሌሎች አውሮፓ ሃገሮች በአፍሪካ ያለውን ዴሞክራሲና ሰብአዊ  መብት ሁኔታ ፍላጎታቸውን እምነታቸው በስልጣን  ለመቆየትና የሃገሪቱንና የሕዝቡን ነንብረትና ሃብት በመበዝበዝ ራሳቸውንና አሽቃባጮቻቸውን ለማቶጀር የሚንደፋደፉትን  የአፍሪካን ፈላጭ ቆረጭ ገዢዎች በመንከባከብ ለውለታ ሰሪነት ሊገዙበት እንደማይገባ አሳስቤያለሁ፡፡

“ሰግታቶርሺፕ (የወሮበላ መንግስት)፡‹‹ በአፍሪካ ከፍተኛው የጦዘ የፈላጭ ቆራጭነት አገዛዝ ደረጃ›› በሚለው አምዴም ላይ እነዚህ የአፍሪካ የቀን ጅቦች ገዢዎች የዘለቀና በጥቅም ላይ የተመሰረተ የወዳጅነት ግንኙነት አላቸው በማለት ሞጋቻቸዋለሁ፡፡ በእርዳታና በንግድ ስም የምዕራቡ ዓለም በተለይም አሜሪካ እነዚህ ሰውበላ ገዢዎች በአፍሪካ ውስጥ እንዲበራከቱ ብርታት ሆነዋቸዋል፡፡ ከጥቂት ወራት በፊት ‹‹ኢትዮጵያ በቦንድ ኤይድ ውስጥ›› በሚለው ጽሁፌ ላይ ዓለም አቀፉ እርዳታ አፍሪካን በአፍራሽ ጎኑ እየጎዳት እንደሆነ  አሳስቤ ነበር፡፡ በ1960ዎቹ አብዛኛው የአፍሪካ ሃገራት ነጻ ከመውጣታቸው አስቀድሞ  አፍሪካውያን በኮሎኒያል ማነቆ ተወጥረው ነበር በማለት ጥፌ ነበር፡፡ በቅርቡ ባሰፈርኩት ማሳሰቢያ ጽሁፌም ኢትዮጵያ ‹‹ምግብ ለችጋር፤እና አስተሳሰብ››  በሚለው አምድ በቅርቡ በዋሽንግቶን የተደረገውን የጂ 8 ስብሰባን አስመልክቼ ስብሰባውና የሚያስተላልፈው ውሳኔ ያለፈውን ለአፍሪካ ሲደረግ የነበረውን የቅኝ ገዢዎች መቀራመት የተካ ነው በማለት አስተያየቴን አስፍሬ ነበር፡፡ የጂ 8 አባላት አዲሱ ጥምረታቸው፤ አፍሪካን ከችጋር ለማላቀቅ፤ ርሃብንና ድርቅን ለማሰወገድ በአፍሪካ ውስጥ የያሉትን ምርጥና ለም ቦታዎች ለጠገቡት የዓለም የናጠቱ ሃብታሞች በመስጠት ማቀዳቸውንም አሳውቄያለሁ፡፡

በኢትዮጵያ አልፎም በመላው አፍሪካ ውስጥ የኦባማ አስተዳደር ሊያደርግ ሲችልላ ባላደረጋቸው የአፍሪካውያን ፍላጎትና ራዕይ ላይ አንዳችም ጉዳይ ባለማድረጉ ካለኝ ቅሬታ ባሻገር  ፕሬዜዳንት ኦባማን በዳግም ምርጫው ወቅት ደግፌያቸዋለሁ፡፡ ከነስህተታቸው ተስፋ የሚጣልባቸው መሪነታቸውን አሳይተውኛልና፡፡ በ2004 ሴነተር ኦባማ ባደረጉት መሪ ንግግራቸው፤ ‹‹ጥቁር አሜሪካውያን፤ነጭ አሜሪካውያን፤ላቲና አሜሪካ፤ኤሽያ አሜሪካ ብሎ ዜጋ የለም፡፡ያለው አንድ የተባበሩት አሜሪካ ብቻ ነው፡፡›› እነዚህ ቃላቶች ምንግዜም እያነቃቁኝና ተስፋዬንም እያለመለሙት ወጣቱ የኢትዮጵያዊያን ትውልድ ወንድ ሴት ሳይል በአንድነት ተሰባስበው በመግባባትና በመፈቃቀር ‹‹ኦሮሞ ኢትዮጵያ፤አማራ ኢትዮጵያ፤ትግራይ ኢትዮጵያ፤ጉራጌ ኢትዮጵያ፤ኦጋዴን ኢትዮጵያ፤ አኝዋክ ኢትዮጵያ…… ብሎ ዜጋ የለም ያለው ፤ ፍትሕ እንደውሃ እኩል የሚፈስባት ህብትና ልማትም እንደታላቅ ምንጭ የሚፈልቅባት   አንድ የተባበረች ኢትዮጵያ እንጂ›› የሚልበት ወቅት እንደሚመጣ  ቁልጭ ብሎ ይታየኛል፡፡

ሰብአዊ መብት 2003ን ረቂቀ ህግ  (“Ethiopia Democracy and Accountability Act of 2007”) ሲካሄድ በነበረው የውይይት መድረክ ላይ በወቅቱ የሴኔተር ኦባማ የሥራ ባልደረቦች ጋር በቢሯቸውና ለበርካታ ጊዜያት ተገናኝተን ነበር፡፡ በዚያን ወቅት ቢሉ በምክር ቤቱ  አልፎ ወደ ሴኔት ሲደርስ ኦባማ ሙሉ ድጋፋቸውን እንደሚሰጡ ምንም ጥርጣሬ አልነበረም፡፡ በፌብሪዋሪ 2008 የምክክር ስብስባችን የባሮክ ኦባማን የፕሬዜዳንትነት ውድድርን ተመራጭነት ሙሉ በሙሉ ድጋፉን ሰጥቷል፡፡ በዚህም ጊዜ አሜሪካ በአፍሪካ ላሉት ፈላጭ ቆራጭ መሰሪ ገዢዎች ድጋፍ ሙሉ በሙሉ እንደሚያቋርጥ ተስፋችን ብሩህ ሆኖ ፖሊሲውም የአፍሪካውያንን ራዕይ የሚያጠናክር ተስፋቸውንም የሚያጎላ እንሚሆን አምነን   ነበር፡፡ ወቅቱም የአሜሪካ ፕሬዜዳንት በኢትዮጵያ ያለውን የሰብአዊ መብት ረገጣ በማጥፋት ይህንንም ሲያደርጉ የነበሩትን ሰው በላዎች ከስልጣናቸው እንደሚያወርዳቸው የላቀ ራዕይ ሰንቀን ነበር፡፡

አፍሪካ በአሜሪካኑ የአጀንዳ ፖሊሲ አወቃቀር ላይ አንሶ በመገኘቱ፤ ባለፉት አራት ዓመታት ፕሬዜዳንቱ በሌሎች ስራዎች በመጠመድና ለሃገራቸው ቅድሚያ በመስጠት በመየያዝ አፍሪካ ከነበረችበት ለባሰ ፈላጭ ቆራጭ የቀን ጅቦች መፈንጫ ሆነች እንጂ ተስፋው አልተተገበረም፡፡ በቅርቡ በተካሄደው ‹‹የውጭ ፖሊሲ ክርክር ላይ› አፍሪካ ለይስሙላ ያህል ነው የተጠቀሰችው፡፡ በዓለም በድህነት በሶስተኛ ደረጃ ላይ ባለች ማሊ  አልቃይዳ ስለመኖሩ እግረመንገድ ገለጻ ነበር የተደረገው፡፡ (እንደ ኢኮኖሚስት መጽሔት ገለጻ፤ ኢትዮጵያ በዓለማችን የመጨረሻዋ ድሃ ሀገር ናት  ናት) ለማቻቻል ሳይሆን እርግጥ ነው ፕሬዜዳንቱ በአጀንዳቸው ላይ በርካታ ፈታኝ ጉዳዮች ነበሩባቸው፤የአረቦች መነሳሳት እንደሰደድ እሳት እየተቀጣጠለ ዘመን ያስቆጠሩ ፈላጭ ቆራጭ ገዢዎች እየመነጠረ ነበር፤ በመካከለኛው ምስራቅም የኒውክሊየር ጉዳይ አሳሳቢ ሆኖ መጥቷል:: ፤ በአውሮፓም የተከሰተው የኤኮኖሚ ውድቀት አውሮፓን ሊሽመደምድ እየዳዳው ነው፡፡

ተስፋ በኢትዮጵያ ብሎም በአፍሪካ ምን ግዜም ዘልዓለማዊ ነው፡፡

በዚህ የፕሬዜዳንት ኦባማ ዳግም የፕሬዜዳንትነት የሥራ ዘመን በአፍሪካ ያለው የሰብአዊ መብት ጉዳይ በፕሬዜዳንት ኦባማ የውጭ ፖሊሲ አጀንዳ ላይ ትኩረት የሚሰጠው ጉዳይ እንደሚሆን የላቀ ተስፋ አለኝ፡፡ ለዚህም አመላካች የሚሆነው በምርጫው ማግስት ፕሬዜዳቱ ማይነማርን (በርማ) ከሁለት ሳምንት በኋላ ለመጎብኘት ማቀዳቸው ነው፡፡ ፋይዳ በሌለው ከአሃምሳ ምስት አመት ወታደራዊ  አገዛዝ ዘመን በኋላ ማይነማር ቀስ በቀስ ወደ ዴሞክራሲያዎ ስርአት እያመራች ነው፡፡ ፕሬዜዳንት ቲየን ሲየን የፖለቲካ እስረኞችን ሁሉ እየለቀቁ ነው፡፡ የዜና ማሰራጫዎችን ሁሉ ማዕቀቡና ቁጥጥሩ እየተነሳላቸው:: ፤ የፖለቲካና የኢኮኖሚ ለውጥሪፎርም እየተካሄደ ነው፡፡ከሃያሁለት ዓመታት የግፍ የቤት አስር ወጥተው አውንግ ሳን ሱዊ ኪ በፓርላማው እውቅና የተሰጣቸው ሕጋዊ ተቃዋሚ ሆነዋል፡፡እንደ አሜሪካ ድምጽ ሬዲዮ ዘገባም፤የስቴት ዲፓርትመንት አፈ ጉባኤም በኢትዮጵያ ስለሚታየው የሰብአዊ መብት ጉዳይ አጽንኦት እንደተሰጠው ተደምጸዋል፡፡ የኦባማ አስተዳደር በአፍሪካ ስላለው ጉዳይ ቆራጥ አቋም ይዞ ሰብአዊ መብትን ለሕዝቡ እንደሚያስገኝ አንዳንድ ምልክቶች እየታዩ ነው፡፡

ፕሬዜዳንት ኦባማ ለአፍሪካ ዘልዓለማዊና የማይነጥፍ የዴሞክራሲ ልዕልና የመመስረት ዓላማ አላቸው

በተለምዶ  ዳግም ምርጫ በአሜርካ አብዛኛው ትኩረቱ በውጪ ፖሊሴ ላይ ያነጣጠረ ነው፡፡ በዚህ ወቅትም በይበልጥ የሚያስቡበትና ሊተገብሩም የሚሹት፤ከአግልግሎታቸው ፍጻሜ በኋላ የሚተዉትንና ዘመን ሊያስታውሰው የሚችለውን መልካምና ዘላቂ ድርጊታቸውን ነው፡፡ፕሬዜዳንት ኦባም ለአፍሪካ የማይዘነጋና በቅርስነት የሚታሰብ የሰብአዊ መብት መከበር ስጦታ ትተው ማለፍ ነው ዓላማቸው፡፡በእርግጠኝነትም እሳቸው ወደ ሥልጣን ከመጡበት ጊዜ በባሰ ሁኔታ ውስጥ አፍሪካን ጥለው መሄድ አይፈልጉም ብዬ አስባለሁ፡፡ ፕሬዜዳንት ኦባማ ወደስልጣን በመጡበት ጊዜ ጦር ሰብቀው አለያም ምርጫን አጭበርብረው፤ወደስልጣን የወጡ የአፍሪካ ገዢዎች የበረከቱበት ነበር፡፡ በአሁኑ ወቅት ደግሞ  አፍሪካ ውስጥ በአብዛኛው ያሉት ገዢዎች የሕግ የበላይነት ጨረሶ የጠፋበትና ሕግ ማለት እነዚሁ ፈላጭ ቆራጭ ገዢዎችና ሆድ አደር አገልጋዮቻቸው የሆኑበት፤ በመሆናቸው ሁኔታው ለአእምሮ የሚሰቀጥጥ ነው፡፡ የሰብአዊ መብት ገፈፋ የዕለት ተዕለት ተግባራቸው ነው፡፡በኢትዮጵያ ውስጥ ጋዜጠኞች፤ የሰብአዊ መብት ተሟጋቾች፤የተቃዋሚዎ ፓርቲ መሪዎች፤ሰላማዊ መብት ጠያቂዎች፤ይታሰራሉ፤አለፍርድ በየዕለቱ በገዢዎቹ በየስለላ ድርጅቶች አባላት ስቃያቸውን ያያሉ፡፡

ምንም እንኳን በአሜሪካ ተወልደው ቢያድጉም ለፕሬዜዳንት ኦባማ አፍሪካ የአባታቸው ሃገር ነው፡፡እንደማንኛውም ኢትዮጵያዊ አሜሪካ ኦባማም አሁጉሩን ከድህነት ማውጣት ብቻ ሳይሆን፤ በአፍሪካ ውስጥ የሰብአዊ መብት ተከብሮ፤ነጻና ፍትሐዊ ምርጫም እንዲካሄድበት፤ የሕግ የበላይነትም የሚጠበቅበት እንዲሆን ምኞት እንዳላቸው አልጠራጠርም፡፡‹‹ከአባቴ ሕልሞች ›› በተባለው መጽሃፋቸው “….በአባቴ ገጽታ ውስጥ ነበር፤ከዚያ ጥቁር ሰው፤ከአፍሪካው ልጅ፤በኔ ውስጥ የተጠራቀመውን መልካም ዋጋ ሁሉ፤የማርቲንን፤ የዱቧንና የማንዴላን ብርታት የተቸርኩት››፡፡ እነዚህ ሰዎች ባሳለፉት የትግል ጥንካሬያቸውና ብርታታቸው እንደራሴ በማየት፤ ባከብራቸውም ያ የአባቴ ድምጽ ግን ምንገግዜም ሳይለየኝ የማደርገውን ሁሉ እየፈቀደልኝና እየመራኝ አብሮኝ አለ፡፡ፕሬዜዳንት ኦባም በዚሀ የሁለተኛው ዘመን አመራራቸው አፍሪካውያን ለሰብአዊ ክብራቸው በሚያደርጉት ትገል አፍሪካውያንን እንደሚያግዙና ለድልም እንደሚያበቋቸው አልጠራጠርም፡፡

በአረብ የመነሳሳት ወቅት የአሜሪካ የውጭ ፖሊሲ ሁኔታ

በአረቦች መነሳሳት ወቅት የአሜሪካን መንግስት የነበረውን የሰብአዊ መብት ፖሊሲሰ ከ ደህንነትና የኤኮኖሚ ጠቀሜታ ጋር ማዋሃዱን ሂደት ከ እብሪተኞች ፈላጭ ቆራጭ መሪዎች ከሚያደርገው አመለካከት ጋር በድጋሚ ማጥናት፤ ሁኔታዎችን ማገናዘብ፤ መመርመር ማስተካከልም እንዳለበት ተገነዘበ፡፡ የአካባቢውን የደህንነትና የመረጋጋት ሁኔታና ዋስትና በዲክታተር መሪዎች አመኔታ ላይ በማድረግ የአረብ ዓለሙን ሕዝቦች ስቃይና መከራ፤ የሚፈጸምባቸውን ግፍ በቸልታ ማሳለፉን ታሪክ ያሳያል፡፡የአረቡ ዓለም የበቃኝ ሂደት ሲፈነዳና ሕዝቡ በእምቢታ ለነጻነት ለሰብአዊ መብት መከበር ለዴሞክራሲ እውነታ ሲነሳሳ የአሜሪካ አስተዳደርም በመደናገጥና ግራ በመጋባት የሚያደርገው ተዘበራረቀበት፡፡

የአሜሪካ መንግስት ከአፍሪካ የፈላጭ ቆራጭ ገዢዎች ጋር ያለውን ሁኔታ አያይዞ የሚመለከተው በአካባቢው ካለው ደህንነትና መረጋጋት ጋር ስለነበር፤የሰብአዊ መብትንና ሌሎችንም ሕዝባዊ መብቶች ማንሳቱ ከእነዚህ አረመኔ ፈላጭ ቆራጭ ገዢዎች ጋር ስለሚያጋጨው ትብብራቸውን ላለማጣት ፍርሃት አለው፡፡ከዚህም በመነሳት ሁኔታዎቹ ሲታዩ የአሜሪካን መንግስት ከዝምታ የዲፕሎማቲክ ፖሊሲና የቃላት ባዶ ተስፋ ከመቸር ያለፈ ተግባር በአፍሪካ ውስጥ አላከናወነም፡፡ ፕሬዜዳንት ኦባማ የአሜሪካ ዘላቂ ዓለም አቀፍ ፍላጎት የሞራል ማስታገሻ ድጎማ ቃላትና ድርጊትን በማውገዝ ብቻ አንዳችም እርምጃ እንደማያስኬድ እንደሚያውቁ አልጠራጠርም፡፡ የፕሬዜዳንቱ አካሄድ በቅድሚያ የዲፕሎማቲክ አካሄዱን በሚገባ ማስኬድና ውጤቱን ተመልክቶ ካልሆነ አስቀድመው ወደመጨረሻው አማራጫቸው እንደማይገቡ የታየ ነው፡፡እንዳሉትም ‹‹የሰብአዊ መብትን ተግባራዊ ማድረግ የሚቻለው በቃላት በሚሰነዘሩ ሂደቶች ብቻ ሊሆን አይችልም፡፡ አንዳንድ ጊዜም እጅጉን በጠነከረ የዲፕሎማሲ ግንኙነትና ድርድር መሞከር አለበት፡፡ እርግጥ የሰብአዊ መብት ሂደትን በተመለከተ ከግፈኛ መሪዎች ጋር የሚደረግ መግባባት በጣሙን አስቸጋሪና በእምቢታና በጀብደኝነት ላይ የተመሰረተ እንደሆነ እገነዘባለሁ፡፡ ማንኛውም ጨቋኝ መንግስት መውጫ መንገድ እስካላገኘ ድረስ ከነበረበት ዝቅ ብሎ መውረድን አይቀበልም፡፡ ባለፉት ጥቂት ዓመታት ጥቂት የአፍሪካ መሪዎች በተከፈተላቸው በር በመውጣት የዴሞክራሲንና የሰብአዊ መብትን መከበር ተቀብለዋል፡፡ አብዛኛዎቹ  ደግሞ የተከፈተላቸውን የሠላም በር በአጉል ንቀትና በማያዋጣቸው ማንአለብኝነት በርግጫ መልሰው ዘግተውታል፡፡ በጣም እርግጠኛ ነኝ ፕሬዜዳንቱ በሁለተኛው የአስተዳደር ዘመናቸው ከቃላትና ከማስታመም አልፈው የአፍሪካን መሪዎች የእርዳታና የችሮታ ከረጢት በእጃቸው ስለያዙ ሸምቀቆውን በማጥበቅና በማላላት አካሄዳቸውን ሊያስለውጡና በአፍሪካ የተናፈቀውን የነጻነት መንገድ እንደሚያስተካክሉት እምነቴ ነው፡፡

ፕሬዜዳንት ኦባማ ፕሬዜዳንት ብቻ ሳይሆኑ የሕገመንግስታዊ ጠበቃም ናቸውና……..

ፕሬዜዳንት ኦባማ መሪ ከመሆናቸው በፊት ያካበቱት ልምድ አሁንም በአስተሳሰባቸውና በድርጊታቸው ላይ ጫና እንደሚፈጥርባቸው አምናለሁ:: እንደ ኮኒስቲቲዩሻናልና የሲቪል የሕግ ባለሙያነታቸው፤  ስለሕግ መዛባትና ስለሞራል ድክመት፤ ስለሰብአዊ ክብር መደፈርና ሌሎችም ተመሳሳይ ጉዳዮች የጠነከረ ልምድና እምነት አላቸው፡፡ ለረጂም ዓመታት በሰብአዊ አገልግሎት፤ በሕብረተሰብ ፍላጎትና ጥቃትን በመከላከል ዘርፍ ብዙ ሰርተው በርካታ ልማድ ያላቸው ናቸው፡፡ የተቸገሩትናና አቅመ ደካሞችን፤ በቤተክርስቲያናት በኩል በማደራጀትና በመርዳት ብዙ ከውነዋል፡፡ የኮሙኒቲ ተግባራቸው የታመቀ ልምድ አስጨብጧቸዋልና ያወውቁቅታል፡፡ ፕሬዜዳንት ኦባማ የሕግን የበላይነት ጥቅሙን ይረዱታል የሚል ጠንካራ እምነት አለኝ፡፡የሕግ ምሁርና የተቸገሩ ምስኪኖች ተሟጋች እንደመሆናቸውም ማንኛቸውም የችግር ምንነት በአግባቡ የገባቸው ናቸው፡፡ስለዚህም ለሕብረተሰብና ለአካባቢ ሰዎች ያላቸው ተሟጋችነት በዚህ የሁለተኛው አስተዳደር ዘመናቸው ጎልቶ ይወጣል እላለሁ፡፡

አንዳንዶቻችን ፕሬዜዳንት ኦባማ ምን ሊያደረጉልን ይችላሉ በሚለው ጥያቄ እንታለላለን፡፡ ትክክለኛው ጥያቄ ግን እኛስ በመደራጀት፤የኦባማን አስተዳደር በእውነተኛው ሁኔታ ላይ በማግባባት፤ጠንካራ የሰብአዊ መብት አጀንዳ እንዲቀርጽ ለማድረግ ምን እያደረግን ነው የሚለው መሆን አለበት፡፡ፕሬዜዳንት ኦባማ ምርጫውን ባሸነፉበት ማታ ባደረጉት ንግግር ‹‹በእኛ ዴሞክራሲ የዜጎች ሚና በሰጣችሁት ድምጽ ብቻ የሚገታ አይደለም፡፡ አሜሪካ ፈጽሞ ለኛስ ምን ይደረግልናል ሃገር ሆኖ አያውቅም፡፡ይልቅስ በእኛስ በኩል ሊደረግ የሚገባው ምንድን ነው፤በዚህ አስቸጋሪና ፈታኝ ወቅት ግን አስፈላጊና የራሳችን በሆነው መንግስት ምን ይጠበቅብናል የሚለው ነው›› ገቨርነር ሮምኒ በመጨረሻው የማክተሚያ ንግግራቸው እንዳሉት ‹‹ በእንዲህ አይነቱ ወቅት እርስ በርስ መነቃቋርና ባለፈው  ጥርስ በመንከስ መለያየት የለብንም፡፡ መሪዎቻችን ባሻገር ተጉዘው የሕዝቡን ፍላጎት ማሟላት ሲገባቸው እኛ ሕዝቦች ደግሞ ጊዜው የሚጠይቀውን ማድርግ ግዴታችን ነው፡፡››……. ይህ ነው የኢትዮጵያዊያን አሜሪካውያን እምነት ሊሆን የሚገባው፡፡ በዲያስፖራውም በሃገራችንም ውስጥ፡፡ ይህንን ነው አምነን በመቀበል መተግበር ያለብን፡፡ካለፈው ስህተታችንና ድክመታችን በመማር እራሳችንን አስተካክለንና ሂደታችንን አርመን የኦባማ አስተዳደር ተገቢውን እንዲያደርግ መጎትጎት ያለብን፡፡ የአረብ አሜሪካኖች፤ኢራንያን አሜሪካኖች፤አርሚኒያን አሜሪካኖች፤ማሲዶንያን አሜሪካኖች፤ሰርቢያን አሜሪካኖችና ሌሎችም ከአስተዳደሩ ጋር በጥንካሬያቸው በመሞገት ተግባራቸው ውጤታማ ሆኗል፡፡ እንደሰብአዊ መብት ተሟጋቾችና ጠበቆች፤የአሜሪካ ቀዳሚ ባለስልጣናት ጋር በመቀራረብና በመነጋገር በመግባባት ስለሰብአዊ መብት የሃገራችን ሁኔታ በማስረዳት ውጤታማ መሆን ይጠበቅብናል፡፡

የአሜሪካን መንግስት ዲክታተሮች የሆኑ  አመራሩ ላይ የተቀመጡት ወዳጆቹን ማንበርከኩን ያወቅበታል፡፡በ1980 የአሜሪካን መንግስት በፊሊፒንስ፤በቺሊ በታይዋን እና በምእራብ ኮሪያ ውስጥ በተካሄደው የዴሞክራሲ ሽግግር ቁልፍ ቦታ እንደተጫወተ ይታወሳል፡፡ በሶቭየት ዩኒየንና በሌሎቹ የሶቭየት ክልል በነበሩት ሃገራት የዴሞክራሲ ሂደትም አሜሪካ ድርድሩን በመምራት ውጤታማ እንዳደረገ ይታወሳል፡፡ጥያቄው አሜሪካ በኢትዮጵያ ወይም በአፍሪካ ውስጥ የሰብአዊ መብት አጀንዳን ያራምዳል ወይ ሳይሆን፤ ይህን ሁኔታ ተግባራዊ ለማድረግ የፖለቲካ ፈቃደኝነቱ አለው ወይ ነው፡፡ በፕሬዜዳንት ኦባማ ሁለተኛ የአስተዳደር ዘመን ፈቃደኝነቱ ይታያል የሚልጠንካራ እምነት አለኝ፡፡

የተቶረገመው ጽሁፍ (translated from):

http://open.salon.com/blog/almariam/2012/11/11/what_should_ethiopians_expect_in_a_second_obama_term

(ይህን ጦማር ለሌሎችም ያካፍሉ::)

ካሁን በፊት የቀረቡ የጸሃፊው ጦማሮችን  ለማግኘት እዚህ ይጫኑ::

http://www.ecadforum.com/Amharic/archives/category/al-mariam-amharic

http://ethioforum.org/?cat=24